አቦይ ስብሃትን ፈቶ ፤ አርበኛ ዘመነ ካሴን ማሰር – አሰፋ በድሉ

(15/01/2015 ዓ.ም)

አቦይ ስብሃት ነጋን ለኢትዮጵያ ህዝብ አላስተዋውቅም፡፡የምን ምልክት እንደሆኑ ራሳችሁ መልሱት! በሌላው ብሔር ላይ የተፈጸመውን ለጊዜው እናቆየው፡፡በወያኔ ትግል ወቅት ወገኔ የሚሏቸውን ትግራዋይ ሰብስቦ በካምፕ ካጎረ በኋላ ምግብ ከልክሎ፤አጥንታቸው ብቻ ሲቀር ያንን በቪዲዮ ቀርጾ ለፖለቲካ ፍጆታ መጠቀምን ስብሃት ካልሆነ ማን ትዝ ሊለው ይችላል? እንታረቅ ብሎ ጠርቶ፤ በተኙበት መረሸንን ስብሃት ካልሆነ ማን ሊያስብ ይችላል? ግን አንድ ነገር ብቻ ላስታውስ፡፡ምናልባት የቀራቸው እንጥፍጣፊ ክፋ ምክር ካለ ተፈጥሮ ሳይቀድማቸው ያንን እንዲያስተላልፋ ምቹ ሁኔታን መፍጠር በሚመስል ሁናቴ ሲፈቱ የተፈጠረውን ስሜት እናስታውሳለን፡፡በወቅቱ በ No More ከፍተኛ ተጋድሎ ሲያደርግ የከረመው ዲያስፖራ ስሜቱ ሳይቀዘቅዝ በተደረገለት የእናት ሃገር ጥሪ አገር ቤት የገባው ብዙ ነበር፡፡ግን የአቦይ ስብሃት መፈታት ውሃ ነበር የቸለሰበት፡፡ታዲያ ጠ/ሚ/ር ዶ/ር አብይ አህመድ ይህንን ማስተባበል ግድ ሆነባቸው፡፡ያሉትን ቃል በቃል አሁን ባላስታውስም ይዘቱን ግን አስታውሳለሁ፡፡ስድባቸውን ለፈጣሪ ልተወው! ያው እንደተለመደው እሳቸው አዛኝ፤ሩህሩህ በሌላ ወገን ለምን ተፈቱ ያልን ደግሞ ጨካኞች አንደሆንን አድርገው አቀረቡት፡፡አሁን “ጉድጓዳቸው የተማሰ፤ልጣቸው የተራሰ”፤ህመምና ዕድሜ የተጫናቸው አዛውንት ቢፈቱ ጉዳቱ ምኑ ላይ ነው አሉን በተጠየቅ፡፡ እግረ-መንገዳችንን የነጻነት/የአርበኛ ወዳጅ የሆኑትን አዛውንቱን ኑሮም፤ዕድሜም የተጫናቸውን ጋዜጠኛ አቶ ታዲዮስ ታንቱ በአሁኑ ሰዓት የት እንደሚገኙ በትይዩ አስታውሰን እንለፍ! ሁለተኛው ጠ/ሚ/ሩ ያነሱት ደግሞ ስለ ፍትህ የተናገሩት ነው፡፡ርዕሴ ያደረግሁት እሳቸው ስለተናገሩት ነው፡፡በወቅቱ ብዙወች ይቅርታና እርቅ ቢኖር እንኳን ፍትህና እውነት እንደ ደቡብ አፍሪካው ማለት ነው መጀመሪያ መረጋገጥ አለበት ባዮች ነበሩ፡፡የአገሪቱ ጠ/ሚ/ር ግን ስለ ምን ፍትህ ነው የምታወሩት? ኢትዮጵያ ውስጥ ፍትህ አለ ወይ ብለውን አረፋት! በወቅቱ እርግማን ይሁን ምርቃት ያላወቅሁት ቃል ተጠቅመዋል፡፡ኡርቱፋ/ሁርቱፋ? በትክክል ማስታወሴን እርግጠኛ አይደለሁም፡፡በእርግጥ ጠ/ሚ/ር ደ/ር አብይ አህመድ እኔ በተረደኋቸው መጠን ስለ Legal or Political Correctness ስለሚባለው ነገር ብዙ ተጨናቂ ሀነው አላያቸውም፡፡ከማስመሰል ይሸላል፡፡ ታዲያ አቦይ ስብሃትን ለመፍታት፤ ሚዛን የሚደፋ ምክንያት ያልፈለገው መንግስት አርበኛ ዘመነ ካሴን ለማሳደድ ለምን እንቅልፍ አጣ? ነው ጥያቄው፡፡ መልሱ ቀላል ነው፡፡ የልማትና ኢኮኖሚያዊ እንዲሁም ፖለቲካዊ ጥያቄወችን እናቆያቸው፡፡ህይወቱን፤ህልውናውን እንኳን ለአደጋ ስናጋልጥበት፤በመንግስት ላይ ህጋዊ ጥያቄ እንኳን የማያነሳውን ህዝብ ለምን ታነቃለህ ነው ወንጀሉ! ሌላው ትርፍ ነው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የኢትዮጵያ ዩኒቨርሲቲዎች የዓይጠመጐጥ ማምረቻ!

ከጦርነቱ በፊት ዘመነ የሚባል ስም  አላውቅም፡፡ህወሃት እየገፋ ሲመጣ ያደረጋቸውን ንግግሮች ከዩ ቲዩብ አዳምጫለሁ፡፡ለብአዴን ያስተላለፈው መልክት፤ ከቻላችሁ ይህን ህዝብ ከጠላት ተከላከሉ፤ ካልቻላችሁ ደግሞ ራሳችንን አደራጅተን እንከላከላለን እንቅፋት አትሁኑን ነው ያለው፡፡ለአመታት በአማራ ህዝብ ላይ በተደረገው ክፋ ትርክት የአማራ ህልውና አደጋ ላይ መውደቁን ለማስረዳት ሞክሯል፡፡መንግሰት ደመወዙን ከእኛ እየተከፈለው እኔም አልጠብቃችሁ፤ራሳችሁንም እንድትከላከሉ አልፈቅድም የሚል መንግስት በታሪክ ስለመኖሩ አልሰማሁምም፤አላነበብሁምም፡፡በሌላ አነጋገር ለምን ዝም ብላችሁ እንደ በግ አትታረዱም የሚል ነው፡፡በዕርግጥ ለምን በከፍተኛ የበቀል ስሜት ለመጣ ጠላት አሳልፎ እንደሰጠን ሰበቦችን ደርዳሪወች ከአገር ቤት እስከ ውጭ አገር ቁስላችንን በእንጨት የሚወጉ አዘጋጅቶ ከሞት የተረፋትን ደግሞ ህሊናቸውን በመስበር ካሳ በመክፈል ላይ ይገኛል፡፡ይህንን የጻፍሁት በወለጋ አሁንም ወገን እያለቀ ባለበት ወቅት ነው፡፡መንግስት ሆይ ዘመነ የፖለቲከኛ እስረኛ ነው፡፡አመለካከትህን ለምን ገለጽህ ነው፡፡ስለሆነም ፍቱት እንላለን! ባይፈታም ጨው አይደለም አይሟሟም፡፡ህዝብን ለአደጋ ያጋለጡ ናቸው ህግ ካለ መጠየቅ ያለባቸው! ለመሆኑ የማንን ጎፈሬ እያበጠራችሁ ነው ከመቶ ሚሊዮን በላይ ህዝብ፤በቁጥርም፤በሃብትም ጨርሶ ለንጽጽር የማይቀርብን ጠላት እንዲህ ያለ ግፍ እንዲፈጽም ዕድል የተሰጠው? ታሪክ የሚመልሰው ነው! መንግስቱ ሃ/ማርያም ሶማሊያን በ 3 ወር ውስጥ 3 መቶ ሺህ ጦር ታጠቅ አሰልጥኖ አዘጋጅቶ አገር አስከብሯል፡፡ግፍን ለምን ታገሳችሁ ነው?

ይቆየን!

 

3 Comments

  1. ብርሀኑ ነጋ ነብስ አረፈች ዘመንም ታሰረ ልደቱን ከሀገር ወጣለት ። ኢዜማን ግንቦት ስብከትን ይዘህ ወደ አማራ ክልል ለምርጫ እግሬን አነሳለሁ ካልክ ውርድ ከራስ

  2. አንድ በወያኔ አመራር ውስጥ የነበረ ሰው ጋር በቅርቡ ስናወራ እንዴት ነው ወያኔ ይህን ያህል ትጥቅ ሊኖረው የቻለ አልኩት። አይ ትጥቁ በአንድ ጊዜ የተገኘ አይደለም። በኢትዮጵያ ሰራዊት ስም እየተገዛ ለ 30 ዓመት የተጠራቀመ ነው አለኝ። የት አስቀምጠውት? እንዴት ሌሎች አመራር ላይ ያሉ የሃገሪቱ ሰራዊት አባላት ጥያቄ አላቀረቡም ስለው ስማ ገዢውም፤ ከፋዪም አንተ ስትሆን ጠያቂ የለብህም። በአብላጫው መገዛቱንም አያውቁም አለኝ። በአንጻሩ የሰራዊቱ ተበላሽተው የቆሙ ወታደራዊ መኪኖች፤ ታንኮች ሌሎችም ድጋፍ ሰጪ ነገሮችን ሁሉ ማዳከም ከሴራው አንድ ክፍል ነበር አለኝ። እንግዲህ ይህን ሁሉ ሴራ የፈጸመውን ቀንደኛ የወያኔ መሪ ስብሃት ነጋንና ቤተሰቡን የአብይ መንግስት የፈታው። ባንጻሩ ጸሃፊዎችን፤ ገጣሚዎችን፤ ጦማሪዎችንና የፋኖ አባላትን የሚያሳደውና የሚያስረው። እኮ ከዘመናት በፊት ይህን ተመልክተው አይደል እንዴ የሃገራችን ገበሬዎች “ኢትዮጵያ ሃገሬ ሞኝ ነሽ ተላላ የሞተልሽ ቀርቶ የገደለሽ በላ ያሉት”።
    በቅርቡ የአውሮፓ ህብረት ተወካይ “የትግራይ መንግስት” የሚል ቃል በንግግሯ ውስጥ ተጠቀመች በማለት ኡኡታው ግሏል። እኔ በዚህ ጭኸት የለሁበትም። ራሱ ወያኔ ከትግራይ መንግስት የተሰጠ መግለጫ እያለ አይደል ወሬውን የሚያናፋው? ምን አዲስ ነገር ተገኘና ነው አሁን በነጭ አፍ ሲነገር የሚያበሳጨው። ሲጀመርስ ነጮቹ አይደሉ እንዴ እንዲህ አድርጉ እንዲያ ሁኑ የሚሏቸው? አውሮፓና አሜሪካ ልክ ዪክሬንን እንደሚያስደበድቡት ኢትዮጵያም ፍርክርኳ ቢወጣ ደንታ የላቸውም። ትላንትም ዛሬም ለእብደታችን እሳትና ጭድ እየሰጡ የሚያጫርሱን እነዚህ ሃይሎች ናቸው። አሁን ከዘመናት በህዋላ ካርቱም ላይ ኤምባሲዋን የከፈተቸው አሜሪካ ለዚህ ተንኮል ቀዳሚዋ ናት። ስለዚህ የአውሮፓዋ ተወካይ ሆን ብላ ያደረገችው እንጂ ተሳስታ አይደለም። ተንኮላቸው ጠሊቅ ነው። የእንግሊዙ የቢቢሲ ድህረ ገጽ ዛሬ ባወጣው ዜና ላይ ለትግራይ የእርዳታ እህል የጫኑ ካሚዎኖች ከአየር በተወረወረ ፍላጣ ለጥቂት አመለጡ ይለናል። ይህ የሴራቸው አንድ አካል የሆነው ወሬን ማጋነን፤ ማወናበድና ሰዎችም እንዳለ እንዲጋቱት ማድረግ በኢራቅ፤ በኢራን በሌሎችም ሃገሮች የሚጠቀሙበትና የተጠቀሙበት ሃገርን የማፍረስ ብልሃት ነው።
    እኔ ሰለ ዘመነ ካሴ የማውቀው ምንም ነገር የለም። ያው ፋኖ ነው ሲባል እሰማለሁ። ቆይቶ ደግሞ ስርዓት አልበኛ ሆነ ግብር ሁሉ ማስገበር ጀመረ እየተባለ ይወራል። ማንም ይሁን ማንም ወንጀል ከሰራ በህጉ መጠየቅ አለበት። ጥያቄው ጠያቂው ከሚጠየቀው ካልተሻለ ምን ህግ ይገዛቸዋል ነው። አንድ ጊዜ አንድ ሰው በፓለቲካ ተጠርጥሮ ይያዝና ያለቅጥ ሲደበድቡት እረ በኢማ…አምላክ ይላል። ድላው አልቆ፤ መንከባለሉም አብቅቶ አንድ ጓደኛው ጠጋ ይልና በማን አምላክ ነበር ያልከው ይለዋል። አይ እኛ ሃገር ያለች ደብር ናት አለው። እንዲህ ያለ ደብር ሰምቼ አላውቅም ሲለው አጥርቶ የሰማው ሌላው ጓደኛው አይ የፓለቲካ ድርጅት ስም ነው የጠራው አለውና ሁሉም በሲቃ ውስጥ የምጽአት ፈገግታቸውን አሳይተው ወደማይመለሱበት ተሸኙ። ኢትዪጵያ የግፈኞች ሃገር ናት። ሌላው ሁሉ መዘላበድ ነው። ይህ ግፍ ደግሞ ከትውልድ ወደ ትውልድ መሸጋገሩ ሃገሪቱን ዛሬ ላለችበት የአፓርታይድ እሳቤና አስተዳደራዊ መዋቅር አድርሷታል። መግደልና መገዳደል እንደ ጀብደኝነት የሚቆጠርባት ምድር። የእህትና የወንድሙ አስከሬን ላይ ቆሞ የሚዘፍንና የሚፎክር እነዚህ የቁም ሙት ካልሆኑ ማን ሊሆን ይችላል? ሰውን መርዝ አብልቶ አሞታል ላኩት ወደ ሃገሩ የሚል የውሻ ስብስብ ነው። በኢትዪጵያ ታሪክ ውስጥ በትግራይ ውስጥ ለ 20 ዓመታ እንደነበረው ጦር ያለ ለአንዲት ክፍለ ሃገር ሲታጠፍ ሲነጠፍ የኖረ ወታደራዊ ሃይል የለም። ግን ያ ሁሉ በጎ ነገር ከወያኔ የሴራ ምት አላዳነውም። ለዚህ ነው ሰው ታሟል የምለው። በዚህ ሰራዊት ላይ የደረሰው ግፍ እንዴት የሰው ልጅ ለሆነ እንቅልፍ ይሰጣል? ዛሬ በኦሮሞ ስም አንገት የሚቆርጡ፤ ሰው የሚያፈናቅሉ፤ ከወያኔ ጋር ቂጥ ገጥመው ህዝባችን የሚያስጨንቁ ሁሉ በወረፋ ሌላ አንገት ቆራጭ ይመጣባቸዋል ወይም እርስ በእርሳቸው ይተራረዳሉ። የሃበሻ ፓለቲካ እንደዛ ነው። የመገዳደል ፓለቲካ። የሚገርመው በቅርቡ ሰራዊት አስመረቅን ብሎ የደነፋው የኦሮሞ ታጣቂ ሃይል መሪ ሲናገር እንዲህ አለ “ይህ ሰራዊት ለኦሮሞ ህዝብ ብቻ ሳይሆን ለአፍሪቃ ቀንድም አኩሪ ተግባር የሚፈጽም ይሆናል”። ትኋንን የት ትሄጃለሽ ቢሏት መተማ ትደርሻለሽ ልብማ እንዳለችው ነው። መሰል ወገኑን ስብሰባ ጠርቶ በመትረጌስ የሚያጭድ እቡድ ድርጅት ለኦሮሞ ህዝብና ለአፍሪካ አኩሪ ሃይል እሆናለሁ ሲል አለማፈሩ። ግን እንዲህ ነው የሃበሻው ነገር ማጥ ውስጥ ተቀርቅሮ ተራራ ጫፍ ላይ ነኝ ብሎ መዳከር። የዚህ የፋኖ መሪ እስራትም ያለ ጊዜው የሆነ የወቅቱን ፓለቲካዊ እንፋሎት ከግምት ያላስገባ የጀብደኞች ድርጊት ነው። ግን የ 70 ዓመት አዛውንቱን ታዲዎስ ታንቱን አግቶ የሚገኝ መንግስት ነገርን መዝኖ ፍትህን ለህዝባችን ይሰጣል ብሎ መገመትም ጅልነት ነው። በሰሜኑ የሃገራችን ክፍል የሚደረገው መገዳደልም ትርፍ የለሽ የህዝባችን መከራ የሚያባዛ ፍልሚያ ነው። ግን ማን ልብ ይበል? ማን ለእናቶችና ለሽማግሌዎች ቃል ይታዘዝ? ሁሉም በደመ ነፈስ ወደ ሞት ይነጉዳል። ይህም ከንቱነት ነው። በቃኝ!

  3. ጎበዝ በተወረወረልን ስጋ ብቻ አንራኮት በእርግጥ ጃል መሮን ትቶ ዘመነ ካሴን ብቻ ጠላት ማድረግ ብዙ የሚያሳብቀው አለ አማራ ይህንን ምርጥ ልጁን ካስበላ ጣጣህን ቻል ነው የምለው፡፡ ተመስገን ደሳለኝ፤ እስክንድር ነጋን፤አቶ ታዲዎስ ታንቱን እንዲህ እርግፍ አድርጎ የሚረሳ ህዝብ ማን ነጻ እንዲያወጣው ይፈልጋል? እነዚህን ሰዎች አሳስረህ አሸማቅቀህ ከኖርክ ብርሃኑ ነጋ፤ሌንጮ ለታ፤ዳውድ ኢብሳ፤ስብሃት ነጋ፤መራራ ጉዲና ነጻ ያውጡህ፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share