ልውጥ ሕያዋን በኢትዮጵያ (GMO) የሚያስከትለውን ስጋት ለመቀነስ – ሰርፀ ደስታ

ሰሞኑን ከወደ ኢትዮጵያ ስለ ልውጥ ሕያዋን (ጂኤምኦ) የሚወሩ ወሬዎች በማህበረ ድረገጾች በዝቶ ተመለከትሁ፡፡ ሆኖም አብዛኞቹ የወሬው አራጋቢዎች ስለጉዳዩ በትክክል የሚገነዘቡ ስላልሆነ የሚያሰራጩትም ወሬ መነሻው እንዴት እንደሆነ በትክክል አልተረዳሁትም፡፡ የሆነ ቦታ የጥጥ ልውጥ ዝርያ ገባ ይሁን ሊገባ አይነት ወሬ አየሁ፡፡ ከማቃቸው ባለሙያ (የዚህ ሳይሆን የሌላ) ከሆኑ ሰዎች ሳይቀር እንደው በወኔ ስለ ልውጥ ሕያዋን ከፍተኛ የሆነ እሳት ለበስ ትንተና ሲሰጡ አየሁ፡፡ እስኪ እኔው እሻል እንደሆነ ብዬ ነው ይችን ጽሑፍ ለግንዛቤ ያህል ለማቅረብ የተገደድኩት፡፡ በመጀመሪያ በአላወቅንውና በአልተረዳንወ ጉዳይ በተለይ ባለሙያ የሆን ሰዎች ባንናገር ጥሩ ነው፡፡ የፌስቡክና ዩቲዩብ አክቲቪስት ቢናገር አለመገንዘብ ነው ተብሎ ይታለፋል፡፡ ከስማችሁ ፊትና ኋላ ዶ/ር ምናምን የሚል ማረጋገጫ ማህተብ እያደረጋችሁ ከአክትቪስትም ባነሰ ለሕዝብ ግር የሚያሰኝ ነገር ባትናገሩ እላለሁ፡፡ ዘመኑ እኮ የተመቸ ነው ማንበብም መጠየቅም ይቻላል፡፡ በዚሁ ወደጉዳዬ

ልውጥ ሕያዋን ማለት በአጠቃላይ በሰው ሰራሽ ዘዴ መለዘሩ (ጄኔቲክ ሜካፕ ዲኤን ኤ ከምለው) የተለወጠ ማለት ነው፡፡ ለሳይንሳዊ ጥናት ከሚሰራባቸው የልውጥ ሕያዋን ባሻገር አሁን አሁን ምርትን ለማሳደግ በሰብሎችና በእንስሳቶችም ብዙ ልውጥ ዘሮች አምራቹ ዘንድ አሉ፡፡ ስለ እንሰሳው ብዙ አላውቅም፡፡ ይኖራል የሚል ግምት አለኝ፡፡ በሰብሎች ግን የሚከተሉት በከፍተኛ ደረጃ በአምራቹ እየተመረቱ ለገበያ ከዋሉ ሰንበትበት ብለዋል፡፡ እስካሁን ድረስ ለሦስት ምክነያቶች የልውጥ ዝርያዎች በስፋት በምርት ላይ ይገኛሉ፡፡

  1. ጸረ-ዓረም የሚቋቋሙ ተደርገው የተለወጡ፡- እነዚህ ዝርያዎች ከሌሎች በተለየ ራውንድ አፕ የተባለን ሁሉንም ሁሉንም በመሬቱ ላይ የሚገኝን ዕፅዋት (አረሙንም ሰብሉንም) የሚገድል ጸረ-አረም የሚቋቋሙ ሆነው ዘረ-መላቸው የተቀየረ ሲሆን፡፡ በሰብል ወቅት ከተፈለገው ሰብል ውጭ ሌላ በመሬቱ ላይ እንዳይኖር በማድረግ ሁሉንም አረሞች የተቀላቀለና ያልተለወጠ ሰብልም ቢሆን ሙሉ በሙሉ ለማጥፋት የጸረ-አረሙ ይረጫል፡፡ በዚህ መልክ መሬቱ ሙሉ በሙሉ ጸረ-አረሙን በሚቋቋማና የተፈለገው ሰብል (ልውጥ ዝርያ) ብቻ ይሸፈናል በዚህ ሁኔታ ከአረም ነጻ የሆነ ሰብል፣ በአነስተኛ ወጭ ከፍተኛ ምርት ማምረት ይቻላል፡፡ የምርት ከፍተኛነቱ ግን አረሙ ስለጠፋ እንጂ ልውጥ በመሆኑ አደለም፡፡ የምርቱ መጠን በተፈጥሮ በሚሆን ማዳቀል ነው፡፡ ምርት ለመጨመር የተሰራ ልውጥ ሕያው አላውቅም፡፡ ለመስራትም አስቸጋሪ ይመስለኛል፡፡ ምርት በብዙ ወሳኝ ዘረመሎች (ጂንስ) ስለሚወሰን፡፡
  2. በሽታን የሚቋቋም ተደርገው የሚለወጡ ፡- ከላይ እንደጠቀስኩት ከምርትና አንዳንድ ምርት ጋር የተያያዙ የእጽዋት ባሕሪዎች በተለየ ብዙ በሽታን ለመቋቋሚ የሚረዱ ወሳኝ ዘረመሎች (ጂኖች) አንድ ወይም በጣም ጥቂት ስለሚሆኑ አንዱን ጂን በመቀየር ወይም ሰብሉ ከሌለው በሽታውን ለመቋቋም የሚያስችል ጂን ከሌላ ሕያው ነገር ወደ ሰብሉ በማስገባት በሽታ የሚቋም ልውጥ ዝርያን ማግኘት ይቻላል፡፡ ለዛም ነው በሽታን የሚቋቋሙት ላይ የሚሰራው፡፡ ሆኖም ብሽታ ሁሉ በአንድ ጂን ብቻ ላይወሰን ይችላል፡፡ እንደነዚህ ያሉትን በሽታዎች የሚቋቋም ልውጥ ዝርያ ማግኘት ከባድ ነው፡፡ ቢቻል እንኳን አዋጭ ላይሆን ይችላል፡፡ በሽታን የሚቋቋም በስፋት እየተመረተ ያለ ሰብል እስካሁን እርግጠኛ አደለሁም፡፡ ግን ከላይ በጠቀስኩት መልኩ ይቻላል፡፡
  3. ተባይን የሚቋቋሙ፡- እንደ በሸታው ሁሉ ተባይንም ለመከላከል የተወሰኑ ወሳኝ ዘረመሎች (ጂኖች) ብቻ ስለሆኑ አንዱን በመቀየር ወይም ሰብሎ ከሌለው ከሌላ ሕያው ነገር ወደ ሰብሉ በማስገባት ተባይን እንዲቋቋም ማድረግ ነው
ተጨማሪ ያንብቡ:  የመለስ ልጆች ድርድር እና “የትጥቅ ይፍቱ” ማጭበርበሪያ (ከአሁንገና ዓለማየሁ)

ሌሎች ለሌላ ተግባር የሚሰሩ ልውጥ ዝርያዎች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ከላይ የጠቀስኳቸው ግን ዋና ዋናዎች ናቸው የሚል እምነት አለኝ፡፡

በአሁኑ ወቅት በስፋት በልውጥ ዝርያዎች የሚመረቱ ሰብሎች

  1. አኩሪ አተር (ሶያቢን)፡- የመጀመሪያው ልውጥ ዝርያ በ1996 በፈረንጆች ለገበያ ሞንሳንቶ በሚባል የዘር ድርጅት የቀረበ እስከ ፈረንጆቹ 2014 ድረስ ብቻ 82 በመቶ የሚሆነው የአለም የአኩሪ አተር ምርት ከልውጥ ዝርያ የተገኘ ነው፡፡ ከዛ በኋላ ያለውን መረጃ አላገኘሁትም፡፡ ይመስለኛ ይጨምራል፡፡ እንደ አሜሪካ ያሉ አገራት ወደ 95 በመቶ በላይ የሶያ ምርታቸው ልውጥ ነው፡፡ እንግዲህ ስለ ልውጥ ዝርያዎች በከፍተኛ ወኔ እየታገላችሁ ያላችሁ ይሄ ሆኖ እያለ ኢትዮጵያ ውስጥ የሚመረተው አኩሪ አተር ልውጥ ዝርያ አደለም ብላችሁ ከማናችሁ ዋናው ማመናችን እንጂ መለወጡ አደለም እንዳይሆን ትግላችሁ፡፡ አብዛኞቹ የአኩሪ አተር ዘሮች ከውጭ መጥተው እየተመረቱ በመሆኑ ደግሞ ይበልጥ እውነታውን እንድንቀበል እንገደዳለን፡፡ የአኩሪ አተር ልውጥ ዝርያ እስካሁን ጸረ-ዓረምን ለመቋቋም ነው፡፡ ኢትዮጵያ ውስጥ እየተመረተ ያለው ልውጥ መሆን አለመሆኑን ለማወቅ የመለዘር ጥናት አያስፈልገውም በትንሽ መሬት ላይ አኩሪ አተር በመዝራት ራውንድ አፕ (ጅምላ ጨራሽ) ጸረ-አረም መጠቀም ነው፡፡ አኩሪ አተሩ ካልሞተ ማን እንደሆነ ይናገራል፡፡ እርግጥ ነው በመዳቀል እንደቀና የመቋቋም ኃይሉ ሊቀንስ ይችላል፡፡ ሆኖም ቢያንስ የተወሰኑ ተክሎች ተቋቁመው ማየት ይቻላል፡፡ ራውንደ አፕን በተፈጥሮ የሚቋቋም አኩሪ አተር የለም፡፡
  2. ካኖላ (ጎንመንዘር)፡- እንዲሁ ከ90በመቶ በላይ በምድረ አሜሪካ የሚመረተው ጎመንዘር የጸረ-አረም (ጅምላ ጨራሹን) እንዲቋቋም የሆነ ዘር ነው የሚመረተው
  3. በቆሎና ጥጥ፡- እነዚህ በስፋት ለጸረ-ኣረም ሳይሆን ለጸረ-ጸባይ የተለወጡ ዝርያዎች ናቸው ያሏቸው፡፡ ሁለቱም የሚቋቋመው ጂን ባሲለስ ቱሪነጊነሲሰ (Bacillus thuringiensis) ከተባለ ባክቴሪያ በተወሰደ ጂን በመጨመር የተሰሩ ናቸው፡፡ በአጠቃላይ ቢቲ ዝርያዎች ይባላሉ፡፡ በአሁኑ ወቅት በአሜሪካ ጥጥም ሆነ በቆሎ 90ና ከዛ በላይ የሆነው ምርት ከልውጥ ዝርያ የሚመረት ነው፡፡ እንደተረዳሁት ወደ ኢትዮጵያም ይግባ የተባለው ይሄው የቢቲ ልውጥ የጥጥ ዝርያ ነው፡፡ በአሁኑ ወቅት በተጨማሪ የጸረ-አረሙንም የሚቋቋሙ ቢቲዎች እየተስፋፉ ነው፡፡
  4. ሌሎች እንደ ፓፓያ፣ ድንች፣ ስኳር ድንች በርካታ ሌሎች እንዲሁ በልውጥ ዝርያ እየተቀየሩ ነው፡፡

እነዚህን የልውጥ ዝርያ ለመጠቀምም ይሁን መዛመታቸውን ለመቀቋቋም ምን ያስፈልጋል

ዝም ብለን ባልተረዳንው ነገር ብዙ ብንል ዋጋ የለውም፡፡ ልውጥ ዝርያዎቹ ከቤታችን ገብተው በአገሬ አይገቡም የሚል ፉከራ አይሰራም፡፡ ባለሙያዎች ደግሞ እባካችሁ የአክቲቪስትነት ነገር ይቅርባችሁ፡፡ እንደ እውነት ይሄን ጉዳይ አክቲቪስቶቹ አልደፈሩትም፡፡ ሆኖም ትንሽ አወቅን ያሉት ናቸው እጅግ የተሳሳተ መረጃ እያሰራጩ ያሉት፡፡ ስለሆነም እኔ በአለኝ አቅም የሚከተሉትን እላለሁ፡፡

  1. ብቃት ያለው የምርምር ተቋም፡- አንድን ነገር ጎጅነቱንም ሆነ ጠቃሚነቱን ለመረዳት በአግባቡም እንደሆኔታው ለመጠቀም ስለ ነገሩ በቂ የሆነ መረጃ ሊኖረን ይገባል፡፡ ለዚህ ደግሞ ጥርት ያለ መረጃ ሊያመነጭ የሚችል የላቦራቶሪ ፋሲሊቲና እውቀት ሊኖር ይገባል፡፡ ዛሬ ችግሩ እንዳይመጣብን የምንፎክረው ምን ያህል አገራችን ውስጥ ገብቶ እንደሚገኝ ለማወቅ የሚያስችል አንዳች የተዘጋጀ ሥራ በሌለበት ነው፡፡ ይሄ ጥፋት ነው፡፡
  2. ሕጋዊ አካሂድ፡-ኢትዮጵያ በሕግ የልውጥ ሕያዋንን ማገድ ትችላለች ግን ለማገድም ምርምሩን ማካሄድና ምን እየሆነ እንደሆነ መረዳት የሚያስችላትን ዝግጅት ማድረግ ይጠበቅባታል፡፡ ከዚህ በፊት የልውጥ ሕያዋንን ለመከላከል በሚል ልውጥ ሕያው ይዞ የተገኘ ማንኛውም ግለሰብ ብዙ ዓመት እንደሚታሰር የሚደነግግ አዋጅ እንዲሁ አክቲቪስት በሚመስሉ ባለሙያዎች ተቀርጾ እንደነበር አስታውሳለሁ፡፡ አስተውሉ ልውጥ ይሁን ደህና ግን በምን መልኩ እንደሚለይ አንዳች ማወቂያ መንግድ የለም፡፡ ይሄ እገዳ ምርምሩንም ጨምሮ ነው፡፡ እንግዲህ ስለሆኔታው ካልተመራምርን፣ ካላወቅንው፣ የምናውቅበትን መሳሪያና እውቀት ካላዘጋጀን እንዴት እንደምንቆጣጠረው አይገባኝም፡፡ለምሳሌ በአውሮፓ ልውጥ ዘረመል ክልክል ነው፡፡ በአንድ ወቅት በኒዘርላንደ የጎበኘሁት የልውጥ ዘረመል ምርምር ተቋም ትዝ አለኝ፡፡ በጋጣሚ ከብዙ ሰዎች እንድንገባና እንድናይ የተፈቀደልን ሶስት ሰዎች ብቻ ነበርን፡፡ ገብተን ያየንው ለማመን የሚከብድ ነው፡፡ በሳይክል እንጂ በእግር ተጉዞ የማይዘለቁ በጣም ትልልቅ ተነሎች (ፐላስቲክ ሀውስስ) በልውጥ ዝርያዎች ተሞልተዋል፡፡ አገሪቱ በማትፈቅድበት ሁኔታ ይሄን ሁሉ እዚህ በምርምር ለውጡ ማኖር ለምን አስፈለጋችሁ ላልናቸው ጥያቄ ወደፊት መለወጡ እንደማይቀር እናውቀዋለን፡፡ ተዘጋጅተን መጠበቅ ይኖርብናል ነበር ያሉን፡፡ ጊዜው 10 ዓምት ነው፡፡ እስካሁን እንዴት እንደሆነ አላወቅም፡፡ የአውሮፓ ሕግ የተቀየረ አልመሰለኝም፡፡ ለአገሬ እመክራለሁ ስለጉዳዩ በትክክል የሚረዱ ባለሙያዎችን ባማከረ ሁኔታ ሕጎች ቢወጡ፡፡ ዝግጅቶችም ቢደረጉ፡፡
  3. በሚያስፈልግ ሁኔታም መጠቀም ቢቻል፡- አሁን የተባለውን የቢቲ ጥጥ ከዓመታት በፊት ታስቦ እንደነበርና እንደውም ገብቶ እንደነበር ነው የማውቀው፡፡ ሰሞኑን አንዳንዶች በአብይ ዘምን እንደሆነ አድርገው ሊከሱ ሞክረዋል፡፡ ከጸሀፊዎቹ አንዱ መዳይኔ ታደሰ ነው፡፡ በጽሁፉ እንደተረዳሁት በወያኔ ጊዜ እንዲህ ያለ ነገር ጥብቅ ቁጥጥር ሲደረግበት እንደቆየና ዛሬ ግን በግድ የለሽነት ልውጥ ዝርያ ወደ አገር እንደገባ ለማሳየት ሞክሯል፡፡ ይሄ መረጃው ከሌለው ቢያጣራ ጥሩ ነው፡፡ ሆን ብሎ ከሆነ ደግሞ እውነታው ከዚህ በፊት ተሞክሮ ነበር፡፡ እንግዲህ የገባው ቢቲ ጥጥ አልተሳካ እንደሆነ አላውቅም፡፡ የሆነ ሆኖ በትክክልና በአግባቡ አውቀንው ከሆነ መጠቀሙ ስህተት አደለም፡፡ ጥጥ የተመረጠበትም ምክነያት ለመብልነት አይውልም ብሚል ነው፡፡ ሆኖም የጥጥ ዘይት ኢትዮጵያ ውስጥ ለምግብነት እንደሚውል አውቃለሁ፡፡ እንዲህ ያሉ ነገሮችን ሲጠቀሙ ሊያመጣ የሚችለውን ጉዳት በመረዳት እንዲሆን ጭምር የሚያስችለው ከላይ የጠቀስኩት የተጠናከረ ምርምር ነው፡፡
  4. ልውጥ ዘረመል ዝርያዎችን ከሌሎች አስተማማኝ በሆነ መልኩ በማራራቅ መትከል፡- ምን ዓልባት ልውጥ የተባለው ዝርያ የአገር በቀሎቹን ወይም ነባሮቹን እንዳይበክል በተቻለ መጠን ለብቻው ተከልሎ እንዲበቀል ቢደረግ፡፡ በተለይ ከልውጥ ዝርያው ጋር ሊዳቀሉ የሚችሉ ሰብሎችን ማራቅ፡፡ ለምሳሌ ካኖላና የእኛው ጎመንዘር ሊዳቀሉ ይችላሉ፡፡ ልውጥ ዘረመሉ በተለይ በአበባ ወንዴ ዱቄት (ፖለን) ይተላለፋልና፡፡ አስቸጋሪ የሚያደርገው ግን ፖለን በንፋስ ብዙ ርቀት ሊሄድ መቻሉ ነው፡፡
ተጨማሪ ያንብቡ:  የዛሬ ወሬዎችና መጪው ጊዜ - መሳይ መኮነን

ከዚህ በተረፈ በአላስፈላጊ መረጃ ከመባዘን የሚያድን የመረጃ ለውውጥ አውድ ቢዘረጋም መልካም ነው፡፡ ዘመኑ ማንም የመሰለውን የሚያወራበት ስለሆነ የተረጋገጠ መረጃ አቀባይ አውድ ያስፈልጋል፡፡ ድረ-ገጽ ሊሆን ይችላል፡፡ የተጠናከረ የምርምር ተቋም ካለ ተቋሙ ለግንዛቤ ሊሆኑ የሚችሉና በቀላሉ ሕዝብ የሚረዳቸውን የምርምር ውጤቶቹን ለሕዝብ ይፋ የሚያደርግበትን ቋት ሊያዘጋጅ ይችላል፡፡

ስጋቶች

  1. የዘረመል መበከል፡- እንግዲህ ከላይ እንደጠቀስኩት በተለይ የባዕድ ጂን የገባላቸው እንደ ቢቲ አይነት ዝርያዎች በወንዴው ዘር (ፖለን) አማካኝነት ወደሌላ ነበር ዝርያ ሊተላለፍ ይችላል፡፡ በተለይ ተመሳሳይ ሰብል ከሆነ፡፡ በእርግጥ ወደሌላም ሰብል ሊተላለፍ ይችላል፡፡ እንግዲህ እንዲሀ ያለ በተለይ እንደ ቢቲ ያሉ ተባይን ወይም በሽታን የሚቋቋሙ በአካባቢው ገበሬው ባይተክላቸው እንኳን በመቋቋም ከተራው ስለሚበልቱ እየቆዩ ነበሮቹን ይወርሷቸዋል፡፡ ይሄ አንዱ ስጋት ነው፡፡ ይሄ አይነቱ የበላይነት ጸረ-አረም በሚቋቋሙት ላይሆን ይችላል፡፡ ምክነያቱም ጸረ-አረሙ ካልተረጨ ምን አልባትም ከአካባቢው ባነሰ አረም የመቋቋም አቅማቸው ደካማ ስለሚሆን፡፡
  2. ሆን ተብሎ ነባር ዝርያዎችን በልውጥ መተካት፡- እንግዲህ ልውጥ ዝርያዎቹ የተሻሉ ሆነው ከተገኙና ላአሰራር ምቹ ከሆኑ እየቆዩ በገበሬው እየተወደዱና ነባሩቹን እየተኩ ከሄዱ ነባሮቹን ሊያጠፉ ይችላሉ፡፡ ይሄ በተፈጥሮ እየተዳቀለ ለገበሬ በምርጥ ዘርነት ከሚሰጠው የተለየ አይደለም፡፡ ምርጥ ዘር ብዙ ምርት በመስጠት ቢጠቅምም ነባሮቹን ገፍቶ በማስወጣት ወደፊት ከነባሮቹ ጥሩ የሆነ ባህሪን ሁሉ ሊያሳጣ ይችላል፡፡ ይሄ አሁንም እየሆነ ያለ ነው፡፡ እንደ ሌሎቹ አገር ሁሉንም ነባር ዝርያዎቹን በመለዘር ባንክ (ጂን ባንክ) ማቆየት ባህል አለ፡፡ ኢትዮጵያም ይሄው ተቋም አላት፡፡ እንደውም ጠንካራ የሚባል ነበር፡፡ ሆኖም ከጊዜ ወደጊዜ ትኩረት እያጣ ያለ ይመስለኛል፡፡ ከዚህ በተረፈ መንግስት እንዳንድ ወሳኝ ቦታዎችን ከምርጥ ዘርም ሆነ ከልውጥ ዘር መከልከል ሊኖርበት ይገባል፡፡ ለምሳሌ በትግራይ አንዳንድ ቦታዎች ሊሆን ይችላል ምርጥ ዘር ክልክል ነው ሲባል ሰምቻለሁ፡፡ ከሆነ ጥሩ ነው፡፡ ትግራይ የአማራ ወሎና ከፊል ሸዋና ጎንደር በብዛሀ ሕይወት ክምችት ከሚታወቁ ቦታዎች ናቸው፡፡ ወደ ደቡብ አሪ፣ ኮንሶ፣ ደራሼና አማሮም በዚህ ከሚጠቀሱት ናቸው፡፡ የዚህ ምክነያቱ በዋናነት የመሬቶቹ ከመጠን በላይ ወጣገባ መሆንና ከቆላ እስከ ደጋ የሚሆን አየር ንብረት ስላላቸው ነው፡፡ እነዚህ ቦታዎች ለሰፋፊ እርሻነትም ስለማይውሉና የአካባቢው ዝርያዎች ከልውጥ ሆነ ከተሻሻለ ዝርያዎች ለቦታው ብልጫ ስላላቸው አምራቾች በራሳቸው ዝርያ እንዲቆዩ ከመንግስት ጭምር በፖሊሲ የታገዘ አሰራር ቢኖር፡፡ ዓምራቹ አንዚህን የአገር ሀብት በማቆየታቸው ልዩ ድጋፍ ቢደረግላቸው፡፡
ተጨማሪ ያንብቡ:  ታሪክ የወረሰ ትውልድ፣ ያልተወለዱ ህልሞችና የማዋለጃው መንገድ - አንዷለም አራጌ

ከሞላጎደል የተወሰነ ግንዛቤ እንዲኖረን ያደረግሁ መሰለኝ፡፡ ምን አልባት በዚህ ጉዳይ ጥያቄ ያላችሁ ካላችሁ በአስተያየት መስጫው ላይ ጥያቄያችሁን ብታስቀምጡ ስለማነበው በሌላ ጊዜ ጥያቄዎቹን ተንተርሼ የተረዳሁትን ያሀል ልመልስላችሁ እችላለሁ፡፡

አመሰግናለሁ

ቅዱስ እግኢአብሔር አገራችንን ይባርክ! አሜን!

ሰርፀ ደስታ

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share