የከሸፈ ፡ ቅሬታ ፡ ይዘት – ኢ.ሀ.ሥ.አ.

ዜመ_ኢ-1_20130428_ዐማርኛ
ዜና ፡ መግለጫ ።
ለንደን ፥ ታኅሣሥ ፡ 28 ፡ ቀን ፥ 2013 ፡ ዓ.ም. ።
ካፈጣጠሩ ፡ ሀገር ፡ ኢትዮጵያን ፡ የከዳው ፡ የውንብድና ፡ እና ፡ የጥፋት ፡ ኀይል ፡ ሕ.ወ.ሐ.ት. (ሕዝባዊ ፡ ወያኔ ፡ ሐርነት ፡ ትግራይ) ፥ ጥቅምት ፡ 24 ፡ ቀን ፡ 2013 ፡ ዓ.ም. ፥ ጨለማን ፡ ተገን ፡ በማድረግ ፥ በሰሜን ፡ ጐንደር ፣ በመላ፟ ፡ ትግራይ ፡ እና ፡ በሰሜን ፡ ወሎ፟ ፡ ክፍላተ ፡ ሀገር ፡ የሰፈረውን ፥ የኢትዮጵያ ፡ ክንድ ፡ የኾነውን ፡ ሀገራዊ ፡ ጦር ፡ ሰራዊት ፥ እንዲሁም ፡ ያካባቢውን ፡ ሰላማውያን ፡ ኗሪዎች ፡ በቀቢጸ ፡ ተስፋና ፡ የሕይወትን ፡ ቅድስና ፡ በካደ ፡ በተለየ ፡ አረመኔነት ፡ ጨፍጭፏል ። ይህ ፡ የወንጀለኞች ፡ ድርጅት ፥ ዅሉም ፡ በዅሉ ፡ በሺሕ ፡ የሚቈጠሩ ፡ ሀገራውያንን ⁽1⁾ ፡ ገድሏል ፥ ዐያሌ ፡ ንብረትንና ፡ መሠረተ ፡ ልማትን ፡ አውድሟል ፥ ሀገርን ፡ ለውጭ ፡ ጠላት ፡ ጥቃት ፡ አጋልጧል ፥ የርኵሰትና ፡ የክዳት ፡ ድርጊቶቹንም ፡ በይፋ ፡ አምኗል ።
ድርጅቱ ፥ ሕ.ወ.ሐ.ት. ፥ በሕግ ፡ ይፍረስና ፡ ይወገዝ ፥ ኀላፊዎቹም ፡ ተይዘው ፥ በሀገር ፡ ክዳት ፣ በፀረ ፡ ስብኣዊነት ፡ ወንጀልና ፡ በጦር ፡ ወንጀል ፡ አንቀጾች ፡ ተከሰው ፡ እሀገራዊ ፡ የፍርድ ፡ ችሎትም ፡ ፊት ፡ ቀርበው ፡ በወንጀለኛ ፡ መቅጫ ፡ ሕግ ፡ መሠረት ፡ ይቀ፟ጡ ፡ ከማለት ፡ በቀር ፥ ይህን ፡ ለመሰለው ፡ ርኵሰትና ፡ ክዳት ፡ ምንም ፡ ዐይነት ፡ የሐዘንም ፡ የውግዘትም ፡ ቃላት ፡ አይገኙለትም ።
ኾኖም ፥ ከክዳቱና ፡ ከጭፍጨፋው ፡ ዠርባ ፡ ምክንያቶች ፡ የኾኑት ፡ ባዕድ ፡ ተከ፟ል ፡ የአፓርትሀይድ ፡ ሥርዐቱና ፡ ሌሎች ፡ ይፋ ፡ ያልወጡ ፡ ተሳታፊዎችና ፡ ተመሳጣሪዎችም ፡ ስላሉ ፥ ጠቅላላው ፡ ጕዳይ ፡ በመሸጋገሪያ ፡ መንግሥት ፡ ወቅት ፡ በዝርዝር ፡ የሚመረመርና ፡ በሀገራዊው ፡ ፈታሒ ፡ ሥልጣን ፡ ሕጋዊ ፡ ፍጻሜውን ፡ የሚያገኘ ፡ ስለሚኾን ፥ የኢትዮጵያውያን ፡ ሀገራዊ ፡ ሥልጡንሕዝባዊ ፡ አንድነት ፡ (ኢ.ሀ.ሥ.አ.) ፡ የፍርድ ፡ ኺደቱን ፡ በተመለከተ ፥ አቋሙን ፡ ወደ ፡ ፊት ፡ ያስታውቃል ።
ይህ ፡ ሕ.ወ.ሐ.ት. ፡ የተባለ ፡ የውንብድና ፡ ድርጅት ፥ ከሀገር ፡ ወዳ፟ዱና ፡ ጨዋው ፡ የትግራይ ፡ ክፍለ ፡ ሀገር ፡ ነዋሪ ፡ አንዳች ፡ ውክልና ፡ አልነበረውም ፤ የፈጸማቸው ፡ የሀገር ፡ ክዳት ፡ ወንጀሎች ፡ ዅሉ ፥ ድርጅቱንና ፡ ከኀምሳ ፡ ዓመታት ፡ በፊት ፡ የፈጠሩትን ፣ የነወዩትን ፣ ያደራጁትንና ፡ ከሩቅ ፡ ኾነው ፡ የዘወሩትን ፡ የምልክዮሽ ፡ ኀይሎችንም ፡ የሚመለከቱ ፡ ወንጀሎች ፡ ናቸው ። የትግራይ ፡ ክፍለ ፡ ሀገር ፡ ነዋሪ ፡ ከደሙ ፡ ንጹሕ ፡ መኾኑን ፡ ራሱም ፡ ያውቀዋል ፥ መላ፟ ፡ የኢትዮጵያ ፡ ሕዝብም ፡ ያውቅለታል ፥ የዓለም ፡ ሕዝብም ፡ ሊያውቅለት ፡ ይገ፟ባ፟ል ። ይህም ፡ ሊታመን ፥ የሕ.ወ.ሐ.ት.ን ፡ ጥሪ፟ ፡ ካለመቀበሉ ፡ ሌላ ፥ ሀገራዊው ፡ ሰራዊት ፡ በተሰማራባቸው ፡ የትግራይ ፡ ቀበሌዎች ፡ ዅሉ ፥ ነዋሪው ፡ የሰራዊቱን ፡ መመ፟ሪያ ፡ በማክበር ፡ ለ”ሕግን ፡ የማስከበር ፡ ዘመቻ”ው ፡ ድጋፉን ፡ አሳይቷል ። ባስፈለገም ፡ ጊዜ ፥ ሲጨቍነው ፡ የኖረውን ፡ የውንብድና ፡ ኀይል ፡ ከሀገራዊው ፡ ሰራዊት ፡ አባላት ፡ ጐን ፡ ተሰልፎ ፡ ወግቷል ።
ይህን ፡ ፋሺስታዊ ፡ የክፋት ፡ ኀይል ፡ ድል ፡ አድርገው ፡ ሕይወታቸውን ፡ በሠዉት ፡ ዠግኖችና ፡ በተገደሉት ፡ ሰላማውያን ፡ ኢትዮጵያውያን ፥ የኢትዮጵያውያን ፡ ሀገራዊ ፡ ሥልጡንሕዝባዊ ፡ አንድነት ፡ (ኢ.ሀ.ሥ.አ.) ፡ የተሰማውን ፡ መሪር ፡ ሐዘን ፡ ይገልጻል ፤ የሞቱትን ፡ ነፍስ ፡ እግዚአብሔር ፡ እንዲምርለትም ፡ ይጸልያል ። ለተጐዱት ፡ ቤተሰቦቻቸውና ፡ ወዳጆቻቸው ፡ ዅሉ ፡ እንዲሁም ፡ ለመላ፟ው ፡ የኢትዮጵያ ፡ ሕዝብ ፡ ጽናቱን ፡ እንዲሰጥለት ፡ ኢ.ሀ.ሥ.አ. ፡ ይለምናል ። ኢትዮጵያ ፥ ሥልጡንሕዝባዊ ፡ መንግሥቷን ፡ መልሳ ፡ ስታቆም ፥ የሕይወት ፣ የአካል ፡ እና ፡ የንብረት ፡ ጕዳት ፡ የደረሰባቸውን ፡ ልጆቿን ፡ ዅሉ ፡ ትክሳቸዋለች ፡ ሲል ፡ ኢ.ሀ.ሥ.አ. ፡ እምነቱን ፡ ይገልጻል ።
እስከዚያው ፡ ድረስ ፦
1) ከሕ.ወ.ሐ.ት. ፡ የ30 ፡ ዓመት ፡ ጭቈና ፡ ነጻ ፡ ለወጡት ፡ የክፍለ ፡ ሀገር ፡ ትግራይ ፡ ነዋሪዎች ፦ እንኳን ፡ ለዚህ ፡ የነጻነት ፡ ቀን ፡ አበቃችኹ ፤ ለዚህ ፡ ዅሉ ፡ መከራና ፡ ሞት ፡ ዳርገዋችኹ ፥ አኹን ፡ ደግሞ ፡ በውስጣችኹ ፡ ተደብቀው ፡ ዐዲስ ፡ ዙር ፡ መከራን ፡ የሚደግሱላችኹን ፡ ጥቂት ፡ ወንጀለኞች ፡ እያወጣችኹ ፡ ለሕግ ፡ አስከባሪው ፡ ኀይል ፡ አስረክቡ ፤
2) አላግባብ ፡ ወደ”ትግራይ ፡ ክልል” ፡ ተዛውረው ፡ ለነበሩት ፡ የጐንደር ፡ ክፍለ ፡ ሀገርና ፡ የወሎ፟ ፡ ክፍለ ፡ ሀገር ፡ ወረዳዎች ፡ ነዋሪዎች ፦ እናንተንም ፥ እንኳን ፡ ለዚህ ፡ የነጻነት ፡ ቀን ፡ አበቃችኹ ! “ክልላዊው ፡ የአፓርትሀይድ” ፡ ሥርዐት ፡ ፈርሶ ፥ ኢትዮጵያ ፡ በዐዲስና ፡ በሕጋዊ ፡ አስተዳደራዊ ፡ አወቃቀር ፡ በሥልጡንሕዝባዊ ፡ መንገድ ፡ እስክትዋቀር ፡ ድረስ ፥ በታላቅ ፡ መሥዋዕትነት ፡ ባስከበራችኹት ፡ መብታችኹ ፡ የያዛችኹትን ፡ ግዛታችኹን ፡ ሳትለቁ ፡ ጸንታችኹ ፡ እንድትቈዩ ፤
3) መላ፟ው ፡ የኢትዮጵያ ፡ ነጻ ፡ ሕዝብ ፡ ሆ�� ፦ እንኳን ፡ ለዚህ ፡ የድል ፡ ቀን ፡ አደረሰኽ ! ምንም ፡ ውጊያው ፡ በወንድማማቾችና ፡ እትማማቾች ፡ መኻከል ፡ መኾኑ ፡ ዕጥፍ ፡ ድርብ ፡ ሐዘን ፡ ቢኾንብን ፡ ቅሉ ፥ ድል ፡ የተመታው ፡ ወንድምን ፡ ከወንድሙ ፥ እኅትን ፡ ከእኅቷ ፡ የሚያለያይና ፡ የሚያፋጅ ፡ ከምዕራቡ ፡ ዓለም ፡ የመጣ ፡ የንኁልዮሽ ፡ ርኩስ ፡ መንፈስ ፡ በመኾኑና ፥ ድሉ ፡ የወደፊቱንም ፡ የኢትዮጵያ ፡ ዕጣ ፡ ፈንታ ፡ መቃናት ፡ ገና ፡ ካኹኑ ፡ በማመልከቱ ፥ ዳግመኛ ፡ እንኳን ፡ ደስ ፡ ዐለኽ ! ባዕድ ፡ ሠራሹ ፡ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፡ የአፓርትሀይድ ፡ ሥርዐት ፡ ከኢትዮጵያ ፡ ምድር ፡ ፈጽሞ ፡ እንዳይነቀል ፥ «ሕገ ፡ መንግሥቱን ፡ እናስቀጥላለን» ፡ የሚሉ ፡ አታላዮች ፡ በሚዋሹልኽ ፡ ግብዝ ፡ ምርጫና ፡ ማንኛውም ፡ ማዘናጊያ ፡ እንዳትዘናጋ ። የኢትዮጵያን ፡ ሀገራዊ ፡ አንድነትና ፡ ብሔራዊ ፡ (ምድራዊ ፡ ወይም ፡ ግዛታዊ) ፡ ሙሉነት ፡ በማስጠበቅና ፡ በማረጋገጥ ፥ ዐዲስ ፡ ሕገ ፡ መንግሥትኽንና ፡ ሥልጡንሕዝባዊ ፡ የርትዕ ፡ መንግሥትኽን ፡ ትመሠርት ፡ ዘንድ ፥ አስቀድሞ ፡ መላ፟ ፡ ሀገርኽ ፡ ኢትዮጵያን ፡ መልሰኽ ፡ እእጅኽ ፡ ለማስገባት ፡ በአንድነት ፡ ተነሥ ፥
ሲል ፡ ኢ.ሀ.ሥ.አ. ፡ ጥሪ፟ውን ፡ ከመልካም ፡ ምኞቱ ፡ ጋራ ፡ በሀገር ፡ ፍቅር ፡ ያስተላልፋል ።
1 ፤ የምልክዮሽ ፡ እጅ ፡ ደም ፡ አለ፟በ፟ት !
ደቡብ ፡ አፍሪቃ ፡ የተፋችውን ፡ የ”አፓርትሀይድ” ፡ ሥርዐት ፥ የተባበሩት ፡ ያሜሪካ ፡ ኹነቶች ፡ መንግሥትና ፡ ጥቂት ፡ ምዕራባውያን ፡ መንግሥታት ፥ በቀልን ፡ በሚያመለክት ፡ አደራረግ ፥ በግንቦት ፡ ወር ፡ 1983 ፡ ዓ.ም. ፡ በቀንደኛዋ ፡ የፀረ ፡ ቅኝ ፡ ግዛት ፣ የፀረ ፡ ምልክዮሽና ፡ የፀረ ፡ “አፓርትሀይድ” ፡ ተዋጊት ፡ ኢትዮጵያ ፡ ላይ ፡ በኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፡ (የኢትዮጵያ ፡ ፌዴራላዊ ፡ ዴሞክራሲያዊ ፡ ሪፓብሊክ) ፡ የ”አፓርትሀይድ” ፡ ይዘት ⁽2⁾ ፡ መልክ ፥ “ፐርል ፡ ሀርበር”ን ፡ በሚያስንቅ ፡ ክዳት ፥ በጕልበት ፡ ጫኑባት ። ይዘቱንም ፡ በከሓዲው ፡ ሕ.ወ.ሐ.ት. ፡ እጅ ፡ ውስጥ ፡ አደረጉት ።
በዚህ ፡ መሠረት ፥ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፡ ይዘት ፡ ዋና ፡ ተጠሪ ፡ ሕ.ወ.ሐ.ት. ፥ 29 ፡ ዓመት ፡ ሙሉ ፡ ይህ ፡ ነው ፡ የማይባል ፡ በደልን ፡ በኢትዮጵያ ፡ ላይ ፡ ፈጸመ ። ሊገለጹ ፡ የማይችሉ ፡ የስርጀታ ፣ የጭቈና ፣ የአመሳሶ ፣ የሙስ፟ና፟ ፡ ዐይነቶች ፡ በገቢር ፡ ታዩ ፤ ባጠቃላይ ፡ ያስተዳደር ፡ ብልሹነት ፥ አንዳች ፡ ከልካይ ፡ ሳይኖርበት ፥ የ”mean”-stream ፡ ማወራኛዎችም ፡ አይተው ፡ እንዳላዩ ፣ ሰምተው ፡ እንዳልሰሙ ፡ እየኾኑለት ፥ በእየዓመቱ ፡ በቢልዮን ፡ ዶላር ፡ የሚገመትን ፡ የሀገር ፡ ሀብት ፡ በውጭ ፡ ምንዛሪ ፡ መዝብሮ ፡ ወደቀረው ፡ ዓለም ፡ በሕገ ፡ ወጥ ፡ መንገድ ፡ አሸሸ ። በዚሁ ፡ ጊዜ ፥ “mean”-stream ፡ ማወራኛዎች ፡ የኢትዮጵያ ፡ ጥርየት ፡ በ”ባለኹለት ፡ አኃዝ ፡ እድገት” ፡ መጠን ፡ ማደጉን ፡ በሰፊው ፡ ከመንዛት ፡ አላቋረጡም ፤ ኾኖም ፥ ይህ ፡ የ”ባለኹለት ፡ አኃዝ ፡ እድገት” ፡ መጠን ፡ ስማዊ ፡ (nominal) ፡ እንጂ ፡ እውናዊ ፡ (real) ፡ የእድገት ፡ መጠን ፡ ባለመኾኑ ፥ ስማዊው ፡ እድገት ፡ በባሰ ፡ “ባለኹለት ፡ አኃዝ” ፡ የዋጋ ፡ ንረት ፡ ፈጽሞ ፡ መበ፟ላቱንና ፡ የሀገሪቱ ፡ ጥርየት ፡ መቀንጨሩን ፡ አልተናገሩም ።
በሕ.ወ.ሐ.ት. ፡ የሚ፟መ፟ራ፟ው ፡ ይዘት ፥ በዋነኛነት ፡ እንዲፈጽማቸው ፡ የተመደቡለትን ፡ ሀገር ፡ ኢትዮጵያን ፡ የመደምሰስ ፡ መደምደሚያ ፡ ተልእኮዎች ፦
1) ኢትዮጵያን ፡ የባሕር ፡ በር ፡ የማሳጣት ፡ የምልክዮሽ ፡ እኩይ ፡ ዐላማን ፡ በሕገ ፡ ወጥ ፡ ፈረዳ ፡ እዳር ፡ ለማድረስ ፥ የባሕር ፡ ምድርንና ፡ የደንከልን ፡ ኢትዮጵያዊ ፡ ከፊል ፡ ሕዝቧን ፣ ከፊል ፡ ምድሯንና ፡ የቀይ ፡ ባሕር ፡ ዳርቻዎቿንም ፡ በሙሉ ፡ ለጠላት ፡ አሳልፎ ፡ በመስጠት ፤
2) የኢትዮጵያን ፡ ሕዝብ ፡ እንዲሁም ፡ ብሔሯን ፡ (ምድሯን) ፡ በ”ዘር” ፡ መክፈልት ፡ ከፋፍሎ ፥ ሀገራዊ ፡ አንድነቷንና ፡ ብሔራዊ ፡ ሙሉነቷን ፡ ለአደጋ ፡ በመዳረግ ፤
3) በባዕድ ፡ ሠራሹ ፡ “ሕገ ፡ መንግሥት” ፡ መሠረት ፥ አንዱን ፡ የኢትዮጵያ ፡ እግዚእ ፡ ሕዝብ ፡ “ሕዝቦች” ፡ ብሎ ፡ ከፋፍሎ ፡ በመጥራትና ፡ ኢትዮጵያን ፡ ባለቤት ፡ አልባ ፡ ለማድረግ ፡ በመሞከር ፤
4) ሀገራዊ ፡ ልሳን ፡ ዐማርኛን ፡ በእንግሊዝኛ ፡ አንጻር ፡ ለማዳከም ፡ በመሞከር ፤
5) ሀገራዊነትን ፡ በውልደተኝነት ፡ ለመተካት ፡ በመሞከር ፥ እንዲሁም ፡ ማኅበረሰብን ፡ ከማኅበረሰብ ፡ ከፋፍሎ ፡ በማገዳደርና ፡ በማጋጨት ፡ በእየዕለቱ ፡ ዕልቂትን ፣ መፈናቀልንና ፡ ስደትን ፡ በማከታተል ፤
6) የተቃወመውን ፡ ዅሉ ፡ አላንዳች ፡ ርኅራኄ ፡ ባሠቃቂ ፡ መንገድ ፡ በማሳደድ ፣ በመሣቅየትና ፡ በመግደል ፤
7) የሀገሪቱንና ፡ የመንግሥቷን ፡ ሀብት ፡ በመመዝበር ፥
8) ሌላ ፡ ሌላም ፡ የረከሱ ፡ ግብሮችን ፡ በመፈጸም ፤
ጠላትነቱን ፡ አረጋግጧል ።
ነገር ፡ ግን ፥ ሕ.ወ.ሐ.ት. ፡ አልተሳካለትም ፤ መጨረሻውን ፥ ሕ.ወ.ሐ.ት. ፡ ራሱ ፡ እንሆ ፡ ተደመሰሰ ።
ከመደ፟ምሰሱ ፡ ሦስት ፡ ዓመታት ፡ በፊት ፥ በ2010 ፡ ዓ.ም. ፡ በተቀጣጠለው ፡ ሕዝባዊ ፡ ዐመፃ ፡ የራሱ ፡ መጨረሻ ፡ ታይቶትና ፡ ተጨንቆ ፥ በሆዱ ፡ ያባው ፡ ቀሪ ፡ የጥፋት ፡ ተልእኮው ፡ እንዳይታጐል ፡ ማምለጫን ፡ ለማግኘት ፡ ሲል ፥ በትረ ፡ ውንብድናውን ፡ ለቀሩት ፡ የቅሬታው ፡ ኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፡ ይዘት ፡ አጋሮቹ ፡ አቀብሎ ፥ ወደመሸሸጊያው ፡ “የትግራይ ፡ ክልል” ፡ ሾለከ ። ሕ.ወ.ሐ.ት. ፡ እስከ ፡ ዛሬ ፡ ድረስ ፡ ለበደለውም ፡ በደል ፦በክተናል ፡ ከማለት ፡ በቀር ፡ አንዳችም ፡ ጸጸት ፡ አላሳየ ። ቅዱስ ፡ መጽሐፍ ፦ውሻ ፡ ወደ ፡ ትፋቱ ፡ ይመለሳል ፡ (2ኛ ፡ ጴጥ. ፥ 2 ፥ 22) ፡ ሲል ፡ እንዳመለከተው ፡ ዅሉ ፥ ዐዲስ ፡ አበባን ፡ ለቆ፟ ፡ ወደትግራይ ፡ “ክልል” ፡ ምሽጉ ፡ ከተመለሰ ፡ በዃላ ፥ ያልተለወጠውን ፥ እውነተኛውን ፡ የከሓዲነት ፣ የፋሺስትነትና ፡ ያጥፊነት ፡ ብልሹ ፡ ጠባዩን ፡ በሚያሠቅቅ ፡ ኹኔታ ፡ በመላ፟ ፡ ሀገሪቱ ፡ በመድገም ፡ ለዓለሙ ፡ ዅሉ ፡ መልሶና ፡ ገልጦ ፡ አሳየ ። ሕ.ወ.ሐ.ት. ፥ ይህን ፡ ወንጀሉን ፡ ሲፈጽም ፥ ዐዲስ ፡ አበባ ፡ እሥልጣኑ ፡ ሰገነት ፡ ላይ ፡ ከቀሩት ፡ አንጋፋዎች ፡ አጋሮቹ ፡ ውስጥ ፥ ኢትዮጵያን ፡ “በዘር ፡ ማጽዳት” ፡ ዘመቻ ፡ ወደ ፡ “ዩጎስላቪያነት” ፡ በመቀየር ፡ አጥፊ ፡ ስያስ ፡ የሚስማሙለትን ፥ የከፊሉን ፡ ተመሳጣሪነት ፣ ወይም ፡ ተባባሪነት ፣ ወይም ፡ ደግሞ ፡ የዐቅም ፡ ድጋፍ ፡ ሳያገኝ ፡ እንዳልቀረ ፡ በገቢር ፡ ተመስክሯል ።
በወልቃይት ፣ በጠገዴ ፡ (ጸገዴ) ⁽3⁾ ፣ በካፍታ ፡ ሑመራ ፡ እና ፡ በጠለምት ፡ (ጸለምት) ፡ ወረዳዎች ፥ በተለይ ፡ በማይ ፡ ካድራ ፡ ከተማ ፡ አካባቢ ፥ ከጥቅምት ፡ 24 ፡ ቀን ፡ 2013 ፡ ዓ.ም. ፡ አንሥቶ ፡ እስከተባረረበት ፡ ቀን ፡ ድረስ ፡ ከ1’500 ፡ ያላነ፟ሱ ፡ ንጹሓንን ፡ ያጠፋ፟ው ፡ አረመኔያዊ ፡ የወያኔ ፡ ጭፍጨፋ ፥ መሠረቱ ፡ የዚሁ ፡ በ1933 ፡ ዓ.ም. ፡ የተሸነፈው ፡ የፋሺዝም ፡ ቂም ፡ በቀልና ፡ ፋሺስታዊ ፡ አስተሳሰብ ፡ ስለ ፡ መኾኑ ፡ ምንም ፡ ጥርጥር ፡ የለውም ። የዩጎስላቪያውን ፡ የ”ስሬብሬኒሽካ” ፡ ጭፍጨፋ ፡ በሚያስታውስ ፡ ኹኔታም ፥ የኢትዮጵያን ፡ መበ፟ታተን ፡ እንዲያስከትል ፥ ኾነ ፡ ተብሎ ፡ ተፈጽሟል ።
የወልቃይት ፣ የጠገዴ ፣ የጠለ፟ምትና ፡ የካፍታ ፡ ሑመራ ፡ ወረዳዎች ፡ [ቢጋር ፡ 1ን ፡ ይመለከቷል፥ PDF] ፡ ከጐንደር ፡ ክፍለ ፡ ሀገር ፡ ግዛትነት ፡ በውንብድና ፡ ውሳኔ ፡ ወደ ፡ “ትግራይ ፡ ክልል” ፡ ወረዳነት ፡ በ1983 ፡ ዓ.ም. ፡ የተዛወሩባቸው ፡ ምክንያቶች ፦
• አንደኛ ፥ ነዋሪዎቹ ፥ በጠቅላላው ፥ በፋሺስት ፡ ኢጣሊያ ፡ ወረራ ፡ ዘመን ፡ (1928-1933 ፡ ዓ.ም.) ፡ እንደ ፡ ቢትወደድ ፡ አዳነ ፡ መኰንን ፡ ባሉ፟ ፡ ሀገራውያን ፡ ዠግኖች ፡ መሪነት ፡ በፈጸሙት ፡ ታላቅ ፡ የዐርበኝነት ፡ ተጋድሏቸው ፥ አካባቢያቸውን ፡ “የፋሺስት ፡ መቃብር” ፡ ያሠኙበትን ፡ የዠግንነት ፡ ዝና፟ቸውንና ፡ የሀገራዊነት ፡ ሟያቸውን ፡ ለመበ፟ቀል ፤
• ኹለተኛ ፥ የምልክዮሽ ፡ ኀይሎች ፡ በ”ሪፓብሊክነት ፡ ትገነጠላለች” ፡ ብለው ፡ ለወሰኑባት ፡ የትግራይ ፡ “ክልል” ፥ በሱዳን ፡ በኩል ፡ መጋ፟ቢያን ፡ ለመስጠት ፤
• ሦስተኛ ፥ ለ”ሪፓብሊክነት” ፡ የታጨው ፡ የትግራይ ፡ “ክልል” ፥ ከወሎ፟ ፡ ክፍለ ፡ ሀገር ፡ ግዛትነት ፡ በ1983 ፡ ዓ.ም. ፡ አላግባብ ፡ የተዛወሩትን ፡ የራያ፟ ፡ እና ፡ የአላ፟ማጣ ፡ ወረዳዎች ፡ አክሎ ፥ በምግብ ፡ ራሱን ፡ ከመቻልም ፡ ዐልፎ ፡ መጀለቻው ፡ የሚኾነውን ፡ ሰፊ፟ ፡ እና ፡ ለም ፡ የዕርሻ ፡ መሬት ፡ ባለቤት ፡ ለማድረግ ፡ ነበር ።
ጥቅምት ፡ 2013 ፡ ዓ.ም. ፡ አጋማሽ ፡ ላይ ፡ በሺሕ ፡ የሚቈጠሩ ፡ ንጹሓን ፡ ሀገራውያንን ፡ (ዐማራዎችን) ፡ ያጠፉ፟ትና ፡ [ቢጋር ፡ 2ን ፡ ይመለከቷል፥ PDF] ፡ በተለመደው ፡ የሐዘን ፡ መግለጫ ፡ ሊታለፉ ፡ የነበሩት ፦
• የ”ኦሮሞ ፡ ክልል” ፡ (በወለ፟ጋ፟ ፥ ጉሊሶ ፣ ቂልጡ ፣ ጃርሶ ፣ ሆሮ፟ ፣ ጕድሩ ፡ … ፡ ወረዳዎች) ፣
• የ”በኒ ፡ ሻንጉል ፡ ጉምዝ ፡ ክልል” ፡ (በመተከ፟ል ፡ አውራጃ ፥ ማንዱራ ፣ ቡሌን ፣ ድባጤ ፣ ካማሺ ፡ … ፡ ወረዳዎች) ፣
• የ”ደቡብ ፡ ክልል” ፡ (ሰሜን ፡ ቤንች ፣ ማጂ ፣ ኮንሶ ፣ ዐማሮ ፣ ማሌ ፡ … ፡ ወረዳዎች) ፡ ወዘተርፈ ፡ … ፡
ሀገራውያንን ፡ ወይም ፡ ዐማራዎችን ፡ ከእየ”ክልሉ” ፡ የ”ማጽዳት” ፡ ጭፍጨፋዎችን ፥ እስካኹን ፡ ችላ፟ ፡ ሲላቸው ፡ የነበረው ፡ በኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ.-ብልጽግና ፡ ፓርቲ ፡ የሚመ፟ራ፟ው ፡ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፡ ቅሬታ ፡ ይዘት ፥ ድንገት ፥ የሕ.ወ.ሐ.ት. ፡ ጥቃቶች ፡ በሰራዊቱ ፡ ክፍለ ፡ ጦሮች ፡ ላይ ፡ በትግራይ ፡ “ክልል” ፡ ውስጥ ፡ በመደ፟ገማቸው ፥ እንደውጭ ፡ ጕዳይ ፡ “ሚኒስቴር” ፡ ቃል ፡ አቀባይ ፡ አገላለጽ ፥ «ቀዩ ፡ መስመር ፡ ታለፈ» ፡ ብሎ ፥ አኹን ፡ የምንመለከተውን ፡ “ሕግን ፡ የማስከበር ፡ ዘመቻ” ፡ ከዘገየ ፡ ሊያውጅ ፡ ተገደደ ። በጦር ፡ ሰራዊት ፡ ክፍለ ፡ ጦሮች ፡ ላይ ፡ ጥቃት ፡ እስከተፈጸመበት ፡ እስከ ፡ ጥቅምት ፡ 24 ፡ ቀን ፡ 2013 ፡ ዓ.ም. ፡ ድረስ ፥ በእየወረዳው ፡ በ”ዘር ፡ ማጽዳት” ፡ ሽፋን ፡ የተፈጸሙትን ፡ ፀረ ፡ ሀገራዊ ፡ (ፀረ ፡ ዐማራ) ፡ ጭፍጨፋዎች ፡ ዅሉ ፡ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፡ ቅሬታ ፡ ይዘት ፡ በሕ.ወ.ሐ.ት. ፡ እያመካኘ ፡ ሕግን ፡ ከማስከበር ፡ እስካኹን ፡ መታቀቡ ፥ የፀረ ፡ ሀገራዊ ፡ (ፀረ ፡ ዐማራ) ፡ ጥቃቶቹን ፡ ውጤት ፡ (ማለት ፥ በዘር ፡ ላይ ፡ የተመሠረቱ ፡ “ክልሎችን” ፡ ለማጠናከርና ፡ ለግንጠላ ፡ ለማብቃት) ፡ ስለሚፈልገው ፡ እንደ ፡ ነበር ፡ በብዙ ፡ ማስረጃዎች ፡ ተረጋግጧል ። ይህን ፡ መግለጫ ፡ አሰናድተን ፡ በምናጠናቅቅበት ፡ ሰዓት ፥ ታኅሣሥ ፡ 16 ፡ ቀን ፡ 2020 ፡ ዓ.ም. ፥ በ”በኒ ፡ ሻንጉል ፡ ጉምዝ ፡ ክልል” ፡ ባንድ ፡ መንደር ፡ ብቻ ፡ ከ200 ፡ ያላነ፟ሱ ፡ ሀገራውያን ፡ (ዐማራዎች) ፡ ተጨፍጭፈው ፡ መገደላቸውን ፡ በታላቅ ፡ ሐዘን ፡ ተረድተናል ። ይህም ፡ የደረሰው ፥ ዶክተር ፡ ዐቢይ ፡ አሕመድ ፡ “ክልሉን” ፡ በጐበኙ ፡ ማግስት ፡ ነው ።
በዚህ ፡ ምክንያት ፥ “ፕሬዚደንቷ”ን ፡ ወይዘሮ ፡ ሣህለ ፡ ወርቅ ፡ ዘውዴን ፡ እና ፡ “ጠቅላይ ፡ ሚኒስትሩ”ን ፡ ዶክተር ፡ ዐቢይ ፡ አሕመድን ፡ ጨምሮ ፥ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፡ ቅሬታ ፡ ይዘት ፡ ዋና፟ ፡ ዋና፟ ፡ ኀላፊዎችና ፡ የክልል ፡ ኀላፊዎች ፥ ከሕ.ወ.ሐ.ት. ፡ ኀላፊዎች ፡ እኩል ፥ በሀገር ፡ ክዳት ፡ አንቀጽና ፡ በፀረ ፡ ስብኣዊነት ፡ ወንጀል ፡ ተባባሪነት ፡ አንቀጽ ፡ በሕግ ፡ ይጠየቃሉ ፡ ሲል ፡ ኢ.ሀ.ሥ.አ. ፡ ዳግመኛ ፡ ያስታውቃል ።
ለብዙ ፡ ዓመታት ፡ በኤርትራ ፡ ሠልጥነውባቸው ፣ ታጥቀውባቸውና ፡ ሰፍረውባቸው ፡ ከነበሩት ፡ ከሕዝባዊ ፡ ግንባር ፡ ሐርነት ፡ ኤርትራ ፡ (ሕ.ግ.ሐ.ኤ. ፡ ወይም ፡ “ሻዕቢያ”) ፡ የውንብድና ፡ ኀይል ፡ የጦር ፡ ሰፈሮች ፥ በ2010-11 ፡ ዓ.ም ፥ በዶክተር ፡ ዐቢይ ፡ አሕመድ ፡ የውንብድና ፡ አገዛዝ ፡ ፈቃድ ፥ ወደ”ኦሮሞ ፡ ክልል” ፡ ከእነሙሉ ፡ ትጥቃቸው ፡ ገብተው ፡ እንዲሰፍሩ ፡ የተደረጉት ፡ “የኦሮሞ ፡ ነጻነት ፡ ግንባር” ፡ ተዋጊዎች ፥ በእንቅስቃሴያቸውም ፡ ኾነ ፡ በሥራቸው ፡ አንዳች ፡ ገደብ ፡ ሳይደረግባቸው ፥ ዓመት ፡ ባልሞላ ፡ ጊዜ ፡ ውስጥ ፥ በብዙ ፡ ሺሕ ፡ የሚቈጠሩ ፡ ንጹሓን ፡ ኢትዮጵያውያንን ፡ መግደላቸውና ፡ በሚልዮን ፡ የሚቈጠሩትንም ፡ ማፈናቀላቸው ፡ ይታወቃል ። ለዚህ ፡ ዅሉ ፡ ወንጀል ፡ የዶክተር ፡ ዐቢይ ፡ አሕመድ ፡ የውንብድና ፡ አገዛዝ ፡ ተጠያቂ ፡ መኾኑን ፡ የኢትዮጵያ ፡ ሕዝብ ፡ ያውቃል ፤ “የሞት ፡ ነጋዴዎች”ም ፡ ይህኑ ፡ ሰው ፡ “የሰላም ፡ ኖቤል”ን ፡ ሸልመውታል ።
በሠኔ ፡ ወር ፡ 2012 ፡ ዓ.ም. ፡ በ”ኦሮሞ ፡ ክልል” ፡ ታጣቂዎችና ፡ በኦ.ነ.ግ. ፡ ታጣቂዎች ፡ በተደራጁና ፡ በተሰማሩ ፡ ዱርዬዎች ፡ በግፍ ፡ የተጨፈጨፉትንና ፡ ንብረቶቻቸው ፡ የተዘረፉባቸው ፣ የወደሙባቸው ፡ በዐሥር ፡ ሺሕ ፡ የሚቈጠሩትን ፡ ጕዳተኞች ፡ ደግሞ ፥ ምንም ፡ ዐይነት ፡ ካሳ ፡ እንደማይክሳቸው ፡ ይህ ፡ ዐምባ ፡ ገነን ፡ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፡ ቅሬታ ፡ ይዘት ፡ በዕብሪት ፡ ማስታወቁ ፡ ይታወሳል ።
ኅዳር ፡ 19 ፡ ቀን ፡ 2013 ፡ ዓ.ም. ፥ “ሕግን ፡ የማስከበር ፡ ዘመቻ”ው ፡ በታወጀ ፡ በ25ኛ ፡ ቀኑ ፥ የኢትዮጵያ ፡ ሀገራዊ ፡ ሰራዊት ፥ የወያኔ ፡ ከሓዲ ፡ ኀይልን ፡ መደምሰሱንና ፡ ማዘዣው ፡ ያደረጋትን ፡ መቀሌ ፡ ከተማን ፡ ሙሉ ፡ በሙሉ ፡ መቈጣጠሩን ፡ ያበሠረውን ፡ የድል ፡ ዜና ፡ በመስማቱ ፡ የኢትዮጵያውያን ፡ ሀገራዊ ፡ ሥልጡንሕዝባዊ ፡ አንድነት ፡ (ኢ.ሀ.ሥ.አ.) ፡ ከፍ ፡ ያለ ፡ ደስታ ፡ ተሰምቶታል ። የኢትዮጵያ ፡ ሀገራዊ ፡ ሰራዊት ፡ አባላት ፡ የኢትዮጵያ ፡ ጥንታዊ ፡ የርትዕ ፡ ሥልጣኔ ፡ የ«ሥልጡንሕዝብና» ፡ ምርቶች ፡ ናቸውና ፥ ምንም ፡ ላለፉት ፡ 50 ፡ ዓመታት ፡ የማያቋርጥ ፡ ንኅለተኛ ፡ ስብከትና ፡ የአእምሮ ፡ ዕጥበት ፡ ቢሞ፟ከ፟ርባቸው ፥ ሀገራቸው ፡ ኢትዮጵያ ፡ የተመሠረተችባቸውን ፡ ዘላለማውያን ፡ ኅልያዎች ፡ ከፍ ፡ አድርገው ፡ በመያዝ ፡ እስከ ፡ ዛሬ ፡ ጠብ፟ቀው ፡ ማቈየታቸውን ፡ በድል ፡ አረጋግጠዋል ። በዚህ ፡ ዕለት ፡ ፋሺዝምን ፡ በ80 ፡ ዓመት ፡ ለኹለተኛ ፡ ጊዜ ፡ ድል ፡ አድርገውታል ።
እዚህ ፡ ላይ ፡ ሳናነሣው ፡ የማናልፈው ፡ ለሤራው ፡ ዅሉ ፡ ማብረሻ ፡ የኾነው ፡ ያልተጠበቀ ፡ ድርስ ፡ አለ፟ ። ጥቅምት ፡ 24 ፡ ቀን ፡ 2013 ፡ ዓ.ም. ፥ የሕ.ወ.ሐ.ት. ፡ የውንብድና ፡ ኀይል ፡ በሰሜን ፡ ኢትዮጵያ ፡ የሰፈረውን ፡ የኢትዮጵያ ፡ ጦር ፡ ሰራዊት ፡ ድንገት ፡ ባጠቃበት ፡ ወቅት ፥ ጦሩ ፡ ክፉኛ ፡ ተጐድቶ ፡ ላጠቃላይ ፡ ድምሳሴ ፡ ተጋልጦ ፡ ነበር ። ማዘዣውን ፡ ባሕር ፡ ዳር ፡ ያደረገውና ፡ አረንጓዴ ፣ ብጫ ፣ ቀይ ፡ የኢትዮጵያ ፡ ሰንደቅ ፡ ዐላማን ፡ ያነገበው ፡ የጐንደር ፣ የወሎ፟ ፣ የጐዣምና ፡ የሸዋ ፡ ክፍላተ ፡ ሀገር ፡ ሕዝባዊ ፡ ሰራዊት ፥ ማንም ፡ ባልጠበቀው ፡ ፍጥነት ፥ በእልኽና ፡ በዠግንነት ፡ ተወርውሮ ፡ ለተከበበው ፡ ሰራዊት ፡ ስለ ፡ ደረሰለትና ፥ የሕ.ወ.ሐ.ት.ን ፡ የሽፍታ ፡ ኀይል ፡ እጅግ ፡ ባነሰ ፡ ትጥቅና ፡ የሰራዊት ፡ ቍጥር ፡ ስላሽቀነጠረው ፥ ይደርስ ፡ የነበረውን ፡ የከፋ፟ ፡ ሀገራዊ ፡ አደጋ ፥ ተኣምር ፡ በሚያሠኝ ፡ ክንዋኔ ፡ አስወግዶ ፥ ከመቀሌም ፡ ከዐዲስ ፡ አበባም ፡ ይጠ፟በ፟ቅ ፡ የነበረውን ፡ ጥፋት ፡ አርክሶታል ። የዚህ ፡ ሕዝባዊ ፡ ሰራዊት ፡ ሟያ ፡ ዃላ ፡ “ሕግን ፡ የማስከበር ፡ ዘመቻ” ፡ ለተባለው ፡ ግብረት ፡ መሳካት ፡ ያንበሳውን ፡ ድርሻ ፡ ይዟል ።
የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፡ ቅሬታ ፡ ይዘት ፡ ኀላፊዎች ፥ ኹኔታው ፡ ከቍጥጥራቸው ፡ በመውጣቱ ፡ ተገደውም ፡ ቢኾን ፥ በመጨረሻ ፡ ይህን ፡ “ሕግን ፡ የማስከበር ፡ ዘመቻ” ፡ ያሉትን ፡ ግብረት ፡ ማወጃቸውና ፥ የውጭ ፡ ኀይሎችን ፡ ተጽዕኖ ፡ ተቋቁመው ፥ በስኬት ፡ ማስፈጸማቸው ፡ ያስመሰግናቸውም ፥ በታሪክም ፡ ለሀገር ፡ እና ፡ ለሕዝብ ፡ እንደዋሉት ፡ ውለታ ፡ ይቈጠርላቸውም ፡ ይኾናል ።
ነገር ፡ ግን ፥ እነርሱ ፡ “ሕግ” ፡ የሚሉት ፡ የኢትዮጵያን ፡ ሕዝብ ፡ የካደና ፡ እግዚእናውን ፡ የረመረመ ፡ ሕገ ፡ ወጥ ፡ አቋማቸውን ፡ ነው ። እውነተኛው ፡ ሕግን ፡ የማስከበሩ ፡ ዘመቻ ፡ የኢትዮጵያ ፡ ሕዝብ ፡ እግዚእናን ፡ እስከ ፡ ማክበርና ፥ ለዚህ ፡ ዅሉ ፡ ፍጅት ፡ ምክንያት ፡ የኾነውን ፡ ባዕድ ፡ ሠራሹንና ፡ ሕገ ፡ ወጡን ፡ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፡ “ሕገ ፡ መንግሥት” ፡ በመሻር ፥ ለሽግግር ፡ መንግሥት ፡ ቦታውን ፡ እስከ ፡ መልቀቅ ፡ ስለሚኼድ ፥ ኀላፊዎቹ ፡ ይህኑ ፡ ለማድረግ ፡ እንዲዠግኑ ፡ ኢ.ሀ.ሥ.አ. ፡ በሀገር ፡ ፍቅር ፡ ዳግመኛ ፡ ያሳስባቸዋል ። በዚህ ፡ ምስቅል ፡ ስያሳዊ ፡ ወቅት ፥ ለሀገርና ፡ ለሕዝብ ፡ ተብሎ ፡ በተፈጸመ ፡ በታላቅ ፡ ወሮታነት ፡ ታሪክ ፡ የሚዘክርላቸው ፡ ይህን ፡ የመጨረሻ ፡ አድራጎታቸውን ፡ ይኾናል ።
2 ፤ ቢፍገመገምም ፥ ቆዳውን ፡ የገለፈፈ ፡ ቅሬታ ፡ ይዘት ።
ከስድስት ፡ ዓመት ፡ በፊት ፥ የተባበሩት ፡ ያሜሪካ ፡ ኹነቶች ፡ ርእሰ ፡ ሀገርና ፡ “የሰላም ፡ ኖቤል ፡ ተሸላሚ” ፡ ባራክ ፡ ኦባማ ፥ በሐምሌ ፡ ወር ፡ 2007 ፡ ዓ.ም. ፡ ኢትዮጵያን ፡ በጐበኙበት ፡ ወቅት ፥ መቶ ፡ በመቶ ፡ የኢ.ሕ.አ.ዴ.ግ. ፡ አባላት ፡ ብቻ ፡ በሚመክሩበት ፡ በአሻንጕሊቱ ፡ የተወካዮች ፡ ምክር ፡ ቤት ፡ ፊት ፡ ቆመው ፥ በኢትዮጵያ ፡ የ”ዴሞክራሲ” ፡ ማበብን ፡ እንዳደነቁለትና ፡ የቢልዮን ፡ ዶላር ፡ ዓመታዊ ፡ ርዳታን ፡ ለውንብድና ፡ ይዘቱ ፡ እንዳስቀጠሉለት ፡ ይታወሳል ። ዘንድሮ ፡ ደግሞ ፥ ኅዳር ፡ 21 ፡ ቀን ፡ 2013 ፡ ዓ.ም. ፥ የዚያ ፡ ዘመን ፡ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፡ ጨቋኝ ፡ ይዘት ፡ የጸጥታ ፡ ኀላፊ ፥ ያኹኑ ፡ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፡ ቅሬታ ፡ ይዘት ፡ ዋና ፡ ተጠሪና ፡ ሌላው ፡ “የሰላም ፡ ኖቤል ፡ ተሸላሚ” ፥ ዶክተር ፡ ዐቢይ ፡ አሕመድ ፥ በዚሁ ፡ አሻንጕሊት ፡ ጉባኤ ፡ ፊት ፡ በሰጡት ፡ ቃል ፥ «ለቀባሪው ፡ አረዱት» ፡ በሚያሠኝ ፡ ኹኔታ ፥ እስከ ፡ ዛሬ ፡ ድረስ ፡ “ምስጢርነቱ” ፡ ተጠብ፟ቆለት ፡ የነበረውን ፡ የይዘቱን ፡ ጨቋኝ ፡ ጠባይና ፡ አሠራር ፡ በዝርዝር ፡ ከሥተውበታል ። ኢ.ሀ.ሥ.አ. ፡ ንግግራቸውን ፡ በጥንቃቄ ፡ አድምጧል ፤ እስካኹን ፡ የነበረውን ፡ መረጃም ፡ ኾነ ፡ ድምዳሜ ፡ አጠናክሮለታል ፡ እንጂ ፡ ዐዲስ ፡ መረጃን ፡ አላገኘበትም ። ዋና ፡ ተጠሪው ፡ ይነግሩናል ፡ ብሎ ፡ ኢ.ሀ.ሥ.አ. ፡ የጠበቀው ፡ በ2010 ፡ ዓ.ም. ፡ ሕ.ወ.ሐ.ት. ፡ በትረ ፡ ውንብድናውን ፡ ለርሳቸውና ፡ ለቡድናቸው ፡ ሲያስረክብ ፡ በምን ፡ ስምምነት ፡ መሠረት ፡ እንደ ፡ ነበር ፥ ምስጢረኛ ፡ ስምምነቱንስ ፡ የትኛው ፡ ወገን ፡ መዠመሪያ ፡ እንዳፈረሰውና ፡ ለዚህ ፡ ስብራት ፡ እንዳደረሰው ፡ ዝርዝር ፡ መረጃን ፡ እንዲሰጡ ፡ ነበር ። ይህ ፡ ለጊዜው ፡ ስላልተገለጠ ፥ በሽግግር ፡ መንግሥት ፡ ወቅት ፡ በሚቋቋመው ፡ መርማሪ ፡ ድርገት ፥ ዶክተር ፡ ዐቢይ ፡ አሕመድ ፡ እና ፡ ቡድናቸው ፥ እንደተረፉት ፡ የሕ.ወ.ሐ.ት. ፡ መሪዎች ፡ ዅሉ ፥ ተጠይቀው ፡ በእነርሱ ፡ በኩል ፡ የሚያውቁትን ፡ ይመልሳሉ ፡ ሲል ፡ ኢ.ሀ.ሥ.አ. ፡ በተስፋ ፡ ይጠብቃል ።
የተወሰኑ ፡ የውጭ ፡ መንግሥታት ፡ ኢትዮጵያን ፡ በረዥም ፡ ዘመን ፡ ሤራ ፡ ለመደምሰስ ፥ በእጅ ፡ አዙር ፡ ይዘቶቻቸው ፡ አማካይነት ፥ ያከታተሉባትን ፡ አጠቃላይ ፡ የጥፋት ፡ ናዳ ፥ እንዲህ ፡ ከይዘቱ ፡ ተጠሪ ፡ ከዶክተር ፡ ዐቢይ ፡ አሕመድ ፡ ገለጻ ፡ በማያጠራጥር ፡ ኹኔታ ፡ ለማረጋገጥና ፡ ለመደምደም ፡ ተችሏል ። ምልክዮሽ ፥ ላለፉት ፡ 30 ፡ ዓመታት ፥ ላይ ፡ ላዩን ፡ ለሰው ፡ ልጅ ፡ መብትና ፡ ለ”ዴሞክራሲ” ፡ ተሟጋች ፡ መስሎ ፡ በመመጻደቅ ፥ ለፍጹም ፡ የንጥቂያ ፡ ዐላማው ፥ ጨቋኙንና ፡ ንኅለተኛውን ፡ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፡ ይዘት ፡ ሲያቋቁመው ፣ ሲደግፈውና ፡ ሲከባከበው ፡ ኖሯል ። የዓለም ፡ ኅብረተሰብ ፡ ሌላ ፡ ማስረጃን ፡ ሳይጠይቅ ፥ የኢትዮጵያን ፡ መበ፟ደ፟ል ፡ እንዲያውቅለት ፡ ኢ.ሀ.ሥ.አ. ፡ ድምፁን ፡ በዚህ ፡ ረገድ ፡ ዳግመኛ ፡ ያሰ፟ማ፟ል ።
በሕ.ወ.ሐ.ት ፡ መደ፟ምሰስ ፡ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፡ ይዘት ፡ ምሰሶውን ፡ ዐጥቷል ፤ መፍረሱ ፡ የጊዜ ፡ ጕዳይ ፡ ኾኗል ። ዛሬ ፡ የትግራይ ፡ “ክልል” ፡ በገቢር ፡ ፈርሷል ፤ ሌሎቹም ፡ “ክልሎች” ፡ ይከተላሉ ። መላ፟ ፡ ኢትዮጵያ ፡ (ባሕር ፡ ምድርንና ፡ ደንከልን ፡ ጨምሮ) ፡ በዐዲስ ፡ የግዛት ፡ አወቃቀር ፡ በምትዋቀርበት ፡ ዋዜማ ፡ ላይ ፡ ትገ፟ኛለች ። መላ፟ው ፡ የኢትዮጵያ ፡ ሕዝብ ፡ እና ፡ ሰራዊቱ ፡ ለመሠረታዊ ፡ ለውጡ ፡ ይነ፟ሣ፟ሉ፟ ። የምልክዮሽ ፡ የ100 ፡ ዓመት ፡ ጥረትም ፥ የመኖር ፡ ምክንያቱን ፡ ዐጥቷል ፡ ባያሠኝም ፥ መዳከሙ ፡ ርግጥ ፡ ኾኗል ፤ በኢትዮጵያ ፡ ላይ ፡ ያጠላ፟ው ፡ አደጋ ፡ ግን ፡ ገና ፡ አልተወገደም ።
የተፍገመገመው ፡ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፡ ቅሬታ ፡ ይዘት ፥ ቆዳውን ፡ እንደገለፈፈ ፡ እባብ ፥ ባዲስ ፡ ገጽታ ፡ ለመታየትና ፥ በረዥሙ ፡ ያቀደ ፡ በመምሰል ፥ ለመጪው ፡ “ምርጫ” ፡ ከመሰናዳትም ፡ ዐልፎ ፥ ስለጠቅላላው ፡ ያፍሪቃ ፡ ቀንድ ፡ አወቃቀርም ፡ ደፋ ፡ ቀና ፡ ማለትን ፡ ይዟል ። ስያሳ ፡ ግን ፡ የሚ፟ሠ፟ራ፟ው ፡ በእውን ፡ መሠረት ፡ ላይ ፡ እንጂ ፥ በምኞት ፥ ያውም ፡ በክፉ ፡ ምኞት ፡ መሠረት ፡ ላይ ፡ ሊኾን ፡ አይገ፟ባ፟ም ። የቅሬታው ፡ ይዘት ፡ መጨረሻ ፡ እንደማያምር ፡ ይህ ፡ ብቻውን ፡ ያስረዳናል ።
ምልክዮሽ ፡ በኢትዮጵያ ፡ ላለበው ፡ ፀረ ፡ ሥልጣኔ ፡ የንጥቂያ ፡ ዐላማው ፡ ፍጡሩን ፡ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፡ ይዘት ፡ ጠጋግኖ ፡ እስከተልእኮው ፡ ፍጻሜ ፡ ድረስ ፡ ሊሠራበት ፡ መሞከሩን ፡ በእልክ ፡ ተያይዞታል ። ይህም ፥ በተለይ ፡ ድልን ፡ በተቀዳጁትና ፡ የይዘቱን ፡ ንኅለተኛ ፡ ምኞት ፡ ፈጽመው ፡ በሚቃወሙት ፡ የኢትዮጵያ ፡ ሰራዊት ፡ ከፍተኞች ፡ መኰንኖች ፡ ላይ ፡ ዐዲስ ፡ ዙር ፡ የወገዳ ፡ ዘመቻ ፡ በቅርቡ ፡ እንደሚዠ፟መ፟ር ፡ ያመለክታል ።
ሲኾን ፡ ቢውል ፡ ግን ፥ ጨለማ ፡ ብርሃንን ፡ አያሸንፈውምና ፥ ኢትዮጵያ ፥ በርትዕ ፡ ሥልጣኔዋ ፡ ብርሃን ፡ ተመርታና ፡ ጸንታ ፥ ይህንም ፡ የጨለማ ፡ ወቅት ፡ በነጻነቷ ፣ በአንድነቷና ፡ በሙሉነቷ ፡ ተሻግራው ፥ ወደ ፡ ብሩህ ፡ ነገዋ ፡ ትዘልቃለች ።
3 ፤ የውሳኔ ፡ ወቅት ።
የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፡ ቅሬታ ፡ ይዘት ፡ ኀላፊዎች ፥ እንደሕ.ወ.ሐ.ት. ፡ ኀላፊዎች ፡ ዅሉ ፥ እነርሱም ፡ ይህን ፡ ሕገ ፡ ወጥ ፡ “ሕገ ፡ መንግሥት” ፦ «እናስቀጥላለን» ፡ በማለት ፡ ወደ ፡ ትፋታቸው ፡ እንዳይመለሱ ፥ ዛሬ ፡ በሕ.ወ.ሐ.ት. ፡ ላይ ፡ የደረሰው ፡ መደ፟ምሰስና ፡ ዐመድ ፡ መኾን ፡ ትምህርት ፡ ይኹናቸው ፡ ሲል ፡ ኢ.ሀ.ሥ.አ. ፡ በአጽንዖት ፡ ሊያመለክታቸው ፡ ይወዳል ።
ይልቅስ ፥ ቀና፟ውን ፡ መንገድ ፡ በመከ፟ተል ፥ የኢትዮጵያ ፡ ሕዝብ ፡ የጠየቀውን ፡ የእግዚእናውን ፡ መከ፟በር ፡ በማረጋገጥ ፥ ዐዲስ ፡ ሥልጡንሕዝባዊ ፡ ሕገ ፡ መንግሥት ፡ የሚረቀቅበትንና ፡ የሚጸድቅበትን ፡ ምዕራፍ ፡ ስለሚከፍተው ፡ የሽግግር ፡ መንግሥት ፡ መቋቋም ፡ ጕዳይ ፥ ከመላ ፡ የኢትዮጵያ ፡ ሕዝብ ፡ ተወካዮች ፡ ጋራ ፡ ለመነጋገር ፡ ሀገራዊ ፡ ጉባኤን ፡ ለመጥራት ፡ እንዲስማሙ ፡ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፡ ቅሬታ ፡ ይዘት ፡ ኀላፊዎችን ፡ ኢ.ሀ.ሥ.አ. ፡ በታላቅ ፡ ዐደራ ፡ ዳግመኛ ፡ ያሳስባቸዋል ።
መደምደሚያውን ፥ ከዚህ ፡ በላይ ፡ በተዘረዘሩት ፡ አንጻር ፡ የአዎንታዊ ፡ አቋማቸው ፡ መታመኛ ፡ ይኾንላቸው ፡ ዘንድ ፥ የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ፡ ቅሬታ ፡ ይዘት ፡ ኀላፊዎች ፦
1) እስካኹን ፡ በሕ.ወ.ሐ.ት. ፡ ሲላከኩ ፡ የነበሩት ፡ በእየክልሉ ፡ የሚፈጸሙት ፡ ፀረ ፡ ሀገራዊ ፡ (ፀረ ፡ ዐማራ) ፡ ጥቃቶች ፥ ከሕ.ወ.ሐ.ት. ፡ መወገድ ፡ ወዲህም ፡ መቀጠላቸውና ፡ በነገሩ ፡ የቅሬታ ፡ ይዘቱ ፡ ከፍተኞች ፡ ኀላፊዎች ፡ እጅ ፡ መኖሩን ፡ ማስረጃዎች ፡ ስላረጋገጡ ፥ እነዚህን ፡ የሀገራዊ ፡ ክዳት ፡ ወንጀሎች ፡ በፍጥነት ፡ ከማዘዣው ፡ እንዲያስቆሙ ፤ ለዚህም ፡ ተደጋጋሚ ፡ ጥፋት ፡ ዋናው ፡ ተጠያቂ ፡ “ጠቅላይ ፡ ሚኒስትር” ፡ ዐቢይ ፡ አሕመድ ፡ ስለ ፡ ኾኑ ፥ ከኀላፊነታቸው ፡ ተወግደው ፥ ምርመራ ፡ እስኪዠመር ፡ ድረስ ፥ በቁም ፡ እስርነት ፡ እንዲቈዩ ፤
2) በሠኔ ፡ ወር ፡ 2012 ፡ ዓ.ም. ፡ በሐሰት ፡ ተወንጅለው ፡ አላግባብ ፡ የታሰሩትን ፡ እንደ ፡ አቶ ፡ እስክንድር ፡ ነጋ ፡ ያሉ፟ትን ፡ የስያሳ ፡ ቡድን ፡ ኀላፊዎችንና ፡ የማወራኛ ፡ ባለሟያዎችን ፡ ከእስር ፡ ቤት ፡ በፍጥነት ፡ እንዲፈቱ ፤
3) የኢትዮጵያ ፡ አንድያ ፡ ባለቤት ፡ የኾነውን ፡ የኢትዮጵያን ፡ አንድ ፡ ሕዝብ ፥ በፋሺስታዊ ፡ እልኽ ፡ “ሕዝቦች” ፡ እያሉ ፡ ሀገሪቱን ፡ ባለቤት ፡ አልባ ፡ የሚያደርጉበትን ፡ ከፋፋይ ፡ የጠላት ፡ አነጋገር ፡ ከኀላፊዎቹና ፡ በቍጥጥራቸው ፡ ሥር ፡ ካሉት ፡ ማወራኛዎች ፡ ገለጻዎች ፡ ፈጽመው ፡ እንዲያስወግዱ ፤
4) በኢትዮጵያ ፡ አንድያ ፡ ሀገራዊ ፡ ቋንቋ ፡ በዐማርኛ ፡ ላይ ፡ እስካኹን ፡ በግልጽ ፡ ደባቸውን ፡ ሲፈጽሙ ፡ የቈዩባቸውን ፡ ነውረኞች ፡ የጠላትነት ፡ አቋምና ፡ አሠራር ፡ በይፋ ፡ አውግዘዋቸው ፥ ለሀገራዊው ፡ ቋንቋ ፡ የሚ፟ገ፟ባ፟ውን ፡ ክብር ፣ ጥንቃቄና ፡ ክብካቤ ፡ በገቢር ፡ እንዲያሳዩ ፤
5) ዛሬ ፡ ዳግም ፡ የተሰነከሉት ፡ የፋሺዝም ፡ የምልክዮሽና ፡ የአፓርትሀይድ ፡ ተምሳሊት ፥ ባለሰማያዊ ፡ መደብ ፡ ዐምስት ፡ እግር ፡ ኮከብን ፥ ቀደም ፡ ሲል ፡ እሰንደቅ ፡ ዐላማችን ፡ ላይ ፡ በውንብድና ፡ ዐዋጅ ፡ እንደለጠፉት ፡ ዅሉ ፥ መልሰው ፡ በራሳቸው ፡ ዐዋጅ ፡ በሰላም ፡ እንዲያስወግዱ ፥
እያለ ፥ ከመልካም ፡ ምኞቱ ፡ ጋራ ፥ ኢ.ሀ.ሥ.አ. ፡ ያሳስባቸዋል ፥ ያበራታቸዋልም ።
ለመላ፟ው ፡ የኢትዮጵያ ፡ ሕዝብ ፥ ሰንደቅ ፡ ዐላማው ፡ የነጻነቱ ፣ የእግዚእናውና ፡ የአንድነቱ ፡ ተምሳሊት ፡ ነው ፤ ወይም ፡ በሌላ ፡ አነጋገር ፥ በራሱ ፡ ሥልጣኔ ፡ የቆመ ፡ ሐራ ፡ ሀገርነቱን ፡ በሰንደቅ ፡ ዐላማው ፡ ይመስ፟ልበታል ። በዚህ ፡ ረገድ ፥ ከማንም ፡ ፈቃድን ፡ መጠየቅ ፡ ወይም ፡ መቀበል ፡ ስለማያሻው ፥ ነጻነቱን ፡ የመዋጀት ፣ እግዚእናውን ፡ የማስከበርና ፡ ሥልጡንሕዝባዊ ፡ የርትዕ ፡ መንግሥቱን ፡ የመመሥረት ፡ የተቀደሰ ፡ ተግባሩን ፡ እዳር ፡ ለማድረስ ፥ ከእንግዲህ ፡ አረንጓዴ ፣ ብጫ ፣ ቀይ ፡ ሰንደቅ ፡ ዐላማውን ፡ ይዞ ፡ ከሰራዊቱ ፡ ጋራ ፡ በአንድነት ፡ ተነሥቷል ። ይህን ፡ በመፃረር ፡ ደፍሮ ፡ የሚመጣበት ፡ የጭቈና ፡ ኀይል ፡ ቢኖር ፡ ደግሞ ፥ የኢትዮጵያ ፡ ሕዝብ ፡ በሰላማዊም ፡ ኾነ ፡ በማንኛውም ፡ መንገድ ፡ ሊከላከለው ፡ ሙሉ ፡ መብት ፡ አለ፟ለ፟ት ፤ የኢትዮጵያ ፡ ሰራዊትም ፥ ተገቢ ፡ መንግሥት ፡ በሌለበት ፡ ባኹኑ ፡ ኹኔታ ፥ ለሕዝብ ፡ እግዚእና ፡ የመታዘዝ ፡ ግዴታ ፡ አለ፟በ፟ት ፨
የጊዜያዊ ፡ ፈጻሚ ፡ ምክር ፡ ጽሕፈት ፡ ቤት ፥
ኢ.ሀ.ሥ.አ. ።
——-
[የኅዳግ ፡ ምልክቶች]
⁽1⁾ • ሀገራዊ፤ የነጻ፡ሕዝብ፡አባል፣ የሀገር፡ባለቤት፣ እግዚእና፡ያለ፟ው፣ ሿሚ፣ ሻሪ፡ኢትዮጵያዊ፡(citizen | citoyen)።
• ዐማራ፡(ዐም፡ሐራ)፤ ነጻ፡ሕዝብ፥ የመላ፟፡ኢትዮጵያ፡ሕዝብ፡የሀገራዊነት፡ወይም፡የሀገር፡ባለቤትነት፡ስሙ፡(citizenry)።
⁽2⁾ ይዘት ፤ በግእዝ ፡ ‘እኅዘት’ ፥ አለሥልጣኑ ፥ መንግሥታዊ ፡ ኀይልን ፡ በእጀ ፡ መናኛ ፡ የጨበጠ ፡ ዐምባ ፡ ገነን ፡ አገዛዝ ፡ (“régime”) ።
⁽3⁾ ጠገዴ፡ወይም፡ጸገዴ፤ ‘ጸ’፡እና፡’ጠ’፡ባማርኛ፡ተወራራሽ፡ፊደሎች፡ስለ፡ኾኑ፥ ግዛቱ፡በኹለቱም፡አጠራሮች፡ይጠ፟ራ፟ል። እንዲሁም፡ጠለምት፡እና፡ጸለምት፥ ሞጣ፡እና፡ሞጻ፥ ጣና፡እና፡ጻና፥ ወዘተርፈ፡…።
=====================================================
የኢትዮጵያውያን ፡ ሀገራዊ ፡ ሥልጡንሕዝባዊ ፡ አንድነት ።
ETHIOPIANS’ CITIZEN DEMOCRATIC UNION
ተጨማሪ ያንብቡ:  በስደት ከሚገኘው ቅዱስ ሲኖዶስ የተሰጠ ወቅታዊ መግለጫ

1 Comment

  1. የድርጂት ስም ጋጋታ እና ከ_ የማያድን መግለጫ ማንበብ እና መስምቱ ሰለቸን፡፡ ዘጠኝ ሱሪ ከእንትን አያድምንም እንደተባለው ከመግለጫ እሩምታ ይልቅ በትግባር የርስን ድርሻ መውጫቱ መልካም ነው፡፡

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share