ይህ ሁሉ ላንቺ ነው እናታለም! – በነስረዲን ኑሩ

ማህጸነ ለምለሟ ኢትዮጵያ በያይነቱ ወልዳለች፤ ከጀግና እስከ ባንዳ፣ ለሀገሩ የገባውን ቃል ኪዳን ከሚያከብር እስከ ቃል አባይ፡፡

ግንቦት 17/2014

ይህች ሀገር፤ ጡቶቿን አጥብታ ሰው ባደረገቻቸው፣ አስተምራ ለወግ ማዕረግ ባበቃቻቸው የገዛ ልጆቿ በተደጋጋሚ ክህደት ተፈጽሞባታል፡፡ ለዘመናት ያጎረሱ እጆቿ ተነክሰዋል፡፡ ወተቷን ጠጥተው፣ ከሜዳዋ ቦርቀው፣ መአዛዋን ምገው ባደጉ ልጆቿ እናት ሀገር ከጀርባዋ ተወግታለች፡፡

ኢትዮጵያ በታሪኳ ባንዳ በሆኑ ልጆቿ ለውስጥም ለውጪም ጠላቶቿ ጥቃት ተጋልጣ ታውቃለች፡፡

የእናት ሀገር ጠላቶች በጦር አውድማ ሊያሳኩ ያልቻሉትን ዓላማ በአፍቅሮተ ንዋይና በስልጣን ጥማት የኖኸለሉ ድኩማን ልጆቿን ተጠቅመው ዓላማቸውን ለማሳካት ሲጥሩ አይታ ልቧ ደምቷል፡፡

ይህ በልጆቿ የመከዳት ሂደት ኢትዮጵያን በቅርቡ አጋጥሟታል፡፡ በሰሜኑ የሀገሪቱ ክፍል መንግሥት ባካሄደው የኅልውና ዘመቻ ወቅት ከላይ ለማተት የተሞከረው የታሪክ ዳራ ታይቷል፡፡

ሳይደግስ አይጣላም እንዲሉ እናታለም ከድኩማን ልጆቿ ፈተና በገጠማት የታሪክ አጋጣሚ ሁሉ እልፍ አዕላፍ የማህጸኗ ፍሬዎች ስለሷ ክብር ደማቸውን አፍሰዋል፣ አጥንታቸውን ከስክሰዋል፤ ክቡር ህይወታቸውንም ለሀገራቸው የገቡትን ቃል ኪዳን ለመጠበቅ ሲሉ አሳልፈው ሰጥተዋል፤ እየሰጡም ይገኛሉ፡፡

የእናት ሆድ ዥንጉርጉር ነውና ኢትዮጵያ በባንዳ ልጆቿ የምታፈሰውን እንባ ማቄን፣ ጨርቄን ሳይሉ የሚያብሱላት የሀገር አለኝታዎችንም ወልዳለች፡፡

ጥቂት ባንዳዎች እና ሆድ አደሮች ከጠላቶቿ ጋር አብረው ኢትዮጵያን ሊያፈርሷት ሲጥሩ እነዚህ ጀግና ልጆቿ ደግሞ ክህደታቸውን ሲመክቱና ህልማቸውን ሲያከሽፉ ኖረዋል፡፡ ዛሬም ይህ ተግባራቸው ቀጥሏል፡፡

እንደዚህ ያሉ ጀግኖቿ በአጥንታቸው፣ በደማቸው ከፍ ሲልም አንዷን ህይወታቸውን ገብረው ኢትዮጵያን አጽንተው ለትውልድ አሻግረዋል፡፡ ዛሬም እየሆነ ያለው ይሄው ነው፡፡ ወደ ፊትም የሚሆነው ይሄው ነው፡፡

ምክንያቱም በየዘመኑ እናት ሀገር ኢትዮጵያን ከገጠሟት የኅልውና አደጋዎች የታደጓት ጀግኖች ልጆቿ መቼም ቢሆን ሀገራቸውን ለባንዳ እና ለታሪካዊ ጠላቶቿ ተላላኪዎች አሳልፈው እንደማይሰጧት ታሪክ ምስክር ነው፡፡

አሸባሪው ትሕነግ በሀገር መከላከያ ኃይል ሰሜን እዝ ላይ የፈፀመውን ክህደት ተከትሎ በትግራይ ክልል በተከሰተው የጸጥታ መደፍረስ ኢትዮጵያ ዛሬም ባንዳና ጀግና፣ ቃል አክባሪና ከሃዲ ልጆችን በእቅፏ ይዛ እንዳለች አይተናል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ብልጽግናና ባሕል

ይህ ሀሳብ እውነት መሆኑን ለማወቅ ደግሞ እንደ ብርጋዲዬር ጀነራል ሻምበል በየነ ያሉ ለቁጥር የሚታክቱ ጀግኖች ኢትዮጵያዊያን በዚህ ትውልድ የዘመን ጉያ ውስጥ መኖራቸውን ማሳየት ብቻ በቂ ነው፡፡

ብርጋዲዬር ጀነራል ሻምበል በየነ ከቀናት በፊት በመከላከያ ቴሌቪዥን ፕሮግራም ላይ ቀርቦ “አለሁ፣ ጠላት እንደተመኘው አልሞትኩም፤ ፊቴ ላይ ጉዳት ደርሶብኝ ነበር፡፡ አሁን አገግሜ ወደ ሥራዬ ተመልሻለሁ“ በማለት ለኢትዮጵያዊን ብስራት ሲያበስር ለጠላቶቹ ደግሞ መርዶ አርድቷል፡፡

ጀነራሉ ፊት ላይ ዛሬም “የኢትዮጵያ ፍቅር“ በደማቁ ታትሟል፡፡ አብዘኛዎቹ ኢትዮጵያዊያን የብ/ጄነራሉን ጽናትና ወኔ ሲያዩ በደስታ አንብተዋል፡፡

ኢትዮጵያዊያን የቁርጥ ቀን ልጃቸውን በቴሌቪዥን መስኮት ሲመለከቱ የደስታ ሲቃ የተናነቃቸው እንዲሁ በዋዛ አልነበረም፡፡

የአሸባሪው ትሕነግ አፈቀላጤዎች፣ አክቲቪስቶች እና መገናኛ ብዙኃን ብርጋዲዬር ጄነራል ሻምበልን ገድለነዋል ሲሉ ከመክረማቸው በተጨማሪ የእርሱ ከሚዲያ መራቅ ሕዝቡ “እውነት ተሰውቶ ይሆን እንዴ?“ በሚል ሀሳብ ሲብከነከን በመክረሙ እንጂ!

ትሕነግ ጥቅምት 24 ቀን 2013 ዓ.ም ምሽት አራት ሰዓት ገደማ በሰሜን እዝ ላይ ክህደት ሲፈጸም ይህ ትንታግ ኢትዮጵያዊ በስፍራው ነበር፡፡

ትሕነግ ገና ይህን ሚስጥራዊ ክህደት ሲጠነስስ፤ ሊጠመዘዙ የማይችሉ እንዲሁም በኢትዮጵያ ሉአላዊነት የማይደራደሩ ተብለው ከተለዩ እና በወታደሮች ታፍነው እንዲገደሉ ከተወሰነባቸው ከፍተኛ የጦር መኮንኖች መካከል ብርጋዲዬር ጀነራል ሻምበል በየነ አንዱ ነበር፡፡

የያኔው ኮሎኔል የዛሬው ብ/ጄነራል ሻምበል በየነ በወቅቱ የ34ኛው ክፍለ ጦር ምክትል አዛዥ የነበረው ሲሆን ትሕነግ እሱን የማስወገድን ኃላፊነት የሰጠው ለክፍለጦሩ ዋና አዛዥና እና የቅርብ ጓደኛው ለነበረው ጄነራል ጆን ነበር፡፡

ጄነራል ጆን የተሰጠውን ትዕዛዝ ገቢራዊ ለማድረግ ይረዳው ዘንድ ምክትሉን ወደ ቢሮው እንዲመጣ መልዕክት ይሰድለታል፡፡ ብ/ጄ ሻምበልን ከጀነራል ጆን ቢሮ ሲደርስ ግን በስፍራው የጠበቀው የክፍለ ጦሩ አዛዥ ሳይሆን ገዳይ ወታደር ነበር፡፡

ብ/ጄ ሻምበል በዚያ ሰሞን ከሚያያቸው አንዳንድ ሁኔታዎች በመነሳት መጠራጠርና ነገሮችን በጥንቃቄ ማየት ጀምሮ ስለነበር ወደ አለቃው ቢሮ ሲሄድ አስፈላጊውን ጥንቃቄ አድርጎ ነበር፡፡ ጥንቃቄውም ከተደገሰለት የሞት ድግስ ራሱን እንዲያተርፍ አስችሎታል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአማራ ሸኔ ይፈጠር እና የአማራ ሸኔ አለ፤ ለየቅል ነው፡፡ ሂሳብን በዚህ ዓነት መልኩ ኃላፊነት የሚሰማው መንግስት አያወራርድም

ትንታጉ ወታደራዊ መኮንን በትሕነግ የተደገሰለትን የመጀመሪያውን ሞት ቀልብሶ ከሄደበት ቢሮ ሲወጣ ከውጭ የጠበቁት የትግራይ ልዩ ኃይል አባላት የተኩስ እሩምታ ነበርና ከእነሱም ጋር ዳግም መጋፈጥ ነበረበት፡፡

ለድል የተፈጠረው ብ/ጄ ሻምበል በጓዶቹ የተፈጸመበት ክህደት ሳያንስ የትግራይ ልዩ ኃይል አባላት በሁኔታው ውስጥ መከሰታቸው እያንገበገበው የለመደውን ድል በአካባቢው በነበሩ የአሸባሪው ቡድን አባላት ላይ በመድገም በካምፓቸው ውስጥ እንዳሉ ከበባ ወደ ተፈጸመባቸው የክፍለ ጦሩ አባላት ገሰገሰ፡፡

ከውጭ የተኩስ እሩምታ በመክፈትና ከባቢውን የሽብር ቡድን በማደናበር ከበባው እንዲሰበርና ታጋች ጓዶቹ ከከበባ ጥሰው በመውጣት ራሳቸውን አደራጀተው እንዲዋጉ ማድረግም ችሏል፡፡

በፍጹም ጀግንነት ከበባውን በመስበር እና የተበታተነውን የወገን ጦር በማደራጀት እየተዋጋ እና እያዋጋ ሳለ ግን እጅና እግሩ ላይ ጉዳት ይደርስበታል፡፡

ጉዳቱ የሚመራውን ጦር እንዲበትን አላደረገም፡፡ የሚመራውን ጦር ከ24ኛ ክፍለ ጦር ጋር በመቀላቀል ከሌሎች የጦር አመራሮች ጋር ወደ ኤርትራ ለማስገባት የቻለ ጀግናም ነው፡፡

ባለከዘራው ጄነራል በደረሰበት ጉዳት ምክንያት እያነከሰ፤ በከዘራ ተደግፎ ከቀናት በኋላም ሰራዊቱን በሞራል እና ሎጂስትክስ አደራጅቶ በመመለስ እንዲታረድ ማዘዣ የጻፈበትን ጠላት አይቀጡ ቅጣት እየቀጣ፣ የሚደመሰሰውን እየደመሰሰ፣ የሚማረከውን እየማረከ የተቀረውን ኃይል ወደ ቴንቤን በረሃ ከጓዶቹ ጋራ ያስገባ የጦር መሪ ነው፡፡

በዚህ ትንታግ የጦር መሪ የጀግንነት ተግባር እርር ድብን ያለው አሸባሪው ትሕነግ ግን ኢትዮጵያን የማፍረስ ህልሙ እንደጉም ሲበተን ብ/ጄነራል ሻምበልን ለማስገደል ያልማሰው ጉድጓድ አልነበረም፡፡

ትሕነግ ጀነራሉን ለማስገደል የተነሳው ለደረሰበት ሽንፈት ቢያንስ መጽናኛ ይሆነኛል ብሎ አስልቶ ሊሆን ይችላል፡፡

ኢትዮጵያ ሁሌም ቢሆን የውስጥ ባንዳን አታጣምና ትሕነግም ባለከዘራው ጀነራልን ለመግደል አሳቻ ሰዓትና ጊዜን መጠበቅ ጀመረች፡፡

በአፋር ጭፍራ ግንባር በተደረገው እጅግ እልህ አስጨራሽ ጦርነት ባለከዘራው ጄነራል በወትሮው ጀግንነት ጦርነቱን እየመራ ባለበት ወቅት ነበር ጉዳት የደረሰበት፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የበረሃው ጂኒ ፣ የባህሩ ጋኔል  - በልጅግ ዓሊ

ይህ ጥቃት እንደ ከዚህ ቀደሙ ቁስሉን አስሮና በከዘራ ምርኩዙ ታግዞ ውጊያዊን ሊያስጥል የሚያስችል አልነበረምና ጀግናውን ለህክምና ከጦር ቀጣናው ማንቀሳቀሰ ግድ ነበር፡፡

ከጀርባ የተወጋላት ሀገሩም ተገቢውን ክብር በመስጠትና በመንከባከብ ጀግናው ውጨ ሀገር ሄዶ እንዲታከም በማድረግ ተመልሶ በጠላቶቹ ፊት በጀግንነት እንዲቆም አድርጋዋለች፡፡

እሱም የእጅ መዳፉን ያህል ወደ ሚያውቀው የሰሜኑ የሀገሪቱ መልከዓ ምድር ተመልሶ ለዳግም ጦርነት እየተሰናዳ ያለውን ጠላት የእግር እሳት ሆኖ ዳግም ሊፋጀው መዘጋጀቱን ለኢትዮጵያ ሕዝብ ቃል ገብቷል፡፡

ሐሰተኛ ዜናን በመፈብረክ አቻ የማይገኝለት ትሕነግ የባለከዘራው ጀነራልን የመሰዋት ዜና በማጽናኛነት ለደጋፊዎቹ እና ጄሌዎቹ እንካችሁ ሲል አስፈንድቋቸው ነበር፡፡

ይህ የመጨረሻው እና ከእይታ ያራቀው ጉዳት ፊቱ ላይ የደረሰ በመሆኑ ከዚህ ቀደም ከደረሱበት ጉዳት አንጻር ጠንከር ያለ ነበር፡፡

እውነተኛ ጀግና ነውና ፊቱ ላይ በደረሰው ጉዳት ምክንያት ከሀገር ውጭ ሄዶ እና አገግሞ ሲመለስም “እስካሁን ሀገሬን አገልግያለሁ፤ አሁን ግን ይብቃኝ“ አላለም፡፡

ከደረሰብኝ ጉዳት አገግሜ ወደ ሥራዬ ተመልሻለሁ ነው ያለው፡፡ ሆስፒታል ሆኖ ሲናፍቅ ወደ ነበረው ቤቱ ተመልሶ ከሚወዳቸው ቤተሰቦቹ ጋር ስለሚያሳልፈው ጊዜ አይደለም የጓጓው፤ ክንዱን እስኪንተራስ ሊጠብቃት ቃል የገባላት ሀገሩን ከገባችበት የኅልውና አደጋ መታደግ እንጂ፡፡

ይህ አይነቱ ቁርጠኝነት ከአንድ በሀገሩ ፍቅር ከወደቀ ኢትዮጵያዊ ጀግና ብቻ የሚጠበቅ ነው፡፡ በፊቱ ላይ የታተመው ጉዳት ግን ፈገግታውን ሊነጥቀው አልተቻለውም፡፡ ምክንያቱም የጄነራሉ ፈገግታ የሚደበዝዘው ጠላት እንዳሰበው ኢትዮጵያን ሲያፈርስ ብቻ ነው፡፡

ያ የትሕነግ ህልም ግን እንደ ባለከዘራው ጄነራል ባሉ ትንታግ የኢትዮጵያ ልጆች ትግልና መስዋትነት እንደ ጉም በኗል፡፡

እናታለም ይህ ሁሉ የሆነው፤ ለወደፊትም የሚሆነው ላንቺ ነው፡፡

ክብር፣ ምስጋና እና ሞገስ ኢትዮጵያን በመስዋዕትነት፣ በደም እና በአጥንታቸው ላጸኑ ጀግኖች ኢትዮጵያዊያን ይሁን!

ዋልታ

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share