““ነጻ”” ይወጣ ይሆን? ( ከአሁንገና ዓለማየሁ)

ምስኪኑ ገበሬ የትግራይ ወገኔ
““ነጻ”” ይወጣ ይሆን ካምሳ አመት ኩነኔ?
ወይስ ለሌላ ዙር ድርቅና ጦርነት
የማይታክታቸው ክህደት ባንድነት
የጃጁት ልጆቹ ይማግዱት ይሆን
አልረታም ብለው ለተረኛው ዝኆን?
ትናንትም ሣር ሆኖ ተረግጦ ነበረ
ካንድ ቤት ሁለት ልጅ ሦስት እየገበረ
በትግራይ ትግሪኝ መርዝ በእንግሊዝ ሰይጥነው
ወገን እንዲጠላ በሁሉ አሰልጥነው
የአድዋ መሳፍንት ሲገዙት ሸብበው
ዙሪያውን በጠላት ወገን አስከብበው
ሀገር አለቡበት እሱን ቅድሚያ አልበው።
ምን በላህ? ምን ጠጣህ? ጓዳህ ምን ተወራ?
ከሚስቱ አልጋ ላይ ምን ሠራ አባወራ?
እያለ ሚሰልል ጎረቤት ከዘመድ
በየሰዉ ጆሮ አስቀምጦ ወጥመድ
በመጡብህ ወሬ በአለቀልህ ሽብር
በወርቅ ፍቅፋቂ በተዘረፈ ብር
በአስቤዛ ካቴና በእንጀራ ቂጣ ፍንጅ
ቀጥቅጦ ከገዛው የሹምባሽ የልጅ ልጅ
ነጻነቱን ከቶ ያገኝ ይሆን ትግሬ
ጦርነት አይደለም ባሉት የጦር ወሬ
ወይስ እንደድሮው ባባእዳን ሴራ
ከወንድሙ አገው ኦሮሞና አማራ
ከሱማሌ አፋር እየተናነቀ
የገዛ ወገኑን ፈጅቶ እያለቀ
መከራው ከዛሬም ይብስ ይከፋ ይሆን
ሹሌ ሲጫወቱ ዝኆንና ዝኆን?

ይልቅስ
ትናንት ላንተ ሹምባሽ ገብራ ሀገሬ
የሹምባሽህ ሎሌ ጌታ ሲሆን ዛሬ
አልገብርም ብለህ አታስቸግር ትግሬ
ገብርና ይልቅስ
ባንዲት ጎጆ እናንባ
ባንዱ ጣራ እናልቅስ።

( ከአሁንገና ዓለማየሁ)

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሰውነት ውሀ ነው! - በላይነህ አባተ

1 Comment

  1. ምን አመጣው እንባ ምን አመጣውስ ለቅሶ
    እየገነባን ጣራችንን በአንድ ምሰሶ
    ሀገሪትዋ ደግ አዳራሹ ሰፊ
    ሁላችንንም በአንድ እልፍኝ አንቀባራ አሳራፊ
    እልል አልንለት ስንረዳ እንደቆረጠ ለመኖር ወያኔን ገርስሶ
    በሸማው የሁላችንንም እንባ አብሶ
    ነገ ጥዋት እንሆናለን ለተቸገረ ተራፊ
    ከጠበቀልን ግብር ሰብሳቢ ምሰሶዋችንን ከገፊ

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share