የመንግሥት ዋና ተግባርና ሃላፊነት የሕዝብን ጸጥታና ደህንነት መጠበቅ ነው! “ጨዉ ለራስህ ስትል ጣፍጥ እለበለዚያ ግን ድንጋይ ነዉ ብለዉ ይጥሉሀል”

ሰኔ 17 ቀን 2014 ዓ.ም.

የአንድ ሀገር መንግስት ተቀዳሚ እና ዋነኛ ሃላፊነቱ የሚያስተዳድረዉን ሕዝብ ሰላም እና ደህንነት መጠበቅ ሲሆን፡ በአንጻሩ ደግሞ ሕዝብ መንግስት ያወጣውን ሕግ፣ ደንብ እና ስርአት ተከትሎ የመኖር መብትና ግዴታ አለበት። ይህ ሳይሆን ቀርቶ መንግስት የሕዝብን ሰላም እና ደህንነት መጠበቅ ከተሳነዉ፡ መንግስት በሕዝብ ዘንድ የተቸረዉን ቅቡልነት እና አመኔታ ስለሚያጣ የጊዜ ጉዳይ ካልሆነ በስተቀረ በመንግስትነቱ እንደማይቀጥል እሙን ነዉ።

ከዚህ በመነሳት ከ አራት ዓመት በፊት በኢትዮጵያ በተከሰተዉ የለዉጥ እንቅስቃሴ አጥቢያ ወደ ስልጣን የመጣዉ በ ጠ/ሚ አብይ አህመድ (ዶ/ር) የሚመራዉ የብልጽግና ድርጅት ተቀዳሚ ተግባሩን መወጣት እንደተሳነዉ ከጊዜ ወደ ጊዜ ግልጽ እየሆነ መጥቷል። ለዚህም ማሳያ እንዲሆን ባለፉት አራት አመታት በሀገራችን ከተከሰቱት ዘግናኝ የዜጎች እልቂት፣ መፈናቀል እና ስደት በጥቂቱ ዋና ዋና ያልናቸዉን በመዘርዘር ለማሳየት እንሞክራለን። እንዲሁም በነዚህ አራት ዓመታት መንግስት የፈጸማቸዉን ስኬታማ ከሚባሉ ስራዎቸ ከብዙ በጥቂቱ በተጓዳኝ በመዘርዘር ለንጽጽር እንዲረዳ ለማሳየት እንሞክራለን።

ለዉጡን ተከትሎ መንግስት በሀገር ዉስጥም ሆነ በዉጭ ያሉን ማናቸዉም ተቃዋሚ የፖለቲካ ድርጅቶች ሀገራቸዉ ዉስጥ ሰላማዊ የፖለቲካ እንቅስቃሴ እንዲያደርጉ የሰላም ዘንባባ የያዙ እጆቹን ከዘረጋበት ቅጽበት አንስቶ ብሔር እና ዘዉግ ተኮር ግጭቶች ወደ ዘር የማጥፋት ጭፍጨፋ ተሸጋግረዉ ይሄዉ ዛሬ ከስድት መቶ (600) በላይ የሚሆኑ ሰላማዊ ዜጎቻችን በአማራነታቸዉ ብቻ እንደ ዶሮ በወለጋ ታርደዋል።

•ከለዉጡ በፊት የነበረዉን የኢህአድግ መንግስት ከሀገር ዉጭ ሆነዉ በትጥቅ ትግል ሲታገሉ የነበሩት የግንቦት 7 እና የኦሮሞ ነጻ አዉጪ ግንባር (ኦነግ) ድርጅቶች ወደ ሀገር ቤት በሳምንታት ልዩነት ሲመለሱ ለአቀባበላቸዉ በተዘጋጀዉ ትእይንት ላይ የተገኙት ደጋፊዎቻቸዉ በያዙት ሰንደቅ ዓላማ ላይ በተነሱ አለመግባባቶች በሰዉ አካል እና በንብረት ላይ መጠነኛ ጉዳት ከማድረሱ ባሻገር ሊመጣ ላለዉ የብሔር እና የዘር ተኮር እልቂት ማሟሻ እና እርሾ ሆኗል።

•ይህንንም ተከትሎ በአዲስ አበባ ዙሪያ በምትገኘዉ በቡራዩ ከተማ የኦነግ ደጋፊ ናቸዉ በተባሉ ዘረኛ አጉራ ዘለሎቸ በንጹሃን የጋሞ፣ የወላይታ እንዲሁም የጉራጌ ብሔር ተወላጆች ላይ በፈጸሙት የዘር ጭፍጨፋ ዜጎች ሲገደሉ አብዛኞቹም ከባድ ጉዳት ደርሶባቸዋል።

•ብዙም ሳይቆይ በአዋሳ ከተማ ኢጄቶ በመባል በሚታወቅ ስም የተደራጁ የሲዳማ ብሔር ተወላጅ ወጣቶቸ የሲዳማ ብሔር አይደሉም ባሏቸዉ ዜጎች ላይ የፈጸሙት እሳፋሪ እና ዘግናኝ ጭፍጨፋ አይረሳም።

•በፖለቲከኛዉ ጃዋር መሀመድ የተከብቤአለሁ የቲዉተር/ፌስቡክ ተማጽኖ በአዲስ አበባ እና በተለይም በኦሮሚያ ክልል ከተሞች በተቀሰቀስ ረብሻ የብዙ ሰዎች ህይወት ሲጠፋ ከፍተኛ የንብረት ዉድመት ደርሷል።

•የአርቲሲት ሃጫሉን አሳዛኝ ግድያ ተከትሎ በመላዉ ኦሮሚያ በሚባል መልኩ በተለይም በሻሸመኔ ከተማ በቃል ለመግለጽ የሚያዳግት በበዙ መቶዎች የተገደሉበት እና የቆሰሉበት ዘር እና ሃይማኖት ተኮር ጭፍጨፋ ተፈጽሟል። በበዙ ሚሊዎን ብር የሚቆጠር ንብረት እና ሀብት ወድሟል። ከጭፍጨፋዉ በኪነ ጥበቡ የተረፉት እዛዉ አድገዉ፣ከብደዉ እና ወልደዉ የኖሩበትን እገር ጥለዉ ላይመለሱ ተሰደዋል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በሱማሌ ክልል በ‹‹ቦምባስ›› ከተማ በተፈጠረው ግጭት አፋጣኝ ፍትህ እንዲሰጥ (ኢዜማ)

•በሰሜን ሸዋ እና በደቡብ ወሎ አጣዬ እና ከሚሴ ኗሪዎች ላይ በጽንፈኛ የኦሮሞ ታጣቂዉች በመቶዎች የሚቆጠሩ የአማራ ተዋላጆች ላይ የተፈጸመዉ ዘግናኝ ጭፍጨፋ እና የደረሰዉ ዉድመት ይሄ ነዉ አይባልም። ሙሉ በሙሉ በሚባል መልኩ አጣዬ ከተማ ወድማለች።

•ላለፉት ሶስት አመታት ያለ ማቋረጥ በ ቤንሻጉል ጉሙዝ ክልል በተለያዩ ወረዳዎች በተለይም በመተከል አዉራጃ ዘር ላይ ያተኮረ በይበልጥም በአማራ ተዋላጆች ላይ ዘግናኝ ጭፍጨፋዎች ተፈጽመዋል። በሺህ የሚቆጠሩ ሲገደሉ እና ሲቆስሉ፡ ለመቁጠር እስኪያስቸግር ድረስ በብዙ ሺዎች ተፈናቅለዉ ለስደት ተዳርገዋል።

•ባለፉት አራት አመታት በኦሮሚያ ክልል በተለይም በወለጋ በቃላት ለመግለጽ በሚያዳግት መልኩ በ 1970 ዎቹ አካባቢ በሰሜኑ የሀገራቸን ክፍል በተከሰተዉ ድርቅ ሳብያ መንግስት በወሰደዉ የነፍስ አድን ዘመቻ ወደ ወለጋ በሰፈራ ከወሎ የሄዱ ዜጎቻችን ላይ በአማራነታቸዉ ብቻ በብዙ ሺህ የሚቆጠሩ በጽንፈኛ የኦሮሞ ሃይሎች በተደጋጋሚ ተጨፍጭፈዋል ታርደዋል። በሺዎች የሚቆጠሩ ተሰደዋል ተፈናቅለዋል። ይሄዉ ዛሬም ዘር ተኮር ጭፍጨፋዉ ቀጥሎ ጠ/ሚኒስትሩ ስልጣን ላይ ከወጡ ከ አራት አመት በኋላ ከ 600 መቶ በላይ ሲታረዱ ብዙ ሺዎች ምድር ቁና ሆናባቸዉ በስቃይ ማጥ ዉስጥ ይዋልላሉ።
•ወደ ሰሜኑ የሀገራችን ከፍል ስናቀና ደግሞ፡ ለተከሰተዉ ዘግናኝ እና አዉዳሚ የእርስ በርስ ጦርነት መንስኤ የተጠያቂነቱን ድርሻ ትህነግ ቢወስድም ጦርነቱ በትህነግ ከመጀመሩ በፊት የነበረዉን ተጨባጭ ሁኔታ በመገምገም መንግስት ይህን እይነት ድንገተኛ ጥቃት ሊመጣ እንደሚችል በተወሰነ ደረጃም ቢሆን ሊገነዘብ እና ቅድመ ዝግጅት ሊያደርግ ይገባ ነበር። ለዚህም ምክንያቱ፤

1. ጥቃቱ ከመፈጸሙ ቀደም ብሎ በነበሩት ወራት መንግስት የሰሜን እዝን ከትግራይ አዉጥቶ ወደ መሐል እገር ለማንቀሳቀስ ባደረገዉ ሙከራ ትህነግ የአካባቢዉን ህጻናት እና እናቶች አሰልፎ መሬት ላይ በማስተኛት ሰራዊቱ ከትግራይ እንዳይወጣ በማር የተለወስ ተንኮል ተጠቅሞ ስራዊቱን እዘናግቶ እዛዉ ለማረድ እንዲቀር ማድረጉ።

2. ጥቃቱ ከመፈጸሙ ጥቂት ሳምንታት በፊት የሰሜን እዝ እዛዥ በትህነግ ተመርዘዉ አዲስ አበባ በጦር ሃይሎች ሆስፒታል በህክምና ላይ መሆናቸዉ።

3. በእርሳቸዉ ምትክ የተላከዉ የጦር ጀነራል ትግራይ እንዳይገባ ከመቀሌ አዉሮፕላን ማረፊያ በትግራይ ልዩ ሃይል ታግዶ መመለሱ።

እነዚህ ከላይ የጠቀስናቸዉን ጥቂት ተጨባጭ ነገሮች በተገቢዉ መንገድ ካለማጤን እና ካለመገምገም የተነሳ ሰራዊቱ ምንም አይነት ጥርጣሬ እና ስጋት ሳይኖረዉ እራሱን ሳያዘጋጅ ሀገር ሰላም ብሎ በተኛበት ለመጨፍጨፍ በቅቷል። አዎ በወቅቱ በሰራዊቱ ዉስጥ የነበሩት አብዛኞቹ ከፍተኛ መኮንኖች የትህነግ ደጋፊዎች ስለነበሩ ሁኔታዎችን በተገቢዉ መንገድ ለመገምገም እና መፍትሄ ለማግኝት እዳጋች ነበር የሚል የመከራከሪያ ሀሳብ ሊነሳ ይችላል። ለዚህ መልስ የሚሆነዉ በወቅቱ የሠራዊቱ ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም የነበሩት የዛሬዉ አምባሳደር ጀነራል አደም ሲሆኑ በተጨማሪም የያኔዉ ም/ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም የነበሩት የዛሬዉ ጠቅላይ ኢታማዦር ሹም ፊልድ ማርሻል ብርሃኑ ጁላ ነበሩ። የሚገርመዉ እና ያሚያሳዝነዉ በሀገራችን ላይ በተለይም በሠራዊታችን ላይ ለደረሰዉ ጥፋት የሠራዊቱ ጠቅላይ ኢታማዦር ሹምም ሆነ የደህንነት እካላት ተጠያቂ እልሆኑም። እንዲያዉም ጥፋታቸዉን እና ድክመታቸዉን ለመሸፈን በሚመስል መልኩ በአምባሳደርነት ተሹመዉ ከሀገር ወጡ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ዘረኝነትን መታገል የሁላችንም ግዴታና ሃላፊነት ነው

ከጦርነቱም በኋላ ለደረሰዉ ከፍተኛ የሰዉ ህይወት እና የንብረት ጥፋት የፌደራል መንግስቱ በከፊልም ቢሆን ተጠያቂ ነዉ። ምክንያቱም ሰራዊቱ በአሽናፊነት መቀሌ ገብቶ ለስምንት ወራት ያህል በተቀመጠበት ወቅት የትህነግ ሠራዊት ከትብያ ተነስቶ ለመደራጀት እና መልሶ ሠራዊታችንን ለማጥቃት እስኪደርስ ድርስ በመንግስት ደህንነት በኩል ያለዉን ስፊ የመረጃ እጥረት ቁልጭ አድርጎ ያሳያል። ለዚህም ይመስላል ጠ/ሚንስትሩ በሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤት ተገኝተዉ ባደረጉት ንግግር ትህነግ (ጁንታዉ ባሳቸዉ አጠራር) ዱቄት ሆኗል ተበትኗል ያሉት። ይህ አባባላቸዉ አቅደዉትም ባይሆን ህዝብን እንዲዘናጋ አድርጓል። በተለይም የአማራ ክልል አመራሮች የጠ/ሚንስትሩን ዱቄት ሆኗል ቧልት ተከትለዉ ይመስላል ሌት ተቅን ትህነግ ከአማራ ጋር የማወራርደዉ ሂሳብ አለኝ ይል የነበረዉን ዛቻ ዘንግትዉ ሕዝቡን በስነ ልቦና እና በትጥቅ ሳያዘጋጁት ለስምንት ወር ተጎልተዉ ይሄ ነዉ የማይባል ዋጋ አስከፍለዉታል።

የዚህ አይነት ተጠያቂነት የሌለበት፣ ነገሮቸን ቀድሞ በመገምገም ሊከሰቱ የሚችሉ አደጋዎችን ካለማጤን እና ተገቢዉን ጥንቃቄ ካለማድረግ የተነሳ በሰራዊታቸን ላይ የደረሰዉ አሳዛኝ ክስተት በወለጋ እና በቤንሻንጉል ጉምዝ የአማራ ተወላጅ ዜጎቻችን ላይ በተደጋጋሚ ላለፉት አራት አመታት እንዲጨፋጨፉ ከፍተኛ አስተዋጾ አድርጓል።

መንግስት ህግን ከማስከበር ባሻገር የሐገሪቱ ፖለቲካ፣ ኢኮኖሚ እና ማሕባራዊ ሕይወት ላይ ከፍተኛ ሚና ይጫዋታል። ለዚህም ጥሩ ምሳሌ የሚሆነን በዶ/ር አብይ የሚመራዉ መንግስት በሀገሪቱ የተጀመሩ እና አዳዲስ ታላላቅ ሀገራዊ ፕሮጀክቶች ላይ የሚያሳየዉ ትጋት እና ብቃት ሊደነቅ ይገባል። እንደ ምሳሌ፤ የታላቁ የህዳሴ ግድብ ግንባታ፤ የኩታ ገጠም እርሻ ፤ የበጋ ወር የስንዴ እርሻ ልማት እና አረንጓዴ አሻራ በመባል የሚታወቀዉ በመላዉ ሀገሪቱ በተከታታይ አመታት የተደረገዉ እና በመደረግ ላይ ያለዉ የችግኝ ተከላ በኢኮኖሚዉ ረገድ ከፍተኛ ዉጤት የሚያስገኙ ናቸዉ። በዲፕሎማሲዉ ረገድ ደግሞ ምንም ተቋማዊ ሂደትን የተከተለ ባይሆንም ከኤርትራ ጋር የተደረገዉ የሰላም ድርድር እንደ ታላቅ ስኬት ይቆጠራል። እንዲሁም፡ የመንግስት እና የሲቪክ ተቋማትን ለማዘመን እና መዋቅራዊ ለማድረግ ታቅዶ የተጀመረዉ ስራ እንደተጠበቀዉ ዉጤት ባያመጣም ሀገሪቱ ካለባት ተጨባጭ የኢኮኖሚ ጫና፣ ከገባችበት የፖለቲካ ቅርቃር እና ተቋማትን ለማስተካከል ከሚጠይቀዉ ረዘም ያለ ጊዜ እኳያ የሚያበረታታ መጠነኛ ለዉጥ ታይቷል። ለዚህም የመከላከያ ሠራዊት፣ የምርጫ ቦርድ እና የኢትዮጵያ ሰባዊ መብት ኮሚሽን (ኢሰመኮ) በምሳሌነት ሊጠቀሱ ይችላሉ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከብሔራዊ ደህንነት ምክር ቤት በወቅታዊ ሀገራዊና ቀጠናዊ፣ የደህንነትና ፀጥታ ጉዳዮች ላይ የተሰጠ መግለጫ

ቱሪዝም እና ማሕበራዊ ሕይወትን በተመለከተ የብልጽግና መንግስት በተለይም ዶ/ር አብይ አመርቂ ስራን ሰርተዋል። ከእንጦጦ ጀምሮ እስከ መስቀል አደባባይ የተሰሩት የህዝብ መዝናኛ ቦታዎች፣ ያብሮነት ቤተ መጽሐፍት፣ የአንድነት ፓርክ እንዲሁም በግንባታ ላይ ያሉ ያሳይንስ እና የአድዋ ሙዚየሞች፣ በየክልሉ ያስጀመሯቸዉ ሆቴሎች እና መዝናኛ ቦታዎች ከብዙ ጥቂቶቹ ናቸዉ። በማሕበራዊዉ ረገድ ጠ/ሚንስትሩ እና ባለቤታቸዉ ተቀዳሚ እመቤት ዝናሽ ታያቸዉ የአዛዉንቶችን ቤት በመስራት እና በመጠገን፡ ትምህርት ቤቶችን በማሰራት፣ የተቸገሩትን እና የታመሙትን በመጠየቅ የሚያሳዩት ግላዊ እርዳታ ለማሕበረሰባችን ታላቅ ምሳሌነት አለዉ።

ይህ ሁሉ ጠቃሚ እና ጥሩ ተግባር ሆኖ እያለ ከላይ እንደገለጽነዉ የአንድ አገር መንግስት ተቀዳሚ እና ዋነኛ ሃላፊነቱ የዜጎችን ሰላም እና ደህንነትን ማስጠበቅ ሲሆን የብልጽግና መንግስት ይህን ማሳካት ፈጽሞ ተስኖታል። የአንድ መንግስት ብቃት መገለጫዎች ናቸዉ ከሚባሉት ባሕርያት መካከል በተቀዳሚነት የሚነሳዉ፡ በሀገር ላይ ችግር በተፈጠረ ወቅት መሪዉ ሙሉ ሃላፊነትን በመዉስድ ሕዝብ ፊት ቀርቦ ሰለጉዳዪ አስፈላጊዉን ማብራርያ ስጥቶ ዜጎችን አጽናንቶ እና አረጋግቶ ተገቢዉን እርምጃ በአፋጣኝ ሲወስድ ነዉ። በዚህ ረገድ ጠ/ሚንስትሩም ሆነ የሚመሩት የብልጽግና ድርጅት በተደጋጋሚ የብቃት ጉድለት አሳይተዋል። ይህም በመሆኑ መንግስት እስካሁን የመጣበትን መንገድ በግልጽ እና በጥንቃቄ መርምሮ እና ገምግሞ እንዳለፉት አራት አመታት በንጹሀን ዜጎቻችን ላይ ጭፍጨፋ በደረሰ ጊዜ ችግሩን ለመፍታት አቅጣጫ አስቀምጠናል ከሚል ትርጉም የለሽ ሽንገላ ተላቆ አስቸኳይ እና ፈጣን እርማት ሊያደርግ ይገባል።

በተጨማሪም እያንዳንዱ ኢትዮጵያዊ ይህንን አስከፊ የንፁሀንን እልቂት ለማስቆም የሚችለውን ሁሉ በማድረግ የዜግነት ግዴታዉን መወጣት ይኖርበታል:: ስለሆነም ፤ የሀይማኖት አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ ታዋቂ ግለስቦች፣ ልሂቃን፣ የሰብዓዊ መብት ተከራካሪዎች፣ የሲቪክ ማህበራት እና ተቋማት፣ መንግሥት የሕዝብን ሰላም እና ደህንነት እንዲያስጠብቅ ጫና ማድርግ ይጠበቅባቸዋል:: እንዲሁም የሚዲያ ተቋማት በተለይም የብሔር ፖለቲካን የሚያስተጋቡ፡ ጽንፈኛ ሃይሎች፡ በንጹሀን ዜጎች ላይ የሚፈጽሙትን ጥቃት ለማስቆም ጥረት ሊያደርጉ ይገባል። በብሔር የተደራጁ ተቃዋሚ ፖለቲከኞችም የሀዘን መግለጫ ከማዉጣት እና ገለልተኛ አጣሪ እንዲቋቋም ከመጠየቅ በተጨማሪ፡ የዘር ተኮር ግድያ፣ ዘረፋ እና ማፈናቀልን በፅኑ ማውገዝና በትጋት መከላከል አለባቸው::

መንግስታት ከነሱ በፊት ከነበሩ እና ካለፉት መማር አለባቸው። አንዱን አካባቢ እና ሕዝብ አኬልዳማ በማድረግ የሚግኝ ትርፍም ሆነ ዘለቄታዊ ድል የለም። እንደውም በሁሉም ዘንድ መጠላትን አስከትሎ መንግስት የሥልጣን ዘመኑ ባልጠበቀዉ ሰአት እና መንገድ ያለጊዜዉ በዉርደት እንዲያበቃ ይዳርጋል። ”ጨው ለራስህ ስትል ጣፍጥ አለበለዚያ ግን ድንጋይ ነው ብለው ይጥሉሃል ሳይሆን ይወረውሩሃል” የሚለው በመንግሥት ላይ ይደርሳል።

2 Comments

  1. ፈንግል ነው ፈንቅል የሚል አንድ መናኛ ፓርቲ ነኝ የሚል የትግሬ እምባ ጠባቂ ነኝ የሚል ሚኪ ነው ማን ነው የሚሉት እንዴት እንደዚህ አይነት እንጭጭ በሃሳብ የተጎዳ ህዝብ እንዲያየው በሚዲያ ይለቀቃል? ፖሊቲካ እንጀራ መብያ ሆነ ማለት ነው? ለነገሩ አቶ ብርሃኑ ነጋ አቶ አረጋዊ በርሄስ ከእሱ በምን ይለያሉ? አቶ የተባሉበት ከአካዳሚክ ህይወት ተፋትተው ለደቂቃን ሮቦት ሁነውበማገልገል ላይ ስለሆኑ ነው፡፡

  2. ሰዳን ኢትዮጵያ ገደለችብኝ ያለችውን የወታደራዊና የስቪሎችን ሬሳ አስጥታ አጻፋ እመልሳለሁ ብላ ትፎክራለች። ወያኔ በመቀሌ ያው እንደለመደው ጎረቤቱ ላይ ሁሉ ተንኮልና ሸር እየፈጸመ ድረሱልኝ እያለ ኡኡ ይላል። በውጭና በሃገር ውስጥ ለ 27 ዓመት እየሰረቀ ባጠራቀመው ሃብትና ንብረት በሃሳብ የዘገዪ ነጮችንና የወያኔ ጭራ የሆኑትን የትግራይ ልጆች በመስክና በሚዲያ በማሰልፍ ውጊያ ከፍቶ ሃገርን ለማፈራረስ ወገቡን ታጥቆ እየሰራ ይገኛል። አሁን ደግሞ የኦሮሞ የጉምዝና የጋምቤላ አልፎ ተርፎም የቅማንት ነጻ አውጭ ነን የሚሉ ድውያንን አሰልፎ አርሶ አደሮችን ያርዳል፤ ያፈናቅላል፤ በሰው ደም ላይ ይነግዳል።
    የኢትዮጵያ ችግር ውስብስብ ቢሆንም 90 % ችግሯ የሚመነጨው ከትግራይ ነው። አዲስ አበባ ላይ ተቀምጠው የወያኔን እንደገና መምጣት የሚናፍቁ ለትግራይ ህዝብ የማይገዳቸው ትግራዪች ስንት እንዳሉ ያውቃሉ? በቅርቡ የስንት ንጽሃንን ደም ያፈሰሰው ሰው ጄኔራል ሲሞት ቀብሩ ላይ ትግራይ ትሰርዕ ማለታቸው የቱን ያህል ስር የሰደደ የዘር ጥላቻ ደማቸው ውስጥ እንዳለ ያሳያል። የማይድን በሽታ። በትግራይ መኖር መስራት የናፈቀ እቃውን ጠቅሎ ትግራይ መግባት ነው ያለበት። ውጭ ሆኖ ያዘው ጥለፈው በለው አለንላችሁ ማለት የድሃውን ልጅ ለማስጨረስ እንጂ ሌላ ትርፍ ነገር የለውም። ወያኔ ከትግራይ መሬት ሲመነጠር ብቻ ነው ኢትዮጵያ ሰላም የሚኖራት። ወያኔዎች ክፋትን የተላበሱ፤ ከሰው ዘር የወጡ ድርቡሾች ናቸው። አሁን በደምቢዶሎና በግንቢ የሆነውን ነገር ስፓንሰር የሚያረጉት ወያኔዎች ናቸው። ኦሮሞው ታጣቂ የወያኔ ትዕዛዝ ሥራ አስፈጻሚ እንጂ ለኦሮሞ ህዝብ ነጻነትና ደህንነት የሚገደው ጥርቅም አይደለም። ለህዝብ የቆመ ህዝብ የሚገለገልበትን የጤና ተቋም የትምህርት ማዕክል፤ የተከመረ የእህል ክምር በእሳት አያጋይም።
    የወያኔ ዓላማ የዶ/ር አብይ መንግስት በህዝብ እንዲጠላና እንዲፍረከረክ ማድረግ ነው። ወያኔ ሽንክ ነው። የወያኔ የስለላ መረብ ዶ/ር አብይ ቢሮ ድረስ የዘለቀ ነው። ይህ ግን እንደ አዲስ ተዋቀረ ለተባለው የሃገሪቱ የስለላ መረብ ግልጽ የሆነለት አይመስለኝም። የዶ/ር አብይ መንግስት የሚያስረው ጋዜጠኛችንና ፋኖዎቹን መሆኑ ደግሞ የበለጠ ለወያኔ ፈንጠዝያ ሆኗል። ቆም ብሎ ማሰብ ይገባል!
    የኦሮሞ ህዝብ በልምድ በባህሉ ሌላውን የማጥቃትና የማሳደድ ተግባር አያውቅም። ሰው አቃፊ ከራሱ በፊት ሌላውን የሚያስቀድም ህብረተሰብ ነው። ኑረንበት አይተነዋል። ወሬአችን በስማ በለው አይደለም። እነዚህ የአድዋ ተኩላዎች የሃገር መሪ ከሆኑ በህዋላ እየከፋፈሉ በጋቱት የክልል ፓለቲካ ሁሉም ጎሳ፤ ዘሩን የፈለጋችሁትን ስም ስጡት አቅራሪና ፎካሪ ሆኖ እንሆ የንጽሃን ደም በከንቱ ይፈሳል። ይህ ሁሉ ሊገታ የሚችለው ገዳይን በመግደል፤ ዘራፊና ከፋፋይን ሃሳቡን በማምከን ነው። የሶሻል ሚዲያና የዘር ፓለቲካ በሁሉም ላይ ጭቃ እየለጠፈ እሞትላታለሁ ለሚሏት ሃገራቸው እንኳን የሚሰሩትን ትግሬ ጠል፤ አማራ ጠል፤ የኦሮሞ ወዳጅ ወይም ጠላት እያልን ስንኩላቸው እንውላለን። እውነቱ ግን ከሚጻፍልንና ከሚነገረን ውጭ ነው። ህሊናው ልክ የሆነ ሰው በሰው መሞት ደስ ይለዋል ብዬ እኔ አላምንም። ከየትም ዘር ይሁን ወይም ሃይማኖት። ግን ጢንቢራው የዞረበት በዘር ፓለቲካ የጠነበዘ ወይም በአክራሪ እምነት ዙሪያ መሬት ላይ ቆሞ ተንሳፋፊ ነኝ ለሚሉ ሞት ቀልድ ነው። እነርሱም በወረፋቸው አንድ እስኪሸኛቸው ድረስ። በሃገራችን የምናየው ያን ነው። በወረፋ የመገዳደል ፓለቲካ። ሰውን በሰውነቱ ያላከበረ ፓለቲካ ወይም ሃይማኖት በአፍንጫዬ ይውጣ።
    የዚህ ጽሁፍ አቅራቢ “ጨው ለራስህ ብትል ጣፍጥ ያለዚያ ድንጋይ ነው ብለው ይጥሉሃል” ብለውናል። ችግሩ ተረቱ ራሱ ፍሬ አልባ መሆኑ ነው። ጨው የድንጋይ አካል ነው። ጨው ጣፍጦ አያውቅም። እስቲ በምላሳችሁ ጨው ላሱና መጣፈጡን እዪት። ፓለቲካችንም እንደዛ ነው ቅራቅንቦ ተረት ብቻ። ለነገሩ ” የተማረ ይግደለኝ” እያሉ አይደል ህዝባችን ፊደል ቆጥረናል በሚሉ ዶ/ር፤ እንጂኒየር ገለ መሌ እየተባሉ በሚጠሩ ሙታኖች በሚፈልቅ የመከራ ዶፍ እየተጠራረገ ያለው። እውቁ የኦሮሞ ፓለቲካ አቀንቃኝ ጃዋር መሃመድ በቅርቡ ሲናገር ” አማራ እየሞተ ኦሮሞ በሰላም መኖር አይችልም” ብሎናል። ልክ ነው። ግን ሰሚ አለ ወይ? ባንዲራዪን አትጠቀም የሚሉ የኦነግ ባንዲራ አምላኪዎች ባሉበት ሃገር ሃገር አቀፋዊ እይታ ሊኖረን ይችል ይሆን? አይመስለኝም።
    ለምሳሌ የአቶ አንዋርን ኮሜንት ከላይ ለተመለከተ – የስንቱን ሰው ስም ጠርቶ ስንቱን ጥላሸት እንደቀባ መመልከት ይቻላል። ያልኮነነው ራሱን ብቻ ነው። ሌላው ሁሉ በእርሱ እይታ ሃጥዕ ነው። የመፍትሄው ምንጭ ሁላችን እንደሆንን ሁሉ የመከራችንም ምንጭ ሁላችን ነን። ግን ያለን ድርሻ ከፍና ዝቅ ይላል እንጂ። ጠቁሞ ያስገደለና ተኩሶ የገደለ ልዪነት የላቸውም። የዛሬው ሞት ብዙው የሚፈጸመው በኢንተርኔት ነው። የውሽት ወሬን በመንዛት፤ ሰዎችን በውሸት በማነሳሳትና በመወንጀል፤ ሰበር ብሎ የፈጠራ ወሬ በመለጠፍ፤ ባጠቃላይ ያልሆነውን ሆኖ ብሎ በማደናገር።
    ሰፊው የትግራይ ህዝብ የፍቅር ህዝብ ነው። አንድ ሻለቃ የነገረኝን ላጫውታችሁ። ጦሩ ሲመታ አምልጦ ጉዞ ወደ ጎንደር ይጀምራል። መንገድን አያውቀውም። በዚህ መካከል አንድ የትግራይ ገበሬ ያገኛል። ምን ሆነህ ነው ይለዋል። የሆነውን ይነግረዋል። እቤቱ ደብቆ አሳድሮ፤ ገንዘብ ሰጥቶ፤ መንገድ አመላክቶ ወደ ጎንደር እንዳሻገረው ከእንባ ጋር አጫውቶኛል። እንዲህ ያሉትን የትግራይ ተወላጆች ወያኔ ባንዳ፤ ከሃዲ እያለ ይገላል። ቀን መጥቶ ያን ሰው ፈልጎ እስኪያገኘው ምጥ ይዞታል። ሌላም ብዙ ማለት ይቻላል። ግን ጊዜና ቦታ አይበቃም። ክፉዎችና ተንኮለኞች ከሁሉም ዘር እንዳሉ ሁሉ መልካምና በጎ አድራጊ ሰዎችም በየጎራው ሞልተዋል። ያን ባህሪ ነው ማጠንከር ያለብን።
    ባጭሩ የተማሪዎች ሰልፍ የዚህም የዚያም ድምጽ ተደምሮ የተሻለ ሃገራዊ እርምጃ እንዲያመጣ አፍራሽ ሃይሎች እንዳይጠቀሙበት መጠንቀቅ ያስፈልጋል። ወያኔ ትርምስ የሴራ ሜዳው ነው። በቀጥታም ሆነ በእጅ አዙር የኦሮሞን ህዝብ በጥቅል እያጥላሉ አማራ ከኦሮሞ ጋር እንዲላተም በ 27 ዓመቱ ዘመናቸው ሰርተዋል አሁንም እሳት በየቦታው የሚለኩሱት ራሳቸው ናቸው። የሱዳንም ሰው ሞተብኝ እበቀላለሁ ማለት ከወያኔ የሴራ ስልት ጋር የተያያዘ ነው። አርማጭሆን ለሱዳን ወልቃይትን ለትግራይ የሚሉት ለዛ ነው። ነቃ እንበል። በቃኝ!

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share