የትግራይ ጉዳይ፤ በረከተ መርገም – ሰማው በላይነህ!

የኢትዮጵያ መንግሥት ሰኔ 21 ቀን ያወጀውን የትግራይ ክልል የተኩስ አቁም አዋጅ በተመለከተ የተለያዩ ሀሳቦች እየተሠነዘሩ ይገኛሉ፡፡ እንደ እውነቱ ከሆነ መንግስት መተቸት ያለበት በመዘግየቱ ነው፡፡ የሕግ ማስከበር ዘመቻው በተጠቃለለ በሳምንታት ጊዜ ውስጥ የተኩስ አቁም አዋጁን አውጆ ወደ ፖለቲካዊ መፍትሄ ቢያመራ መልካም ነበር፡፡ ምናልባት ግን ከፊት ለፊቱ የነበረው ሐገራዊ ምርጫ ውሳኔውን እንዲያዘገይ እንዳደረገው ይታመናል፡፡

የኢትዮጵያ መንግስት ከዚህ በላይ የትግራይን ጉዳይ መሸከም አልነበረበትም፡፡ ቀድሞም የተለያዩ የውስጥና የውጭ አካላት ይሄንን ጉዳይ አንስተው ሞግተዋል፡፡ አውሮፓና አሜሪካ ጠንካራ ማእቀብ ለመጣል እየተዘጋጁ ነው፡፡ ይህ ማእቀብ የኢትዮጵያን ምርቶች እስካለመግዛት የሚደርስ ነው፡፡ ይህ ሁኔታ ለኢትዮጵያ ኢኮኖሚ ከባድ ሸክም ነው፡፡ አሜሪካና የአውሮፓ ህብረት የትግራይ ችግር በፖለቲካ መፍትሔ የማይፈታ ከሆነ ኢትዮጵያን በሰብአዊ መብት ጥሰት ለመክሰስ ኮሚቴ አቋቁመው እየሠሩ ነው፡፡ በአንድ በኩል ለማንም ክልል የማይሰጥ በጀት 100 ቢልዮን ብር ለትግራይ እየዋለ፤ በሌላ በኩል ምንም ብድርና ርዳታ እየተከለከለ መጓዝ አያዎ ነው፡፡  አሜሪካ ሁኔታውን በራሷ ብቻ አታየውም፡፡ አለም አቀፍ የገንዘብ ተቋማትንና አለም አቀፍ አጋሮቿን የመጠቀም አዝማሚያ አሳይታለች፡፡

በየትኛውም ታሪክ ጦርነት በጦርነት አይጠናቀቀም፡፡ ጦርነት የሚጠናቀቀው ሌላ ጦርነት ባልሆነ መፍትሔ ነው፡፡ በፖለቲካ መፍትሔ፣ በሽምግልና ወይም በሌላ መንገድ፡፡ ጦርነት አማጺውን ወደዚህ መንገድ አስገድዶ የማምጫ መንገድ ነው፡፡ በዘመናችን የተደረገውን የኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ማስታወስ እንችላለን፡፡ ኢትዮጵያ ውጊያውን ብታሸንፍም ዘመቻውን ግን አላሸነፈችም፡፡ በጦርነቱ ያገኘችውን ድል በፖለቲካው አስነጥቃዋለች፡፡ አሜሪካ በኢራቅና በአፍጋኒስታን ያደረገችውን ጦርነት በውጊያ የበላይነት ብታጠናቅቅም በፖለቲካ መፍትሔ የታጀበ ባለመሆኑ ከ29ና ከ30 ዓመታት በኋላ አሜሪካ የጦርነቱን ዋጋ እየከፈለች ትገኛለች፡፡

ኢትዮጵያን በተመለከተ የአሜሪካና የአውሮፓ ዲፕሎማቶች በተደጋጋሚ የሚያነሱት አንድ ጉዳይ ከራሳቸው ሁኔታ የሚመነጭ ነው፡፡ የትግራዩ ግጭት በፖለቲካ መፍትሔ መቋጨት አለበት ሲሉ የራሳቸውን የኢራቅና የአፍጋኒስታን ጦርነት እንደ አንድ ማሳያ ያነሡታል፡፡ በተለይም ደግሞ ችግር እፈታለሁ ብሎ ጦርነት ያወጀ አካል በጦርነቱ የበላይነትን በያዘ ጊዜ በአስቸኳይ ወደ ፖለቲካዊ ወይም ሌላ መፍትሔ መጓዝ አለበት የሚለውን ሐሳብ ከዚህ የራሳቸው ውድቀት ተነስተው ያቀርባሉ፡፡ የባይደን አስተዳደር ዲፕሎማቶችም ከሰሞኑ ይሄንኑ ሐሳብ አንስተዋል፡፡

የትግራዩ ጦርነት ከመጀመሩ በፊት ሕወሐት በአራት ምሶሶ የቆመ ሐይል ነበር፡፡ ክልሉን የሚመራ የፖለቲካ ሐይል ነበር፡፡ የሀገሪቱን ኢኮኖሚ ያካበተ የኢኮኖሚ ሀይል ነበር፤ የሰሜን እዝን መሳሪያ ሊታጠቅ የሚችል ወታደራዊ ሐይል ነበር፤ የትግራይ ሕዝብ ድጋፍ ያለው ሕዝባዊ ሀይል ነበር፡፡ ሕወሐት ይሄንን በአራት ምሶሶ የቆመ አቅሙን ተጠቅሞ ኢትዮጵያን እንደ አጠቃላይ፣ የአማራ ክልልንና ኤርትራን እንደ አጎራባች የሚያስፈራራ የስጋት ሀይል ነበር፡፡

በትግራይ የተደረገው ጦርነት ሕወሐትን ባለ አንድ ምሰሶ አድርጎታል፡፡ ክልሉን የሚመራው ፖለቲዊ ሀይል ግማሹ ተገድሎ፣ ግማሹ ተማርኮ፣ ጥቂቱ በረሀ ወርዷል፡፡ በጦርነቱ አካሔድና መፍትሄ ላይ በተፈጠረ ልዩነት እርስ በርሱ ተከፋፍሏል፡፡ የተፈጠሩት ሦስት ቡድኖች የጋራ ጠላት እንጂ የጋራ መፍትሄና አካሄድ የላቸውም፡፡ አንድ ያደረጋቸው የጋራ ጠላታቸው ነው፡፡ ይሄ የጋራ ጠላት ከትግራይ ሲወጣ የአንድነታቸው መዘወሪያ ይጠፋል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  (የሚኒሶታው መድሃኔዓለም ቤ/ክ ጉዳይ) ከወገብ በላይ ታቦት ከወገብ በታች ጣኦት!!

አንዳንድ ቡድኖች የኤርትራ ሰራዊት ከወጣ፤ በትግራይ ተወላጆች ላይ የሚደረገው ተጽእኖ ከተወገደ እንዲሁም በወንጀል ያለ መከሰስ መብት ከተሰጠ በተሻለ ሁኔታ ከመንግስት ጋር ለመነጋገር ዝግጁ ናቸው፡፡ የነ ጌታቸው ቡድን ግን ባይዋጋም ውጊያ የሚያምረው፤ በተገደሉትና በተማረኩት አመራሮች ቦታ ራሱን መሾም የሚፈልግ ቡድን ነው፡፡ የሕወሐት የኢኮኖሚ ምሰሶ የነበሩ ኩባንያዎቹ ተነጥቀዋል፤ ደክመዋል፡፡ በእጃቸው የነበረውን ገንዘብም በረሐ ለበረሐ ይዘውት በመዞር ከአማራ ክልል መሣሪያ ለመግዛት ተጠቅመውበታል፡፡ በነገራችን ላይ በረሀ የወረደው የሕወሐት ክንፍ መሣሪያ በከፍተኛ ዋጋ ይገዛ የነበረው ከአማራ ክልል ነው፡፡ ከሰሞኑ እንኳን በጎንደርና በወሎ የመሳሪያ ገበያው ደርቶ ነበር፡፡ መከላከያ ትግራይን ለቅቆ ሲወጣ ሕወሐት የሚረከባት ትግራይ ባዶ ቀፎዋን ነው፡፡ የርዳታ እህል፤ ጥቂት ነዳጅ፤ የቢሮ ዕቃዎችና ሌሎች የተራረፉ ነገሮችን ያገኛል፡፡ ከፌዴራል መንግስት የሚሄድ ባጀት አይኖረውም፡፡ ባንኮቹና የፋይናንስ ተቋሞቹ አይሰሩም፡፡ ኢንዱስትሪዎቹ ቆመዋል፡፡ በተለይ ፌዴራል መንግስቱ ወደ ክልሉ የሚገቡ ነገሮችን በሚገባ መቆጣጠር ከቻለ ሕወሐት ሰሐን እንጂ ፍትፍት አይኖረውም፡፡ የፋይናንስ ኢንተለጀንስ ክፍሉ በሚገባ ከሰራ ለሕወሐት ከውጭ ሊላክ የሚችል ገንዘብ አይኖርም፡፡

ከዚህ በፊት በነበረው ጊዜ ሕወሐት ለምሽግ መገንቢያ ያዋለውን ስሚንቶ ለማምረት የጥሬ እቃ ችግር ነበረበት፡፡ በተለይም ደግሞ ከውጭ በውጭ ምንዛሬ የሚገቡ እቃዎች ይቸግሩት ነበር፡፡ ይኄንን የተወጣው በኢትዮጵያ ከሚገኙ የግል የሲሚንቶ ፋብሪካዎች እነርሱ ያስገቡትን ጥሬ እቃ መልሶ በከፍተኛ ወጭ በመግዛት ነው፡፡ መንግስት አሁን እንዲህ ባሉት አካላት ላይ ነው ጠንካራ ቁጥጥር ማድረግ ያለበት፡፡

ሕወሐት ጦርነቱን ሲጭር ተስፋ ያደረገው ያሰለጠነውን 200ሺ ሚሊሻና የሠሜን እዝን መሣሪያ ነው፡፡ በትግራይ የነበረው መሳሪያ የኢትዮጵያን 60 በመቶ መሣሪያ የሚሸፍን ነበር፡፡ በኢትዮ ኤርትራ ጦርነት ወቅት ገብቶ በዚያው የቀረ ነበረ፡፡ ከዚያም በኋላ ለሀገሪቱ የተገዙ የጦር መሳሪያዎች ዋነኛ መቀመጫቸው ትግራይ እንዲሆን ተደርጎ ነበር፡፡ ከለውጡ በኋላም ቢሆን በመከላከያ ውስጥ የነበሩ የሕወሐት ወታደራዊ አዛዦች በሰሩት ሴራ የመከላከያ የኢንተለጀንስ፣ የመገናኛና የውጊያ መሣሪያዎች በትግራይ እንዲተከሉ ተደርጎ ነበር፡፡ ሌላው ቀርቶ የአንዳንድ መሳሪያዎች የማዘዣ ስርዓት ከአዲስ አበባ መሆኑ ቀርቶ ከመቀሌ እንዲሆን ተደርጎ ነበር፡፡

ከወታደራዊ መሳሪያዎች በተጨማሪ ከአዲስ አበባው የቴሌኮሚኒኬሽን አቅም ያልተናነሠ የቴሌኮሚኒኬሽ ቴክኖሎጂ በመቀሌ ተዘርግቶ ነበር፡፡ በለውጡ የመጀመሪያ አመታት ከውጪ ወደ ኢትዮጵያ የሚገቡና ከኢትዮጵያ ወደ ውጭ የሚወጡ የስልክ ጥሪዎች የአዲስ አበባውን ማዘዣ ትተው በመቀሌ በኩል እንዲሆኑ እስከ ማድረግ ተደርሶ ነበር፡፡ ይህም ቀደም ብሎ በኢሕአዴግ ዘመን በተዘረጋ መሳሪያ ነው፡፡ በንጉሱና በደርግ ዘመን የነበሩ የአማራ ክልልና የደቡብ ክልል የአውሮፕላን ጣቢያዎች ተዘግተው በትግራይ አምስት መደበኛ የዐውሮፕላን ማረፊያዎችና አንድ ምስጢራዊ የአውሮፕላን ማረፊያ እንዲገነባ ተደርጎ ነበር፡፡

ባለፉት ስምንት ወራት እነዚህ የጦር መሣሪያዎች ከትግራይ ውጭ ሆነዋል፡፡ የቴክኖሎጂ መሣሪያዎቹም ወድመዋል፡፡ የአንዳንድ የቴክኖሎጂ ሲስተሞች የማዘዣ ሥርጭትም ወደ አዲስ አበባ እንዲመለስ ተደርጓል፡፡ ከአራት ዓመታት በፊት፣ ለውጡ እንደመጣ፣ የኢትዮጵያ መንግስት በትግራይ የነበረውን መሳሪያ ለማውጣት ሞክሮ ነበር፡፡ የትግራይ መንግስት ተቃወመ፡፡ ሕዝቡንም አሰልፎ መንገድ ዘጋ፡፡ በተደጋጋሚ በተደረጉ ውይይቶችም የትግራይ ክልል መንግስት የሰሜን እዝን ለቅቆ መውጣት ተቃወመ፡፡ እንደ ምክንያት ያቀርብ የነበረውም ኤርትራ ለትግራይ ስጋት ናት የሚለው ነበር፡፡ በዚህ የስምንት ወር ጊዜ የተገኘው አንዱ ውጤት እነዚህን መሳሪያዎች ለማውጣት መቻሉ ነው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ታላቁ የፖለቲካ ቅሌት በኢትዮጵያ፤ ነጠብጣቦቹን ያገናኙና ምስሉን ይመልከቱ!

ሕወሐት የሰሜን እዝን መሳሪያ በመተማመን፤ በሱዳን በኩል በነበረው ደንበር በኩልም ተጨማሪ መሳሪያዎችን እየገዛ በማስገባት ያጠናከረው 200 ሚሊሻ ተበትኖበታል፡፡ ይህ ሚሊሻ ራሱን ቀልቦ ሊያድር የሚችልበት የኢኮኖሚ አቅም የለውም፡፡ ከክላሽ በላይ ሊታጠቅበት የሚያስችል ምቹ ሁኔታ የለም፡፡ በሱዳን በኩል ተጨማሪ መሳሪያ ለማግኘት የሚያስችለው የምእራቡ በር አሁን በመከላከያና በአማራ ሚሊሻ ተዘግቷል፡፡ በላይኛው የተከዜ ድንበርም የኤርትራ ወታደር ድንበሩ ላይ አለ፡፡  አሁን ያለው የሕወሀት ጀሌ ስትራቴጂካዊ መሣሪያ የለውም።  ወደ 3ኛ ደረጃ ወርዷል። ጦርነቱ ሲጀመር ወታደራዊ ቁመና ነበረው። በህግ ማስከበሩ ሂደት ወደ ሽፍታዊ ቁመና ወረደ። አሁን ጅምላዊ(ሞብ)  ሆኗል።

አሁን ሕወሐት የተረፈው ምሶሶ ሕዝቡ ነው፡፡ የትግራይ ሕዝብ ሁለት ሀገራዊ ጠባዮች አሉት፡፡ አንዱ ጥንታዊ ጠባዩ ሲሆን ሁለተኛው ከጊዜ በኋላ ያዳበረው ጠባይ ነው፡፡ ጥንታዊ ጠባዩ ኢትዮጵያዊነቱ ነው፡፡ የተለመደው የኢትዮጵያ ታሪክ መነሻውና ማዳወሪያው ትግራይ ነው፡፡ ክርስትናም ሆኑ እስልምና በኢትዮጵያ ጥንታዊ አሻራቸውን ያሳረፉት በትግራይ በኩል ነው፡፡ ለኢትዮጵያ ሉአላዊነትና ነጻነት ዋጋ የከፈለ ሕዝብ ነው፡፡ አስከሬኑን በኢትዮጵያ ባንዲራ ሸፍኖ የሚቀብር ሕዝብ ነው፡፡

ከዛሬ 60 ዓመት ወዲህ ደግሞ ሌላ በሱፍ ላይ ገበርዲን የሆነ ጠባይ አምጥቷል፡፡ እርሱም ከሕወሐት ጋር የፈጠረው የባህሪ ውህደት ነው፡፡ ራሱን የህወሀት ፈጣሪ ከማድረግ በላይ የህወሐት አምላኪም ሆኗል፡፡ ሲምል ‹ውድብና› ብሎ እስከ መማል ደርሷል፡፡ ምንም ያህል ጥፋት ቢያይ መውቀስ አይፈልግም፡፡ ምንም ያህል ቢበድለው ሕመሙን መታገስ ይፈልጋል፡፡

የትግራይ ሕዝብ ሀገራዊ ስሜቱ ሰፊ ነው፡፡ መላዋ ኢትዮጵያን ብቻ ሳይሆን በመንፈስ የጥንቷን ናግራንን እና ኑቢያን የሚጨምር ነው፡፡ የሕወሃት ስሜት ጠባብ ነው፡፡ ትግራይን ብቻ ወስኖና ቀንብቦ የያዘ ነው፡፡ እነዚህ ሁለቱ እርስ በርሳቸው የሚቃረኑ ናቸው፡፡ የትግራይ ህዝብም በእነዚህ ሁለቱ ተቃርኖዎች ውስጥ  ይኖራል፡፡ ህወሃት ሲገዛ ሀገራዊ ስሜቱን ይፈልገዋል፡፡ ይህ ስሜቱ ለኢኮኖሚና ለግዛት ምቹ ነው፡፡ ትግራይ የተተከሉ ፋብሪካዎችና የተቋቋሙ ኩባንያዎች ሁሉ ኢላማ የሚያደርጉት የሌላውን የኢትዮጵያ ክፍል ገበያ ነው፡፡ የትግራይ ባለሃብቶችም የመላዋን ኢትዮጵያ አንጡራ ሐብት ነው የሚጠቀሙት፡፡ ሰፊውን ህዝብና ሀገር ለገበያና ለስራ እድል ይፈልገዋል፡፡ ከአናሳ ህዝብ ወጥቶ ብዙሐንን ለመግዛት አስችሎታል፡፡

በሌላ በኩል ደግሞ ህወሃትን ሲነኩበትና ጥቅሙ የተነካ ሲመስለው እንደ ቀንድ አውጣ ወደ ሼሉ ይገባና የትግራይ ብሄርተኝነትንና የህወሐት ምልኪን ያነሣል፡፡ ሲጠቀም ኢትዮጵያዊ፣ ሲቸገር ትግራዊ ይሆናል፡፡ በዚህ ስምንት ወር የታየውም ይሔ ነው፡፡ ሕዝቡ ራሱን ወያኔ አደረገ፡፡ የኢትዮጵያን መከላከያ እንደ ሌላ ሀገር ወታደር ቆጠረው፡፡ ከኢትዮጵያ ጋር ሆኜ ከምኖር ከሕወሃት ጋር ሆኜ ልሙት አለ፡፡ እርዳታውን ይፈልገዋል፤ የኢትዮጵያን የቴሌ፣ የመብራት እና የጤና አገልግሎቶችን ይፈልጋል፡፡ ራሷን ኢትዮጵያን ግን አይፈልጋትም፡፡ ላሚቱን እየደበደበ ወተቷን ማለብ ይፈልጋል፡፡ የተጠቀመው ጥቂቱ ትግራዋይ ቢሆንም ብዙሃኑ ግን ስነ ልቦናዊ ጥቅም እንዳገኘ ይሰማዋል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  30ኛው የኢትዮጵያውያን ባህልና ስፖርት ፌዴሬሽን ዝግጅት እንዴት አለፈ?

ሕወሃት ህዝቡን ወደተሻለ ኑሮ ከወሰደው ይህ የህዝብ ድጋህ ይቀጥላል፡፡ ካልወሰደው ግን ትግሉ በሕወሀትና በህዝቡ መካከል ይሆናል፡፡ አሁን ባለው የሕወሃት ኢኮኖሚያዊ አቅም ግን ያ የሚቻል አይደለም፡፡ ሕወሃት ይሄን እድል የሚያገኘው በሁለት መንገዶች ነው፡፡ የመጀመሪያው በ1977 ድርቅ ጊዜ የህዝቡን ርዳታ እየሸጠ ሃብት ከማፍራት አልፎ ታላላቅ ኩባንያዎችን መስርቷል፡፡ ዛሬም ይሄን ለማድረግ መሞከሩ አይቀርም፡፡ ይሄን የመቆጣጠሪያ መንገዱ የኢትዮጵያ መንግስት የርዳታ አሰጣጡን ሲከታተልና የርዳታ መሸጫ ኮሪደር የሆነው የሱዳን ድንበርን ሲዘጋበት ነው፡፡ ሁለተኛው አማራጭ ራሱን እንደ ሶማሌ ላንድ ቆጥሮ የርዳታ ሰጭዎችን ኢኮኖሚያዊ ርዳታ እንደ መንግስት ሆኖ ከተቀበለ ነው፡፡ ይሄንን የመከላከል ሙሉ ግዴታና ሀላፊነት የኢትዮጵያ መንግስት ነው፡፡ ግዛታዊ አንድነቱን ለማንኛውም ውይይትና ርዳታ ማቅረብ የለበትም፡፡

ሕወሃት ከአስር ወር በፊትና በኋላ ተለያይቷል፡፡ ሌላው ቀርቶ ጦርነቱ ሲጀመር የነበረውን ግዛታዊ ዐቅም አሁን አያገኝም፡፡ ራያና ወልቃይት፤ ጸለምትና ሁመራ ከእጁ ወጥተዋል፡፡ የተወሰኑ አካባቢዎችም ወደ አፋር ተመልሰዋል፡፡ የአማራ ክልል በዚህ ዘመቻ የሰላሳ አመት ጥያቄውን  ከዘመቻው ትልቁን ዲቪደንድ አግኝቷል። ያን በቀጣይ ወራት ሕጋዊና ፖለቲካዊ መልክ ማስያዝ አለበት፡፡ ከዚህ በኋላ የሕወሐትን ርዝራዥ ከአደጋ ለመከላከል ወሳኙ ክልል የአማራ ክልል በመሆኑ ለትግራይ ክልል ተመድቦ የነበረውን በጀት ወስዶ ስራ መስራት አለበት፡፡ ከዚህ በፊት ለራያ፣ ለወልቃይትና ለፀለምት የተመደበው በጀት ለትግራይ ክልል ተሰጥቶ የአማራ ክልል ሲቸገር የነበረበት አሰራር መቆም አለበት፡፡ ጠላት አይናቅም አይደነቅም እንደሚባለው ካልሆነ በቀር ለአሁኑ ህወሀት የአማራ ሚሊሻ ከበቂው በላይ ነው።  አማራን በህወሀት ማስፈራራት የሚፈልጉ ሰዎች አንበሳን በፍየል ለማስፈራራት የሚከጅሉ ናቸው።

በሰሜናዊ ትግራይ ድንበር ላይ ነቅቶ ከሚጠብቀው የኤርትራ ሰራዊት ጋር ሒዌ ሰፋጣ ለመግጠም የሚያስችል ሞራል የለውም፡፡

መከላከያ ዘግይቷል፡፡ ከዚህ በላይ ግን በጦርነት ሙድ ውስጥ መቆየት የለበትም፡፡ ከዚህ በኋላ ከቆየ ሁለት ችግር ይፈጠራል፡፡ አንደኛው በሕዝቡ ሌላኛው በሰራዊቱ፡፡ ህዝብ በጭፍን ድጋፍ ከሕወሃት ጋር ቆሞ መከላከያውን ደጀን አሳጥቶታል፡፡ ሕወሃት በሚያደርገው ውጊያ ከፊት ህጻናትና ሴቶችን አሰልፎ ከኋላ ሚሊሻውን ያሰልፋል፡፡ በዚህ የተነሳ በከፍተኛ ሁኔታ እየሞተ ያለው ሕዝቡ ነው፡፡ ይህ ሁኔታ ከቆየ ደግሞ ጦርነቱ ሕዝብ ጨራሽ ይሆናል፡፡ ሰራዊቱ ሕዝብን እንደ ጠላቱ ወደ መገመት ይሄዳል፡፡ በዚህ እምነት በሰራዊቱ ላይ ጥላቻና ንዴት መፈጠሩ አይቀርም፡፡ ይህ ጉዳይ በጊዜ ማናጅ ካልተደረገ የሚፈጥረው ቀውስ ከባድ ነው፡፡

ከዚህ በኋላ ማሰብ የሚሻለው ትግራይ እንዴት ትተዳደራለች፣ ርዳታ እንዴት ይደርሳል፤ በትግራይ ውስጥ ለሚፈጠር ነገር ተጠያቂ ማነው? የአማራና የአፋር ክልሎችን አጠናክሮ እንዴት መጠበቅ ይቻላል? ውይይት ካስፈለገ ከየትኛው አካል ጋር ይደረጋል? ሕግ የማስከበር ሂደቱንና ፖለቲካዊ መፍትሔው እንዴት ጎን ለጎን ማካሄድ ይቻላል? የሚሉትን አጥርቶ ማሰብ ነው፡፡

 

ፀሃፊ፦ ሰማው በላይነህ!

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share