አይ ስኳር!- በላይነህ አባተ

እንደ በለስ ፍሬ አዳም እንደጋጠው፣
ተልሰህ ተቅመህ ስንቱን አስከዳሃው!

አይ ስኳር!

ተበለሱ ኃጥያት ሔዋንን ያወጣው፣
ታንተ ሊያድን ደሞ መቼ ይሆን መምጫው?

አይ ስኳር!

አንተ እንደምትሟሟው ሙቅ ውሀ ሲያስገቡህ፣
የላሰህን ሁሉ እንደ እምቧይ አፈረጥክ!

አይ ስኳር!

ሲልሱህ ሲቅሙህ ምላስ እየጣፈጥክ፣
በጉረሮ ወርደህ ክርስንም ተሻግረህ፣
ተአንጀት በደም ሥር ውስጥ ወደ ልብ ተጉዘህ፣
ስንቱን ልብ አፍርሰህ ስንት እግር አስቆረጥክ?

አይ ስኳር!

ስንቱ ምላሰኛ አንተን የቀመሰ፣
እሬብ እያሰፋ ተአይምሮው አነሰ!

ስንቱ ስኳር ቃሚ የዘነጋ ሞትን፣
ገላን እያፋፋ አቃጠላት ነፍሱን!

ስንት ስኳር ፈላጊ ተጉንዳን ያነሰ፣
በሕዝብ ተረማምዶ ወንበር ቁጢጥ አለ!

አይ ስኳር!

እንደ ጨው እንደ አንኳር ላም እንዳስጎመጀው፣
ስንቱን ምሁርን ነኝ ባይ እም…ቡዋ አሰኘኸው፡፡

አይ ስኳር!

የበቃው ባህታይ ማር ይስሐቅ እንዳለው፣
አንተን ቅሞ ቅሞ ዓለምን አፍቃሪው፣
ስንቱ ጳጳስ አቡን ቆቡን ወረወረው!

አይ ስኳር!

አንተን በሚቅመው በከርሳም ምክንያት፣
ስንት ሕዝብ አለቅ በሰላሳ ዓመት ውስጥ?

አንተን እየላሰ እየቃመ ሊኖር፣
ስንቱ ገረድ ሎሌ የገዥ እግር ያጥባል?

አይ ስኳር!

ታጋዩ ጎመራ ነፃ ወጣ ሲባል፣
አንተን ይልስና ባርያ ሆኖ ያድራል፡፡

ብረት መዝጊያ አገኘን ብሎ ሲያስብ አእላፍ፣
ነድፈህና አሳስተህ ጥጥ አርገኸው እርፍ!

አይ ስኳር!

ሕዝብን አስጨርግዶ አድር ባይ ሲቅምህ፣
ምነዋ በቁጪት መርዝ መሆን አቃተህ?

አይ ስኳር!

ተበለሱ ፍሬም ብሰህ በማማለል፣
ለሰይጣን ሰጠኸው ስንቱን ነጥቀህ ተእግዜር!

አይ ስኳር!

በላይነህ አባተ ((abatebelai@yahoo.com)
የካቲት ሁለት ሺ አስራ አራት ዓ. ም.

ተጨማሪ ያንብቡ:  እሥከቀራኒዮ (የመኮንን ሻውል ግጥም)

2 Comments

  1. ማለፊያ ግጥም ነው። ዝንተ ዓለም ይህኑ ሲያልሱንና ስንልስ ነው ሃገሬው ሃገሩን የከዳው፤ ወንድም ወንድሙን የገደለው፤ አሁንም በየምክንያቱ በክልል ፓለቲካና በይገባኛል ጥያቄ የምንዣለጠው። ዓለም የጉልበተኞች መሆኗን ይኸው ዛሬ ነግቶ በዓይናችን አይተናል። ራሺያ ዪክሬንን በማጥቃቷ። ብቸኛው ሃያል ሃገር የተባለችው አሜሪካ የሶስተኛ ሃገሮችን በዚህም በዚያም ጉዳይ ጣልቃ እየገባች ከማፈራረሷ አልፎ ራሽያን ማስቆም አይቻላትም። የጀርመኑ የመከላከያ ሚኒስቴር ዛሬ ቦን ላይ እንዳለው “ጀርመኖች ራሺያን የሚገታ የጦር ሃይል የላቸውም”። ያኔ ከነጮች 1991 በፊት ታላቋ ሶቪየት ሳትፈራርስ አብረው የነበሩ ሃገሮችና በህዋላ በቃን ብለው ሃገር የሆኑ ሁሉ እንደ ዪክሬን በራሺያ ጥቃት ሊደርስባቸው ይችላል። ኔቶ አባል ሆንክ አልሆንክ ለራሺያ ግድ አይደለም።
    ይህ የራሺያ አካሄድ ለሌሎች ሃገሮች ሁሉ የከፋ ትምህርት የሚሰጥ ነው። የገቢያ ግርግር ለሌባ ይመቻል እንዲሉ በራሷ ልጆች በምትታመሰው የሃበሻ ምድርም አዲስ ጉድ ሊፈጠር ይችላል። ጉረኞቹ ሱዳንና ግብጽ ወረራ ሊጀምሩ ይችላሉ። አይደረግም ከማለት ሊሆን ይችላል በማለት መዘጋጀቱ መልካም ይመስለኛል። ያው ከላይ በግጥሙ እንደተገለጠው በቀጥታም ሆነ በእጅ አዙር እየላሱ የሚያስልሱን ስኳር አይደል ከነጻነት ወደ ባርነት፤ ከባርነት ወደ ነጻነት የሚያገላብጠን? አይጣል። የምችለው ስጠኝ ያሰኛል የአለማችን ሁኔታ። በቃኝ።

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share