ሰው መሆናችንን አውቀን ለፍቅር ከተገዛን  ኢትዮጵያን  ኃያል እናደርጋታለን።  – መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ

    ስው ማሰቡን የሚያቆመው ሲሞት ብቻ ነውና ሃሰቡን ለመሰሎቹ በማካፈሉ የሚወገዝበት ዘመን ማክተሙን  ክቡር ጠቅላይ ሚኒሥተራችን  ዶ/ር አብይ አህመድ ከቃል በላይ በትግባር ዕውን እነዲሆን ከመላው ኢትዮጵያዊያን ጋር እንደሚሰሩ በማረጋገጣቸው በእጅጉ ተደስቻለሁ፡፡
    ” ለምን ታስባለህ? ሃሰብህንስ ለምን ታካፍላለህ ?”በማለት የሚገድበው ሳይኖር ፣”ህዝብን ታነቃለህ፣የግለሰብን ህሊና በማንቃትና የግንዛቤ እጥረቱንም በመቅረፍ፣በድምርም ህዝብ እንከኔን እንዲያይ በማደረግ ህግ እና ህገመንግስት  እኔ ራሴ ሆኜ ሳለ፣ህገመንግስቱን ጥሰሃል፣በሥልጣንም ያለአግባብ ባልገሃል፣በማሰኘት እነደጠላ ታደርጋለህ፡፡…አንተ እኔ ህዝብን እንዳሻው እየመራው የምሰራው ሥራ የማይታይህ  ፀረ-ልማትና ፀረ-ህዝብ ነህ፡፡ፀረ ህገመንግስት ነህ፡፡ወዘተ፡፡”በማለት ሰዎች በሰብአዊ እና ዴሞክራሲያዊ መብታቸው እነዳይጠቀሙ የሚያደርግ ሥርዓት አክተሞል፡፡  እነኚህ – ” ሊበልዋት ያሰቧትን አሞራ – ጅግራ ናት ይሏታል፡፡ “በሚል ቅኘት የሚጓዙ ና የሚጓዙ  “ሸባቢ” መንግስታዊና ሥልጣናዊ አሰተሳሰቦች ና ” ኩንን  ድረጊቶች ” በዚህ በዲጂታል(ዓለም በቴክኖሎጂ ተራቆ ምድር እፍኝ በሆነችበት ዘመን)ላይመለሱ ተሰናበተዋል፡፡” በማለት የልብ ልብ ለዴሞክራሲ ርሃብተኞች ሰጥተዋል፡፡በርግጥም  እንዳንናገር  “የሥልጣንን አለንጋ ” ይዞ በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ “ዋ !ውርድ ከራሴ…” በማለት የሚየሥፈራራን ና የሚዠልጠን ፣ አምባ ገነን ባለሥልጣን ፣ ባለጠብንጃ ( ገራፊ፣አሣሪ ና ገዳይ) ለጊዜው ገለል ማለቱን ብናውቅም ቆይቶ  ” አቶ ገለሌ ! …” ፡፡ እንደማይል  ምንም ማረጋገጫ የለንም፡፡
     በብዙ ቅን ልቦች  እምነት  እንደሚታሰበው፣ለሰው ተፈጥሯዊ ነፃነቶች(ለመናገር፣ለመስማት ሃሳብን በነፃነት የማካፈል፣ነፃነቶች ) “ደንታ የለንም፡፡ የሚሉ በዚች ሀገር በመንግስት ሥም ከሌሉ መጪው የኢትዮጵያ ዜጎች ህይወት ደሥታው የበዛ እነደሚሆን ከወዲሁ መመሥከር እንችላለን፡፡
      ህይወት በደስታና በሥቃይ መሞላቷ እርግጥ ነው፡፡ ነገርግን ደሥታችን ይበዛ ዘንድ ፣ሁላችንም ሰው መሆናችንን በቅድሚያ ማመን ይኖርብናል፡፡ዜጎች ይህችን በደሥታና በሥቃይ የተሞለች አጭር ህይወት ደስታዋን የሚያበዙት ከሁሉ በፊት ሰው መሆናቸውን ሲገነዘቡ ብቻ ነው፡፡  ሰው መሆናቸውን እና ከሌላው ሰው ፈፅሞ የማይበልጡና የማያንሱ አለመሆናቸውን ሲረዱ ነው፡፡ሀብታም ሆኑ ደሃ፤ሥልጣን ኖራቸው አልኖራቸው ሁሉም ሰው እና ነገ አፈር መሆናቸውን ሲያውቁ ነው፡፡የመሞት የመበስበስና ከምድር ህይወት የመፋቅ ዕጣ ፈንታ የነሱም መሆኑን ሲገነዘቡ ነው፡፡
     በዓለም ላይ ያሉ ፣ በተመድ ድምፅን በድምፅ የመሻር ጉልበት ባላቸው የኒኩለር ኃይል እና በሥልጣኔያቸው ምጥቀት ያገኙ ሀገሮች፣ ይህንን የሰው ህልፈት ና ውልደት በውል ተገንዝበው፣  እውነቱን ለህዝባቸው ካሳወቁ ዘመናት ተቆጥረዋል።
      ዛሬ እነሱ ፣ በአሥተሳሰብ እጅግ ልቀው ፣የእኛን ዜጎች በየሀገራቸው አስጠግተውና ዜግነት ሰጥተው በድንቅ እእምሯቸው በመጠቀም ሀገራቸውን እነድትበለፅግና የበለጠ  ታላቅ ሀገር እነድትሆን እያደረጉ ነው።
      የበለፀጉት ሀገሮችን በማስተዋል ፣ የኢትዮጵያ ምሁራን ፣ዜጎችን በማንቃትና ሰው መሆናቸውን በማሰወቅ፣ ይህችን አጭር ህይወት በመገዳደል የበለጠ ለማሳጠር መቀዥቀዣቸውን እንዲያቆሙ ማደረግ ይጠበቅባቸዋል፡፡
        ለዚች ሀገር ታላቅነት ዜጎች በተሰማሩበት የሥራ መሥክ ሁሉ ጠንከረው በመሥራት በድምር ውጤት ለመላው ኢትዮጵያዊያን ብለፅግናን አውረሰው ማለፍ እነደሚገባቸው አበክረው እነዲያስቡ ባገኙት መድረክ ሁሉ መምከርና መዘከርም ሳይማር ያስተማራቸው ህዝብ እነደውለታ የሚቆጥረው ነው፡፡
      በሀገራችን የሚገኙ ብሄሮችና ብሄረሰቦች ሁሉ የተለያየ ቋንቋ እና ባህል፣እምነትናኃይማኖት ወዘተ፡ዠ (…)ቢኖራቸውም ፤መልካቸው ቢለያይም ፤ሁሉም የወል ሥም ያላቸው አንድ ፍጥረት ናቸው፡፡ የወል ሥማቸውም “ሰው” ይሰኛል።  ይህንን በቅጡ ሳንገነዘብ ጎረምሳ ዓመታት፣ወደጉልምሥና ተሸጋግረዋል።
    ብዙዎቻችን  በ21ኛው መክዘ እንኖራለን እንላለን እንጂ ከቆዳ ማወደድ ዘመን ፣  ከዘመነ መሳፍነት አስተሳሰብ ገና አልተላቀቅንም፡፡  ዛሬም ሙሉ ለሙሉ ” የሰው ሰው መሆንን የማንቀበል” እና ቆዳችንን የምናዋድድ ፣ በመላ ሀገሪቱ እዘና እዚህ አለን ፡፡(…)
     ትላንት ና እና ዛሬ  ፣ መንግስታት ሰውን በራሳቸው ርዕዮት ለማስጓዝ አለንጋን እንደብቸኛ አማራጭ ሲጠቀሙበት የሚሥተዋሉት በየሀገሮቻቸው፣ሰው መሆናቸውን የዘነጉ ፣ በህዝብና በራሱ መንግሥት በተባለው መዋቅር ውሥጥ በዝተው ሥለማገኙ ነው፡፡
     መንግስት የተባለው አሥተዳዳሪ አካል፣አለንጋን እነደብቸኛ አማራጭ የሚጠቀምበት ከሆነ ደግሞ፣  ከሚያሥተዳድረው ህዘብ ጋር ብዙ እርቀት ለመጎዝ አይችልም፡፡ይሁን እነጂ የመንግስት አለንጋ ህዝብ ያመነበትን የሀገሪቱን ህግ ለማስከበር የሚገለግል፣በሀዝብ ቅቡልነት ያለውን በፍትህ፣በዴሞክራሲና በመልካም አስተዳደር ማቀፍ ውስጥ ያለና የይስሙላ ያልሆነ ፣መንግስትን የሚቆጣጠር መሳርያ ከሆነ፣የአለንጋው መኖር ጠቃሚ እንጂ ጎጂ አይሆንም፡፡
        በእረግጥ ለዘመናት ሰዎች ባሰለፉት የሰው ልጅ ታሪክ ውሰጥ መንግስት የተባለው ተቋም ህግ አልቦ አርጩሜና ኃይለኛ ገራፊ ነበረው፡፡ኢፍትሃዊነትና  ” አባቱ ዳኛ ፣ ልጁ ቀማኛ ።” የሆነበት መንግስትም  በአፍሪካ ተንሰራፍቶ ይታይ ነበር፡፡ህግ ለሁሉም እኩል አልነበረም፡፡ህግ ገዢዎች የሚፈሩት የበላያቸው ፈፅሞ አልነበረም፡፡ የገዢዎች የበላይነት እንጂ!!
   (በመንግስቱ ለማ ግጥም “የአንበርብር ጎሹን ሞት – ሰበብ አንዘነጋውም፡፡”አንድ ኮማሪትን ለንጉስ ለአንድ ቀን አዳር በመመኘቱ ነበር፣ በሰላይ ተይዞ እነዲገረፍ የተፈረደበት፡፡የተፈረደበት ሰለሳ ጅራፍ ነበርና ሰላሳው ሳይሞላ ነው እዛው ፈግም ያለው፡፡)
        ዕድሜ ለባለቅኔው አብዬ መንግስቱ ይሁንና እጅግ ከረቀቀ እና ከተዋበ ግጥማቸው ፣ እንደተረዳነው  በቀዳማዊ  ኃይለ ሥላሤ ዘመነ መንግስት ፣መንግስት የተባለው ተቋም ፣ተቀዳሚ ሥራው ግለሰባዊና ቡድናዊነትን በማንገስ ግለሰቦችን ከህግ በላይ ማደረግ ነበር ሲገዛ የነበረው፡፡ ያም አካሄድ ሥሙን በመቀየር መንፈሱ እየተንከባለለ ቀጥሎ ዛሬ ላይ ደርሰናል፡፡
በደምሳሳው፣ እኩል ፍትህ አልነበረም፡፡የነበረው ገራፊነት፣ጨቋኝነት፣ፈላጭ ቆራጭነትና አምባገነንነት  መሆኑንን ያለፈ ታሪካችን “ጮክ ብሎ ” ይመሰክራል፡፡
      የዓለም ታሪክ እንደዘገበው ዓለማችን፣ የእኛን ዘራያቆብን ጨምሮ፣እስታሊን፣ሞሶሎኒ፣ሂትለር፣በአፍሪካ ደግሞ  እነ ኢዲያሚን፣ጋዳፊና ቦካሳን አቅፎ ሌሎች እናንተ የምታወቋቸው  በትረ መንግስትን የጨበጡ፣እጅግ አምባገነን፣ጨቋኝና ምህረት ቢስ  ገራፊዎች ነበሯት፡፡”…ከነሱ ሃሰብ በተቀራኒ ሆኖ ማሰብም ፈፅሞ የማይቻል እና ወደተለያየ የማሰቃያ ሥፍራ የሚስገባ ነበር፡፡”
    የራሰችንን የትላንት ታሪክ ይህንን እውነት የበለጠ ያስረዳናል፡፡፣ በራሰችን መንግስት እጅግ ወራዳና እና ዘግናኝ የግፍ ተግባር የሚፈፀምበት “ማአከላዊ የማሰቃያ እስርቤት”የሚባል ከደርግ ወደ ኢህአዴግ የተሸጋገረ ተቋም ነበረን፡፡ ወደ ሙዜምነት እነዲቀየር ከመወሰኑ በፊት አያሌ ንፁሃን ወድምና እህቶቻችን ተሰቃይተውበታል፡፡…
       ያም ሆነ ይህ ትላንት መንግስት የተባለው ህዝብን እነዲያሥተዳድር በህዘብ ወይም በጉልበት ፈቃድ የአገዛዝ ሥልጣንን የያዘ ግለሰብና ቡድን ፣በወረቀት የተፃፈ ወይም ያልተፃፈ  የመገረፍ፣የማሰቃየት፣በአደባባይም  የመስቀልና የመረሸን መብት እነደነበረው አይካድም፡፡ ዛሬም በአንዳንድ ሀገሮች አለ፡፡ (…)
           ከታሪክ የምንረደው አውነት፣መንግስት  በአደባባይ ሰዎችን በሚዘገንን ሁኔታ በማሰቃይት ሲገድል ድርጊቱን በማወደስ በታላቅ ሆታና ፈንጠዝያ በጭካኔ የተሞላውን ድረጊት ያወደሱ ነበሩ፡፡…(መላውን የአንድ ሀገር ህዝብን ግን አየወክሉም)
      ለምን እና እንዴት እንዳወደሱ፣ለአረመኔው አገዛዝ እንዳበዱለት እና እንዳረገዱለት፣በሥሜታዊነትም እንደሞቱለትም በዛሬ መነፅር ስናየው ግራ ይገባናል፡፡ ይሁን እንጂ በወቅቱ ቁጥሩ ትንሽ የማይባል ህዝብ በሶሻሊስትና በካፒታሊስት ጎራ ተከፍሎ እረስ በእርሱ ተጋድሏል፡፡
      የእኛን  የ1967 ዓ/ም ቱን ህዝባዊ አብዮትና የአብዮቱን አርጋዦችና አዋላጆች እንዲሁም፣በአጋጣሚው ድንገት ሥልጣን በእጃቸው የገባችላቸውን ደርጎች ፣የደርጎችንም ነፃ እርምጃና በኢሕአፓ ሥር ያሉት ወጣቶች የከተማ ትግል…ኢዲዩ፣ኢጫት፣መኢሶን፣አብዮታዊ ሰደድ፣ወዝሊግ ፣… የተባሉ ፓርቲዎች ሽኩቻ…ኢማሌዲህ፣እሰፓኮ፣ኢሠፓ… የአሥራ ሰባት አመት የህዝብ ድጋፍና፣ እንደ ተአምር የሚቆጠረውን የውርደት ስንብቱን ማስተዋል ብቻ የህዝብን ወቅታዊ ንቃትና በመሪዎች ሃሰብ የመጎዝን እውነት ይመሰክርልናል፡፡
         የጠበንጃ ሥልጣን የግለሰቦችን የሚያጓጓ ህይወትን ይቀይራል እንጂ በእያንዳንዱ ዜጋ ላይ አወንታዊ ለውጥ አያመጣም።ደርግ እና ባለጠበንጃው ወያኔ ያሳየን ይህንኑ እውነት ነው። ቅን፣ለእያንዳንዱ ዜጋ ዕድገትና ብልፅግ ና የወገነ ፣ ፎጋሪ ያልሆነ ፣ምድር የረገጠ ሃሳብ ነው ፣ሁላችንንም አሥማምቶ ሊያኖረን የሚችለው።ጥልቅ እውነትን የያዘ ና
ያለአድሎ  ለሰው ብልፅግና ና የወገኑ  ሃሰብ እንጂ፤ጠመንጃ ፣ጊዚያዊ ደሥታ ብቻ እንደሚያሥገኝ ከደርግ ና ከህወሓት
በቀላሉ መገንዘብ ይቻላል ።
      ደርግ ብዙ ልማታዊ ሥራ ሳይሰራ ዕድሜ ልኩን ሀገርና ድንበር እያለ ባለው ተፈጥሯዊ ባህሪ ሙጭጭ ብሎ እነደበጋ ጉም ተኗል፡፡
    ደርግ በህዝብ አልገዛም ባይነትና በቀዝቃዘው ጦርነት ማከተም (እድሜ ለጎርቫቸው ይሁንና) ሰበብ የእብድ ገላጋይ በመጥፋቱ ምክንያትም ጭምር ነው እነደ በጋ ጉም የተነነው፡፡ ከዛስ…
    ኢህአዴግ የሚባለው ገዢ በእርሱ እግር ተተካ፡፡የኢህአዴግን ወደሥልጣን መምጣት የደገፈና የተቃወመ፣ ቢኖርም አብዛኛው ህዝብ ግን ደጋፊም ተቃዋሚም አልነበረም፡፡ህዝቡ ፣ሁሉም ነገር በጥድፌያ እና በወከባ፣በላይ በላዩ ፣ድንገት እንደ ደራሽ ውሃ ሥለተከሰተበት ግራ ተጋብቶ ነበር፡፡
       ከዛስ? የብሔር ብሔረሰቦች የቋንቋ እኩልነት፣ ዴሞከራሲ ወዘተ፡፡ የሚለቱ ቋንቋ ገኖ ግን ደግሞ የቋንቋዎች እኩልነትን በማረጋገጥ በቋንቋ ሥም ክልሎች እነዲዋቀሩ በማደረግ፣ኢትዮጵያ የምትጋግረውን ኬክ ጥቂቶች ብቻቸውን  እነዲያጋብሱ ማደረጊያ በር ከፈተ፡፡ “ከኢትዮጵያዊነትም  በፊት ብሔር ይቅደም፡፡”አለ፡፡ሀገር ተከለለ፡፡ክልል ሳይበግረው በሚኖረው ዜጋ ላይ ታላቅ ውዠንብርን በመፍጠር ጥላቻን በልቡ እንዲዘራ አደረገው፡፡
      ይሁን እና ፣ የተባለው የብሔር  ብሔርብሔረሰቦች መብት በተነገረውና በተፃፈው ልክ ሊከበር ባለመቻሉና ገዢው ፓርቲ የወጣቱን የሥራ ጥያቄ በወጉ መመለስ  ሥለአቃተው ለ23 ዓመት በእፎይታ የቆየው አህአዴግ በአራቱም ማዕዘን በተቃውሞ ተናጠ፡፡
             በመጨረሻም ሰው በዓለማዊ ሥርአት አስገዳጅነት ያለእውቀት፤ እንዲሁም ዕወቀት በሚባለው መሳርያ፣በመሪነትና በተመሪነት ጎራ ቢመደብም፣የሰው
 ማህበራዊ፣  ፖለቲካዊ፣ኢኮኖሚያዊ መብቱና ሰብአዊ ክብሩ በእኩልነት እስካልተከበረለት ጊዜ ድረስ በዚች ዓለም ላይ ዘላቂ ሰላም ከቶም እንደማይኖር በሚያስተምር መልኩ እህአዴግ በረሱ ውስጥ አብዮት ተፈጥሮ፣ የቸከለው የቋንቋ ግድብ ፈርሶ፣ ሰው ሰው ብቻ እና አንዳችም ልዩነት የሌለው መሆኑ ከራሱ ውሥጥ በተገኙት በለማ መገርሳና በደ/ር አብይ አህመድ ተመሰከረና በኢህአዴግ በራሱ ካብ ውስጥ “የሰውነት፣የእኩልነት፣የፍቅር፣የመተሳሰብና የመደመር አብዮት ፈነዳ፡፡”ኢትዮጵያዊነት ሱስ መሆኑን አቶ ለማ መገርሳ አረጋገጡና የሁላችንንም አእምሮን አለሙት፡፡ በለውጡ መሪዎች ፈር ቀዳጅነትም፣የቋንቋ ፖለቲካ የአንድ ሀገር ዜጎችን ሰው መሆናቸውን አስረሥቶ እርስ በእረስ የሚያጋድላቸው መሆን እነደሌለበት በሰፊው ተሰበከ፡፡
   እያንዳንዱ የኢትዮጵያ ዜጋ እኩልና አንደኛው ከሌላው በፍፁም እነደማይበልጥና እነደማያንስም እነዲያምን እና ሲኖርም ኢትዮጵያዊ መሆኑን ሲሞትም ደግሞ ኢትዮጵያ ሆኖ ከአፈሯ ጋር እነደሚቀላቀል ተቀኘ፡፡
    የለውጥ መሪው ፣ ከኢህአዴግ ውስጥ ቢወጣም ፈጽሞ ከኢህአዴግ የተለየና በፈጣሪ እምነት ያለው በመሆኑ ይህንን ኃይማኖተኛ ህዝብ ፈፅሞ ቀየረው፡፡
            “እኔ ብቻ ልጠቀም ፡፡እኔ ብቻ ልብላ፡፡ሌላው ሰው ቢፈልግ አራት እገሩን ለምን አይበላም? የሚሉ አስተሳሰቦች በኣለም ላይ ከተንሰራፉ የዓለም ህመሞ ተባብሶ ሰው ሁሉ በፈጣን እና በሚዘገንን ሁኔታ ወደሞት መጎዙ አይቀሬ ይሆናል፡፡”በማለት  አብይ አህመድ በአብይነት  ሰበከ፡፡( በቋንቋ የተመሰረተ ክልል የሚባል የልዩነት አውድ መሰረዝ አለበት፡፡በምትኩም፣ በአፍመፍቻ ቋንቋ ሁሉም ዜጋ መጠቀሙ እነደተጠበቀ ሆኖ ሥያሜው እና የአስተዳደር ሥፈቱ ሊወሰን ይገባል፡፡በሁሉም  የሀገሪቱ ግዛቶች ሁሉም ዜጎች መኖርና ሰርተው መብላት እንዲችሉ ብቻ ሳይሆን  ፣  ” ሀገሬ ነው።” ብለው ደፍረው እንዲናገሩ ልዩነትን የሚያጎላ ሥያሜ መቅረት ይኖርበታል፡፡ አዲሰ አበባ፣ አዳማ ፣ድሬ፣አዋሳ፣በህር ዳር፣ጎንደር ወዘተ የጋራችን ነው፡፡ እያልንና ሀበት እያፈራንበት አዋሣ፣ መቀሌ፣ጅጅጋ፤አሳይታ የኢትዮጵያዊያን ሁሉ ሀገር እንዳይሆኑ ለማድረግ በሰው ህሊና ውስጥ ጥላቻን መዝራት ተገቢ አይደለም፤ ብቻ ሳይሆን የሚኗኑረንም አይደለም፡፡ )
       ሰላማዊውንም አብዮት ለማና አብይ ከነደጉና ከነደመቀ ጋር “ሀ” ብለው ጀምረው ታሪክን ሙሉ ለሙሉ በመቀየር ኢትዮጵያ በአውነተኛ ፍትህ እንድትተዳደር በፍፁም ትህትና ህዝቡን ማገልገል እነደሚያስፈልግ ደጋግመው ተናገሩ፡፡ከኢትየጵያ እስከ አሜሪካ፡፡
   ” የመሪዎች ሥግብግብነትና አልጠግብ ባይነት ሞት መኖርን ያለመገንዘብና ለትውልድ ደንታ ቢስነት ነው ። “በማለትም ከሶርያና ከጎረቤታችን ሱማሊያና ደቡብ ሱዳን ልንማር ይገባናል ። በማለት፣ፍቅርና ይቅር ባይነት ብቻ ሳይሆን ” ሆደ ሰፊነትና አርቆ አሳቢነት በሁላችንም ልብ ውስጥ ይንገስ።” በማለትም ሰበኩ፡፡
              እርግጥ ነው፣ሥብከታቸው መሬት ጠብ የማይል ነው፡፡ “ጭካኔ የወለደው ስግብግብነት እና በዘረፋ የመበልፀግ ሩጫ ይቁም፡፡አእምሮ ያላቸው እና ነገ አፈር መሆናቸውን በቅጡ የልተገነዘቡ ሰዎች ፤ በጉልበተኝነት በአስገዳጅ ዘዴ ተጠቅመው ዘርፈው እያበለፀጉ፣ ዜጎቻቸውን በችጋር እየገደሉ ነው፡፡በኢኮኖሚ ወደኋላ የቀረው ህዝብ ግን በእነሱ ሁሉን አቀፍ ስግብግብነት በችጋር እየተቆላና በተለያዩ መሰረተዊ ፈላጎት እጥረት ተሰንጎ የመከራን ንሮ እየገፋ ነው፡፡ጥቂቶች ከሰው ይልቅ ገንዘብ እና ቅንጡ ነሮ በልጦባቸው  እንደእነስሳ ለከርሳቸው በማድላት እነሱ በቁንጣን ተጨናንቀው  ዜጋውን እያስረቡ ነው፡፡”የሚል በአውነትና በመረጃ እና በማሥረጃ ላይ የየተመሰረተ በመሆኑ የሚደገፍ ነው።፡
                ሰው በሰው በህሪ ውስጥ በማይገኝበት እና የሰውነት ፀጋውን በተገፈፈበት ሁኔታ ውስጥ ሲገኝ፣ ሚፈፅመው ድርጊት ከአራዊትነት ተርታ ያሰልፈዋል፡፡የሰውነትን ባህሪ ከሚየሳጡ ነገሮች አነዱና ዋነኛው ሰው ሰው ሆኖ ሳለ ሰውነቱን ሲረሳና ራሱን ከሌላው ሰው እጅግ የበለጠ እና አምሳያው ከሱ አነፃር የሰውነት ሥያሚ ሊሰጠው አይገባም ብሎ ሲያምን ነው፡፡ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ሂትለራዊ አስተሳሰብና አመለካከት ነው፡፡ብእርግጥ እነ እስታሊንም ሆኑ ማኦ የረሳቸውን የማምለክያ ቲዎሪ በመፈጠርና በሚቃወማቸው ዜጋ ላይ ታርጋ በመለጠፍ አያሌ ንፁሃንን ረሽነዋል፡፡መሰል ተግባረትም በየአህጉሩ በሚገኙ ሀገራት ሁሉ ተፈፅሟል፡፡የአፍሪካ ግን የተለየና ዛሬም የቀድሞዎቹ ቅኝ ገዢዎች ቀብረው በወጡት የመከፋፈል ፈንጂ ደጋግማ የምትናጥ ከእወቀት፣ከእውነትና ከማስተዋል የራቀ ህዝብ የበዛባት አህጉር  ናት።ለዚህም ነው ፣ ተደጋጋሚ የእርስ በእርስ መጠፋፋት የሚከሰትባት፡፡
         በአፍሪካ በተለይም ዛሬ በሀገራችን በኢትየጵያ የአንድ  አገር ዜጋ ክልላዊ፣ብሔራዊና አለም አቀፋዊ ባህርያት እንዳለው እየታወቀ፣ይህንን እውነት ባለመገንዘብ ብቻ ሳይሆን በእያንዳንዱ ጎሳ ውስጥ ያሉ የበቁና የነቁ ገለሰቦች ፤ ለግል ጥቅማቸው ሲሉ ብቻ በህዝብ ውስጥ መረጋጋትና የሰከነ ሰላም እነዳይኖር ሁሌም፣በዘር፣በጎሳና በክልል ሰበብ ሆዳቸውን ለመሙላት  ሲያሴሩ ይስተዋላሉ፡፡
        ለመሆኑ ክልላዊነት ምንድነወ ?ክልላዊነት የአንድ ቋንቋ ተናገሪነት፣በአንድ በተወሰነ ክልል ውሰጥ ጎልቶ በመገኘቱ በግል ሚታሰብ በህሪ ነው፡፡‹‹ትግራዊነት ፣ኦሮሞነት፣አማራነት፤ሱማሌነት፣ጉራጌነት፣ከንባታነት፣ሲዳማነት፣ወዘተ፡፡ ቀጥታ ከቋንቋ ጋር የሚገናኙ የልዩነት ገጽታዎች ናቸው፡፡(ግን በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ ሰውነትን የሚያስክዱ አይደሉም፡፡ እኔ ሰው አይደለሁም፡፡ ትግሬ ነኝ፡፡ኦሮሞነኝ፡፡አማራነኝ፡፡ሱማሌነኝ ፡፡ወዘተ፡፡ማለት ግን ያለመስተዋል ነው፡፡ሰው ሰው እንጂ ቋንቋ ፈፅሞ ሊሆን አይችልም፡፡ለኑሮ ሲሉ በአንድ ሥፍራ በብዛት ሆነው አንድ ቋንቋ በመናገራቸው ሰው አይደሉም ቋንቋ ናቻው ለማለት ፈፅሞ አንችልም፡፡ )
     ይህን የክልላዊነት ባህሪ   ብሔራዊ በህሪ ይገዛዋል፡፡  ኢትዮጵያዊነት፣አሜሪካዊነት፣ቻይናዊነት፣ራሻዊነት ወዘተ፡፡ሲሆን ገፅታው የወል ሃሰብን የያዘና የዜጎችን አበሮነትን የሚሳይ ገፅታ በመሆኑ ግለሰቦችን ሁሉ በዜግነት አንድ ማዕድ እንዲቆርሱ ያደርጋቸዋልና፡፡
             ዓላምአቀፋዊ ባህሪ  ደግሞ ፣ሰው መሆን ነው፡፡በቃ፡፡እያንዳዳችን የዓለም አካል ነን፡፡
   ታዲያ ይህ አውነት ሆኖ ሳለ በእኛ ሀገር ሰዎች በቋንቋ ሰበብ ብቻ ለምን ይገዳደላሉ?እኛ ኢትየጵያዊያን እንዲህ የሚያናቁረን፣ሰውነታችንን  እንድንዘነጋ ያደረገን በቋንቋ ላይ የተመሰረተ ግን በሁሉም በሔርና ብሔረሰቦች ውስጥ ሊተገበር የማይችል፣ ለጥቂት ገዢ መደቦች የቆመ የፖለቲካ ሥርአትና በደንብ ያለጠራው ህገመንግስታችን ሰበብ ሆኖን ነውን ?
    እርግጥነው ይህ ቋንቋን ያነገሰ ፊደራሊዝም ፣ከሱማሊያ ፣ከኦሮሚያ ከትግራይና ከአማራ ክልል በሥተቀር ሌሎች አምስት ክልሎችን ብሔራዊ አደረጃጀት እነዲኖራቸው አድርጎ ሲያበቃ፣አማርኛ የሥራ ቋንቋቸው እነዲሆን አድርጓል፡፡የሚገርመው ኢሕአዴግ(ገዢው ፓርቲ እንደ ኢሕአዴግ ሲሰበሰብ የሚወያየው እንደ ኢሕአዴግ ሆኖ ሳለ፣ከእረሱ በላይ ያለው የሕዝብ ተወካዮች ምክር ቤትም ስብሰባዎቹን በአማርኛ እያደረገ፣ለምንድነው የበዛው ኢትዮጵያዊ ለመግባባት የሚጠቀምበትን የጋራ ቋንቋውን ብሔራዊ ቋንቋ በማደረግ በሁሉም ክልሎች በኩል ደረጃ አማርኛ የሥራ ቋንቋ እንዲሆን ማደረግ ያዳገተው?
    የእንጊሊዘኛ ቋንቋ ለእንጊሊዞች ብቻ እንደልተሰጠና የአለም ቋነቋ እነደሆነ ሁሉ አማርኛ የእኛ የኢትዮጵያዊያን ቋንቋ መሆን እነዴት ያደግተዋል?
      በማስተዋል ከተመለከትን ለቋንቋቸው ማደግ ከፍተኛ ተጋድሎ ያደረጉትን አንጊሊዝ፣ ፈረሣይን እና የአረብ ሀገራትን ትተን ቻይና እና ሩሲያ ቋንቋቸውን በአለም ላይ ለማሳወቅ  የሚደርጉትን ጥረት በማደነቅ አንቆምም ነበር፡፡የእነሱና የእኛ የሚለውን ኋላ አስቀሪ አመለካከትም ከህሊናችን በመፋቅ ” በኢትዮጵያ የሚነገሩ የ84 በሔረሰቦች ቋንቋዎች በሙሉ የዜጎች ሁሉ ንብረት ናቸውልንከባከባቸውናለነልናሳድጋቸው ይገባናል።” ለምን አንልም???
     አማርኛ የአማራ ነው፡፡ትግሪኛ የትገሬ ነው፡፡ኦሮምኛ የኦሮሞ ነው፡፡ወዘተ፡፡በማለት ሰውን በቋንቋ መጥራትና መከፋፈል ከቀጠልን የቋንቋን ምንነት ያልተረዳን ብቻ ሳንሆን ከቋንቋ ጋር አብረን እንደተወለድን የምናስብ ሆነናል፡፡ይህ የተሳሳተ አስተሳሰብ ነው፡፡  ቋንቋ ስውና ሰውን ለማግባባት የተፈጠረ እንጂ ለመለያየት የተፈጠረ አይደለም፡፡…
      ለሀገራችን አስተማማኝ ደህንነት ሲባል የቋንቋ አምልኮ ከእኛ ከኢትዮጵያዊያን ፈፅሞ መወገድ ይኖርበታል፡፡ቋንቋን ማምለክና በቋንቋ መታጠር ለዚህ እጅግ በቴክኖሎጂ ለተራቀቀ ክፍለ ዘመን የተገባ አይደለም፡፡
    ጊዜ በራሱ እሽቅድምድም በሆነበት፣ ከባድ ሩጫና ተግባራዊ ክንውን በሚያስፈልገው  ዘመነ ግሎባላይዜሽን እንደምንገኝም መርሳት የለብንም ። ( እንደሰማይ የራቁን ኃያላን ሀገሮች ወገብ ጋር እንኳ  ለመደረስ ከእነሱ እጥፍ መሥራት እንደሚኖርብንም አንዘንጋ፡፡የትላንትንም  የውድቀት ታሪክ እናስታውስ፡፡)
    ቀዳማዊ ኃ/ሥላሴ “ቀኃሥ” የአገዛዝዎትን ፖሊሲ ቀይሩና እንደ እንጊሊዝ ዓይነት ፓርላማ እና የህዝብ አሥተዳደር በመፈጠር በሰላም ተከብረው ኑሩ፡፡ ቢባሉ “እንቢ! አሻፈረኝ “በማለትና “በአጥንቴ ካልገዛው ሞቼ እገኛለሁ!” ብለው በመድረቃቸው፣መጨረሻቸው አላማረም፡፡በእሳቸው ጦሥና ጥንቡሳስም የብዙ መልካም ሃሰቢዎች ህይወት ጠፋ፡፡ንፁሓን ፀረ-ዓብዮት እየተባሉ ብቻ በግፍ ተገደሉ፡፡(ደርጉ ለአብዮቱ ሲል ረሸናቸው ፡፡በወቅቱ የነበረው ወጣትና ጎልማሳም እሰየው እያለ አጨበጨበ፡፡)
             ወያኔ ሥሙን ኢሕአዴግ አሰኝቶ በዘመቻ ዋለልኝ፤ቴዎድረስና ፒሊሱማ ውልቂጡማ ግንባር ቀደምትነት ሥልጣንን በኃይል ከደርግ ሲቀማ ፣የኢትዮጵያ ህዝብ የፍትህ፣የብለፅግ ና የዴሞክራሲ ጥማቴን ያረካልኛል ብሎ አጨበጨበ፡፡(አጨበጨብን፡፡አጨበጨብኩ፡፡ ) ለማለት  ባንደፍርም፣ቢያነስ የብሔር ፖለቲካ ተጠቃሚ ያደርገኛል ብሎ ያሰበ እና ቋንቋ በደል አድርሶብኛል ብሎ የሚያምን ሁሉ በደንብ ማጭብጨቡን እኛ ብንክድ  ኢቲቪ ይመሰክርብናል፡፡…
      ቀስ፣በቀስ ግን ኢሕአዴግ ፀረ ዴሞከራሲ እየሆነ በመምጣት “እኔ አውራ ነኝ !ሥራዬም ማስወለድ ነው፡፡” በማለት እንቅጩን በመናገሩ የነጻ ምርጫ ሃሳብ ገደል በመግባቱ የኢህአዴግ የመጀመርያው መጨረሻ ሆነ ፡፡
           ከጅምሩ ግን  ኢሕአዴግ የሚጎዝበት መንገድ ትክክል እነዳልሆነ  በወቅቱ እንደአሸን  በፈሉ መፅሔቶች እና ጋዜጦች ላይ ይገለጽ ነበር፡፡ በነዚህ መጽሔቶች አማካኝነት ፓርቲው የሚጎዝበት መንገድ ሀገርና ህዝብን የማይጠቅም እነደሆነ፣በተባ እና በበሳል ብዕራቸው የተቹ፣እንደ የዓለም ሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን ቀዌሳ(ሀሁ-ፐፑ የተሰኘውን ትያትር ያስተውሷል፡፡)፣አሰፋ ጫቦ፣አበርሃም ያዬ፤ሐሰን ኡመር አብደላ፣ መራራ ጉዲና በሥማቸው፡፡በብዕር ስም ደግሞ እነ ጎሞራው፣ፀጋዬ ገ/መድህን አርአያ፣ሥንሻው ተገኘ፣ ወዘተ፡፡የኢሕአዴግን መንገድ በተደጋጋሚ በመተቸት፣ ለኢትዮጵያ የማየበጅና ተሪክና ባሃልን ብቻ ሳይሆን የአካባቢውንም ሆነ የዓለምን ሁኔታ ያላገነዘበ ነው፡፡በማለት ተችተዋል፡፡ ወንዝ የማያሻገር አስተሳሰብንና አመለካከትን የሙጥኛ ማለቱን በተደጋጋሚ  ገልፀው እነደነበር እናስታውሳለን፡፡
      የዓለምን የፖለቲካ ሁኔታ በተጨባጭ ያለመረዳትና በዓለም ላይ ከሚካሄደው ለውጥ ጋር አበሮ ያለመጎዝ የሚየስከትለው መዘዝ ብርቱ መሆኑን ዛሬ በኢህአዴግ ፓርቲ  መሀፀን ውስጥ ተረግዞ የተወለደው የአብዮት መሪ፣በመገንዘብ  ይቅርታና ፍቅር ሰውን ሁሉ ወደ አንድነትና መተሳሰብ ያመጣል ብሎ በማመን የረሳነውን ፍቅርና ይቅር ባይነትን በልባችን እንዲሰርፅ በማድረጉ በሀገራችን በጎ ለውጥ እየታየ ነው፡፣
    ግን ፣ግን በግለሰቦች ግትርነትና አርቆ ያለማሰብ የተነሳ ዛሬም በሀገራችን የበዙ ችገሮች ሊቀረፉ እንዳልቻሉና ይዘናቸው እየተጓዝን መሆኑን መዘንጋት የለብንም፡፡ከዚህ አንፃር ድግሞ ይህንን ሚያሳዝን እና እጅግ የሚያጓጓ የፍቅር የእኩልነት ፣የዴሞክራሲ፣የፈትህ፣የእውነት፣የበርሃን ፣የአንድነትና የመደመር ሃሰብን ይዞ ሚመራንን ሰው፣ጠ/ሚ ዶ/ር አብይ አህመድን በቅንነትና በታማኝነት ልንደግፈው ይገባናል፡ብብዬአምናለሁ።
      መሪነቱን  አሜን ብሎ የተቀበለው እና ሙሉ ድጋፉን የሰጠው አብዛኛው ኢትዮጵያዊ  ልብ ውስጥ የተከለው የታላቅ ሀገር ህልም እውን እንዲሆንም ቅንና ቀና ነገር አሳቢ መሆን ይጠበቅብናል፡፡  በለውጥ አራማጁ ኃይል ፊት የተደቀነ ከባድ ችገር መኖሩንም መገንዘብና ማወቅ ጠንቆይ አያሰኝምና፣ችግሩን  ለማሶገድ ከጠ/ሚ ዶ/ር/ አብይ አህመድ ጎን እንቁም።(ሿሿ ይሰራናል ብዬ አላሥብም)
          በኢህአዴግ  በራሱ ውስጥ ያለው  ችግር በራሱ ቀላል ባይሆንም የሀገራችን ችግር ሥር የሰደደና ከ150 እና ከ200  ዓመት በፊት የተፈጸሙትን የሚካትት የብዙ አሉታዊ ሃሳቦችን እና የጥላቻ መርዞችን በውስጡ ያጎረ ነው፡፡ ይህንን ተውልድ የማይመለከቱ የዘር ማንዘር በደሎችን ያካተተ ነው፡፡(ዛሬ ላይ የሥንቱ ዘር ከስንቱ ጋራ መደበላለቁን ስንቶቻችን ይሆን የምናውቀው?) ይሁኑ እንጂ አብዛኛዎቹ የዚህ ጉዳይ አቅንቃኞች ዛሬን በዛሬ መነፅር እንጂ ከመቶ አመት በፊት በተሰራ መነፅር አጥርቶ ማየት እንደማይቻል አንገነዘብም ና ከዚህ አወዳሚ ችግር ፈጣሪነት ለመውጣት አቅቷቸዋል፡፡
         ሥንቶቻችን ነን ግትርነት የቀኃሥን(የቀዳማዊ ኃይለሥላሴን)  ዓይነት ዋጋ እንደሚያስከፍል የምንገነዘበው? እድሜ ለለውጥ አራማጆቹ፣ለአቶ ለማ፣ ለዶ/ር አብይና ለጓደኞቻቸው እንበል እንጂ እጣ ፈንታችን ከቀኃሥም የከፋ ይሆን ነበር፡፡ይህንን እውነት በመገንዘብ ዛሬም በማይረባ እና ለህዝብ በማይበጅና ፋይዳ ቢስ ሃሰብ ዙርዬ እየተነተረክን ጊዜችንን ማጥፋት ብናቆምና ህዝብን በሚጠቅመው ፣ሰሰውውወ በሚሸት ሥራ ላይ ብናተኩር ለትውልዳችን ይበጃል።
     ሥለቋንቋም መግባቢያነት በቅጡ በመገንዘብና ቢያንስ  ከአፍሪካዊያን  ወንድሞቻችን በመማር የእኔ፣የእኔ ከማለት የኢትዮጵያዊያን ቋንቋ ሁሉ የእኛም ነው በማለት 84ንም ቋንቋዎች እንደራሳችን ቋንቋ በመቁጠር ለሁሉም ቋንቋ ክብር በመስጠት አሁን ሁላችንም የምንነጋገርበትን ወይም አብላጫው ህዝብ የሚግባበትን እንደራሳችን ቋንቋ በመቀበል ሀገራችንን በዓለም ፊት የራስዋ ፊደልና ቋንቋ ያላት ጥንታዊ ሀገር መሆንዋን እናስመስክር፡፡ለሆድ ሞችነትና ተላላኪነቱ ይብቃን፡፡
   ለምንድነው አንዳአንድ አፍካዊያን ወድሞቻችን ኬንያን ጨምሮ፣ከራሰቸው ሀገር ህዝብ ቋንቋ ውጪ የባእዳንን ቋንቋ ፈረሳይኛና እንግሊዘኛን የሥራ ቋንቋ ያደረጉት?ለምንስ በዚህ ሰበብ የእርስ በእርስ ግጭት አለተፈጠረም?ለምንስ የእኛ ብሔረሰብ ቋንቋ ፣ለምን የስራ ቋንቋ አለሆንም? በማለት ሞተን እንገኛለን አላሉም? ይህንን ጥያቄ ከመለስን በእኛ ቋንቋ እጅግ ኩረት እንጂ ሀፍረት አይሰማንም፡፡
      በዚች ሀገር ከቶም የማይጠቅም ቋንቋ ተኮር “ጉነጭ አልፋ ክርክር” ማከተም ይኖርበታል፡፡አንድ ብሔራዊ ቋንቋ እንደሚያስፈልገን  ግን ኢትዮጵያዊያን  ሁሉ የጋራ መግባባት ላይ መድረስ ይኖርብናል፡፡ይህም ብሔራዊ ቋንቋ አማርኛ እንደሆነ በግሌ አምናለሁ፡፡ምክንያቱም በሀገራችን ከጠረፍ እሰከ ጠረፍ የአማርኛ ቋንቋ ከመነገሩም በላይ የብዙዎቹ የክልል መንግስታት ቋንቋ አማርኛ በመሆኑ አማርኛን ብሔራዊ ቋንቋ ማደረግ እና የስራ ቋንቋዎቹን ግን በተጨማሪነት ተዳብለው እነዲሰሩ ማደረግ የወቅቱን የቋንቋ ውዥንብር በመፍታት ግጭቶችን ያስቀራል ብዬ ሥለማስብ ነው፡፡
          “በዘህ ወቀት፣ጊዜና ሰዓት፣አንድ ትልቅ የለውጥ ሃሳብ በሀገራችን ተወልዷል‹‹በዚህ የህዝብ ትልቅ ሃሳብ ልዕልና ሰንል አሮጌውንና የማያራምደንን ሃሰብ ከህሊናችን አውጥተን ልንቀብረው ይገባናል፡፡ያ የምንቀብረው ሃሳብ በዛ ዘመን ትልቅ እና ሁላችንንም የዘመርንልነት ቢሆን እንከዋ ለዛሬ የማይጠቅምና ዛሬችንን ብቻ ሳይሆን ነጋችንንም የሚያጨልምብን ከሆነ ለመቅበር ማወላወል የለብንም፡፡የታላላቆቹን መንገስታት ታሪክ ተመልከቱ፡፡ወደታሪክ አዙሪት ያልገቡትና ሁልጊዜም አዳዲስ እና የሚወደስ ታሪክን እየፃፉ የሄዱት ብዙሃኑ የሚጠቀምበትን ቋንቋም ሆነ መልካም ሃሳብ የራሰቸው በማደረግ ነው፡፡
         ቻይናን፣ሩሲያን፤ኩባን በአንድ ወገን፤ኢጣሊያንን፣እንጊሊዝን፣ፈረሳይን፣ጀርመንን በሌላ ወገን አደርጋችሁ ስታበቁ አሜሪካንና እስራኤልን ደግሞ በጋራ ተመልከቱ፡፡ለትውልድ የሚተላለፍ ሥራ የሰሩት እጅግ በሚያስደንቅ የአንድነት እና የህበረት መነፈስ ነው፡፡ለዛሬ ሥኬት የበቁት የታላቅ ሀገር ሥሜት እነዲኖራቸው ባደረጉ ታላላቅ መሪዎቻቸውም ጭምር  ነው፡፡በታላላቅ መሪዎቻቸው አርቆ አሳቢነትና የመሪነት ጥበብ መጥፎ ጅምራቸው በመጥፎነት አልቀጠለም፡፡…
    የአፍሪካ የታሪክ “ሰነድ ሲሰጣ” በውስጡ እጅግ “አሳዛኝ ጉዳጉድ” ይዞ እናገኘዋለን፡፡አብዛኛው ግን የቅኝ ገዢዎች ታሪክ ነው፡፡ ያ ያለፈና በዚህ በ21ኛው መ/ከ/ዘ ተነስቶ የሚያወዘግበንም አይደለም፡፡ታሪኩ  ሲነበብም የራሱ ትልቅ የታሪክ ጉድፍ ያለውና በቅጡ ያልተጠና ቅኝ ገዢዎችም ለቀጣይ ሥራቸው ያመቻመቹትን እኩይ ሃሰብ በውስጡ ደብቆ የያዘ ነው፡፡ አውነትንም ያለነገሰ እና ” በቅኝ ገዢዎች እርሾ የተቦካ ” የዘረኝነት አስተሳሰብ፣ እንዲሁም በአድርባይ የታሪክ ፀሐፍያን ብዕር የሰከረ ህሊና የቀመረው አደገኛ መርዝ ነው፡፡  በአጭር አማርኛ፡፡
   እረግጥ ነው፤ ሁሉም ነገር ባለበት አይቆምም፡፡ሰውም ሆነ ህይወት ያለው ነገር ሁሉ በለውጥ ሂደት ያልፋል፡፡ሰው የፈጠረውም ቴክኖሎጂ በየጊዜው እየዘመነ ይሄዳል፡፡ሁሉም የፖለቲካ ዓይነቶች በየጊዜው ይለዋወጣሉ፡፡ምንም ነገር ባለበት አይቆምም፡፡ የዓለምን ፖለቲካ ዛሬ ላይ ሆነን፣በቅኝ ግዛትና በቀዝቃዘው ጦርነት ፖለቲካ አይን ለማየት መሞከር ፣በጭቃ በተለወሰ መስታወት የራስን ፊት እንደማየት ይቆጠርብናል፡፡ግን፣ግን ሳይረፍድብን ወደቀልባችን በመመለስ ይህንን በጭቃ የተለወሰ የታሪክ መስታወት በማፅዳት መጪው ትውልድ (የልጅ ልጆቻችን) የሚኮሩበትና በፍቅር፣በመከባበር፣በአንድነት እጅ ለእጅ ተሳስረው ወደብልፅግና የሚጎዙበትን መንገድ መጥረግ ለትውልዳችን የበጀል፡፡
    ትውልዳችን ያጎናፀፍነውን ብልጽግና በማድነቅ ለዘላለም እያወደሰ እሱም ከእኛ  የተሸለች ሀገር ሀገሩ እነደትሆንለት እኛን በክብር እያታወሰ የሚጥርበትን የቅንነት ታላቅ የፍቅር ፣የቅንነት፣የመከባበር፣የትህትናና የአርቆ ሃሳቢነት ድልድይ እጅለእጅ ተያይዘን ለመገንባት ቃል እንግባ፡፡
   እንጂነር ሥመኝ በቀለ እንደሞተ ሁሉ  እኛም ሞት አይቀርልንም፡፡ሞት የሰው ሁሉ የማይቀር ፅዋ ነው፡፡በፊታችን ሁሌም የተቀመጠ፡፡አንድቀን ሳናስበው የምነጨልጠው ፅዋ ነው፡፡ይህንን ፅዋ ቀናችን ደርሶም ሆኖ ሳይደርስ በድንገት ከመጨለጣችን በፊት ግን፣ዛሬ ቆም ብለን እነደናስብ የሚያደርግ አጋጣሚ ተፈጥሮልናል፡፡በዚህ መልካም አጋጣሚ በመጠቀም ለተውልድ የሚተላለፍ መልካም ሥራ እንሥራ፡፡እኛ ኢትዮጵያዊያን ጠንክረን በመስራት ወደጥንቱ መተባበራችን ካልተመለስን በአለም ፊት ሞገስ ያለን ህዝቦች መሆናችንን እነደገና ማስመስከር አንችልም፡፡
    የፈጣሪያችንን ዐይን በእነጨት እንዳንወጋው የሰጠንን መልካም አጋጣሚና ፍቃዱን እንጠቀም፡፡በእውን ፈጣሪአችን ከዚህ በላይ ምን ያድረግልን?አሜሪካ ድረስ ሄዶ በጠላቶቻችን ፊት ራሳችንን በዘይቱ ቀባን፡፤እንባችንንም አበሰለን፡፡ሰው መሆናችንንም አሳወቀን፡፡ከእንግዲህ እኛ ኢትዮጵያዊያን ዘር፣ቀለም፣ጎሳና ኃይማኖት ሳንል ለፍቅር ተገዝተን ፣ፍትህ፣እኩልነት፣ዴሞክራሲ እና ብልፅግና ተሟልተው የሚገኙባትን ሀገር በጋራ እንገንባ፡፡ፈጣሪ ኢትዮጵያንና ህዝቧን ይባርክ፡፡
ተጨማሪ ያንብቡ:  ሰላም ጦርነትን ሲያሸንፍ፣ የደቡብ አፍሪካው ስምምነት፣ ይዘቱ፣ ተፈጻሚነቱና ተግዳሮቶቹ - ባይሳ ዋቅ-ወያ
Share