ትዕግሥተኛ ሰው – መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ

ትዕግሥተኛ ሰው ከኀያል፥ጥበብ የለው ሰውም ሰፊ ርስት ካለው፥በመንፈሱ የሠለጠነ ሰውም ሀገርን ከሚገዛ ሰው ይሻላል።

መጽሐፈ ምሳሌ ምዕራፍ 16 ቁ 32

 

አላዋቂዎችን ከጥበብ መራቅ እንደሚገድላቸው ፣ደጋግማ ጥበብ አሣይታናለች።ሂትለር፣ሞሶሎኒ፣ፖልፖት፣ጋዳፊ፣ሳዳም፣ወዘተ።ተዘርዝረው የማያልቁ አምባገነኖች ፣ከጥበብ መራቅና ትእቢት ነበር በህዝብ ተጠልተው በውግዘት እንዲሞቱ ያደረጋቸው።

እነዚህ መሪዎች፣   ለህዝቡ የማውቅለት እኔ ነኝ።ህዝብ ምን ያውቃል?ተመሪ ነው።ግኡዝ ወራጅ ውሃ ነው። ” በማለት የሚመፃደቁ ነበሩ።

ህይወት ባለው ወንዝ በሚመሠለው ህዝብ፣ አንደኛው ሲመጣ አንዱ እሥከወዲያኛው ሲሄድ በየዕለቱ በሚታይበት የምድር ገዢ በሆነው በወንዝ በተመሠለው፣ በዓለም  ህዝብ  ውሥጥ ፣ አያሌ ምጡቅ ጭንቅላቶች አሉ።  እነዚህን ምጡቅ ጭንቅላቶች ግን ብዙ ሀገሮች ሳይጠቀሙባቸው እንደዋዛ  አልፈዋል።

የአብዛኛው አገር መንግሥት ፣ እሥር ቤትን እና ባለጠመንጃውን ተማምኖ ህዝብን በኃይል ለመግዛት የሚጠር ከመሆኑም በላይ፣ ራሱን እንደአዋቂ ሌላውን ዜጋ  ወይንም ህዝብ እንዳአላዋቂ ሥለሚቆጥር ፣ ሀገሩ ባላት የሰው ጥበብ ለመጠቀም አልቻለም።ከጥበብ የራቀ የሰው ሥብሥብ መንግሥት ደግሞ በማንኛውም ሀገር ተጨባጭ ለውጥን በመፍጠር አሣደናቂና አሥገራሚ ብልፅግናን መጎናፀፍ እንደማይችል ከታሪክ ለመገንዘብ እንችላለን ።…

በእኛ ሀገርም      ከጥበብ የራቁ ፖለቲከኞች በኢትዮጵያ የለውጥ ጉዞ ላይ አውቀውም ሆነ ሣያውቁ መሠናክል በተደጋጋሚ በማሥቀመጣቸው፣የለውጥ ኃይሉ መሠናክሎቹን በማንሳትና መንገዱን በማፅዳት ሥለሚደክም ህዝቡ የሚጠብቀውን ለውጥ በፍጥነት ፣ እውን ለማድረግ አልቻለም።

በየጊዜው አደገኛ መሳናክሎችን በለውጡ መሪዎች ላይ የሚያሥቀምጡ  ፣ ከጥበብ የተጣሉ ፖለቲከኞችም ፍጥነቱን ገተውታል።እነዚህ ከጥበብ የራቁ ፖለቲከኞች፣ “የህዝብን ቁጣ ና ኃያልነት ለመገንዘብ የኢትዮጵያን የስልሳ ዓመት የፖለታካ ታሪክ ፍሰት እንዴት እንደነበር ቆም ብለው በመመርመር ለመማር ዝግጁ ያልሆኑ ናቸው።

እነዚህ ከጥበብ የራቁ ፖለቲከኞች ፣ቆም ብለው ማሠብ ቢችሉ ዛሬ እነሱ  የሚያቀነቅኑትን ሃሳብ ሲያቀነቅኑ የነበሩ ብዙዎቹ አፈር መሆናቸውን በተገነዘቡ ነበር።ያ ፊውዳላዊ አገዛዝ፣ ያ፣የመደብ ጎራ፣ያ፣የማርክሲስት አሥተሣሰብ ፣እነዛ ፈላጭ ቆራጭ  መሪ ተዋንያን  ዛሬ የሉም።ታሪካቸውን ለትውልዱ ጥለው አልፈዋል።

ከጥበብ የራቃችሁ ፖለቲከኞች ሆይ፣ነገ እናንተም ተልፋላችሁ።ሁሉም ኃላፊ ነው። ሁሉም ነገር ዛሬ እንዳሥቀመጥነው አይገኝም።ተፈጥሮ ምንጊዜም ተለዋዋጭ ናት እና ሰውም በየዘመኑ ከተፈጥሮ እየተማረ ፣በቴክኖሎጂ እየተራቀቀ በሃሳብ እየመጠቀ ሥለሚሄድ ነገ ፍፁም ሌላ ነገ ሆኖ ነው የምታገኙት።ምናልባት ዕድሜ ከሰጣችሁ ።

በጥበብ ላሥተዋለው፣ ነገ ዛሬን በፍፁም አይመሥልም።የተፈጥሮ አካል የሆነው ሰውም ዛሬ ከሚያሥበው ፍፁም የተለየ ሃሳብ ነገ ሊያሥብ ይችላል ።የዛሬ አቋሙ ነገ ቢቀየር አያሥገርምም።

ሰው ዳጎስ ባለ መፅሐፍ ይመሠላልና በየገፁ የሚያሥደነግጠን ፣እጅግ የሚመሥጠን፣ የሚያሥደሥተን፣የሚያሣዝነን፣አጅግ የሚገርመን ወይም አይረቤ ነው፣ወዘተ የሚያሠኘን ድብቅና ግልፅ ማንነት እንዳለው አንዘንጋ! ሰውን መሉ፣ለሙሉ ማወቁም  መቆጣጠርም አይቻልም።ይሄን ለማድረግ መሞከረም  ከጥበብ እጅግ ርቆ መገኘትን ይመሠክራል ።

ከዚህ እውነት አንፃር የሀገሬ ፖለቲከኞች ጥበብን ለመሸመት ወይም ለመግዛት ሁሌ በትጥሩ ፣የድህነት ማጥ ውሥጥ ያለውን ዜጋ በአጭር ጊዜ ውሥጥ በብልፅግና ሠገነት ላይ ልተሥቀምጡት እንደምትችሉ ተገንዘቡ።ይህንን   እውነት ካልተገነዘባችሁ ግን የኢትዮጵያ ህዝብ የዘወትር ፀሎት “ከእነዚህ ነቀረሳ ከሆኑ ‘ ሱሪ በአንገት ካልወለቀ ፣ ሞተን እንገኛለን።’ ባይ ፣ ከጥበብ የራቁ ፖለቲከኞች ፈጣሪያችን ሆይ ገላግለን።የሚል እንደሚሆን አሥባለሁ።

ትላንት ወያኔ ኢህአዴግ ፣ከጥበብ በመራቅ የኢትዮጵያን ህዝብ፣በድህነት ማጥ ውሥጥ ከቶ፣ራሱን ግን የሀብት ማማ ላይ አሥቀምጦ ተገዶ መንበሩን ለቋል።

ወያኔ ኢህአዴግ ለ 27   ዓመት ቋንቋን መሠረት አድርጎ እና ብሔር ማለት በግእዝ ሀገር ማለት መሆኑን ክዶ ፣የአማራ ሀገር፤የትግሬ ሀገር፤የኦሮሞ ሀገር፤የሱማሌ ሀገር፤የሲዳማ ሀገር፤የሐረሪ ሀገር፤ የአፋር ሀገር፤  የቤንሻንጉል ሀገር።ወዘተ።እየለ በዛ     ሀገር በተሰኘ  ክልል ውሥጥ የሚኖር ሌላ ቋንቋ ተናጋሪ እንደሁለተኛ ዜጋ እንዲታይ እና እንዲገለለ አድርጎታል ።ዛሬም ይህ ሁኔታ ሥህተት መሆኑ፣ ከመታመኑ የዘለለ ፣ለኢትዮጵያዊው ዜጋ የሚበጅ ለውጥ እውን አልሆነም።እውን ያልሆነበት ዋንኛ ምክንያትም ፣ የማንነት ፖለቲካ ለ27 ዓመት ነግሦ በኖረበት ሀገር  ዜጎች የሚፈልጉትን የሠረዓት ለውጥ ለማምጣት ተከታታይ ውይይት እና ብሔራዊ መግባባት ሥለሚያሥፈልግ ነው።

አንዳንዶቻችን ይህንን እውነት ሣይገነዘቡ፣ ጠቅላይ ሚኒሥትሩ በአንድ ቀን ጀንበር ሁላችንንም የሚያረካ ታላቅ ለውጥ እንዲያመጡ ይወተውታሉ።ይህ ደግሞ ጠቅላይ ሚኒሥተሩን እንደእግዚአብሔር መቁጠር ነው።ጠ/ሚ  ሰው ናቸውና ተአምር ፈጥረው፣ “ሱሪ በአንገት ለማውለቅ“ አይችሉም። የሀገራችን የፖለቲካ ችግር ውሉ እንደጠፋ ልቃቂት የተወሳሰበ ነው።የተተበተበ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ጭፍን ድጋፍና ጭፍን ተቃውሞ የኢትዮጵያና የህዝቧ ዋና ጠላቶች ናቸው!!! - መሰረት ተስፉ

የሀገራችን የፖለቲካ ችግር ለ27 ዓመት የተበተበ በመሆኑ ውሉን ለማግኘት ያሥቸግራል።ውሉን ለማግኘትም በቅንነት ላይ የተመሠረተ  ውይይትና መግባባት  ፖለቲከኞች በጠረጴዛ ዙርያ ማድረግ ይጠበቅባቸዋል።…

ጠ/ሚ አብይ አህመድም ቢሆኑ እንደው እንደዋዛ  ብድግ ብለው በዘፈቀደ የሚወስኑት የፖለቲካ አጀንዳ በቢሮአቸው ጠረጴዛ ላይ አልተቀመጠላቸውም። ብዙዎቹ ፀሐፍት ና ምሁራንም “ሱሪ በአንገት ካልወለቀ …” በማለት በየሚዲያው የሚሰጡት ሥሜታዊ አሥተያየት ና የቢሆናል ሃሳብም፣   አውዳሚ     እንጂ ገንቢ አይሆንም።

ጠቅላይ ሚኒሥቴር አብይ አህመድም ጥያቄዎችን በችኳላ መመለሥ ያሥከተለውን ጣጠና ፈንጣጣ በሲዳማ ክልል መሆን ብቻ በቅጡ  የተገነዘቡት ይመሥለኛል። ይኽ የእኔ እምነት ነው። “የውሳኔው መጣደፍ በደቡብ ያሉት ሌሎች ጎሣዎች በቋንቋዬ ለምን ሀገር አልተሠኘሁም ? ” በማለት የክልልነት ጥያቄ እንዲያነሱ የበለጠ ገፋፍቷቸዋል።ብዬም አሥባለሁ።ጥያቂያቸው ተገቢ ነው።ግን ደግሞ ጥያቂያቸውን በቀላሉ መመለሥ አይቻልም። መንግሥት ህግና ሥርዓትን ሣይከተል በዘፈቀደ የሚተገብረው የለምና ጊዜ ይፈልጋል።ደሞም  ማንነትን መሠረት አድርጎ መከፋፈል “ክልል”ከሚለው ቃል ጋር ከ29 ዓመት በፊት የመጣ መሆኑን አትዘንጉ።ሁሉም ነገር  ከቃል ይጀምራል ። በእእምሮም ሰርፆ ህያው ይሆናል ።…

እውነት ነው። ሁሉ  ነገር ከቃል ይጀምራል” ክልል ” ሲባል፣ የአሥተዳደር ወሰን መሆኑ ቀርቶ እንደ ራሥ ይዞታ ወይም ሉአላዊ ሀገር በመቆጠሩ ፣እያንዳንዱ ጎሣ ቡድን ፈጥሮ ፣ጥቂቶች ተጠቃሚ ሊሆኑ የሚችሉበትን ክልል ዛሬም ካልፈጠርኩ እያለ እየተሞገተ ነው። ይህ ሁሉ ምሥቅልቅል ሁኔታ የተፈጠረውና ሱሪ በአንገት  ይውለቅ የተባለው ፣ከፋሺስት ሞሰሎኒ ወያኔ ኢህአዴግ በኮረጀው፣ የከፋፍለህ ግዛ የቃል ሥያሜ ነው። ሰዎችን፣ “ኦሮሞ አማራ፣ትግሬ፣ወላሞ፣ከንባታ፣ሱማሌ፣ጉራጌ፣ወዘተ።” ናችሁ በማለት የክልሉን ቋንቋ ተናጋሪ የሆኑትን አግዝፎ ና ያልሆኑትን አኮሥሦ በማሣየት እርሥ በእርሳቸው እንዲጣሉና እንዲገዳደሉ በማድረግ፣በሌሎች ሞት ማትረፍን ከፋሽሥት አገዛዝ መኮረጁን ታሪክ ይነግረናል።

ወያኔ ኢህአዴግ ቋንቋን  ያነገሰ ፣በማንነት ላይ የተመሠረተ ሥርዓትን ለሃያሠባት ዓመት ገንብቶ እንደነበር ይታወቃል ።ያ የወያኔ ሥርዓት ዛሬ የለም።  የአብዮታዊ ዴሞክራሲ መሪዎች ዛሬ  በወንበራቸው ላይ የሉም። እጅግ በረቀቀ ሤራ፣የኢትዮጵያ ዋና ፣ዋና ጎሣዎች ኦሮሞና አማራ የተሰኙት ሰዎች፣ ህብረት እንዳይኖራቸው በማድረግ  ጥቂት የወያኔ መሣፍንቶች እና ተባባሪዎቻቸው  በቻ  የኢትዮጵያን ሀብት እንዲዘርፉ በማደረጋቸው ና በሌብነት እና በሰው ደም እጃቸው በመቆሸሹ፣በተነሳባቸው ህዝባዊ ተቃውሞ ሠበብ ፣ከከፋፍለህ ግዛ አገዛዛቸው በትግል ተወግደዋል።

ወያኔ ኢህአዴግ   ከ84 ዓመት በፊት እንደነበረው፣ ወራሪው ኢጣሊያ፣ጨካኝ እና ግፈኛ ከመሆኑም በላይ፣  የኢትዮጵያን ዜጎች በቋንቋና በጎሣ ከፋፍሎ እርስ በእርሥ በማጋጨት የታወቀ ነበር።ጣሊያን የቀደመውን የአድዋ ቂሙን ለመወጣት፣በማጨው ጦርነት ወቅት፣ የመርዝ ጋዝ ተጠቅሞ አሠቃቂ ጭፍጨፋ ከመፈፀሙ በፊት፣ ቀኃሥ እና  በየክፍለ ሀገሩ የነበሩ ገዢዎች  እንዲቃቃሩ አድርጎ ነበር።ይህንንም በማድረጉ ፣ለወራሪው ኢጣሊያን ብዙዎቹ  የተመቹ ሆነው ነበር።… ጦረነቱን ዳር ሆነው  በመመልከት ቀኃሥን የጎዱ መሥሏቸው ሀገራቸውን ለጠላት አሣልፈው ሠጥተዋል።

ወያኔ ኢህአዴግም በዋና፣ዋና የኢትዮጵያ ጎሳዎች መካከል ህብረት እና ፍቅር እንዳይኖር አድርጓል። ከዚህ እውነት የተነሳ ይህንን ለሃያ  ሰባት አመት ጠርንፎ ሲገዛ የነበረን ሥርዓት  በፍጥነት እና በአጭር ጊዜ ውሥጥ በሪፎርም ደረጃ  መለወጥ እጅግ  አሥቸጋሪ ነው።ብቃት እና አቅም ያላቸው  የለውጥ ሐዋርያቶችን መመልመል ና ወደ ለውጥ ሥራ ማሥገባት በራሱ ትልቅ ራሥ ምታት እንደሆነባቸው ከክቡር  ጠ/ሚ  አብይ አህመድ ( ዶ/ር) በላይ የተገነዘበ ያለ አይመሥለኝም።

ይሁን እንጂ በታሪክ አጋጣሚ የተረከቡትን ሥልጣን፣በአግባቡ ለመጠቀም እና በሥልጣን ርክክብ ወቅት ለኢትዮጵያ ህዝብ የገቡትን ቃል ለመፈፀም እጅግ ጥንቃቄ በተሞላው መንገድ ኢትዮጵያ እየተገራገጨችም ቢሆን በለውጥ ጎዳና ላይ እንድትጎዝ ብርቱ ትግል እያደረጉ እንደሆነ ብዙዎቻችን እንገነዘባለን።

ለ27 ዓመት በሥልጣን ላይ የቆየው ኢህአዴግ የተባለ የፖርቲ ሥምን በዘዴ ከሦሥቱ አባል ድርጅቶች በማውለቅ፣ብልፅግና የተሠኘ አዲስ  ፖርቲ ከሌሎች ሥድሥት ክልሎች ጋር ሆነው መመሥረታቸው በራሱ አንድ ትልቅ የለውጥ እርምጃ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  አስተምህሮቶታችንን ለችግሮቻችን መፍቻነት ካልተጠቀምንባቸው በራሳቸው ፋይዳ አይኖራቸውም! - ጠገናው ጎሹ

በበኩሌ፣ “አዲስ አበባ በአንድ ቀን ጀንበር አልተገነባችምና የብልፅግና ፖርቲ  ሱሪውን በአንገት ያውልቅ አልልም።  የብልፅግና ፖርቲ ለቀጣዩ ትውልድና ለሀገር ካሠበ ፣  ከመሪው ከዶ/ር አብይ እኩል ወይም የተሻለ ሁለንተናዊ ብቃት ያላቸውን ዜጎች  ፖርቲውን እንዲቀላቀሉ ማድረግ ይኖርበታል። በማለት ግን ትሁት ምክሬን እለግሳለሁ።ይህንን ቀላል ተግባር መከወን ካቃተው፣ በደመነፍሥ ተመሪ ና አጨብጫቢ የሆኑ አባላትን ብቻ አብዝቶ ሃሳብ አመንጪ ሳይሆኑ፣ ከላይኛው የፖርቲ መዋቅር፣የወረደላቸውን ለህዝብ የሚጠቅም ሥራ እንኳን በቅጡ በማይፈፅሙ፣ግዴለሽ የፖርቲ አባላቱ ሥሙ ይጠለሻል። በሚሠሩት ተደጋጋሚ ጥፋትም  አገልግሎት ፈላጊው ህዝብ ይማረራል።

ሃይ ባይ በሌለው የጥፋት  ዲርጊታቸውም ፣ ነገ  ተጠያቂ ሲሆኑ  “እኔ ምን አቃለሁ ከላይ፣ ትእዛዝ ተሠጥቶኝ ነው የተገበርኩት።” በማለት የፖርቲውን ከፍተኛውን አመራር ያሳጣሉ።  ፖርቲውም ፣ራሱን በራሱ ጠልፎ የሚጥል ፖርቲ ሆኖ ያርፈዋል።

እናም፣ ራሳቸውን እንኳን በሥርአት መምራት በማይችሉ ሠርክ ለግል ጥቅም በሚያሥቡ አባላት ፣ ፖርቲው ከተጥለቀለቀ ፣ ድንገተኛ ሞቱ የማይቀር ይሆናል።

የብልፅግና ፖርቲ ያለጋዜው  በድንገተኛ ሞት እንዳይሰናበት፣ፖርቲው ፣ፖለቲካ ሣይንሥ መሆኑን በተረዱ ዜጎች፣ መበልፀግ ይኖርበታል።በአርቆ አሣቢ ሁለገብ እውቀት በዘለቃቸው ዜጎች መደርጀትና አቅሙን መገንባት ይጠበቅበታል ።

እርግጥ ነው፣የብልፅግና ፖርቲ  ፣ ከጎሣ የፀዳ ሥያሜ እንዳለው ፣ግንባርና ዴድ እንዳልሆነ እናውቃለን።   ፣የዘጠኙን ክልሎች ይሁንታ ያገኘው ይህ ፖርቲ ግን፣ቋንቋን ሳይመርጥ በሁሉም ክልሎች የዜጎችን አባልነት የሚያረጋግጥበትን መንገድ አለመቻቸም።  ይህንን  ማድረግ ጊዜና ተደጋጋሚ ውይይቶችን ማድረግ እንደሚጠይቅ እገነዘባለሁ።

ወደዘመናዊው እና ፣ወደሣይንሣዊው  የፌደራል ሥርአት ክልሎችን ለማምጣትም ለሃያሰባት ዓመት የተበተበውን ፣የጥላቻ ፣ የጠልፎ መጣል ና የከፋፍለህ ግዛ “መተት” ውሉን ፈልጎ መፍታትና ፣የሐሰት ትርክቶችን በሣይንሣዊ እውነት መተካት ቅድሚያ የሚሰጠው የቤት ሥራ ይሆናል ብዬ አሥባለሁ።እናም ለዚህ ነው፣  ለውጡ፣ሣይንሥን የተከተለ ፣በድርጊት የተሞላ፣ እውነተኛውን ሣይንሣዊ ፖለታካ የተከተለ መሆን እንዳለበት አፅኖት ሠጥቼ ለማሳሰብ የፈለኩት።

ብልፅግና መከተል ያለበት፣ሥይንሣዊ እውነት የሆነውን፣ ሣይንሣዊ ፖለቲካ ነው። ሣይንሣዊው ፖለቲካ ሰው ሰው እንጂ ቋንቋ ነው ብሎ አያምንም።ሳይንሳዊ ፖለቲካ ና አሥተሣሠብ “ሁሉም ሰው ከአንድ በላይ ቋንቋ ለማወቅ በተለያየ የኢትዮጵያ ቋንቋ ተናጋሪዎች ውሥጥ ለአንድ ዓመት ብቻ የነሱን ቋንቋ በመሥማት መኖር ይበቃዋል። “ ብሎ ያምናል።

አንድ ሰው፣ ለአሥር ዓመት በተለያዩ ቋንቋ ተናገሪዎች ዘንድ፣ በየዓመቱ እየተዘዋወረ ቢኖር አሥር ቋንቋ ሊያውቅ ይችላል።እነዚህን አሥር ቋንቋዎች በማወቁ በአሥሩም ሥም ሰውነቱ ተሰርዞ አይጠራም።ከሰውነቱ ከፍም ዝቅም አይልም።ዓለም  ላይ ያለ ሰው ሁሉ ሲወለድ  “ህፃን ልጅ ” በሚባል የወል ሥም ይጠራል ።ሲሞት ደግሞ   “ሬሣ ወይም አሥከሬን” ነው የሚባለው። ይህ ሣይንሣዊ እውነት ብቻ ሣይሆን የተፈጥሮ እውነትም ነው።

ሆኖም ይህ የተፈጥሮ እውነት በእኛ ሀገር ተዘንግቶ ፣ከጥሬው እውነት ባፈነገጠ፣የግል ጥቅም ላይ ባተኮረ ፣ በተጣመመ መንገድ ፖለቲካችን ለ27 ዓመት በተወሰኑ የመግባቢያ ቋንቋ ተመርቷል።ዛሬም አንዳንድ ሆድ አደር ምሁራን እና ቆሞ ቀር የፖለቲካ ኢሌቶች የራሥ ወዳድነት በሽታ ሥር ሰዶባቸው ፣ለያዙት ሥልጣን እና ላሥገኘላቸው ጥቅም  ብቻ ሲሉ፣ ቋንቋን ሙጭጭ አድርገው በመያዝ ፣ ቋንቋን የሥልጣን ማሥጠበቅያ መሣሪያ አድርገዋል።ይህንንም መንገድ   ሙጥኝ በማለታቸው የ21ኛው ክ/ዘ ሥልጡን ፖለቲካ ፣የተማረ እና የተደባለቀ ህዝብ በሚኖርበት በሁሉም የኢትዮጵያ ከተሞች ውሥጥ፣በአማርኛ ቋንቋ እየተግባባ በዜግነቱ ኮርቶ ፣  በነፃነት እንዳይኖር በአውዳሚ እና በአሸባሪ የሴራ ፖለቲካቸው እያወኩት ነው።

ዛሬም ከተሞች ሠላም የላቸውም።በከተማ የሚኖሩ ዜጎች ሁሉ በባለሥልጣናቶች እኩል አይታዩም።እኩል አገልግሎት አይሰጣቸውም።ከተሞቻቸውንም እንዲያሥተዳድሩ  የሚደረጉት ፣የከተማው ኗሪ ያልሆኑ ከሌላ ከተማ የመጡ ዜጎች ናቸው። ይህ የሹመት አሠራር፣በቀደመው ኢህአዴግ ነበረ። ዛሬም ቀጥሏል።

ይህንን ከለውጡ መንግሥት ከተሜው አልጠበቀም። በተጨባጭ  በለውጡ አሥገዳጅነት ያልተቀባባ እኩልነት፣ፍትህና ዴሞክራሲ ከተሜው አገኛለሁ  ብሎ በመጠበቁ፣ መሞኘቱን ለማመን እየተገደደ ነው።ከተሜው እኮ የበዙ የገዘፉ ጭንቅላቶች ባለቤት ነው።ይህንን መዘንጋት ዘጠና ሰባትን መናፈቅ ነውና ብልፅግና ለዚች ሀገር ቀጣይነት ላለው የብልፅግና ጉዞ ሲል ከወዲሁ ቆም ብሎ ቢያሥብ መልካም ነው።እንደ ቀድሞው ወያኔ ኢህአዲግ በድራማዊ መንገድና በካድሬ ሆይሆይታ ሀገርን በሠላም መምራትና ህዝቦቿን ማሥተዳደር  እንደማይቻል አሻጋሪው መንግሥት ከማንም በላይ አሣምሮ ያውቀዋል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ድምፅ አሰጣጣችን በምን ሰሌት ቢሆን ያዋጣል? - ዳዊት ዳባ

ደግሞም ህዝብ ትውልድ የሚፈራረቅበት ወንዝ እንደሆነ መረዳት አሻጋሪው መንግሥትን  ከላይ ከተጠቀሰው አጓጉል ተግባር እንዲታቀብ የሚረዳው ይመሥለኛል ። ያለማቋረጥ በሚወርደው  የትውልድ ወንዝ ውሥጥ ድንገት የሚከሰቱ  “ማርክ አንቶኒ ና ብሩተሥን ” የመሠሉ ሰዎችም እንደሚኖሩ ማሠብም ፣ድፍረት ከተሞላበት ሥህተት  እንደሚያድነው አምናለሁ። ህልማችን ከተሰማ ማለቴ ነው።(የጁሊየሥ ቄሳርን ፊልም ይመለከቷል።)

ለማንኛውም “ጨው ለራሥህ ሥትል ጣፍጥ።” ነው የምለው።”በበኩሌ  ያለኝን ቅን  ሃሳብ ከመወርወር ባሻገር ሀገሬን የምረዳበት ሌላ የተሻለ መንገድ የለኝም።

እናም፣  ከ2013/14 ዓ/ም ምርጫ በኋላ ፣ አዲስ አበባም ሆነ ሌሎች ከተሞች በራሳቸው ምክር ቤት አባላት የተወከለ ከንቲባ እንደሚኖራቸው ተሥፋ አደርጋለሁ ።

ከተሞች  በ2013/14 ዓ/ም የሚካሄደው ሀገራዊው ምርጫ፣በሴራ ያልተሞላ፣የይሥሙላ ያልሆነ፣ከማጭበርበር እና ከኮሮጆ ግልበጣ የፀዳ ሆኖ፣ ለ21ኛውን ክ/ዘ የሚመጥን ዴሞክራሲያዊ ምርጫ በማካሄድ  ከተማቸውን የማሥተዳደር ነፃነት ይጎናፀፋሉ ብዬ አሥባለሁ።ካለሆነሥ? “አዲዮስ ዴሞክራሲ !” ከማለት በሥተቀር  ምን እላለሁ ?

ለማንኛውም ድልድዩን የምንሻገረው ሥንደርሥበት ነውና፣   በኢትዮጵያ ጠ/ሚ አብይ አህመድ (ዶ/ር) የሚመራው ለውጥ፣ለእውነተኛ ለውጥ መቆሙን  ማረጋገጥ የምንችለው፣በ2013 /14 ዓ/ም ፣ የምርጫ ሂደትና ምርጫው ፣ነፃ ፣ግልፅ፣ተአማኒ ፣ዴሞክራሲያዊ ና ሁሉም ዜጋ የተሳተፈበት መሆኑን ሥናረጋግጥ  ብቻ ነው።

የሚሻገሩበትን የፍትህና የዴሞክራሲ   ድልድይ ከሩቅ እያዩ፣ ዛሬ ላይ ሆነው፣በውጪና በውሥጥ ባሉ በኢትዮጵያ ጠላቶች ፣በህቡና በግልፅ እየተከናወነ ያለውን ሀገር አፍራሽ ሤራ ለማክሸፍ ያላሠለሰ ትግል የሚያደርጉ ፣አያሌ ሀገር ወዳድ ዜጎች፣በውሥጥ እና በውጪ ሀገር  አሉ። ይህቺን የጀግኖች ሀገር  ጠልፎ በመጣል ከብልፅግና ጉዞዋ ለማደናቀፍ የሚጥሩትን በመመልከት ሥጋታቸውን ደጋግመው በመገናኛ ብዙሃን ሲገልፁም ይሰማሉ።መጪው ሀገር አቀፉ ምርጫ፣እንከን በእንከን እንዳይሆን የሚሠጉ  ፣ የሥጋታቸውንም ምክንያት፣  በየአጋጣሚው የሚናገሩ ፣የሀገር ፀጥታ ና የህዝቦቿ ሠላም የሚያሥጨንቃቸው ቅን ኢትዮጵያዊያንም በእውነቱ ጥቂት አይደሉም።

ከነዚህ በተፃራሪ ደግሞ ትሁት ምክር ከመሥጠት በተቃራኒው፣ዘለው፣ጠብ የለሽ በዳቦ እያሉ፣ ሰው ራሥ ላይ ፊጥ የሚሉ ደፋሮች አሉ።እነዚህ የሣይንሣዊ ፖለቲካ ትርጉሙ ያልገባቸው ፣ ትህትና እና ቅንነት ያልፈጠረባቸው፣ ተምረው እንዳልተማረ ፣ እንደ ተራ ና ጀብራራ ሰው፣  በግልፅ ና በአሽሙር   መሪዎችን የሚዘልፉ ለመብላት ሲሉ ብቻ የሚኖሩ፣ ፖለቲከኞች እንደሆኑ የህይወት ታሪካቸው ይመሠክራል። እነዚህኞቹ አንድም  የፖለቲካ ትርጉም ያልገባቸው ሲሆኑ፣በሌላ በኩል ደግሞ፣ እየገባቸው ለእንጀራ ብለው  ከኢትዮጵያ ጠላቶች ጎን የተሰለፉ ናቸው።

በነገራችን ላይ፣ ፖለቲካ ማለት ምንድነው?የፖለቲካ ፓርቲሥ?

ፓለቲካ፣ፖሊቲ ከሚለው የግሪክ ቃል የመጣ ሲሆን፣ጥንታዊ የግሪክ መንግሥታዊ ተቋማት መጠሪያ ሆኖ ያገለግል ነበር።

ፖለቲካ የህብረተሠብ አደረጃጀትን፣የመንግሥት ይዘትን፣ዓይነትን፣ቅርፅንና ተግባርን፤የተለያዩ የህብረተሠብ ክፍሎች፣ጥቅማቸውን ለማሥጠበቅ፣የሚያደርጉት የእለት እለት እንቅሥቃሴ እና ሠላማዊ የመብት ትግል፣እንዲሁም በመንግሥታት መካከል፣የሚፈጠሩትን ግንኙነቶች ፣ማለትም የውጪ ግንኙነት ፖሊሲን ጨምሮ፣የሚኖራቸውን ኢኮኒያሚያዊና ማህበራዊ ትሥሥር በምን ዓይነት መንገድ እንደሆነ የሚወሥን ነው።ፓለቲካ በይበልጥ የታወቀው መንግሥት የተባለው ተቆም ከተፈጠረ በኋላ ነው።

የፖለታካ ፖርቲ ማለት፣ ተመሣሣይ ሃሳብ፣አመለካከት፣አሥተሣሡብ እምነትና ዓላማ፣ባለቸው ሰዎች የሚቋቋምና የራሱ መተዳደሪያ ደንብ ና ፕሮግራም ያለው ተቋም ነው።

ከእነዚህ ትርጉሞች ተነሥተን በኢትዮጵያ ያሉትን ፖርቲዎች ብንመለከት፣ ከፓለቲካ ትርጉም አንፃር፣የፖርቲነት ሥም የማይሰጣቸው የበዙ እንደሆኑ እናሥተውላለን።በደምሳሳው የበዙት ፖርቲዎች ቋንቋን ተገን በማድረግ በማንነት ፖለቲካ ላይ ተመሥርተው ፕሮግራማቸውን በመንደፋቸው፣ ዜጎች ሱሪያቸውን በአንገታቸው እንዲያወልቁ የሚያሥገድዱ  ሆነው ተገኝተዋል ።

በከተማ ውሥጥ ሥትኖር አንተና ና ጎረቤቶችህ የምትግባቡትን ቋንቋ የሚወሥኑልህ እነዚህ የማንንነት ፖለቲካ አራማጆች ናቸው።እነዚህ በቋንቋ እና በማንነት ላይ ተመሥርተው፣ የፖለቲካ ሥልጣንን ለመጨበጥ እና መንግሥት ለመሆን የሚታገሉ ፖለቲከኞች ፣ በእሥታሊን እና በሞሶሎኒ ድብልቅ የአገዛዝ አሥተሳሰብ የተካኑ በመሆናቸውም “ለውጡ” እንደታሰበው ወደፊት እንዳይጓዝ በተለመደው ገመድ ጉተታ ወጥረው ይዘውታል።

 

መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ

1 Comment

  1. Unfortunately your article tripped on itself when you put Abiy and the party you have high regard for as the answer to your theory. The truth and the bare fact that most are finding out is Abiy and the party in question is a continuation of Ehadeg. Abiy has never even tried to bring in new people but is just shuffling the old deck. See prosperity does not come without peace. Abiys commitment to the current constitution if one calls it that and his public declaration aganst those who wish to change it the only cause to prosperity not coming to Ethiopia and Ethiopians. He is not and will never be the person to bring peace leave alone prosperity.

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share