ከጌታቸው ስሜ
ቴዲ አፍሮ የሚነያሳቸው የኢትዮጵያዊነት ወይም የተለያየ ማህበረሰብ በፍቅር እንዲተሳሰር የሚያነሳሱ መልዕክቶች፤ የኢህአዴግ ባለስልጣናትን ለምን ያስደነግጣቸዋል? ለምን እንዲጠሉት ያደርጋቸዋል? የሚለው መሰረታዊ ጥያቄ ነው፡፡
ቴዲ አፍሮ አልበም ባወጣ ቁጥር የገዢው ፓርቲ መሪዎች፤ ተከታዮችና ደጋፊዎች ለምን ይንጨረጨራሉ? ጥላቻቻውን ለከት በለቀቀ ወይ ስነ ምግባር በጎደለው መንገድ ያንፀባርቃሉ፡፡ ግለሰብ የፓርቲው ደጋፎዎችና አባላት ስሜት በፓርቲው ቱባ መሪዎች በተለይ በህወሃት ደጋፊዎች ዘንድ ሲንፀባረቅ ይታያል፡፡
ይህንን ጥያቄ ሚዛናዊ ሆኜ ለማየት ሞክሬያለሁ፡፡ ነገር ግን የቴዲ አፍሮ በኢህአዴግ እይታ እንደ አንድ ስርዓቱን እንደሚገዳደር ተደርጎ መታየቱ፤ የስርዓቱን በመንግስት ቁመና ያለማሰቡን ያሳየናል፡፡ ከአንድ ለአገር የሚቆረቆር ድምፃዊ ጋር እንደ አንድ ጠላት (potential threat) ፍትጊያ ውስጥ መገባቱ፤ ገዥው ፓርቲ ድምፃዊው ለሚያነሳቸው መሰረታዊ የማህበራዊ ፍትህ ጥያቄዎች መልስ ለመስጠት አቅም እንደሌለው ያሳያል፡፡
የራሴን እይታ ልስጥ፡፡ ኢህአዴግ ኢትዮጵያዊነት የሚያስበረግገው ከሆነ በራሱ ድርጊት ኢትዮጵያን እንደማይፈልጋት ማሳያ ነው፡፡ አንድነትና ፍቅር ወይም ተከባብሮ መኖር የሚያስበረግገው ከሆነ፤ ማህበረሰቦች ወይም የተለያየ ባህልና እምነት ያላቸው በፍቅር እንዲኖሩ አይፈልግም፡፡ ምክንያቱም ይህንን የሚሻ ፓርቲ ይህንን ልዕልና የሚሰብክ ድምፃዊ ካለጠፋሁ ብሎ ሌት ተቀን አይብሰከሰክም፡፡
ደጋፊዎቹ አንደ ግለሰብ የሚያንፀባርቁት ጥላቻ አደገኛ ቢሆንም፤ እንተወው ቢባል አንኳ፤ የፓርቲው አባላት ግን የሚያሳዩት ጥላቻ እንደ መንግስት አያስቡም የሚለውን ማረጋገጫ ይሰጣል፡፡ እንደ መንግስት ቢያስቡ፤ በኢቲቪ የተቀረፀ የቴዲ አፍሮ ቃለ – መጠይቅ እንደ አንድ ፓርቲውን ለአደጋ የሚዳርግ ተደርጎ አንዳይሰራጭ እገዳ ባልተደረገ ነበር፡፡ በኢህአዴግ አሰራር ደግሞ አንዳችም ነገር የፓርቲው ቁንጮ መሪዎች ሳያቁት የሚከናወን ነገር የለም፡፡ ስለዚህ እገዳው የአንድ የቴሌቪዥን ጣቢያ ስራ አስኪያጅ ውሳኔ ብቻ ተደርጎ መወሰድ የለበትም፡፡ የፓርቲው መሪዎች ውሳኔ በቀጥታ አለበት፡፡
ለዚህም ነው፤ ፓርቲው ቴዲ አፍሮን ልክ እንደ አንድ ስርዓቱን የሚያፈርስ ግዙፍ አደጋ አድርጎ የሚያየው፡፡ ድምፃዊው የሚያስተላልፋቸው መልዕክቶች በስርዓቱ አራማጆች ዘንድ ‹‹ለስልጣናችን አደጋ ናው›› ብለው ከማሰብ የመነጨ ነው፡፡
እስቲ አንድ ቅን አእምሮ ያለው ዜጋ ኢትዮጵያ ሁሉም ማህበረሰቦች ተከባብረው በእኩልነትና በልዮነት አንድነት እንዲኖሩ የሚሰብክን ድምፃዊ በጥላቻና የስርዓቱ አደጋ አድርጎ ማየት፤ ግፋ ሲልም አንዲሰናከልና እንዲሸማቀቅ መተብተብ ምን ይባላል፡
ሼህ መንደፈር፤ ጃህ ያስተሰርያል፤ ሃብ ዳህላክ፤ ኢትዮጵያ …. ሌሎችም የቴዲ አፍሮ ዘፈኖች የስርዓቱ መሪዎችና ደጋፊዎች ቢቻል የህዝብ ድምፅና እንጉርጎሮዎች መሆናቸውን አውቀው ልብ ሊገዙባቸው እንዲችሉ የማድረግ ሃይል ነበራቸው፡፡ አልተጠቀሙበትም፡፡
ድምፅዊው የማህበረሰቡን የኃላ፣ አሁንና የወደፊት ቀለም የማየት ሃይል አለው፡፡ የተሰራንበትን ማህበረሰባዊ ፈትል (social engineering) ልቅም አድርጎ አውቆታል፡፡
ድምፃዊው በዘፈኑ የሚያንፀባረቃቸው አርቆ ላስተዋለም ህገ መንግስቱ መግቢያ ላይ አንድ የኢኮኖሚና የፓለቲካ ማህበረሰብ ለመፍጠር… የሚለውን በጥልቀት የሚገልፅ ነው፡፡ አንድ የፖለቲካና የኢኮኖሚ ማህበረሰብ የሚኖረው ወደ አንድ ማህበረሰባዊና ኢኮኖሚያዊ የጋራ ተጠቃሚነትና አንድ የጋራ ማዕከላዊ አስተሳሰብ ሲኖር ነው፡፡ አሁን የሚሰራው ከዚህ ተቃራኒ ነው፡፡