የኢትዮጵያ ማነቆዎች

ኢትዮጵያ በቀላሉ ሊቀረፉ በማይችሉ ሁለት አጣብቂኝዎች ውስጥ ገብታለች። ኢትዮጵያ በአንድነቷ፣ በጀግንነቷና በበርካታ ታሪካዊ ክስተቶችና ሁነታዎች የምትታወቅ ቢሆንም የአሁኑ ትውልድ ግን በሁለት ከባድ ፈተናወች/አጣብቂኝዎች/ ውስጥ ገብቶ አንዱን ክንፉና አንዱን እግር እንደተሰበረ አሞራ መብረርም መጓዝም አቅቶት ሲቃትት ይታያል። እነዚህ ማነቆዎች ሰብረን መውጣት ከአልቻልን ነገና ከነገ በኋላ ኢትዮጵያዊ ነኝ ብሎ በአንደበቱ የሚመሰክር ትውልድ እንደሚጠፋ ምንም ጥርጥር የለውም ከእዚህም አልፎ ኢትዮጵያ በኢትዮጵነቷ የመቀጠሏ እጣ ፈንታ አስቸጋሪ እንደሚሆን ነብይነት የሚሻ ጉዳይ አይመስለኝም።

ኢትዮጵያን ኢትዮጵያ ሊያሰኛት የሚችለው እምነቷ፣ ባህሏ፣ አንድነቷ በአጠቃላይ ከእነሙሉ ታሪኳ ስትኖርና ወደፊትም ስትጓዝ ብቻ ነው። ከዚህ በአለፈ ግን አዲስ ኢትዮጵያ እንጂ አባቶቻችን ደማቸውን አፍሰው፣ አጥንታቸውን ከስክሰው ሰንደቃላማዋን የአውለበለቡላት ያቺ ታሪካዊዋ ኢትዮጵያ አትሆንም። ዛሬ ላይ ያለነው ትውልድ ግን ይችን አገር አባቶቻችን በአስረከቡን መልክ ሳይሆን እየኖርንባት ያለነው አዲስ ገፅና አዲስ መልክ ሰጠን አገራዊ ወኔ ጠፍቶብንና ኢትዮጵያዊ ማንነታችንን አጥተን የምራቡን ባህል ተከትለን ልንወድቅ በመንገዳገድ ላይ እንገኛለን። “ተቀምጠው የሰቀሉት ቁሞ ለማዉረድ ያስቸግራል” እንደሚባለው ዛሬ ላይ ዝም ብለን ያየነው ነገር ነገ ለማስተካከልም ሆነ ለአገሩ የሚያስብ ዜጋ ለማግኘት በጣም አስቸጋሪ ነው የሚሆነው። ምንም እንኳ ይህ ችግር የሚያሳስባቸው እና  እንቅልፍ የሚነሳቸው በርካታ እውነተኛ የኢትዮጵያ ልጆች በተዋበ ስነ ጽህፋዊ አጻጻፍና ከመረጃ ጋር የጻፉ ቢኖሩም እኔም እንደ አንድ ኢትዮጵያዊ ችግሩ ስለሚመለከተኝና ስላሳሰበኝ እነዚህ ለኢትዮጵያ ከባድ ማነቆዎችን እና መፍትሔዎችንም ለመጠቆም ወደድኩ።

እነዚህ ሁለት ማነቆዎች ብዬ በርዕሴ ላይ ያስቀመጥኳቸው ዘረኝነትና ግሎባላይዜሽን/Globalization/ ዓለም አቀፍ ትስስር ናቸው። እንዲሁ ከላይ ስንመለከታቸው ብዙም ፈታኝና አስቸጋሪ ላይመስሉን ይችሉ ይሆናል። ነገር ግን በጥልቀትና በስፋት ከአየናቸው በጣም አስቸጋሪና አሳሳቢ ጉዳዮች እየሆኑ ከመጡ ዘመናትን አስቆጠሩ።

1.    ግሎባላይዜሽን/Golobalization/

የነገ አገር ተረካቢ የምንለው ትውልድ በዘረኝነት የቀረውም በግሎባላይዜሽን ውስጥ ገብቶ ለኢትዮጵያዊነት የማይጨነቅ፣ የማይገደውና የማያስብ የኢትዮጵያንም ታርክ ማወቅ የማይፈልግ ትውልድ እየሆነ ከመጣ ዘመናትን አስቆጠረ። በእርግጥ ግሎባልይዜሽን በጥበብና በማስተዋል መቀበልና መተግበር ቢቻል ለአገር እድገት በር ይከፍታል እንጂ ጉዳቱ ባልጎላ ነበር ምንም እንኳ ኃያላን አገሮች የራሳቸው  የሆነ ውስጣዊ ትልዕኮ ቢኖራቸውም፤ ዳሩ ግን እኛ በትክክለኛ ዓላማው ሳይሆን በሌላ በኩል እየተጓዝን ስለሆነ ነው አስቸጋሪ እና ማነቆ ብዬ ከዘረኝነት ጎን ማስቀመጥ የፈለኩት። ኃያላን አገሮች ዓለምን እየመሩና በእነርሱ ስር ለማድረግ ይመቻቸው ዘንድ ትናትና በቅኝ ግዛት የራሳቸውን ባህልና እምነት በግድና በግፍ ለማስፋፋት እንደሞከሩት ሁሉ ዛሬ ደግሞ በዘመናዊ መልክ ግሎባላይዜሽን ብለው የእነርሱን ባህልና እምነት በውዴታ እንድንቀበለው እያደረጉን ይገኛሉ። እኛ ኢትዮጵያውያን ደግሞ የራሳችን የሚያኮራ ባህል፣ እምነትና ታሪክ ያለን እንጂ ከሌላ የምንዋስበት ምንም ምክንያት የለንም። በነገራችን ላይ የአደጉ አገሮችን ብንመለከት በእድገት ደረጃቸው ሁሉ ባህላቸውን፣ታሪካቸውንና ቋንቋቸውን ጨምረው ነው ያደጉት እንጂ የእነሱን በመተው በሌላ ባህልና ታሪክ አይደለም ያደጉት።በእርግጥ ዛሬ ዛሬ የአደጉ አገሮች በደመ ነፍስ ብቻ የሚንቀሳቀስ ትውልድ በመገንባት ውድድር ላይ ናቸው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንደተለመደው ይወርፏቸዋል፤ እንደራሴዎቹ ግን በሳቅ ያጅቧቸዋል - ከመርሐጽድቅ መኮንን አባይነህ

ዛሬ የኢትዮጵያ ወጣት ስለ ምዕራቡ ዓለም የሚያውቀውን ሩብ ያክል ስለ ኢትዮጵያ አያውቅም። የሌላ አገር ታሪክ ማወቁ ባልከፋ  ነበር ግን የራሳችንን ታሪክና ባህል መናቅና ማንቋሸሽ ከየት የተማርነው ታሪክ ነው፣ ወደየትስ እየተጓዝን ነው? የትስ ለመድረስ ነው? ባህልና ታሪክ የሌላትን አገር ለመመስረት? የትናት አኩሪ ታርኳን ረስተን ሌላ ኢትዮጵያ ለመመስረት? የመከባበረ፣የመቻቻል፣ የመረዳዳት፣ አብሮ የመብላት ባህሏን ረስተን ሌላ የማናውቀንና የምዕራባውያንን ባህል ለማሳደግ? ግሎባላይዜሽን እንዲህ ከሆነ ባህልን፣ ታሪክን፣ እምነትንና ቋንቋችንን የሚደበላልቅብን ከሆነ ባናድግ ቢቀርብን ይሻለናል። “ጎመን በጤና” ይላል ያገሬ ሰው እውነት ነው ያገኙትን በሰላም፣ በፍቅርና በጤና እየበሉ የአገርን ባህልና ታሪክ እየጠበቁ መኖር ታላቅ ጀግንነት ነው። ታሪክ ነውና አይረሳም ትናት መንግስት ሳይቀር ግብረ ሰዶምን ለማስፋፋትና ለማበረታታት የውጭ አገር ግብር ሰዶማውያንን እንዲዎያዩና እንዲመካከሩ ኢትዮጵያን ባርኮ  ሰጣቸው፡፡ በእርግጥ አይደንቅም ትውልዱ የምዕራብያውያንን ባህል ቢናፍቅ ምክንያቱም መንግስት በኢትዮጵያ ባህል ፈጽሞ የማይታሰበውን ድርጊት እንዲወያዩባት አገራችንን ከፈቀደ። ለዚህ ትውልድ መጥፋት ተጠያቂው ማነው? ምናልባት በዋናናት ተጠያቂ የምናደርገው አንድ አካል ልንል እንችላለን ነገር ግን ሁላችንም በትንሹም ቢሆን ከተጠያቂነት አናመልጥም። ምክንያቱም በቀጥታም ሆነ በተዘዋዋሪ፤ በአንድም ሆነ በሌላ መንገድ ለችግሩ መባባስ አስትዋጾ እያደረግን ስለሆነ። የአገር ሃላፊነትን ለመወጣት በትንሹም ቢሆን ይህን ትውልድ ባገኘነው አጋጣሚ ኢትዮጵዊነቱን እንዳይለቅ ማስተማርና ማስረዳት እንዲሁም ዘመናዊነትን በትክክል ከባህላችን ጋር አስተሳስሮ አብሮ እንዲያስኬደው  ትውልዱን የማስረዳት ሂደት ከእያንዳንዳችን የሚጠበቅ ታላቅ ተግባር ነው።

2. ዘረኝነት

መቼም ስለ አንድነት ለኢትዮጵያ ህዝብ መናገር ለቀባሪ ማርዳት እንዳይሆንብኝ እፈራለው። ሁላችንም እንደምናውቀው አንድነት ማለት መለያየት፣ መከፋፈልና መጠቋቆም የሌለበት ህብረት፤ እንዲሁም ለአገርና ለወገን እድገትና ብልፅግና በጋራ መስራት ማለት ነው። ዘመናዊና አገር ተረካቢው ትውልድ ግን እየተጓዘ  ያለው ከዚህ ፈጽሞ ተቃራኒና በተለየ አካሔድ ነው። ዛሬ አዲሱ ትውልድ እንደ ኢትዮጵያነታችን ሳይሆን እያሰብን፣ እየሰራን ያለነው፤ በብሔር፣ በዘር፣ በጎሳ፣ በሃይማኖትና በቋንቋ ፍጹም ተለያይተን እንደ አንድ አገር ህዝብ ማሰብና መናገር ተስኖናል። ይህ አካሄድ ደግሞ በዚሁ ከቀጠለና ችግሩን ከወዲሁ መፍታትና ማስቆም ካልቻልን ለአገራችን ኢትዮጵያ እጅግ አስቸጋሪና መድኃኒት የሌለው በሽታ እንደሚሆን ዛሬ ላይ የምናያቸው ነገሮች ከበቂ በላይ ማስረጃዎች ናቸው። ለአገራችን ማነቆ ብዬ ርዕስ የሰጠሁበት ምክንያትም ይህን ጠባብ አመለካከታችንን በቀላሉ ትተን ወደ ቀደመ አንድነታችን ለመመለስ እጅግ ከፍተኛ ዋጋ የሚጠይቅ በመሆኑ ነው። ጎሳዊና አካባቢያዊ ስሜታችንን ትተን ወደ አገራዊ ስሜት ከአልተሸጋገርን፣ መለያየትን ትተን አንድነትን ከአልሰበክን፣ መጠቋቆርና መተቻቸትን ትተን መተራረምንና መረዳዳትን ባህል ከአላደረግን፣ በቋንቋ በዘርና በሃይማኖት መለያየትንና መከፋፈልን ትተን ለአገር እድገትና ብልጽግና ህብረት መፍጠር ከአልቻልን በቀላሉ የወጋን እሾህ በቀላሉ አይነቀልም። ይባስ ብሎ እያመነቀዘ አካለ ጎደሎ ሊያደርገን ይችላል እንጂ። ስለዚህ ከወዲሁ ከምንም በላይ ትኩረት በመስጠት ሃይ ልንለው የሚገባ ተግባር ነው ባይ ነኝ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ተባሿል - አስቻለው ከበደ አበበ

ይህ የዘረኝነት በሽታ በጣም አሳሳቢና አስከፊ መሆኑን የምንረዳው የነገ አገር ተረካቢ ትውልድ የእውቀት ባለቤት ሁኖ ይወጣበታል ተብሎ በሚታሰብበት በከፍተኛ የትምህርት ተቋማት ሳይቀር በዚህ የዘረኝነት መንፈስ መጠቃቱ ነው። ተማርዎች ብቻ ሳይሆን መምህራንም ሳይቀሩ በዚህ በሽታ መለከፋቸው ችግሩን ይበልጥ ትኩረት እድንሰጠው አመላካች ነገሮች ናቸው። በሚገርም ሁኔታ ግን የአልተማረው የህብረተሰብ ክፍል የዚህ ችግር ተጠቂ አይደለም ብሎ መናገር ይቻላል፤ እዚህ ላይ ግን ሁሉም የተማረው ክፍል የዘረኝነት መንፈስ አለበት እያልኩ እንዳልሆነ ይታወቅልኝ። እንዳው ብዙ አወራህ እንዳትሉኝ እንጂ ዛሬ ኢትዮጵያ ውስጥ ያሉ ከፍተኛ ት/ት ተቋማት ለዘረኝነት መንፈስ መስፋፋት ትልቅ አስትዋጾ እያደረጉ ነው ቢባል ማጋነን አይሆንም። አንድ የከፍተኛ ት/ት ተቋም ተማሪ የሚያጠናውን የት/ት መስክ ጨርሶ በሚመረቅበት ወቅት በዘረኝነት መንፈስም አብሮ  ጎን ለጎን እንደሚመረቅ ተማሪዎች ከተመረቁ በኋላ የሚያሳያቸው እንቅስቃሴዎች ማስረጃዎች ናቸው። ስለዚህ መንግስትም ሆነ/የትኛውን መንግሥት እንዳትሉኝ እንጂ/ ሁላችንም ጉዳዩ ለአገር በጣም አደገኛ ስለሆነ በከፍተኛ ት/ት ተቋማት ላይ ልዩ  ትኩረት በመስጠት የዘረኝነት መንፈስ ሊቀንስ የሚችልበትን ሁኔታ ማየቱና አስፈላጊ የሆነ ጥናት መደረግ አለበት የሚል አቋም አለኝ።

እንዲሁም ለአገራችን ኢትዮጵያ በማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ፖለቲካዊ ፋይዳ ይኖረዋል ተብሎ የሚጠበቀው በውጭ የሚኖሩ ትውልደ ኢትዮጵያዋን ከአገር ውስጥ በከፋና በባሰ ሁኔታ በዘረኝነት በሽታ በክፉ ተጎድተዋል። በዚህ በውጭው ዓለም እናተ እና እኛ እያሉ የሚያወሩ የዘረኝነትን በሽታ በወረርሽኝ መልክ የሚያስፋፉ ብዙዎች እንዳሉ በተለያየ መልክ ከማገኛቸው ሰዎች ተመልክቻለው፤ ስምን እና የሚያወራውን ቋንቋ ከሰሙ በኋላ እነሱ ከሚፈልጉት ወገን ከአልሆነ ፊታቸው የሚጠቁርና ደስቶኞች የማይሆኑም በቁጥር ጥቂቶች አይደሉም። ግን እስከ መቼ በዚህ መልኩ እንቀጥላለን? የሚለው ጥያቄ መልስ ባላገኝም የዘወትር ጥያቄዬ ነው።

እጅግ የሚገርመው ደግሞ ሃገር እመራለሁ እያለ ያለው ‘መንግሥታችን’ የብሔር እኩልነት እያለ ሲያዎራ ትንሽ አለማፈሩ ነው። በእውነት ሁሉም ብሔሮች በመንግሥት በኩል እኩል ናቸው??? እንደ እኔ ግን የብሔር እኩልነት ተብሎ  ከሚወራ “የብሔር ልዩነት ተረጋግጧል” ተብሎ ቢወራ ሥራቸውን በሚገባ ይገልጠዋል ብየ አስባለሁ። ትናት እና ከትናት በስተያ በይፋ የተፈጸመው የብሔረ አማራ ከቦታቸውና ከአገራቸው መፈናቀል ዘረኝነቱ ምን ያክል ጎልቶ  እንደወጣ ጥሩ ማሳያ ነው። እንግዲ እኛም ዘረኝነቱ ያለብን ሰዎች የመንግሥት ዋና አስፈጻሚ አካላት መሆናችንን መገንዘብ ይኖርብናል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ያለ ዴሞክራሲያዊ አርበኝነት  ዴሞክራሲያዊ ድል አይታሰብም! - ጠገናው ጎሹ

አንድ ያጋጠመኝን ገጠመኝ ላውራችሁ። በስደት የምኖርበት አካባቢ ከዋናው ከተማ ትንሽ ወጣ ይላል፤ ለዋናው ከተማ አዲስ ነኝ ማለት እችላለው። በትራንስፖርት ምክንያት አልፌበታለው እንጂ ብዙ አላውቀውም። አንድ ቀን ከምኖርበት ከተማ ወደ ዋናው ከተማ ለግል ጉዳይ ሄድኩኝና አውቶብስ ተራ/ buss station/ አካባቢ ሰው እየጠበኩ ቁሚያለው፤ አበሻ ማየት በዛን ስዓት ለእኔ ብርቅ ሁኖብኛል ምንም እንኳ በመልክ አበሻ የሚመስል ሰው ባይም አይኑን ወደ እኔ የሚያዞር ማንም አልነበረም። እኔም የአገሬን አውቶብስ ተራ እያሰብኩ እስካሁን እዛ ብሆን ኑሮ የስንት ሰው አይን ያርፍብኝ ነበር እያልኩ በትዝታ አገር ቤት ገብቻለው። በዚህ ሁኔታ እያለው አንድ በእድሜ ሸምገል የአሉ ሰውዬ ከርቀት አየሁኝ። አበሻ ለመሆናቸው ከቁመና እስከ መልካቸው ይናገራል።  እኔም እንደማነኛውም ሰው ዝም ብለው ያልፋሉ ብዬ ብዙም ትኩረት አልሰጠዋቸውም ነበር፤ እርሳቸው ግን ያ የናፈቀኝን የአበሻ ፈገግታ ከቅርብ እርቀት ቸሩኝ እኔም በደስታ የፈገግታውን አፃፋ ጋበዝኳቸው። እርሳቸውም ወደኔ ጠጋ አሉና የመጀመሪያውን ማንኛውም ሰው የሚጠይቀውን ጥያቄ “አበሻ ነህ” ብለው ጠየቁኝ። እኔም ኢትዮጵያዊ አክብሮት የተሞላበት ሰላምታ ለመስጠት እየተዘጋጀው በፈገግታ አዎ ብዬ መለስኩላቸው። ጥያቄያቸው አሁንም አላቆመም “ኤርትራዊ ነህ ኢትዮጵያዊ” አሉኝ እኔም ኢትዮጵያዊ በማለት በአጭር መለስኩላቸው። ሦስተኛውና እጅግ የገረመኝንና ያልጠበኩትን ጥያቄ ቀጠሉ “ምንድነህ አሉኝ” ጥያቄአቸው ግራ አጋባኝና  ጥያቄ በሚመስል አነጋገር አቤት አልኳቸው እርሳቸውም ትግሬ ነህ አማራ ወይስ ኦሮሞ አሉኝ። እጅግ በጣም ደነገጥኩኝ እኔ ከእርሳቸ ስጠብቅ የነበረው ለአገሩና ለከተማው እንግዳ መሆኔን ተረድተው ምን ልርዳህ? ኑሮ እንዴት ነው? የሚል ጥያቄ ስለነበረ የእርሳቸውን ጥያቄ በስዓቱ ለመመለስ ቃላት አጠረኝ። ከብዙ ዝምታ በኋላ “ኢትዮጵያዊ  መሆኔ በቂ አይሆንም” ብዬ ስመልስላቸው በመጀመሪያ ያሳዩኝን ፈገግታ ደግመው ሳያሳዩኝና ሰላም ዋል የሚል የስንብት ድምፅ ሳያሰሙ መንገዳቸውን ቀጠሉ እኔም እዛው ለተወሰነ ጊዜ በሃሳብ ተክዤ ለምን ይህን ጥያቄ ጠየቁኝ ብዬ እራሴን ጠየኩት መልስ ግን ማግኘት አልቻልኩም። አሁን ላይ ግን እርሳቸውንም የዘረኝነቱ መንፈስ በእጅጉ እንደጎዳቸው ተረዳው። እናተ ብትሆኑ ምን ትሏቸው ነበር?

ይህ ነው እንግዲህ የኢትዮጵያ የእድገት ደረጃ፤ ህጻን፣ ወጣት፣ ትልቅ፣ አዛውንት፣ ተማሪ፣ ሙህር ሳይቀር በዘረኝነት መንፈስ መመታት። ታዲያ ይህ ለኢትዮጵ አገራችን ከማነቆም በላይ ማነቆ አይሆንባትም ትላላችሁ? ከወዲሁ መፍትሔ ማፈላለጉ ጊዜ የማይሰጠው ጉዳይ መሆኑን ተረድተን በበሽታው የተጠቁትን ህክምና፤ ያልተጠቁትን ደግሞ  የመከላከል ስራ ለመስራት ቆርጠን መነሳት ይኖርብናል።

 

 

 

 

 

 

2 Comments

  1. ትንታኔዎ ጥሩ ነው። ግን ግሎባላይዜሽን እና ዘረኝነትን በአንድ ላይ መከላከል የሚቻል አይመስለኝም። ከሁለት አንዱን መቀበል ግድ ይላል። ግሎባላይዜሽን በአማራው ህዝብ ላይ ዘርፈ ብዙ ቀውስ በማስከተል ላይ ስለሚገኝ አጥብቀን ልንከላከለው የሚገባ ጉዳይ ነው። ሆኖም አለማቀፋዊ ትስስርን እንከላከል እስካልን ድረስ ድረስ ድንበር አበጅተን ዘረኝነትን ተቀበልን ማለት ነው። ጥያቄው ድንበሩ የቱጋ ነው የሚል ብቻ ነው። በአፍሪካ ደረጃ ሊሆን አይችልም እኛ አማሮች የሀበሻ ዘር እንጂ አፍሪቃውያን አይደለንምና። በኢትዮጲያ ደረጃም ሊሆን አይችልመ፣. ኢትዮጲያ እያንዳንዳቸው እጅግ ብዙ ህዝብ ያለቸው ብዙ ህዝቦች ያሉባት ሀገር ነችና፣ እያንዳንዱ ህዝብ ደግሞ የራሱ የሆነ ቋንቋና ባህል ባለቤት ነው። ስለዚህ እያንዳንዱ ሰው የራሱን ታሪክ ባህልና ቋንቋ እንደማንነቱ መገለጫ ቢወስድ ፍፁም ጤናማ የሆነ አስተሰሰብ ነው። ጤናማ ሆኖ የማይታየኝ አብዛኛው አማራ በራሱ ማንነት የሚያፍር ይመስል ዘሬን አትጠይቁኝ ዘሬ ኢትዮጲያዊነት ነው የሚለው ነገር ነው።

    በተረፈ የዘር ልዩነታችን ብዙ አያስጨንቅህ መስማማት ካልችልን መለያት እንችላለን። በኦሮሞና በአማራ መካከል በትብብር ላይ የተመሰረተ ግንኙነት መፍጠር ቀላል ነው፣ ስነልቦአነችን በጣም ስለሚቀራረብ። የሚያስፈልገው ኦሮሞ ማለት ከሌሎች የሚለየው ቋንቋ ባህልና ታሪከ (በአጠቃላይ ማንነት) እንዳለው መቀበል ብቻ ነው። በአማራና በትግሪያኖች መካከል ካሁን በሁዋላ ህብረት መፍጠር ግን በጣም ከባድ ነው። ለኛም ለነሱም የሚበጀን አትድረሱብኝ አልደርስባችሁም ብለን በሰላም መለያት ብቻ ነው። ስልጣን ከጨበጡበት ጊዜ አንስቶ ሲፈፅሙብን የኖሩትን ግፍ ምንጊዜም አንረሳውምና።

    • what the hell u talking about we all ethiopian are African and most of all Black in race. are u saying habesha is not african like the egyptian say they r not african ha…

Comments are closed.

Share