የህሊና  እስረኞችን  ፍቱልን!!!! – ፊልጶስ

አምባገነኖች ከትላንቱ  ያለመማር  አባዚያቸው የሚገርም ነው፤ያውም እኮ የሚጠቅማቸው ለራሳቸው  ነበር። በተለይም የአፍሪካ አምባገነን ገዥዎች እትብታቸው በአንድ ምላጭ የተቆረጠ ይምስላል።

አንድነታችን ኣየፈረሰ፤ በጦርነት እየተለበለብንና   በተመጽዋችነት በምንሰቃይባት በ’ኛዋ  አገር፤ ገዥዋቻችን ከትንላቱ ለመማር ያለምፈልጋችን ግብዝነት  የሚያውቁት እነሱ ብቻ ይመስሉኛል።

—– የትላንቱ እንቅፋት፣ ዛሬም ይመታናል

የትላንቱ እሽከላ፣ ዛሬም ይጠልፍናል

ላለመማር-መማር ፣ እኛ ተምረናል።——

የኦነጋዊ ብልጽግና ኃይል ከጡት አባቱ ከወያኔ እንኳን ለመመራ ፍቃደኛ አይደለም።  በ’ርግጥ  አሁንም መምበሩን ተፈናጠው የሚፈነጩብን ትላንት ወያኔ ጠፍጥፎ የሰራቸው   ”እሰሩ ሲሏቸው- የሚደበድብ፤ ደብድቡ ሲሏቸው- የሚገሉ፤” በአጠቃላይ ”ሳይጠሯቸው አቤት!ሳይልኳቸው ወዴት፣!” ሲሉ የነበሩና፤ የህዝብን የስር -ነቀል ትግል ጠልፈው ”በተረኝነት” በህዝብና በአገር ላይ የሚፈነጩ የወያኔ ወራሾች ናቸው።

ለአገር አንድነትና ሰላም  እንዲሁም ለቤተሰብ ሲባል ኃላፊነት የሚሰማው መንግሥት የፍርድ ወንጀሎኞችን እንኳን በይቀርታ ይፈታል። የኛዎቹ ተረኞች ግን  መጀመሪያ ”ሳናጣራ አናስርም ” ብለው  የሰበኩበት እንደበታቸው ሳይዘጋ፣   የካንጋሮ ፍርድ ቤት እንኳን ያልፈረደባቸውን  የባልደራስ አመራራ አበላትን ፤ እስክንድር ነጋ፣ ስንታየሁ ቸኮል፣ አስቴር ስዩም እና አስካለ ደምሌ እስከዚች  ሰዓት ድረስ  ከአንድ ዓመት በላይ ያለፍርድ እስር ቤት ታጉረው ይሰቃያሉ።  ከዚህ ላይ በጣም ”ቋቅ” የሚለው ነገር እነ እቶ እስክንድር በሽብርተኛነት መከሰሳቸው ነው። ተረኝነት፣ የወያኔ ግልባጭ።

አገራችን በውስጥም በውጭም እንደ ገና ዳቦ በምትነድበት በዚህ  ሰዓት፤  የህሊና እስረኞቹ እነ  አቶ እስክንድርን ይፈታሉ ብለን ስንጠብቅ፤ ይባስ ተብሎ  ”ሃሳባችሁን ለምን በነጻነት ገለጻችሁ ” ተብልው፤  አቶ ታምራት ነገራ ፣ ወ/ት መዓዛ መሐመድና ሌሊችንም ጋዜጠኞች ወደ እስር ቤት ተወረወሩ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከሰሞኑ በብጹዕ አቡነ ጴጥሮስ ላይ የደረሰው እንግልት አንጀቴን በላው።

‘’ሽግግር መንግስት መስርተናል!” ያሉ፤  በአራትና በስድስት ኪሎ ጎዳናዋች እየተጎማለሉና እየደነፋ፤  እነ አቶ እስከንደር  ነጋንና  ሃሳብን በነጻነት የመግለጽ  መብታቸውን ገፎ ጋዜጠኞችን  አስሮ ማሰቃየት ፤ የተረኞች ዓልማና ግብ ቢሆንም ህዝብ ግን  ራሱን መጠየቅና ለማስፈታት መንቀሳቀስ  አለበት። ፍትህ ከሌለ የአገር አንድነትም ሆነ ኢትዮጵያዊነት ሊጸና አይችልምና።

ፓለቲከኞች  በፓለቲካ መለካከታቸው፣ ጋዜጦኞች በሚሰጡት ሃሳብ  ላንስማማ እንችላለን፤ ግን ለተረኞቹ ማስገንዘብ የምንፈልገው  ፍጹም መብታቸው መሆኑንና፤ ነገ – ከነገ ወዲያ ዋጋ  ዋጋ እንደሚያስከፍላችሁ ልናሳስባችሁ እንወዳልን።

ህዝብንና አገርን በጦርነት አሮንቃ ውስጥ ከቶ፤ ሌላ ነገር እንዳይሰማ  በማደናቆር ፣ በአስቸኳይ አዋጅ ስም እንደፈልግን ”ማሰርና መግደል” እንችላለን የሚለው መንገድ የትም አያደርስም።  ህዝብ ከአገር እንድነትና ከኢትያጵያዊነት የሚበልጥ የለም ብሎ ስለታገሰ ፤ ትግሥቱን መፈታተን ለማንም አይበጅምና  ፍትህን እንጠይቃለን።

መቸም እውነት  እንነጋገር ከተባለ ፤ እቶ እስክንደር የታሰረበትን  ምክንያት ከማናም የበለጠ  በወያኔ ዘመን የትግል አጋሮቹ የነበራችሁ፤  ፎቶውን ጨረታ እያወጣችሁ የነገዳችሁ  በውጭና በአገር  ውስጥ የምትኖሩ ኢትዮጵያዊያንና በእስር ቤት አብራችሁ የተሰቃያችሁ ሁሉ ሃቁን ታውቃላችሁ ፤ ታዲያ  በ’ሱ ጉዳይ ዝም ብትሉ ህሊናችሁና ታሪክ ዝም አይላችሁምና፣ አሁንም አልዘገያችሁም ፤ ለፍትህ ስትሉ ድምጻችሁን አሰሙ።

ጋዜጠኞች የሆናችሁ፤ የሞያ አጋሮቻችሁ እነ እቶ ታምራት ነገራ፣ እነ ወ/ት መዓዝ መሃመድን  ሌሎቹን ጋዜጠኞች አሳስራችሁ ፤ ድምጻችሁን ማጥፋታችሁ፤ የሙያው ሥነ-መግባርም አይፈቅድላችሁም፤ ከታሪክና ከህሊና ተጠያቂነትም ነጻ አትሆኑምና ለትጮሁላቸው ይገባል።

ከዚህ ላይ እንደ ምሳሌ   የህሊና እስረኞችን የባልደራስ አመራር አባላትንና  የጋዜጠኞች ጉዳይ  አነሳሁ እንጂ፤  ፍትህ ሙያ ወይም ጾታ ወይም ሃይምኖት የሌለው፤ የሰው ልጅ  ተፈጥሯዊ መብት  በመሆኑ ሁላችንም በአንድነት ለፍትህ መታገልና መጮህ እንዳለብን  ማስገንዘብ እወዳለሁ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የኢትዮጵያ ካሽሚር የሆነው የወልቃይት ጠገዴ ጉዳይ ሊፈታ የሚችለው በወታደራዊ ሃይል ብልጫ ነው!!!

እናም ……ፍትህ ለህሊና እስረኞች!!!!!!

 

ኢትዮጵያ ለዘላለም ትኖራለች

——-//——ፊልጶስ

E-mail: philiposmw@gmail.com

ታህሳስ 2014

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

 

1 Comment

  1. ህሊና በጠፋበት ምድር ላይ የህሊና እስረኞች ይፈቱልን ማለቱ ያስቸግራል። ግን ድምጻችን ስለ እስረኞቹ ከማሰማት ወደ ኋላ አንልም። እየቆየ የዶ/ር አብይ መንግስት ወያኒያዊ ባህሪ እያሳየ ለመሆኑ ማስረጃዎች አሉ። የሚገርመው ግን በፊትም ዛሬም የሚታሰሩትና በግፈኞች ሃበሳቸውን የሚቆጥሩት ለሃገር አንድነትና ለህዝቦች ጥምረት ቆመው ኢፍትሃዊ የሆኑ ነገሮች እንዲገቱ የሚጠይቁት ናቸው። ከዚህ በላይ ደግሞ የሚያሳዝነው የታሰሩትን ለመጠየቅና ስንቅ ለማቀብል የሚንገላቱት ወገኖቻችን ሰቆቃ ነው። የዘረኛው ግልምጫ፤ የሉም እዚህ፤ እዚያ ናቸው ተብሎ መንገላታቱ፤ ሲልላቸውም አፍሰው ማሰራቸው የክፋታቸውን ጥግ ያሳያል። አሁን ህሊና ያለው ሰው መዓዛንና ታምራትን ያስራል? እውነቱን ከሚናገሩ ወገንን ከሚረድ ጥቂት ድምጾች ፊት ለፊት የሚታዪት ነበሩ። የሰው ልጅ የመናገር፤ የመጻፍ፤ የመሰብሰብ፤ አንድን የመተቸት መብቱ ያልተጠበቀባት ይህች ሃገር እየቆየ የተሻለ ነገር ይመጣል ብለን ስናስብ ተመልሰን የፓለቲካ አሻጥር ማጥ ውስጥ መግባታችን የሃገሪቱን የላሸቀ የፓለቲካና የእይታ መሻገት ያሳያል። በማፈን፤ በመግደል፤ በመሰወር፤ ከሃገር በማስወጣት፤ ከሥራ በማባረር የሰውን እምነትና አስተሳሰብ መቀየር አይቻልም። ያው የፍትጊያችን ቋጥሮ ያጠብቀውና የመፍቻ ውል ያሳጣናል እንጂ። ይህ የፓለቲካ አሻጥር በየደረጃው ከንጉሱ እስከ ወያኔ ተሞክሮ ታይቷል። አልሰራም። አይሰራም።
    የእስር ቤቶችን ሁሉ ወና እናረጋለን፤ ፍትህና የሰው ልጆች መብት የተከበረባት ኢትዮጵያ እንመሰርታለን ተብለን ብዙም ሳይቆይ ወያኔ መብረቃዊ ጥቃት ፈጽሞ አሁንም ሰማዪ ሳይጠራ እያጉረመረመ በመገዳደል ላይ እንገኛለን። በውጭ ያለው የሃበሻ ክምችት ብዙው በሃገሩ ጥቂቱ በዘሩና በቋንቋው ተሰልፎ ይፋለማል፤ ያፋልማል፤ እሳት ያቀብላል። ዛሬ በትግራይ ከአንድ ቤት አንድ ልጅ ተብሎ ያ ሁሉ አልበቃ ብሎ አሁን ደግሞ ለታላቋ ትግራይ ከአንድ ቤት ሁለት ልጅ አምጡ ተብለው በማዋጣት ላይ ይገኛሉ። ሰው ግን እንዴት አይነቃም? የትኛዋ ትግራይ ናት ይህን ሁሉ ህዝብ የምታስገብረው? ማን ቆሞ ማን ሞቶ ነው እፎይታ የሚመጣው? አፋቸው ለከት የሌላቸው የዘር ፓለቲከኞች ከዚህም ከዚያም ጎራ አካኪ ዘራፍ እያሉ መጨራረስ ማንን ነው የሚጠቅመው? በቅርቡ ሁለት የትግራይ የኦርቶዶክስ ቤ/ክ መሪዎች ስለ ሰላም መስቀላቸውን አስቀድመው በአማረ የአማርኛ ቋንቋ ጥሪ ሲያደርጉ በትግራይ ቲቪ አየሁ። ሌላው ሲቪል ለባሽ ደግሞ እነርሱን ተከትሎ ተመሳሳይ ቃል አሰማ? ጥያቄው ግን እነዚህ ሰዎች የት ነበሩ? ይህ ሁሉ እልቂትና ደም መቀባባት ሳይመጣ ለምን ድምጻቸው አልተሰማም? መልሱ አጭር ነው። ያኔ ቢፈልጉም ወያኔ አይፈቅድላቸውም። አሁን ወያኔ መጠራቅቅ ውስጥ ስለገባ ተናገሩ ተብለው ነው የሚለፈልፉት። ይህ ነው የትግራይ ነጻ አውጭ ድርጅት ባህሪ ገደል በገባ በሬ አርሳለሁ ብሎ ሞፈርና ማረሻ ማንሳት። አሁን ማን ይሙት የአማራና የአፋር ህዝብ ከትግራይ ጋር አብሮ መኖር ይመኛል? ጭራሽ። የወያኔ ጭፍራ በሆቴሎች፤ በት/ቤቶ/በህክምና ተቋማት/በንግድ ቤቶች በቀይ፤ በቢጫ፤ በአረንጓዴ ቀለም የጻፉትን ብቻ መዝግቦ በመያዝ (በትግርኛና አማርኛ ነው የተጻፉት) የተፈጸመውን በደል ካፈረሱትና ከዘረፉት ሃብት ጋር ለትግራይ ህዝብ ማሳየት ይቻላል። አብሮ የሚኖር ሰውን አህያ እያለ መነኩሴ፤ ህጻናትን አይደፍርም። ከባልና ከልጆች ፊት ሚስትን ደፍሮ የቤቱን አባወራ አይገልም። ወያኔና ጭፍሮቹ የሰው አውሬ ናቸው የምንለው በመረጃ ነው። የአሜሪካና የአውሮፓ የወያኔን በደል ማስተባበልና ደጋፊ ሆኖ መቅረብ ሊቢያን፤ ሶሪያን፤ ኢራቅን፤ ወዘተ ያፈረሱ ሰይጣኖች በመሆናቸው በእነርሱ የወያኔ ድጋፋዊ የአዞ እንባ የወያኔ ፋሽሽት መሆን አይሸፈንም። ስራቸው ለህዝባችን በግልጽ ታይቷንልና።
    ወያኔ ሰላምን ከጅምሩ ጀምሮ አያውቃትም። የሚገባው እሳትን በእሳት ሲመለስለት ብቻ ነው። ጀግና፤ ወርቅ ህዝብ፤ ደርግን ያንበረከከ፤ ተራራን ያንቀጠቀጠ እየተባለ በፈጠራ ታሪክ ውሸት የተጋተው የወያኔ መንጋ አሁን ገበሬው በማጭድና በአካፋ ጠበንጃ ሲቀማው ምን ይሰማው ይሆን? ይህ የወያኔ እብደት ከፈጸመው አንድ እውነተኛ ታሪክ ላካፍላችሁና ይብቃኝ። አንድ ከፍተኛ ወታደራዊ መኮነን አንዲት የትግራይ ሴት አግብቶ ለ 20 ዓመት በትግራይ መሬት ሶስት ልጆች ወልደው ይኖሩ ነበር። በወያኔው ጥቃት እጆቹ በስንሰለት የታሰረው መኮነን የትግርኛ ቋንቋን አቀላጥፎ የሚያውቅ፤ በወታደሩ ተወዳጅ በወያኔ አሽቃባጮች ሳይቀር ክብር ያገኘ ሰው ነው። እየገፈተሩ ሲወስድት ሚስቱና ልጆቹ ያያሉ። ሚስቱ ከፊታቸው ወድቃ ስትለምን በእርግጫ አንድ የወያኔ ሰው ይመታታል። ሌላው የትግራይ ወታደር የመታትን ይቆጣና አቁም ብሎ አንስቶ ልጆችን ከመኖሪያ ግቢያቸው አስገብቶ እንደሚፈታው ቃል ገብቶ መኪና ላይ በማሳፈር ታሳሪውን ወታደራዊ መኮነን ይወስድታል። የ 15 ዓመት እድሜ ያላት ሴት ልጅ እያለቀሰች እኔንም አብራችሁ ውሰድኝ እያለች ከህዋላ ከቀሩት የወያኔ ወታደሮች ጋር ትጮሃለች። ዝም በይ ግቢ አንቺም በጊዜሽ ትወሰጃለሽ ይላታል። እናትም ጎትታ ወደ ቤት ወስዳ በሩን ትዘጋለች። የባሏ ወሬ የጠፋባት ይህች የትግራይ ተወላጅ ሴት በየስፍራው ታጠያይቃለች። ከዚያ የኢትዪጵያ ሰራዊት መቀሌ ሲገባ መኖሩ ይነገራትና ለጊዜው መቀሌ እንዲቆይ ተመድቦ በቃ የእኔ ዘመዶች ደቡብ ኢትዮጵያ ይኖራሉ እንሂድ አድርሸሽ ልምጣ። ምንም አይቸግራችሁም ቢላት ትግራይን ትቼ አልወጣም ትላለች። በዚህ መካከል እሱ ይቀየራል። እሷም በድጋሚ አልሄድም ትላለች። ወያኔ ሽዋ መሬት ድረስ ሲገባ አዋጊ ሆኖ በአፋር፤ በሰሜን ወሎ ሲጓዝ ከተማረኩት መካከል የልጅን መሞትና የሞተችበት ቦታ ይነገረዋል። በሥፍራው ሲደርስ የልጅን አስከሬን ያገኝና አልቅሶ ይቀብራል። የልጇ እድሜ 16 አመት ከ 6 ወር ገደማ ነበር። የሃበሻ የውሻ ፓለቲካ እንዲህ ነው። በዘሩና በቋንቋው የሰከረ፤ ለሰው ልጅ መብትና ነጻነት ያልቆመ፡፤ ለዚያ ነው የዛሬዎቹ ገዥዎቻችንም የፓለቲካ እይታቸው ያላማራቸውን፤ ጋዜጠኞችንና ሌሎችንም እያፈሱ ባዶ ይሆናል የተባለውን እስር ቤት ከገጠር እስከ ከተማ የሞሉት። የጠራ እይታ ላለው ሃበሻው ያበደ ህዝብ ነው። የተከመረ ክምር አቃጥሎ ተራብኩ የሚል የጨካኞች ስብስብ። እውነተኛ ለውጥና አብሮ መኖር በሃበሻዋ ምድር ይሰምር ይሆን? አይመስለኝም። በቃኝ!

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share