ቀና በይ አፍሪካ ! – መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ

Africaተናገር ኢትዮጵያዊው ! ተናገር ! አንተ ኩሩ !
ዳግም ምኒልክ ተፈጠር አፍሪካውያን ይኩሩ !
ኢትዮጵያዊ እንደሆን ጥንትም ፤ የአፍሪካዋው ደም ሥሩ !
የነፃነት ፋና ወጊው ፣ አንገቱን ቀና እንዲያደርግ ጥቁሩ ።
ይወቁ ፣ይረዱ ከታሪክህ ይማሩ …
በቅኝ ያለመገዛትህ አይደለም
የድህነትህ ምሥጥሩ
ይገርማል ! …
እንደዘበት እንደው እንደዋዛ
ነፃነትን መናኛ አድርጎ በህሊና ድንዛዛ !!
” በነ ነጭ ዓምላኩ” በበቀለ፣ የጥገኝነት አዝመራ…
አዳሜ መኖር ፈቅዶ በሆድ ቁዘራ
ለከርሱ ባርያ ሆኖ ” ሥለመገዛት አወራ ።
ድሮም ለሆድ ሟች ነው ፣ ያደረገን የዓለም ጭራ
ፊተኞች የነበርነውን
ኋለኞች ያደረገን
የኛው ባንዳ ነዉ
የእኛው ነጭ አምላኩ !
ግና …
እኛ ኢትዮጵያዊያን
ዛሬም ወደፊትም
የመቅደላ ልጆች ነን !
የአደዋ ልጆች ነን !
የእሣት ሠደድ እጅ ያለን ።
ከቶም አይበርድም እቶን እጃችን ፣ በባንዳ ወሬ
መኩርያና መመኪያዋ ይሆናል እንጂ ዘላለም ለአገሬ !!
ነዲድ ! እቶን ! ክንዳችን ፤ ከቶ መች ይበርድና !
ይበልጥ፣ እየፈመ ! እየጋመ ! ይሄዳል ገና ! …
ተናገር ኢትዮጵያዊው ! ተናገር ! አንተ ኩሩ !
ዳግም ምኒልክ ሲፈጠር ታዝበው አፍሪካውያን ይኩሩ !
አንተ እንደሆን ያሥታውሱ ጥንትም ፤ የአለም መምህሩ !
የነፃነት ፋና ወጊው ፣ አንገቱን ቀና እንዲያደርግ ጥቁሩ ።
ይወቁ ፣ይረዱ ከታሪክህ ይማሩ …
በቅኝ ያለመገዛትህ አይደለም
የድህነትህ ምሥጥሩ
አይደለም በለው ፣ ለዛ ለባንዳ
በሆድ ተገዝቶ አገር ለሚጎዳ ።
ለዛ ሆድ ሟች ፤ “ለአያ ነጭ አምላኩ ”
ለመብለት ለሚኖር ለህሊና ድንኩ ።
ንገረው !
መገዛት እንዳልሆነ የሥልጣኔ ምንጩ
ባርነት መሆኑንን አንገት አስቆራጩ ።
ቢቀጥንም አንገትነው ራሱን ከቻለ
ከተቆረጠማ ምኑንን አንገት ተባለ ?
ይህንን አስተውል ፣ በቅጡም ተረዳ
” አያ ነጭ አምላኩ” አገሬን አትጉዳ !
ተናገር ኢትዮጵያዊው ! ተናገር ! አንተ ኩሩ !
ዳግም ምኒልክ ሲፈጠር ታዝበው አፍሪካውያን ይኩሩ !
አንተ እንደሆን ያሥታውሱ ጥንትም ፤ የአለም መምህሩ !
የነፃነት ፋና ወጊው ፣ አንገቱን ቀና እንዲያደርግ ጥቁሩ ።
ይወቁ ፣ይረዱ ከታሪክህ ይማሩ …
በቅኝ ያለመገዛቴ አይደለም
የድህነቴ ምሥጢሩ …
ብለህ ንገራቸው ፤ “ለነ ፍሊት ማን ”
ከጅለዋልና ” የወሬ ፍሊት ነፍተው ” በሆድ ሊገዙን ።
ተጠቅመው በወያኔ ፣ ኢትዮጵያን በጠላ
የነጭ አሽከር ሆኖ በጠገበ ፣ አገር እየበላ
በህሊና ቢሥ ባንዳ ፣ አገሬ አትፈርሥም
ለዘመናዊው ኮሎኒያሊዝም ፣ አፍሪካን አሣልፋ አሠጥም …

ተጨማሪ ያንብቡ:  ጨው ኮርማን ጠለፈው!

መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ
ታህሣሥ 27/2014 ዓ/ም
አዳማ /ናዝሬት

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share