ወደ ሃቀኛ ብሄራዊ መግባባት! – ገለታው ዘለቀ

በኢትዮጵያ ውስጥ ብሄራዊ መግባባት ወይም ምክክር የምንለው ሃሳብ ከጦርነት አቁም ስምምነት ሁሉ በላይ ነው። ሃገራችን ወደ ለውጥ መሄድ ካለባት አሁን ያለው ጦርነት ባይኖርም ብሄራዊ መግባባት ያስፈልጋል።  ብሄራዊ መግባባት አስፈላጊ ጉዳይ የሆነበት ምክንያት ሃገራችን ኢትዮጵያ የረጋ ቅርፀ መንግስት የሌላትና እንዲሁም በአያሌው ስምምነት ላይ ያልተደረሰበት መተሳሰሪያ መርሆዎችን ታቅፋ የምትኖር ሃገር ስለሆነች ነው። ስለሆነም የሽግግራችን ምክክሮች በአብዛኛው መተሳሰሪያ መርሆዎቻችንን ሁሉ እንደገና እየከለስን በፅሞና እንድናይ በር የሚከፍቱ መሆን አለባቸው።

የመተሳሰሪያ ዋና ዋና መርሆዎቻችንን እያነሳን ስንወያይ ህገ መንግስታዊ ማሻሻያዎችን እንድናደርግ የሚያስገድድ ሁኔታ ውስጥ ያስገባናል። ችግሮቻችን ሁሉ ከዋና ዋና መተሳሰሪያ መርሆዎች በታች ቢሆኑ ኑሮ ውይይታችን ሁሉ በህገ መንግስቱ ማእቀፍ ስር ብቻ ይወድቅ ነበር። ነገር ግን ህገ መንግስቱ ላይ ያሉ አንዳንድ ገዢ መርሆዎች ራሳቸው ጥያቄ ውስጥ የወደቁ በመሆናቸው ህገ መንግስቱ ለሃገራዊ ምክክሩ መውጫ ሆኖ አይታይም። ለዚህ ነው ሃገራችን ወደ ተሻለ ምእራፍ እንድትገባ ሁሉን አቀፍ ምክክር ያስፈልጋል የሚያሰኘን። ምክክሩ ፈጭቶ አሳምሮ ያመረተው ሃሳብ ለህገ መንግስት ማሻሻያ ዋልታና ማገር እያቀበልን የጋራ ቤታችንን ጥሩ አድርገን እንድንሰራ ያደርገናል። በመሆኑም ብሄራዊ መግባባቱ ሁሉን አቀፍ ሆኖና ሃቀኛ ሆኖ ፍሬ ካፈራ በውጤቱ በተሻለ መተሳሰሪያ መርሆ በተከሸነና በፀዳ ህገ መንግስት ወደፊት ሊያራምደን ይችላል። ለዚህ ምክክር አጀንዳ ናቸው ያልኳቸውን ሃሳቦች እንደገና ከዚህ ቀጥሎ ላንሳቸው። ጠቃሚ ናቸው።

1. በህብረታችን ወይም በአብሮነታችን ፍፁምነት  ላይ። ህብረታችንና የጋራው ቤታችን በምን ያህል አቅም ወይም በምን ያህል የአብሮነትና የወዳጅነት የቃልኪዳን ልክ ይታተም? የሚለው ዋና የምክክር አጀንዳ ነው። አሁን ያለው መተሳሰሪያ መርሆ የህብረታችንን ልክ በመገንጠል የወሰነው ሲሆን አሁን ይህንን የህብረት ልክ እንዴት እናሳድገው የሚለውን ቁልፍ ጉዳይ ነው :: ለዚህ ነው Towards a More perfect Union እያልኩ የፃፍኩት:: ውይይታችን የጋራውን ቤት ፍፁም ወደ ማድረግ እንዲሆን መወያየት ያስፈልጋል ::
2.  በቅርፀ መንግስት ላይ ምክክር ያስፈልጋል ። ቅርፀ መንግስት በምርጫ መንግስት ሲመጣና ሲሄድ የሚቀየር አይሆንም። በዚህ አንድ ኢትዮጵያን የመሰለ ቅርፀ መንግስት መስፋት አለብን። ይህ ጉዳይ ሀገሪቱ ፓርላመንታሪ ትሁን ወይስ ፕሬዝደንሺያል? የፌደራል ሥርዓቱ ምን መልክ ይያዝ? የመንግስት ቅርፁ ምን ይጨምር ምን ይቀንስ? ለምሳሌ የህገመንግስት ዳኛ ይኑር ወይስ እንዴት እንቀጥል ወዘተን ይመለከታል ::
3. ብሄራዊ ማንነትንና የብሄር ማንነትን እንዴት እንንከባከብ። በምን አይነት ምህዋር ይዙሩ? እንዴት ሳይጠላለፉ ይኑሩ በሚለው ላይ ምክክር ያስፈልጋል።በማንነቱ ፖለቲካ ላይ ውይይት ያስፈልጋል ::
4. ብሄራዊ ምልክቶችን በተመለከተ መመካከር ያስፈልጋል። ባንዲራን መዝሙርን ወዘተ ይመለከታል።
5. የመሬት ላራሹ ጥያቄ ምክክር ውስጥ መግባት አለበት። የፓሊስ ቀጭን ጉዳይ አይደለም ይህ አጀንዳ።
6. ያለፈ መጥፎ ትውስታዎች እንዴት ይታዩ? (Past bad memories) የሚለውን ማንሳት ተገቢ ነው።
7. ቋንቋና ተግባቦትን በሚመለከት ውይይት ያስፈልጋል። ይህ ጉዳይ የአንድ ፓርቲ ፓሊሲ ሳይሆን የቋንቋ አያያዛችን ላይ የጋራ አቋም መያዝ ይቻላል።
እነዚህ ናቸው አጀንዳዎቻችን። በነዚህ ላይ የምናደርገው ስምምነት ህገ መንግስት የሚያሻሽሉ ሃሳቦችን ያመርትልንና ወደ ህገ መንግስት መሻሻል ስራ እንገባለን ስምምነቱ በጋራ ቃል ኪዳን ይፀናል ማለት ነው። ህዝቡም በዚህ ስምምነት ላይ ተሳትፎ ሊኖረው ይገባል። እግዚአብሔር ኢትዮጵያን ይባርክ።
ተጨማሪ ያንብቡ:  ያማራ ሕዝባዊ ትግል የመጨረሻ ግብ - መስፍን አረጋ

2 Comments

  1. ውድ አቶ ገለታው ዘለቀ፤

    ሃሳብህ ጥሩ ነው። በሌላ ወገን ግን በአገራችን ምሁራን ዘንድ ያለው ትልቁ ችግር ለምን ምን ዓላማ እንደምንታገል አለማወቃችን ነው። እንደምታውቀው ታጋይ ነኝ የሚል ወይም ደግሞ በፖለቲካ ዓለም ውስጥ እስታፈለሁ የሚል ሰው የግዴታ ለምን እንደሚታገል ወይም የመጨረሻ መጨረሻ ምን ላይ ለመድረስ እንደሚፈልግ ማወቅ አለበት። ማንኛውም በፖለቲካ ዓለም ውስጥ የሚሳተፍ ሰው ከመጀመሪያውኑ ማወቅ ያለበት ነገር ለራሱ ሳይሆን ለሌላ ሰው ወይም ለተበደለ ሰው ወይሞ ሰዎች እታገላለሁ በማለት ነው። ለምሳሌ በአንድ አገር ውስጥ ግለሰብአዊ ነፃነት ከሌለ፣ አብዛኛው ህዝብ በድህነት ዓለም ውስጥ የሚኖር ከሆነ፣ እንደሰው ለመኖር የሚያስፈለጉት መሰረታዊ ነገሮች የሚጎድሉት ከሆነ፣ አብዛኛው ህዝብ ከውጭ በሚመጣ ዕርዳታ በሚሉት ነገር የሚኖር ከሆነ፣ ብሄራዊ ነፃነቱ ከተገፈፈ፣ በአገር ውስጥ ከአንድ ቦታ ወደ ሌላ ቦታ የመንቀሳቀስ መብት ከሌለው፣ የህግ የበላይነት ከሌለ፣ ወይም ፖሊስ በጉልበት እየተነሳ በሰብ በአስባቡ አንዳንድ ግለሰቦችን የሚያስር ከሆነ፣ መንግስት የሚባለው ፍጡር ለህዝብ ተጠያቂ መሆኑን የማያረጋጋጥ ከሆነና የሚጠበቅበትን ተግባር የማያሟላ ከሆነ… ወዘተ. የዚያን ጊዜ እነዚህ ነገሮች በሙሉ እንዲስተካከሉና የመጨረሻ መጨረሻም ጠንካራ አገር መገንባት አለብኝ ብሎ የሚታገል መሆን አለበት። ለዚህ ደግሞ የግዴታ የጠራ ፍልስፍናና ሳይንሳዊ መሰረት እንዲኖር ያስፈልጋል። ምክንያቱም የአንድን አገር የተወሳሰቡ ችግሮች በትክክለኛው ሳይንሳዊና የቲዎሪ መመርመሪያ ዘዴዎች ማንበብና መፍትሄም ማቅረብ ስለሚቻል ነው። ከዚህ ሁኔታ ስንነሳ በመሀከላችን ያለው አለመግባባት በጠቅላላው ሰለሰው ልጅ ያለን አመለካከት ግልጽ አለመሆኑና፣ አንድ ምሁር ነኝ ባይም ምን መስራት እንዳለበት ወይም ተልዕኮው ምን እንደሆነ አለማወቃችን ነው። ይህ ግልጽ ከሆነና ሳይንስን ወይም ርዕይን መሰረት ያደረገ ትግል የምናካሄድ ከሆነ ስለሎች ጉዳዮች በሙሉ ቀስ በቀስ እያልን መነጋገር እንችላለን።
    ሌላው ያለው ትልቁ ችግር በፓለቲካ ውስጥ የሚሳተፍ ሁሉ ለስልጣን የሚበቃ ወይም ስልጣን ላይ ቁጥጥ የማለት መብት ያለው ይመስለዋል። አንድ ምሁር ነኝ ባይ የግዴታ ለስልጣን መታገል የለበትም። እንዲያውም አንድ ምሁር ነኝ ባይ በሰለጠነበት ሙያ ጥልቅ ምርምር በማድረግና አንድ ነገር በመፍጠር ህብረተሰብአዊ ኃላፊነቱን መወጣት አለበት መሆን አለበት። ለምሳሌ አንድ ፊዚክስ፣ ባዮሎጂ ወይም ሶስይሎጂ ወይም ደግሞ ኢኮኖሚክስ የተማረ ሰው የግዴታ በፖለቲካ ውስጥ ገብቶ ጊዜውን ማጥፋት የለበትም። እንደምታውቀው በፖለቲካ ዓለም ውስጥ የሚሳተፉ ወይም ስልጣን ላይ ቁጥጥ ያሉ ሁሉ ምንም ዐይነት የተፈጥሮ ሳይንስ ግንዛቤ የላቸውም። ስለሆነም አንድ ፊዚክስ ወይም ባዮሎጂ ወይም ደግሞ ኢኮኖሚክስ የተማረ ሰው ከእንደነዚህ ዐይነት ሰዎች ጋር በመግጠም ጊዜውን ማባከን የለበትም። ማድረግ ያለበት ራሱን ከእንደነዚህ ዐይነት ሰዎች በማራቅና ከተመሳሳዩ ጋር ሃሳብ ለሃሳብ በመለዋወጥ ሳይንስና ቴክኖሎጂ የሚዳብሩበትን መንገድ መፈለግ ያለበት።
    ስለሆነም በእኛ ፖለቲከኞች ነን በምንለው መሀከል ያለው ትልቁ ችግርና አለመግባባት ትግላችን በሙሉ ከሳይንስ ውጭ የሆነና ያለውን የህዝባችንን ችግር የሚያባብስ መሆኑን ያለመረዳታችን ነው። በእኔ ዕምነት ሳይንሳዊ መንገድን ተከትሎ የማይታገልና ለብሩህ አስተሳሰብ መዳበር አስተዋፅዖ የማያደረግ ሰው የኢትዮጵያን ውድቀት ነው የሚያፋጥነው። ከዚህ ስንነሳ ለብሄራዊ ዕርቅ ዋናው መፍትሄ በመጀመሪያ ደረጃ ራስን ማወቅ። ሰው መሆናችንን መገንዘብ አለብን። ራሳችንን ስናውቅና ሰው መሆናችንን የምንረዳ ከሆነ ሌላውን ተመሳሳዩን ወንድማችንን ወይም እህታችንን የምንገድልበት ምክንያት የለንም። አገርንም የምናመሰቃቅልበትና የህዝባችንን ኑሮ የምናከብድበት ምንም ምክንያት የለንም።
    ዶ/ር ፈቃዱ በቀለ

  2. ሁለተኛ ትችት ወይም አስተያየት መስጠት ከተፈቀደልኝ አንዳንድ ነገሮችን ማለት እፈልጋለሁ።
    እንደሚታወቀው በአገራችን ምሁሮች ዘንድ፣ በተለይም የብሄረሰብን አርማ አንገበው በሚታገሉ ሰዎች ዘንድ ያለው ትልቁ ችግር የኢትዮጵያን ታሪክ እንደፈለጋቸው የመተርጎሙ ላይ ነው። አንድን ብሄረሰብ እወክላለሁ ብሎ የሚነሳ ወይም የሚታገል ድርጅት ብሄረሰቤ ይጨቆን ነበር፣ ታሪኬና ባህሌ ተረግጦ ነበር፣ ረጋጩና ታሪኬንም ያንቋሸሸው እንደዚህ ዐይነት ብሄረሰብ ነው የሚል ከሆነ ከእንደዚህ ዐይነት አንድን ብሄረሰብ እወክላለሁ ከሚል ድርጅት ጋር ራሽናል በሆነ መልክ ለመነጋገርና አንድ የጋራ መፍትሄ ለመፈለግ አይቻልም።
    በአገራችን ያለው ትልቁ ችግር አብዛኛው ምሁራን የብሄረሰብን ትግልና ጥያቄ እንደመነሻ መወሰዳቸውና የእነሱን የታሪክ አተረጓገም አሜን ብለው መቀበላቸው ነው። ይህ ዐይነቱ አሜን ብሎ መቀበል በተለይም አንድ ህብረተሰብ እንደማህብረሰብ እንዲኖር ከተፈለገ ምን ምን ነገሮች ያስፈልጉታል? ከሚባለው መሰረታዊ ጥያቄ እንድናፈገፍግና ከሳይንስ ውጭ የሆነ ትግል እንድናካሄድ ወይም እንድንጨቃጨቅ ተገደናል። የህብረተሰብን ዕድገት ታሪክ በደንብ የተረዳ ካለ ማንኛውም ሰው በንጹህ መልኩ ከዚህ ብሄረሰብ ነው የተፈጠርኩት፣ ስለዚህም ከሌላው ጋር የሚያገናኘኝ ታሪክ የለኝም ሊል አይችልም። አንትሮፖሎጂስቶች ያረጋገጡት አንድ ነገር የሰው ልጅ ባፈጣጠሩና ባኗኗሩ ከእንስሳ ይህን ያህልም እንደማይለይ ነው። ቀስ በቀስ እያለ ግን ራሱ በራሱ ማግኘት ሲጀምር ፍራፍሬዎች እየለቀመ መብላት ይጀምራል። ራሱንም ከአውሬዎች ለመከላከል ሲል የግዴታ በአንድነት ከአንድ ቦታ ወደሌላ ቦታ ይጓዛል። እንደዚህ እያለ ፍራፍሬ እየለቀመ በመኖር ባለመደሰቱ አዳኝ ይሆናል። በመጀመሪያው ወቅት የገደለውን እንስሳ ወይም አውሬ ሳይጠብስ ነበር ጥሬውን የሚበላው። የኋላ ኋላ ግን እንዳጋጣሚ እሳትን በማግኘቱ እየጠበሰ መብላት ይጀምራል። እንደዚህ እያለ ከአዳኝነት ወደ እርሻ ተግባርና ወደ ተሻለ የስራ-ክፍፍል በመሸጋገር የተደራጀ ማህብረሰብ እየሆነ ይመጣል። ይህ የረጅም ጊዜ ታሪክ ሲሆን፣ በሂደት ውስጥ ሂራርኪያል ማህበር ሲፈጠር አንዱ ተሻልኩ ነኝ የሚለው ሌላውን በመዋጥ እይተቀላቀሉና ቋንቋንም በማዳበር ወደ ተሻለ የእድገት ደረጃ ይሸጋገራሉ ማለት ነው።
    ከዚህ ስንነሳ በአገራችን ምድር በፖለቲካ ስም የሚደረገው ትግል ተጣሞ መቅረቡና፣ ወድ ኋላ በመሄድ እንደዚህ እባል ነበር፣ ተጨቁኜ ነበር፣ በተሻለ ሁኔታ ውስጥ በምኖርበት ጊዜ አንድ ብሄረሰብና መሪ መጥቶ በመውረር ታሪኬንና ስልጣኔዬን አፈራረሰብኝ፤ ተዋርጄም እንድኖር አደረገኝ በማለት ከህብረተሰብ ህግና ከሳይንስ ውጭ የሆነ ነገር ይናገራል። እንደዚህ እያሉ የሚታገሉና በተለይም ባለፉት ሰላሳ ዓመታት ስልጣንን ተቆናጠው የህብረተሰብን ህግ ሲያጣጥሙ ከነበሩና፣ ዛሬም ስልጣን ላይ ቁጥጥ ካሉ አንዳንድ ሰዎች ጋር ራሽናልና ሎጂካል በሆነ መልክ በፍጹም ማውራት አይቻልም። ወደ ኋላ ተመልሶ ታሪክን ባዲስ መልክ ለመጻፍ የሚመከር ከሆነ ዛሬ በምድር ላይ አፍጠው አግጠው ያሉ እንደ ድህነትና ረሃብን የመሳሰሉ ነገሮችን እያነሱ መፍትሄ ለመፈለግ ጥረት አይደረግም ማለት ነው። ባጭሩ በአገራችን ያለው ትልቁ ችግር በአብዛኛዎች አገሮች የማይታይና የማይነሳ ጥያቄ እየተነሳ ማፋጠጡ ነው። ዋናው ትግላችን ሳይንስና ቴክኖሎጂና፣ በእነዚህም አማካይነት ህዝባችንን ከድህነትና ከረሃብ ማላቀቅ መሆኑ ቀርቶ ጭንቅላታችን መፍትሄ በማይገኝለት ነገር ላይ መያዙና መጨቃጨቁ ነው። ጥያቄዬ ለመግባባት ከተፈለገ ወይም ወደ ብሄራዊ ዕርቅ ለመምጣት ከተፈለገ ከላይ ያነሳኋቸውን ጉዳዮች በምን ዘዴ እንፈታቸዋለን ነው? ለማንኛውም ትልቅና ከአቅማችን በላይ የሆነ የቤት ስራ ተሰጥቶናል። እንደዚህ ስል ግን ተስፋ እንቁረጥ ማለቴ አይደለም። ከዚህ ዐይነቱ ትረካ ለመምውጣትና ራሽናልና ሎጂካል ወደ ሆነ የአስተሳሰብ ዘዴ ለመምጣት ስልት እንቀይስ ማለቴ ነው። ሳይንስን ወይም ትክክለኛ የሆነ ዕውቀትን የመፈተኛና የመታገያ ዘዴ እናድርገው ማለቴ ነው። አርባ ዓመታት ወይም ከዚያ በላይ በሄድንበት መንገድ መቀጠል አንችልም። ዘመኑ የሳይንስና የቴክኖሎጂ ዘመን እደመሆኑ መጠን አትኩሮአችን የበለጠ ዕውቀትን በመጎናፀፍና፣ በዚህ አማካይነት ዕውነተኛ ነፃነትን ለማምጣት የምንችልበትን ዘዴ መፈለግ አለብን ማለቴ ነው።
    ዶ/ር ፈቃዱ በቀለ

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share