በሻይ ቡና መላ፤ አለ ብልፅግና (መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ)

ዛሬም ፣ በዚህ የህዝብ የፍትህ ፣ የእኩል ተጠቃሚነት ፣ የእውነተኛ  ዴሞክራሲ መሥፈን ጥያቄ በወለደው  መንግሥትም ውሥጥ ጥቂት የማይባሉ  ከቀበሌ እሥከ ክልል ፤ እንዲሁም ልዩ የአሥተዳደር ክልሎች ( አዲስ አበባ ና ድሬድዋ ) ፤ በፊደራልና በክልል በሚገኙ የአሥተዳደር ና አገልግሎት ሠጪ ተቋማት ውሥጥ ያሉ ግለሰቦች  ያለ ጉቦ በዘመኑ አጠራር ፣ “ያለ ሻይ ቡና  ” አይሰሩም ።

” ሻይ ቡና ” የሚለውን ሥም ያወጡላቸው ደላሎች ናቸው ። ” ሻይ ቡና ካልክ መላ አይጠፋም ። ” ይሉሃል ። ምላጮቹ የአገሬ ደላሎች ።  ዘመናዊን የአሠራር  መንገድ  ለኪሳቸው መደለበ ሲሉ ” እንደሰማይ የሚያርቁ ”  የመንግሥት ተቋማት ነፍ ናቸውና የደላሎቹ  ጥቆማ ውሸት ነው ካልክ ጉዳይህን በእግርህ ብቻ አገልግሎት ሰጪው ቢሮ በመመላለስ ልተኩሥ አትችልም ። እንኳን መተኮሥ ማቀባበል እንኳን ይሣንሃል ።

አገልግሎት በሥርዓት የምታገኘው ፣ ሥርዓቱን በዘመነው በቴሌ ብቻ ነው ። ማለት ይቻላል ።

እርግጥ ነው ፣  ከቴሌኮሚኒኬሽን  በሥተቀር ከደላሎች ጋር  ተሻርከው ” በሻይ ቡና” ተጨማሪ   ደሞዝ ከአገልግሎት ፈላጊው  የሚከፈላቸው አገልግሎት ሰጪ የመንግሥት  መ/ቤቶች  እንዳሉ የታወቀ ነው ። መረጃ አለ ። ማሥረጃ ግን የለም  ።እናም ሌባ እጅ ከፍንጅ ካልተያዘ መሥረቅ ይችላል ። መሥረቅ ሥራ ነው የተባለው ዛሬም አልቀረምና ፣ ሌብነት ተጨማሪ ገቢ ማግኛ እሥከሆነ ድረሥ  ሌቦች መሥረቃቸውን አያቆሙም  ። አንተንም ማንም ቢሰርቅህ ( አውቀኽም ሆነ ሣታውቅ ) ሌባውን     ሢሠርቅህ እጅ ከፍንጂ እሥካሌያዝከው  ጊዜ ድረሥ በህግ ፊት ልታቆመው ከቶም አትችልም   ። ሌባ ብለህ ሥም ልታወጣለት አትችልም ።  ( ሻይ ቡና ያልከው እኮ ወደኽና ፈቅደህ ነው ። )

እናም በሻይ ቡና ሰበብ  የሚሰርቁ   የመንግሥት ሠራተኞች ሌቦች አይደሉም ።ናቸው ካልክ ጉቦ ሥትሰጣቸው    እጅ ከፍንጅ እንዲያዙ ማድረግ ይኖርብሃል ።እጅ ከፍንጅ እሥካልተያዙ ድረሥ   ሌቦች አይደሉምና !…

በየአገለግሎት ሰጪ የሠንግሥት ተቋማት ሁሉ   ፣ በመብራት ኃይል ፣ በውሃ አገልግሎት ፣በቀበሌ ፣ በማዘጋጃ አገልግሎት ፣ በየግብር ሰበሳቢ መሥራ ቤቱ፣ በየመንግሥት ሆሥፒታሉ ጭምር  ግለሠብን እና መንግሥትን የሚሰርቁ አሉ ። በየቀበሌው  ፣ ተራ አገልግሎት ሰጪዎች ፣ የፍትህ አካላትን ጨምሮ ያለሻይ ቡና ግዴታቸውን ለመወጣት  እጅግ ዳተኞች የሆኑ ግለሰቦች እንዳሉም ይታወቃል  ።  ወቅታዊ ምላሽ የሚጠይቅ የቃልና የፅሑፍ አቤቱታን ጭምር  ሻይ ቡና የሌለው መሥሎ ከታያቸው ጆሮ ዳባ ልበሥ በማለት  ፣ ለማሥተናገድ ፍቃደኞች  ያልሆኑ በሽ ናቸው ። እነዚህ የሻይ ቡና ልክፍተኞች   ሁሌም ሥብሠባ ላይ መሆናቸውን ፣ሁሌም በቀጠሮ ባለጉዳይ ሸኝነታቸውን  ፤ አሁኑኑ መጥተን እንፈፅማለን እያሉ የውሃ ሽታ መሆናቸውን    ፤     ወዘተ ። በማለት ሲሸነግሉህ ፣ በማሥተዋል  ሻይ ቡና በለን “ እንድትላቸው መፈለጋቸውን በቀላሉ ትረዳለህ   ። ግን እኮ ደሞዝ የሚያገኙበት መደበኛ ሥራቸው  ነው ። ለ ምን ይሆን መንግሥት የጣለባቸውን ከባድ ኃላፊነት ዘንግተው  ፣ ህዝብ መንግሥትን እንዲያማርር የሚያደርጉት ?

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከዕዉነት ሽሽት…አስከ የት ? - ማላጂ

ለምን ይሆን ፣ ያለአንዳች ይሉንታ  ከደላሎች ጋራ ተመሣጥረው  “የሻይ ቡና መንገድ ”  አመቻችተው የግል ኪሳቸውን በመሙላት የመንግሥትን ከፍተኛ አመራር ተወቃሽ ለማድረግ ያለዩልንታ ዜጎችን እጃቸውን በመጠምዘዝ ገንዘብ የሚቀበሉት ?

ይኽ ጥያቄ ፣ በወጉ መልሥ ማግኘት እንዲችል ፣ ከፍተኛው የመንግሥት  አመራር ቆም ብሎ ራሱን መፈተሽ አለበት   ። …

ዛሬ፣ዛሬ ፣ ለግል ኪሣችው መሙላት ሌት ተቀን የሚጣጣሩ ፣ ያለጉቦ የማይሰሩ  ፣ አይደለም በሲቪል ሠርቪሱ በመንግሥት የልማት ድርጅቶችም እየተበራከቱ ነው።  በጨረታና በግዢ ወዘተ ። ኮሚሽን የተለመደ ነው ። …

በግለሰብ ደረጃ ከላይ እሥከ ታች ተቧድኖ መጠቃቀም ፣ በትርፍ ሰዓት ክፍያ  ግለሰቦች ሻይ ቡና እየተባባሉ መጠቃቀም ። ሆን ተብሎ በሚቀነባበር ለ15 ቀን እና ለወር በሚቆይ የመሥክ ሥራ አሳበው   ውሎ አበል የሚከፈላቸው …  በዕደገት ፣ በቅጥር ፣ ወቅት በሻይ ቡና ተደልለው ፈተና የሚሸጡ ና ለቦታው የማይመጥን ሰራተኛ የሚቀጥሩ  እንዳሉ  ፣  ከሠራተኞች ብሶት መረዳት ይቻላል ።

በጨረታዎች ፣ ግዢ ና ሽያጮች በሙሉ ላይ “ የሻይ ቡና መላ “ ም  ይሥተዋላል ። ይኽ  የግለሰቦችን ኪሥ የሚያደልብ  አገርን የሚያከሥር  “የሻይ ቡና የሌብነት መላ ” እንዲወገድ መንግሥት  ዘመናዊ የቁጥጥር ሥልትን እና ከሌብነት የፀዳ ከፍተኛ አመራርን በየተቋማቱ በመመደብ የሌብነትን መንገድ መዝጋት  ለወደቀው ኢኮኖሚ ማንሠራራት ዐይነተኛ ሚና ይጫወታል ተብሎ የታመናል ። ይኽን አይነቱን  ህዝብን  አሥመራሪ ና አሥኮራፊ  ተግባር ባልተራዘመ ጊዜ ውሥጥ ለማጥፋትም  አዲስ የአሠራር መንገዶችን ከቀደመው ኢህአዴግ በተለየ መልኩ መቀየሥና መገንባት አሥፈላጊ ነው   ። …

አዲስ ከሙሥና የፀዳ  መንገድ ከመገንባቱ    ጎን ለጎን ፣  ጥብቅ ቁጥጥር የሚያደርግ አንድ ወጥ ሀገራዊ ተቋም ያሥፈልጋል ። ይኽንን ተቋም በአዲሥ  መመሥረት ሣያሥፈልግ  የፀረ ሙሥና እና የሥነምግባር ኮሚሽንን የአሠራር ክፍተት በመገምገም ጥርስ እንዲኖረው አድርጎ    ማደራጀት  ብቻ በቂ ነው  ።  አሁን በፊደራል ደረጃ  ሆነ  በየክልሉ ያለ ፀረ ሙሥና ኮሚሽን የሚገባውን ያህል ሙሥናንን የመከላከል ሚና ያልተወጣው ፣ ደሞዝ የሚከፍለውን እና የበላዩ የሆነን የአንድ የመንግሥት ተቋምና ድርጅት ተጠያቂ የማደረግ አቅም ሥለሌለው ነው ። በመሆኑም ኮሚሽኑ ከተፅዕኖ ነፃ ወጥቶ ጥርሥ ያለው አንበሣ ካልሆነ በሥተቀር የመንግሥት ባለሥልጣናት ( ከዝቅተኛ እሥከ ከፍተኛ አመራር ያሉት )  ኮሚሽኑንን ፈርተው በሥርዓት ህዝብን ማገልገል አይችሉም ። በአንድ ሥርዓት ውሥጥ ተቆጪ እና ቀጪ የመንግሥት ባለሥልጣን እሥከ ሌለለ ጊዜ ድረሥ የመንግሥት ሌብችን መቆጣጠር አይቻልም ። የመንግሥት አሠራር  አሠራርም ግልፅ በሆነ በተጠያቂነት መንገድ ሊሣለጥም አይችልም ።የመንግሥት አሠራር   ግልፅ  መሆን የሚችለው ያልተወናበደ የአሠራር ሢሣተም በመዘርጋት ና በዛ ውሥጥ አገልግሎት ሰጪውና ተቀባዩ እንዲያልፉ በማድረግ  እንደሆነ ይታወቃልና ይህን መንገድ ለመገንባት የግድ የፀረ መሥና እና የሥነምግባር ኮሚሽኑንን አሠራር  ፣ ሥልጣንና ኃላፊነት  ከወቅቱ ጋራ ማዘመን ያሥፈልጋል ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የኒዎ-ሊበራል ኢኮኖሚ ፖሊሲ ያስከተለው አሉታዊ ውጤት በኢትዮጵያ!!

አሠራርን ማዘመን ሲባል ፣ የግለሰቦችን ብዝበዛ በማሶገድ የመንግሥትን ገቢ ማሣደግ የሚያሥችል ግልፅ የአገልግሎት ሥርዓት ከተጠያቂነት ጋር መዘርጋት ማለት ነው ። ለምሳሌ ብንመለከት    ከመብራት   ኃይል ጀምሮ የአሠራር ሲስተሙ መቀየር አለበት ። የመንግሥት መ/ቤቶች የገንዘብ አሠባሠብ  ለምንተፋ የተጋለጠ መሆን አይገባውም ።  የገንዘብ አሰባሰብ ግዴለሽነት  እና የቡድን ዘረፋን ለማሥቀረት የመንግሥትን ገቢ በሚሰበስቡ መ/ቤቶች ሁሉ ጥብቅ ቁጥጥር ለማድረግ ዛሬውኑ መነሣት አለበት ።

በሻይ ቡና ሠበብ ምርታቸው እንዳይሸጥ የሚያደርጉ የመንግሥት የልማት ድርጅቶችም አሠራራቸው በቅጡ ሊፈተሽ ይገባዋል ። ፋብሪካዎቹ እየከሰሩ ኃላፊዎቹ እየበለፀጉ መታየቱ ሠበቡ ምንድነው ?? የሚል ጥያቄም መንግሥት ሊጠይቅ ይገባዋል ።     ለምን የጥሬ እቃ ግዣዎች ጨረታ ግልፅና ተጠያቂነት ያለበት የማይሆነው ? የውጪ ምንዛሬ የአገር ሀብት አይደለም ወይ ? በጥሬ ዕቃ ግዢ መዘግየትሥ ፋብሪካዎች ለምን ይቆማሉ ? ለወራት ያለምርት   ለሠራተኛ ደሞዝ  መክፈልሥ  ኪሳራ አይደለም ወይ ?  ወይሥ በአገር ውሥጥ ግዣ ጨረታ ሻይ ቡና እንዳለ ሁሉ ፣ የውጪ የጥሬ ዕቃ ግዢ ላይም ሻይ ቡና አለወይ ? የሚሉ  ጥያቄዎችን የሚመለከታቸው   የመንግሥት ከፍተኛ አመራሮች ማንሳት ይጠበቅባቸዋል ።      ። (…)

በደምሣሣው ፣ ህዝብን በሻይ ቡና ካልሆነ ለማሥተናገድ ዳተኛ የሆኑ የመንግሥት ባለሥልጣኖች እየበዙ መጥተዋል ።አደጋ ካልደረሰ ማንኛውንም የህግ መሥከበር ሥራ ለመከወን ተነሳሽነት የሌላቸው የፖሊሥ አካላት አሉ ። የትራፊክ ፖሊሰሶችን ጨምሮ  ።  አደጋ እሥኪደርሥ የሚጠብቁ ፤ ሊወድቅ ያዘመመን ጎዳና ላይ ያለ የኤሌትሪክ  ፖል እያዩ  ሥጋት ያለው ሰው ሻይ ቡና ካላለን ፖሉን አንቀይርም ። ፖሉ ድንገት ወድቆ ፣ ኤሌትሪኩ እሣት ፈጥሮ ፣፣…   የሰው ህይወት ቢጠፋ ፤ በሚሊዮን የሚቆጠር ንብረት ቢወድም አይበርደንም ። አይሞቀንም ። ባይ የመብራት ኃይል ሠራተኞችም አሉ ። በየቀበሌው ማዘጋጃም ከቀበሌ መታወቂያ ጀምሮ የሻይ ቡና መላ ከሌለ በህግ አግባብ ለማሥተናገድ ቅር የሚላቸው ፣ የሌለ ቢሮክራሲ በመፍጠር ተገልጋዩን የሚያጉላሉ ሞልተዋል ። በገቢ ሰብሳቢ መሥራ ቤት ና በጉምሩክ ሂደቶም የሻይ ቡና መላ ከነደላላው ጓዙን ጠቅልሎ ገብቷልና መንግሥት በጊዜ አዲሥ መላ ና ዱላ ማዘጋጀት አለበት ብሎ ይኽ ፀሐፊ ያምናል ።

በነገራችን ላይ የሌባ ብሔር የለውም ። ሌባ ሌባ ነው ። የእኔ ብሔር ነውና የሚዘርፈው ተውት ። ማለት ከጀመርን በዚች አገር የይሥሙላ ፍትህን እንጂ እውነተኛ ፍትህን አናሰፍንም እና የፊደራል መንግሥት በሁሉም ተቋሞቹና የልማት ድርጅቶቹ ሌቦችን የማያፈናፍን የቁጥጥር ሥርዓት ዘርግቶ ሥራዎች በጥራት የሚከናወኑበትን እና አገር ከድህነት የምትወጣበትን የሥራ መንገድ መቀየሥ ወቅታዊ ግዴታው ይመሥለናል ።

መንግሥት በሚኒሥትሮች ምክር ቤት አማካኝነት ልዩ አጣሪ ቡድን ፈጥሮ ፣ የመንግሥት መ/ቤቶችን አገልግሎት አሠጣጥጥ  ቢመረምር  ፣ በእያንዳንዱ የፊደራል  መንግሥት ና  የልማት ድርጅት ከዋናው ተቆጣጣሪ ባለሥልጣን እሥከታች ካለው ሥራ አመራር  ያለውን  ለብክነት የተጋለጠ አሠራር ህመም በቀላሉ ማወቅ ይችላል  ።

ተጨማሪ ያንብቡ:      “ ስጋት የተላበሰው ተስፋ” - ከገዙ በቀለ (ዶ/ር)

በምርመራውም ወቀትም  ከህሊና አንፃር በጣም ትንሽ የሚሆኑበትን ፣ ሥራ አሥኪያጆችና ምንም ችሎታ ሳይኖራቸው ኃላፊነት የተጫነባቸውን ዳሬክቶሬቶችን ያገኝና ጉድ !ጉድ ! ማለቱ አይቀርም ። ( በአበሽኛ ነው ጉዱ ። በእንግሊዘኛውማ  it is unbelievable ነው ። የሚለው ። )

እውነት ነው ። በእነዚህ ህሊና ቢሥ ትንሽ ና ትልቅ የመንግሥት ባለሥልጣናት አማካኝነት በየተቋማቱ አገር እየተዘረፈች ነው ። የህዝብ ኪሥም እየታለበ ነው ። የህዝብን ኪሥ ለማለብ ትልቁን ሚና የሚጫወቱት   አቀባባይ ደላሎች ናቸው ። “በሻይ ቡና ” ሥም ።

እነዚህ ደላሎች በሻይ ቡና ሥም ተገልጋዩን እያግባቡ ፣ ከጥቃቅን ሙሥና ( መታወቂያ እሥከ 1000 ብር ከማሥከፈል ) እሥከ ከባዱ ሙሥና ( ግብርህ ዝቅ የሚልበትን መላ በመፍጠር እሥከ 100000 ሺ ) ጉቦ የማሥከፈል ሤራ ውሥጥ   አታጣቸውም ።

እነዚህ ደላሎች ፣ አንተን የሙሥና ተባባሪ ለማድረግ የማይፈነቅሉት ዲንጋይ የለም ። ጤፍ በሚቆላ ምላሳቸውም እንዲህ እያሉ አዳሜን ያሳምኑታል።

” የሻይ ቡና ክፈልና  በመላ ጉዳይህን ሣይውል ሣያድር  እናሥፈፅምልህ ። ሞኝ አትሁን ። አንድ ሃቀኛ በሌለበት ምድር ሃቅ ፣ እውነት ፣ ህግ ና ፍትህ አትበል ። በፍትህ አካላትም መሠል ሻይ ቡና ነፍ ነው ። ከእኛ የተሰወረ የለም ። ወንጀልን ተከላካይ እና ለሃቅ ሞች ፖሊስ እንዳለ ሁሉ ፣ ወቅትን ፣ ጊዜን እና ሁኔታዎችን ተጠቅሞ ፣  ከአቅም በላይ የሻይ ቡና ክፈል የሚልህ ህሊናውን የሸጠ የፍትህ ተቋም አባል አለ ። … እውነት ፣ ሃቅ ፣ ፍትህ ፣ እርትህ ፣ የማያዳላ አሠራር በየክልሉ በእኩል መጠን በሁሉም ቀበሌ የማታገኘው ሲስተሙ ያውና የው በመሆኑ ነው ። …ህዝብ ዛሬም ለምን ብሎ የመጠየቅ እና መልሥ የማግኘት ነፃነት በሁሉም ክልሎች በእኩል ደረጃ የለውም ። በእርግጥ በአዲስ አበባ ያለው ጠያቂ ህዝብ በአዳማ ባይኖር ፣ በሠበታ ባይኖር፣ በድሬደዋ ባይኖር አይግረምህ ?  እወቅ ህዝብን ማሥተዳደር ና መምራት ከራሱ ከህዝቡ የተሰጠው መሆኑንን የማይረዳ ሁሉ ለምን ? ይህ ህጋዊ አይደለም ? የሚያሥጠይቅና ዘብጥያ የሚያወርድ ነው ቢል ፣ ማነው ያንን ሌባ ፣ ዘራፊ ፣ ፍርደ ገምድል ባለሥልጣን ዘብጥያ የሚያወርደው ? ማን ላይ ነው የምትከሰው ? አባቱ ዳኛ ልጁ ቀማኛ ሆኖ የሚገኝበት ጊዜ አለ ። በዛ ላይ ደግሞ ገና በቋንቋ ሰው ከመፈረጅ አለወጣንምና “አይሰማም ! ” የሚልህ ከፍተኛ ባለሥልጣንም ያጋጥመሐል ።  የመንግሥት አገልግሎት አሠጣጥ ብቻ ሣይሆን  ግብይት በራሱ   ደላላ መር ሆኗል ።  በሻይ ቡና መላ ደላላ የሚዘውረው ።…

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share