ህወሀት ዘንድሮን የፍልሚያ ዘመን ሲል አውጇል – መሳይ መኮነን

እሳትና ጭድ አይዋሃድም ባለው በሰሞኑ መግለጫው ለትግራይ ህዝብ ብርቱ ትግል የሚገጥምበት ዓመት መሆኑን በመጥቀስ ወገቡን ጠበቅ እንዲያደርግ ጥሪ አቅርቧል። በቁም እስር የሚገኙት የህወሀት አዛውንቶች በእስተርጅና በረሃን መናፈቅ ጀምረዋል። ውስኪ ሲጨልጥና ጮማ ሲቆርጥ የሰነበተው የህወሀት አመራር በምን ወኔና ሀሞት ከደደቢት ዳግም እንደሚገባ የሚያውቁት እነዚያ በእድሜ መግፋትና በተለያዩ በሽታዎች ሞትን በቅርበት እያሸተቱ የሚገኙት አዛውንት መሪዎቹ ብቻ ናቸው። ከ42ዓመት በፊት ወደ በረሃ የገቡበት ዓላማ እነሱን ቱጃር፡ የትግራይን ህዝብ ግን እዚያው በድህነቱ የሚማቅቅ ከማድረግ ሳያልፍ ዘንድሮም የክተት ጥሪ አዋጅ መለፈፋቸው አጥፍቶ የመጥፋት ክፉ መንፈስ እያሰቃያቸው ለመሆኑ ትልቅ ማሳያ ነው።

የሰሞኑ መግለጫ የቁም ኑዛዜ ነው። ህወሀት በህይወት እያለ ተስካሩን የበላበት መግለጫ ነው ማለትም ይቻላል። ከመቃብር አፋፍ ላይ ሆኖ የሚፎክረው ህወሀት የትግራይን ህዝብ ከቀሪው የኢትዮጵያ ወገኑ ጋር ደም ለማቃባት ቋምጧል። ውሳኔው በትግራይ ህዝብ እጅ ላይ ነው። በእርግጥም ዘንድሮ የሞት ሽረት ይሆናል። ህወሀት በለውጡ መሪዎች ያገኘውን ቶምቦላ ሳይጠቀምበት፡ የኢትዮጵያን ህዝብ ይቅር ባይነት ረግጦ ለዳግም ዕልቂት ጥሪ ባደረገበት አዋጅ የራሱን ሞቱን ጨልጦ በታሪክ ውስጥ ከጥቁርና አዳፋ ስብዕናው ጋር ፋይሉ ተዘግቶ የሚሰናበትበት ዘመን እንደሚሆን ጥርጥር የለውም።

ህወሀትና ጽንፈኛ ብሄርተኞች ዘንድሮን መሻገራቸው አሳስቦአቸዋል። ከጫፍ የደረሰውና እውን ሊሆን አጭር ጊዜ የቀረው ውህድ ፓርቲ ገና በዋዜማው ጽንፈኞችን ጸጉር አስነጭቷል። ብሄርተኝነት ጥቃት እየተፈጸመበት ነው ከሚለው እሮሮ ጀምሮ የሰነበቱበትን የቀውስ ማቀጣጠል ተግባራትን በእጥፍ ለመጨመር እጃቸውን እያሟሟቁ ነው። አስገራሚው ነገር ህወሀት ወደ መቃብር እያዘገመም እድለኛ ነው። ቀውስ በመፍጠርም ሆነ በፕሮፖጋንዳው በኩል የሚያግዘው አላጣም። በአንድም ይሁን በሌላ ዓላማውን የሚስማሙና የሚደግፉ፡ ባይነጋገሩም ስለአንድ ግብ የሚሰሩ፡ ሃይሎች ለህወሀት ምርኩዝ ሆነውለታል። እያነከሰም ለጥቂት ጊዜያት በህይወት እንዲቆይ እየረዱት ነው። ልሶ የሚነሳውን አፈር የሚያመርቱ ጽንፈኞችና የጥላቻ ማለያ ያጠለቁ አክቲቪስትና ጋዜጠኞች በጎራ መደበባለቅ ውስጥ አንድ ላይ ተሰልፈዋል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአዳነች አቤቤ ተቺዎች ኢትዮጵያዊ ከሆናችሁ አስተውሉ - ሰርፀ ደስታ

የሰሞኑ አጀንዳቸው ተመሳሳይ ነው። የዶ/ር አብይን የኖቤል ሽልማት ጥምብ እርኩሱን ማውጣት የህወሀትና የጽንፈኛ ብሄርተኞች/ተንታኞች አንዱ ስትራቴጂ ነው። በዚህ ውስጥ ዶ/ር አብይን ሀገር ሻጭ፡ ለስልጣኑ ሲል ኢትዮጵያን ለገበያ ያቀረበ ከሃዲ፡ የምዕራቡ ዓለም አሻንጉሊት፡ የአረቦች ተላላኪ የሚሉ መገለጫዎች የቃላት ልዩነት በሌለው መልኩ በህወሀት ሚዲያዎችና በጽንፈኞቹ/ተንታኞቹ መድረኮች ላይ በብዛት የሚደመጡ የሰሞኑ መልዕክቶች ሆነዋል። የዚህ ጥምረት የመጨረሻ ግቡ ዶ/ር አብይ ከስልጣን እንዲለቁ ህዝባዊ ንቅናቄ መፍጠር እንደሆነ በተለይ በዚህ ሳምንት ውስጥ በገሃድ እየተጠየቀ ነው።

ትላንት እሳትና ጭድ የሆኑት ህወሀትና በተቃዋሚነት ተሰልፈው የነበሩ ሃይሎች እጅና ጓንት ሆነዋል። የህወሀት ሚዲያዎች፡ የጽንፈኛ ብሄርተኛና የጥላቻ ተንታኞች የሚጠቀሙባቸው መድረኮች የባህሪ መወራረስ፡ የዓላማ መመሳሰል፡ የስትራቴጂ መደበላለቅ እየተንጸባረቀባቸው ነው። የህወሀት ቴሊቪዥኖች፡ ራዲዮ ጣቢያዎች፡ የህትመት ውጤቶች፡ የኦንላይን መድረኮች ለጊዜው እፎይታን ያገኙ መስለዋል። ለህወሀት ዓላማ መሳካት ሁነኛ የሆኑ፡ እጥፍ ድርብ አድርገው ጸረ አብይ፡ ጸረ ለውጥ ስብከቶችን የሚያዥጎደጉዱ ፡ ጽንፈኛ ብሄርተኞችና በጥላቻ የተነከሩ ተንታኞች የሚቆጣጠሯቸው ሚዲያዎች ስለተፈጠሩ ህወሀቶች ስራ ቀሎላቸዋል። የጊዜው መፈክራቸው ደግሞ አብይ ከስልጣን ይልቀቅ ሆኗል።

በእርግጥም ይህ ዓመት ህወህት እንዳለው የሞት ሽረት ትግል የሚታይበት ይሆናል። ኢትዮጵያ ደሟን እየጠጣ፡ አጥንቷን እየጋጠ፡ ስጋዋን እየበላ ሊጨርሳት ከጫፍ ከደረሰው የጎሳ ፖለቲካ የምትገላገልበት ዘመን እንዲሆን የሚመኙ ወገኖች መንቃትና ሚናቸውን መለየት አለባቸው። ውዥንብሩ አሁን እየጠራ ነው። ማን ከማን ጋር እንደተሰለፈ ፍንትው ብሎ የሚታይበት ጊዜ ላይ ደርሰናል። ዶ/ር ምህረት ደበበ እንዳሉት ሀገር ልትፈርስ የምትችለው በአላዋቂዎች ድፍረትና በአዋቂዎች ፍርሃት ነው። አላዋቂዎች፡ ደፋሮች ሆነው አንድ ላይ ተሰልፈዋል። ከቤታቸው የተደበቁ፡ በፍርሃትም ይሁን በአርምሞ ውስጥ የሰመጡ ብዙሃን ኢትዮጵያውያን አደባባይ የሚወጡበት ጊዜው ዛሬ ሳይሆን አሁኑኑ ነው። ምርጫው ግልጽ ነው። በህወሀት ለታጀቡትና የመጨረሻ ግባቸው ኢትዮጵያን ማፈራረስ ለሆኑ ለጀብደኛ ደፋሮች፡ ጽንፈኞች፡ የጥላቻ ሰባኪያን እጅ መስጠት አልያም ኢትዮጵያን ከቅርቃር ውስጥ ለማውጣት ትንቅንቅ ውስጥ ከሚገኘው የለውጥ ሃይል ጋር መሰለፍ። ከእነዚህ ሁለቱ ሌላ ምርጫ የለም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ለመለስ ሙት አመት ማስታወሻ (ከፋሲል የኔአለም) ጋዜጠኛ

የሚቀጥሉት ሁለት ወራት ለኢትዮጵያ ወሳኝ ነው። የጀርባ አጥንቱ ተሰብሮ፡ በአንካሴ እግሩ መቀሌ ላይ ቆሞ የእልቂት ጥሪ የሚያስተጋባው ህወሀት ቤተመንግስት የመግባት እድሉ ፈጽሞ የጠበበ ነው። ማድረግ የሚችለው እነዚህ ጽንፈኛ ብሄርተኞችና ጥላቻ አራጋቢ ተንታኞችን ከፊት አስቀድሞ የኢትዮጵያን ስቃይና ምጥ ማራዘም ብቻ ነው። ይህን ደግሞ በሚቀጥሉት ሁለት ወራት ውስጥ በስፋት ያደርገዋል። በኑዛዜ መግለጫው ላይም አጽኦንት በመስጠት ከጎኔ ተሰለፉ ሲል ተማጽኗል። በሌላ በኩል የለውጥ ሃይሉ ከመጋረጃው በስተጀርባ፡ በዝግታ አካሄድ፡ ድምጹን አጥፍቶ ጽንፈኝነት ድባቅ እየመታ ነው። የህወሀትን የጥፋት እግሮች እየተከታተለ በመቁረጥ ላይ መሆኑን እያየን ነው። አውቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት አይሰማም ካልሆነ በቀር የለውጥ ሃይሉ ኢትዮጵያን ለማዳን ግልጽና ጠንከር ያሉ እርምጃዎችን በመውሰድ ላይ ነው። ፈተናው ቢበዛም፡ ማዕበሉና ወጀቡ ቢጠነክርም እየተንገዳገደና እየተወዛወዘም ቢሆን የጀመረውን መንገድ አለቀቀም። በእነዚህ ቀጣይ ሁለት ወራት የለውጥ ሃይሉ የቤት ስራውን በማጠናቀቅ አንዳች ውጤት ላይ ይደርሳል ተብሎ ይጠበቃል።

ፈጣሪ እግዚያብሄር ኢትዮጵያንና ህዝቧን ይጠብቅ! አሜን!

6 Comments

  1. እነኝያ ዉርጋጦች ወጥተዉ Ethio 360 የሚባል ያገጠጠ የጥላቻ ፕሮፓጋንዳ ሲከፍቱ፤ ኢሳት ይሰበሰባል ብዬ ገምቼ ነበር። ነገር ግን እንድዉ ባሰባቸው እንጂ ምንም መሻሻል አልታየም። ምላሱ ላንቃዉ ዉስጥ የሚወተፈዉና የሚናገረው ሁሉ intellectual substance የለለው ግዛዉ ለገሰን አመጡና ኢሳትን ገደል ከቱት። ሲሳይማ ሁሉን አዋቂ አድርጎ ቢቀርብም አንዳንድ ጊዜ ቀላል ክብደት ያላቸዉን እንደ እነ ወንድማገኝን በተለይም ፋሲል የኔዓለምን፤ አላዋቂነታቸዉን በማጋለጥ ይሞግታቸዋል። ለምሳሌም ፋሲል አረርንጓዴ ብጫ ቀይ ባንዲራ ከጥንት ጀምሮ የኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን አርማ ነዉ ብሎ አፍጦ ሲናገር ሲሳይ ልክ ልኩን መናገሩ ነዉ።

    ወደ ለከት የለሹ መሳይ መኮንን ስንመጣ የሚያሳስበዉ ነገር አንድ ቀን መድረክ ላይ እያለ ልቡ ፈንድቶ እንዳይሞት ነዉ። ውሸቱ፤ ቅጥፈቱና እሱ የሚፈልጋቸዉ ነገሮች ባለመሆናቸዉ የሚመጣበትን ንዴት ሁልጊዜ ማየት በጣም የሚያዝናና ነው። ፋረንጆች entertaining ይሉታል። አለማፈርነቱ ደግሞ ያንን የደለበ ሰንጋ የሚመስለውን ሰዉነቱን በጣም ትንሽ ያረገዋል። ሕዝቡን ያነጋገረ ይመስል ሁልጊዜ ሕዝቡ ያላለዉን አለ ይላል። ለምሳሌም የኦሮሞ ሕዝብ ፌዴራሊዝምን አይፈልግም፤ አቶ ሺመልስ ያሉትን አይደገፍም፤ ኦነግንና ባንዲራዉን አይፈልግም። ተገዶ ነዉ ኢንጂ የትግራይ ሕዝብ ሕወአትንና ፌዴራሊዝምን አይፈልግም። ሕዝቡ እኮ እንደዚህ እያለ ነዉ በሎ ሕዝቡ ያላለውን ይነገራል። መሳይ ሕዝብ ጋ ሂዶም አያዉቅም። አንድ ጊዜ ጅግጅጋ ሂዶ ከኢሳት ጓደኞቹና ከከተማዉ ነፍጠኞች ጋር በሽርጥ ሱማሊኛ ሲያስራግጥ አይተናል። በቅርብ ደግሞ አመጽ ለመቅስቀስ (ነዉ ይባላል) ሀዋሳ ሄዶ ሳይሳከለት ተመልሶኣል። (በነገራችን ላይ ሲሳይም የባልደራስን ሰልፍ ለመዘገብ ፊንፊኔ ሄዶ ትልቅ ሀፍረት ተከናንቦ ተመልሶኣል።) በመጨረሻ መሳይ መዋሸቱን የሚያስቆም psychiatric counselling ልቡ እንዳይፈነዳ ደግሞ የታወቀ cardiologist ያሰፈልገዋል።

  2. ፈጣሪ ቅማንትንና ትግሬን ያጥፋ ብለህ የማትጸልይ ይመስል “ፈጣሪ እግዚያብሄር ኢትዮጵያንና ህዝቧን ይጠብቅ” ትላለህ። ባንተ ኢትዮጵያ ዉስጥ እኮ ከአማራ በስተቀር ሌሎች መኖር እንደማይገባቸዉ ኢሳት ላይ የማትሰብክ ይመስል የእግዚአብሔርን ስም ታነሳለህ። ዶክቶር አብይን ለመምሰል ነዉ እንደዚህ የምትለው? ወዴት ጠጋ ጠጋ ነዉ ቆምጫምቤ? ሀፍረተ-ብስ!

  3. አረረረረረ!! እዉነትክን ነዉ ወንድሜ ጦና ዛሬም እነመሳይ ዉሸታቸዉን ለቀቁት። መሲ ሊፈነዳ ነበር።
    ለኦዴፓ ያላቸዉ ፍቅርማ ገደብ አጣ። ኦዴፓ ነገ ዞር ሲል ደግሞ ገንጣይ ይሉታል።

  4. የኔን አስተያየት ምን በላው? ወይ ልፍኣተይ!
    ካስታወሥኩት እንዲህ ይል ነበር፦
    መሣይ እንዲህ ይለናል “በሌላ በኩል የለውጥ ሃይሉ ከመጋረጃው በስተጀርባ፡ በዝግታ አካሄድ፡ ድምጹን አጥፍቶ ጽንፈኝነት ድባቅ እየመታ ነው። የህወሀትን የጥፋት እግሮች እየተከታተለ በመቁረጥ ላይ መሆኑን እያየን ነው። አውቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት አይሰማም ካልሆነ በቀር የለውጥ ሃይሉ ኢትዮጵያን ለማዳን ግልጽና ጠንከር ያሉ እርምጃዎችን በመውሰድ ላይ ነው። ፈተናው ቢበዛም፡ ማዕበሉና ወጀቡ ቢጠነክርም እየተንገዳገደና እየተወዛወዘም ቢሆን የጀመረውን መንገድ አለቀቀም።”
    ሀፍረትን ባወጣ ቸርችሮ በመሸጥ ሥልጣን ከያዘ አምባገነን ኃይል ጋር ተመሣሥሎ መኖር ይሏል ይህን ጊዜ ነው። መሣይ ላለፉት በርካታ ዓመታት ከወያኔ ጋር ያደረገውን የሚዲያ ትግል በዚች ጽሑፍ ምክንያት በአንዴ በዜሮ አባዝቶ ራሰን ትዝብት ውሥጥ አሥገባ። ለሆድ ነው ማለት ይከብደኛል፤ለሥልጣን ነው ማለትም ይከብደኛል። ምክንያቱን አንድዬ ይወቅ መሣይ ግን አሁን ትልቅ ነጥብ ጥሏል።
    ከጽዳትና ዘበኛ እስከ ሚንስትርና ጠ/ሚ የፌዴራል ተብየው መዋቅር ሙሉ በሙሉ ሊባል በሚችል ደረጃ በአክራሪ ኦሮሞ በተረኝነት ስሜትና አባዜ እየተወረረ ሌላው በተለይም አማራው ለመፈናቀል፣ለሞትና እሥር፣ ለሥደትና ለሥቃይ… ተጋልጦ ኤሎሄ እያለ ባለበት ሁኔታ እንደዚህ ያለ የፕሮፓጋንዳ ድጋፍ ከታዋቂ “የሕዝብ ሰው” ጋዜጠኛ መሣይ መኮንን መስማትም ሆነ ማንበብ ጆሮንና ዐይንን እንድንጠራጠር ያደርጋል።ይሁን ግዴለም።ዓለም የክህደትና የመገለባበጥ ናት፤ ነገም ሌላ ቀን ነውና የላይኛውን እውነተኛ ፍርድ መጠበቅ ይሻላል፣ ዱሮውንም ሰው ሰው ነውና ከመዋቲ ሰው ብዙ መጠበቅ ሞኝነት ነው።
    ይህን ሁሉ ለፍቼም በሉ አሁንም ቅርጫታችሁ ውሥጥ አሥገቡት ዘሃበሾች።

  5. የኔን አስተያየት ምን በላው? ወይ ልፍኣተይ!
    ካስታወሥኩት እንዲህ ይል ነበር፦
    መሣይ እንዲህ ይለናል “በሌላ በኩል የለውጥ ሃይሉ ከመጋረጃው በስተጀርባ፡ በዝግታ አካሄድ፡ ድምጹን አጥፍቶ ጽንፈኝነት ድባቅ እየመታ ነው። የህወሀትን የጥፋት እግሮች እየተከታተለ በመቁረጥ ላይ መሆኑን እያየን ነው። አውቆ የተኛን ቢቀሰቅሱት አይሰማም ካልሆነ በቀር የለውጥ ሃይሉ ኢትዮጵያን ለማዳን ግልጽና ጠንከር ያሉ እርምጃዎችን በመውሰድ ላይ ነው። ፈተናው ቢበዛም፡ ማዕበሉና ወጀቡ ቢጠነክርም እየተንገዳገደና እየተወዛወዘም ቢሆን የጀመረውን መንገድ አለቀቀም።”
    ሀፍረትን ባወጣ ቸርችሮ በመሸጥ ሥልጣን ከያዘ አምባገነን ኃይል ጋር ተመሣሥሎ መኖር ይሏል ይህን ጊዜ ነው። መሣይ ላለፉት በርካታ ዓመታት ከወያኔ ጋር ያደረገውን የሚዲያ ትግል በዚች ጽሑፍ ምክንያት በአንዴ በዜሮ አባዝቶ ራሰን ትዝብት ውሥጥ አሥገባ። ለሆድ ነው ማለት ይከብደኛል፤ለሥልጣን ነው ማለትም ይከብደኛል። ምክንያቱን አንድዬ ይወቅ መሣይ ግን አሁን ትልቅ ነጥብ ጥሏል።
    ከጽዳትና ዘበኛ እስከ ሚንስትርና ጠ/ሚ የፌዴራል ተብየው መዋቅር ሙሉ በሙሉ ሊባል በሚችል ደረጃ በአክራሪ ኦሮሞ በተረኝነት ስሜትና አባዜ እየተወረረ ሌላው በተለይም አማራው ለመፈናቀል፣ለሞትና እሥር፣ ለሥደትና ለሥቃይ… ተጋልጦ ኤሎሄ እያለ ባለበት ሁኔታ እንደዚህ ያለ የፕሮፓጋንዳ ድጋፍ ከታዋቂ “የሕዝብ ሰው” ጋዜጠኛ መሣይ መኮንን መስማትም ሆነ ማንበብ ጆሮንና ዐይንን እንድንጠራጠር ያደርጋል።ይሁን ግዴለም።ዓለም የክህደትና የመገለባበጥ ናት፤ ነገም ሌላ ቀን ነውና የላይኛውን እውነተኛ ፍርድ መጠበቅ ይሻላል፣ ዱሮውንም ሰው ሰው ነውና ከመዋቲ ሰው ብዙ መጠበቅ ሞኝነት ነው።
    ይህን ሁሉ ለፍቼም በሉ አሁንም ቅርጫታችሁ ውሥጥ አሥገቡት ዘሃበሾች። ለዚያውም በውድቅትና በደቃቃ ሞባይል!

  6. ወቀሣየን አንስቻለሁ ዘሃበሻዎች። ስላልደረሣችሁ ነው ያልወጣልኝ። “በምን አወቅህ?” አትሉኝም? ስልከው ‘your comment is awaiting moderation.’አላለኝም ነበር። አሁን ስልከው ግን እንደዚህ አለኝ – ስለዚህ ፓሲፊክንና አትላንቲክን ተሻግሯል ማለት ነው።

Comments are closed.

Share