የአማራ ክልል ደኅንነትና የጸጥታ ካውንስል የጋራ መግለጫና ውሳኔዎች – የአማራ ብሔራዊ ክልል የደኅንነትና የፀጥታ ካውንስል

በማዕከላዊ እና በምዕራብ ጎንደር ዞኖች፣ በጎንደር ከተማ እንዲሁም በቅማንት ብሔረሰብ አስተዳድር ማንነትን ሽፋን በማድረግ ባለፉት አምስት ዓመታት የዘለቀው የጸጥታ መደፍረስ ለሰው ህይዎትና ለንብረት ጥፋት ምክንያት ሆኖ መቀጠሉ የሚታወስ ነው፡፡ የክልሉ መንግስት ህግና ሥርዓትን በተከተለ አኳኋን ለተነሱ የማንነት ጥያቄዎች የቅማንት ብሔረሰብን ጨምሮ ምላሽ መስጠቱ የሚታወስ ነው፡፡ ለተነሱ የማንነት ጥያቄዎችና መልሶች ቅሬታ ያቀረበ ኃይል፣ ቡድንና ማኅበረሰብ ህግና ሥርዓትን በተከተለ መንገድ ሀሳባቸውን፣ ጥያቄያቸውንና ቅሬታቸውን አቅረበው መስተናገድ እየተቻለና ለዚህም በርካታ ዕድሎች ብሎም ጊዜያት ተሰጥተው እያለ በሃይል ፍላጎትን ለማሳካት መሞከር ጸረ ህገ መንግስትና የለዬለት ጸረ ሰላም ተግባር መሆኑ በግልጽ ሊታወቅ ይገባል፡፡

የቅማንት የራስ አሥተዳድር ኮሚቴ የተከተለው አቅጣጫም ከላይ የተገለጹ ተግባራትን በመፈጸም ፍላጎትን በኃይል በብሔረሰቡና በክልሉ መንግስት ላይ የመጫን ኢ ህገ መንግስታዊ እንቅስቃሴ ነው፡፡ ይህንን ለመቀልበስ የሚወሰድ አጸፋዊ እርምጃም በአንጻሩ ከፍተኛ ጉዳት እያደረሰ ይገኛል፡፡ ከመስከረም 15/2012 ዓ.ም ጀምሮ የተከሰተው ግጭትና እያደረሰ ያለው ከፍተኛ ጉዳትም የዚህ መገለጫ ነው፡፡ ለአካባቢው ጸጥታ መደፍረስ ምክንያት ሆኗል፤ ለሌሎች የጥፋት ሃይሎችም ምቹ ሁኔታ እንዲፈጠር እያደረገ ነው፡፡ በዚህም የተለያዬ ኢ መደበኛ አደረጃጀትን ይዘው የሚንቀሳቀሱና በጸረ ሰላም ተግባር ላይ የተሰማሩ ቡድኖችና ግለሰቦችም ትልቅ መሳሪያ አድርገው እየተጠቀሙበት ይገኛሉ፡፡ በዚህም በሰው ህይዎትና በንብረት ላይ ከፍተኛ ጉዳት እየደረሰ ይገኛል፡፡

ይህ እንደተጠበቀ ሆኖ በክልልና በፌዴራል መንግስት በትዕግስትና በአርቆ አስተዋይነት ችግሩን በሰላማዊ አግባብ ለመፍታት በርካታ ጥረቶች ቢደረጉም ወደ ውጤት ሊቀየር አልቻለም፡፡ ይባስ ብሎም አካባቢውን ወደ ተሟላ ትርምስ የሚያስገባና ለክልሉ ብሎም ለመላው ሃገሪቱ የጸጥታ ስጋት ወደ መሆን ተሸጋግሯል፡፡ የሰው ህይወትና ንብረት በየቀኑ ይጠፋል፡፡ ማኅበራዊና ኢኮኖሚያዊ እንቅስቃሴዎች በከፍተኛ ደረጃ ተዳክመዋል፡፡ ከጎንደር-መተማ ያለው አከባቢ የንግድ መስመር ከመሆኑ ጋር ተያይዞም በገቢና ወጪ ንግድ ላይም ከፍተኛ አሉታዊ ተፅዕኖ አሳድሯል፡፡ በመሆኑም የክልሉ መንግሥት ለፌዴራል መንግሥት ጉዳዩን ጣልቃ ገብቶ እንዲያስተካክል በጠየቀው መሠረት የፌዴራል የፀጥታ ኃይል መከላከያን ጨምሮ ማንኛውም ህጋዊ እርምጃ ወስዶ ቀጠናውን በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ ተሟላ ሰላም እና መረጋጋት እንዲያሸጋግር መመሪያ ተላልፏል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ጀነራል አበባው ታደሰ በወሎ ግንባር በሰሜን ወሎ ግምባር

የተላለፈውን መመሪያ በመከተል የክልሉ የፀጥታና ደኅንነት ካውንስል በማዕከላዊ፣ በምዕራብ ጎንደር፣ በቅማንት ብሔረሰብ አስተዳድር እና በጎንደር ከተማ ቀጥለው የቀረቡ ክልከላዎችና ውሳኔዎች ተግባራዊ እንዲደረጉ መመሪያ ሠጥቷል፡፡

1.ማንኛውም የኃይል እንቅስቃሴን የኃይል እርምጃ በመውሰድ የሰው ህይወትና ንብረትን ከአደጋ ማዳን፣ በድርጊቱ ላይ የተሳተፉትን በኃይል መቆጣጠር፣ ለህግ ማቅረብ፣ ተመጣጣኝ የኃይል እርምጃን በመውሰድ የኃይል ተግባርን ፍፁም እንዳይቀጥል ማድረግ፣

2.አሁንም የሰላም አማራጮችን ለማስፋትና በአከባቢው ሰላምና መረጋጋት ለመፍጠር ሲባል በተለያዩ ምክንያቶች ወደ ግጭት የገቡ ቡድኖች እና ግለሰቦች በአስቸኳይ ወደ ጠረጴዛ ዙሪያ በመመለስ ያሏቸውን ልዩነቶች እንዲፈቱ ጥሪ ተላልፏል፡፡ ከዚያ ውጪ ምንም ዓይነት የኃይል እርምጃ ተቀባይነት አይኖረውም፡፡

3.ማንኛውም ግለሰብ ወይም ቡድን በቀጠናው ላይ ለሚደረገው የፀጥታ ኃይል ስምሪት የመተባበር፣ ወንጀለኛን አሳልፎ የመስጠትና የአከባቢውን ሰላም ለማረጋገጥ የሚደረገውን ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ ድጋፍ የማድረግ ግዴታ አለበት፡፡ ይህንን የሚያደናቅፍ ማንኛውም ተግባር በህጋዊ እርምጃ የሚስተካከል ይሆናል፡፡

4.በግልፅ በታወቁ የፀጥታ ኃይሎች ከተያዙት ትጥቅና መሳሪያ ውጪ በተጠቀሱት የክልሉ ዞኖች ላልተወሰነ ጊዜ ትጥቅ ይዞ መንቀሳቀስ የተከለከለና የሚወረስ ይሆናል፡፡
5.የቅማንት ብሔረሰብ አስተዳድር ከዚህ ቀደም በተወሰነው ህጋዊ ውሳኔ መሠረት በአፋጣኝ በሕዝብ ይሁንታ የሚደራጅ የራስ አስተዳድርን በማቋቋም ሁሉም አገልግሎት እንዲጀምር ማድረግ፡፡ ይህንን የሚያደናቅፍ የኃይል እርምጃ ፍፁም ተቀባይነት አይኖረውም፡፡

6.በተለያየ ምክንያትና ሰበብ ተደናግሮም ይሁን በንቃት በኃይል ፍላጎትን ለማሳካት በተደረገው እንቅስቃሴ ውስጥ ተሳትፎ የነበረውን ኃይል፣ ቡድንና ግለሰብ እስከ ጥቅምት 20/2012 ዓ.ም ድረስ ባለው ጊዜ ወደ ሰላማዊ ሁኔታ እንዲመለስ የክልሉ መንግሥት በድጋሜ ይቅርታ አድርጎለታል፡፡ በሰው ግድያ ቀጥተኛ ተሳትፎ የነበራቸው ግለሰቦች ጉዳያቸው በህግ አግባብ የሚታይ መሆኑ እንደተጠበቀ ይሆናል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  በእስር ላይ የሚገኙት አቶ በረከት ስምኦን በጠና ታመዋል ተባለ

7.በየዞኑ፣ በየወረዳውና ቀበሌ ውስጥ፣ አቅራቢያና አከባቢ ለሚፈጠሩ ወንጀሎች ፀረ-ሰላም ድርጊቶችና እንቅስቃሴዎች በየደረጃው ያለው አመራር፣ ነዋሪና ዜጋ የመቆጣጠር፣ የማሳወቅ፣ እርምጃ እንዲወስድ የማድረግ ኃላፊነት አለበት፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ተጠያቂነትን ከማስከተልም በተጨማሪ በአከባቢው የሚገኘው ትጥቅ ሙሉ በሙሉ ተራግፎ ለመንግሥት ገቢ ይሆናል፡፡

8.በኢ- መደበኛ አደረጃጀትና ባልተሠጠ ኃላፊነት ህግን ለማስከበር በሚል ሰበብ የሚደረግ ማንኛውም እንቅስቃሴ የተከለከለ ነው፤ ተጠያቂነትም ያስከትላል፡፡

9. ከጎንደር-መተማ ፣ ከጎንደር-ሁመራ፣ ከጎንደር-ባሕር ዳር፣ ከጎንደር- ደባርቅ የሚወስዱ መንገዶች እንዲሁም በጎንደር ከተማና ዙሪያው ብሎም ሁሉም መጋቢና ዋና ዋና መንገዶች በማንኛውም ጊዜ ነፃ ይሆናሉ፡፡ የሕዝብ እንቅስቃሴም ከመቼውም ጊዜ በበለጠ ነፃ ይሆናል፡፡ ይህንን ለማደናቀፍ የሚደረግ እንቅስቃሴ ላይ ህጋዊ እርምጃ የሚወሰድ ይሆናል፡፡

10.የሀገር መከላከያ ሰራዊት፣ የፌዴራል ፖሊስ፣ ክልል የፀጥታ ኃይል፣ በየደረጃው ያለው የክልሉ መስተዳድር፣ የብሔራዊ መረጃና ደኅንነት በቅንጅትና በጥምረት በመሰማራት በአከባቢው ላይ የተሟላ ሰላምና መረጋጋትን እንዲፈጠር ያደርጋሉ፡፡

11.በመጨረሻም ሁሉም የሰላም ኃይሎች ማለትም የሃይማኖተ አባቶች፣ የሀገር ሽማግሌዎች፣ ወጣቶች፣ ብሔርን እና ማንነትን ሳይለይ በአከባቢያችን የተሟላ ሰላም እንዲረጋገጥ ለፀጥታ ኃይሉ የተሟላ ድጋፍ ታደርጉ ዘንድ ጥሪያችን እናስተላልፋለን፡፡

የአማራ ብሔራዊ ክልል የደኅንነትና የፀጥታ ካውንስል፡፡

ጥቅምት 05/2012 ዓ.ም

1 Comment

  1. Medemer is said to be an excellent novel written by the one and only Nobelity-Abiy Ahmed that clearly guides the publi in identifying the trouble makers amongst ourselves. . Ever since this fanatic Addis Ababa KINIJIT vigilantes got let in to Ethiopia with mercy , the Kinijit cadres had been creating unrests allover the country. The whole world is happy to dump Kinijit cadres back to Ethiopia where the famous Nobelity-Abiy Ahmed accepted them back winning himself prizes such as the Nobelity for it.

    In Addis Ababa children of the honest hardworking poor were said to be overqualified for free food doomed to continue starving, while the children of Kinijit ginbot7 affiliated corrupt tax evaders career Arab maids got qualified for free food.

Comments are closed.

Share