ዝምተኛው ዳያስፖራ አንበሳ ሆኖ ተነሳ! – ሰማነህ ታምራት ጀመረ

እግዚአብሔር ዓዳምንና ሔዋንን ሲፈጥር ከእንስሳት ለይቶ የማስተዋል፤ የማሰብና በአግባቡ የመምራት ክህሎት ሰጦ በምድር ላይ አንግሶታል። ብዙ ተባዙ ምድርንም ሙሏት ሲል ቀደሰው። ኢትዮጵያንም የሰው ዘር መገኛ አርጎ ፈጠራት። በግዮን ወንዝ ተከባ የምትገኘውን ቅድስት ሃገር በቅዱስ መጽሃፉ ከአርባ ጊዜ በላይ ኢትዮጵያን አወድሷል። ዘሯም በዓለም ዙሪያ እንዲበዛ ፈቅዷል።

ለዚህም ነው ኢትዮጵያዊያን በዓለም ዳርቻ ሁሉ እንደ አሽዋ ተበትነው፤ እንደ ፅጌረዳ ፈክተው፤ በቀስተ ደመና ደምቀው፤ እንደ እንጉዳይ በዝተው በዓለም ዙሪያ የሚገኙት። በየሄዱበትና በሚኖሩበት አካባቢ ሁሉ ጨዋነትን ከነስብእናው፤ ትህትናን ከነግብረገብነቱ፤ ፈሪሃ እግዚአብሔርን ከነቅድስናው፤ እውቀትን ከነአስተዋይነቱና ከነስነምግባሩ ይኖሩታል። በጨዋነታቸውና በመልካም ግብረገብነታቸው ምክንያት አንዳንድ ሃገራትና ሃገር ከሃዲዎች የኢትዮጵያዊያንን ትእግስት እንደ ፍርሃት፤ መልካም ስነምግባራቸውን እንደ አጎብዳጅነት ሲቆጥሩት ቆይተዋል።

የኢትዮጵያ ፖለቲካ በዓለም አቀፍ ደረጃ ሲጦዝ አገሬን አትንኩብኝ የሚል በእንድ ወገን በሌላው በኩል ዓይኑን ጨፍኖ ጆሮው ላይ ተኝቶ የነበረው ዳያስፖራ በንዴትና በቁጭት ማንነቱንና አገር ወዳድነቱን ዓለም ጉድ እስኪል እያሳየ ነው። ዳያስፖራው ትዕግስት፤ አስተዋይነትና ረግታን ተላብሶ ነገሮችን በማቻቻል ሲአስተውል አርባ ዓመት አስቆጥሯል። ይህን የኢትዮጵያዊያንን ቻይነትና የማስተዋል ስነምግባር ያልተረዱ የፖለቲካ አቀንቃኞች ጭንቅላቷን በአሽዋ ውስጥ እንደደበቀች ዔሊ አስመስለው ሲአጣጥሉትና ሲሳለቁበት አንዳንዴም በጥርጣሬ ዓይን እየማተሩ በአድርባይነት፤ በፈሪነት ወዘተ ሲፈርጁት ቆይተዋል።

ዛሬ ይህ ሃይል ሃገሩ በውስጥ አጥፊዎችና ክሃዲዎች ለድርድር ስትቀርብ፤ በኢትዮጵያ እውቅ ጠላቶች ስትጠቃ፤ ስትደፈርና ስትንገላታ ሃይማኖት ሳይገድበው፤ እራስ ወዳድነት ሳያሸንፈው ዝምታውን ሰብሮ ከተኛበት ዓለም ወጦ ሃገሩን ለመታደግ ሆ! ብሎ ተነስቷል። አይዞሽ ሃገሬ እኛ እያለን አትደፈሪም እያለ ለኢትዮጵያ አለኝታነቱን በገቢር ገልጿል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ህወሓት የፈጠረችው ዘረኛ ስርአት እና የአሀዳዊነት እውነተኛ ግጽታ - መንግስቱ ሞሴ

በዓለም አድባባይ በሰልፍ ወጥቶ ኢትዮጵያን የነካ የለውም በረካ እያለ በየአሃጉሩ የተመመው ብዙ ይናገራል። በዴሞክራሲና በሰብዓዊ መብት መከበር ሰበብ፤ በውሸት ፕሮፖጋንዳ ታጅበው ሃገሩን ሊበትኑና የኢትዮጵያን ሕዝብ ሊአንበረክኩ የተነሱትን ሃያል ሃገራትና የዓለም አቀፍ መገናኛ ብዙሃንን በቃቻሁ (# NO MORE) እያለ በገሃድ መገዳደር ጀምሯል። ለሃገሩም ዝብ ቆሟል።

ከሰሜን አሜሪካ እስከ ደቡብ አፍሪካ፤ ከአዎርፓ እስከ መካከለኛው ምስራቅ፤ ከአውስትራሊያ እስከ አስያ ድምፁን ጎላ፤ አንገቱን ቀና፤ ባንዲራውን ከፍ፤ አለቃውንና መሪውን በክብር አቅፎና ደግፎ አትንኩን የአድዋ ልጆች ነን ሲል ዓለምን ያለመሳሪያ አንቀጥቅጧል።

በሃብት ተመክተው ሊአንበረክኩን የሞከሩ ሃያል ሃገራትን ሃብታችሁ ይቅርብን እንጂ ክብራችንና ኩራታችንን፤ አይበገሬነታችንን ልትነኩብን አይገብም ሲል መልእክቱን አስተላልፏል። እውነተኛ ሰብዓዊነት የተላበሳችሁ ሃገራትና ሕዝቦች ካላችሁ ሃገሬን እወዳለሁ የሚለውን ልታዝኑለት፤ ልትረዱትና ልትንከባከቡት ይገባችሗል እንጂ ሰብዓዊ ክብሩን፤ ሕዝባዊና ሃገራዊ ኩራቱን በማስፈራራት ልትወስዱበት አይገባችሁም ሲል ድምፁን አሰምቷል።

ከሰልፉ ባሻገር በተለያዩ የዓለማችን ከተሞች  ልዩ ልዩ የእርዳታ ማሰባሰቢያ መርሃ ግብሮችን በማዘጋጀት ከፍተኛ የሆነ የገንዘብ፤ የቁሳቁስና የሙያ ማሰባሰብ ተግባሮችን እያደረገ ይገኛል። በቶሮንቶ፤ አልበርታ፤ ዋሽንግተን፤ ሎሳ አንጀለስ፤ ሌባኖን፤ ብራሰልስ፤ ስዊስ፤ ደቡብ አፍሪካ ወዘተ ያሸለበው ብዙሃን (silent majority) ዳያስፖራ በነቂስ ወጦቶ በብዙ ሽህ የሚቆጠር ዶላር ( ብዙ ሚሊዮን የኢትዮጵያ ብር) የማዋጣት ተግባሩን በሰፊው፤ በፍላጎትና በቁጭት  ተያይዞታል። በእርዳታ ስም ሃገሩን ቅኝ ግዛታቸው ለማድረግ የቋመጡትን ባንዳዎችና የውጪ ጠላቶቹን ቅስም ሰብሯል። በተለይ ሃያላን ሃገራት እርዳታችሁን በጉያችሁ ይዛችሁ አትምጡብን ብሏል።

ብዙሃኑ ዳያስፖራ በራስ መተማመን ስነምግባር የታነፀች እትዮጵያን መልሶ ለማቋቋም ቃል ገብቷል። ያሸለበው ዳያስፖራ ቀፎው እንደተነካ ንብ ሆብሎ ተነስቷል። በዝምታና በትዕግስት ተሸብቦ የነበረው ደግሞ ሲአገሳ ከፊቱ የሚቆም ወንበዴና ሃገር ሻጭ ባንዳ አይኖርም። ከሰሞኑ የሚስተዋለው የኢትዮጵያዊነት ሃይልና የዳያስፖራ አትንኩን ባይነት ወኔ ከቆፎው ወጥቷል። ከዚህ በኋላ የሚአቆመውም ሆነ የሚገዳደረው ምድራዊ ሃይል አይኖርም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የትግራይ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን መግለጫ "ከፍትፍቱ አጉርሱኝ ከመረቁ ግን ጾመኛ ነኝ!"

በመጪው ጃንዋሪ 2022 ከአንድ ሚሊዮን በላይ ዳያስፖራ መሪው ባደረጉለት ጥሪ መሰረት ሃገሩ ሄዶ ኢትዮጵያን፤ ዘመዶቹንና ወገኑን ይጎበኛል። ተጨባጩን ሁኔታ አይቶ ይመለሳል። በዚህ ወደ ሃገር ግቡ እንቀስቃሴ ሃገሪቱ ከፍተኛ ተጠቃሚ እንደምትሆን ጥርጥር የለውም። በግርድፉ ከትኬት ሽያጭ US$1.1 ቢሊዮን ዶላር፤ ተመላሹ ዳያስፖራው ከሚአስገባው ቁሳቁስ ወደ US$300 ሚሊዮን ዶላር፣ ለዘመዱ የሚሰጠው ድጎማና ለአንድ ወር መቆያ ወጪ ከሚአደርገው US$1.5 ቢሊዮን ዶላር፤ እያንዳንዱ ዳያስፖራ ቦሌ ሲገባ ሙዳየ እርዳታ ሳጥን (ካሳ ፎርቶ) US$100  ቢከት US$100 ሚሊዮን ዶላር፣ ከቱሪስት ቪዛ ክፍያ በንፍስ ወከፍ $50 ቢከፍል US$50 ሚሊዮን ዶላር ይገኛል። በጥቅሉ ከዚህ ወደ እናት ሃገር የመመለስ ተንሳሽነት ኢትዮጵያ ከUS$ 4.5-US$ 5.5 ቢሊዮን ዶላር ገቢ ልታገኛ ያስችላታል ተብሎ ይገመታል። ይህ ደግሞ አሜሪካ በዓመት ለኢትዮጵያ የምትሰጠውን እርዳታ በአራት እጥፍ የሚአስከንዳ ይሆናል። እራስን መቻል ከዚህ በላይ ሌላ ምን ሊሆን ይችላል። እሰይ ዳያስፖራ በያላችሁበት ኑሩልኝ፤ ክበሩልኝ ትላለች ኢትዮጵያ።

ከዚህ በሗላ ዳያስፖራው ተመልከት ባንዲራህን፤ እይ ዓላማህን፤ ተከተል መሪህን እያለ ጉዞ ወደ እናት ሃገር ኢትዮጵያ ጀምሯል። አንበሳው እንደ ቀደምት አያቶቹ፤ ቲዎድሮስ፤ ምኒሊክ፤ አሉላ፤ አቢቹ እያገሳና ታሪክ እየሰራ ሃገሩን ያሻግራል። ከዚህ በኋላ ዳያስፖራ አንበሳ ሆኖ ስለተነሳ እጅ ለእጅ ተያይዞ-ይደረግ ወደ ኢትዮጵያ ጉዞ እያለ የዘመቻ ከበሮውን መጎሰም ጀምሯል። ኢትዮጵያም እጇን ዘርግታ እንኳን ደህና መጣችሁ ግቡ ብና ጠጡ ልትላችሁ ተዘጋጅታ ትጠብቃለች። መልካም የፈረንጆች ገና እና አዲስ ዓመት እንዲሆንላችሁ ሃገራችሁ ትመኛለች። መልካም ጉዞ።

ኢትዮጵያ በልጆቿ ታፍራና ተከብራ ለዘላለም ትኑር፤

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአማራን ዘ ር የማጥፋት እኩይ የወያኔ ሤራ

 

ሰማነህ ታምራት ጀመረ፤ ዖታዋ ካናድ

ታሕሣስ 10፣ 2021

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share