የአማራ ሕዝብን በማንነት ማጥቃቱ ጦርነት ባልነበረበት ወቅትም ያልተቋረጠ ወንጀል ሆኖ ኗሯል። ከወለጋ፣ ከሸገር ከተማና ከአዲስ አበባ በጅምላ ተፈናቅሏል። በከተሞች ሳይቀር ቤቱ እየፈረሱ ተባርሯል። አማራው በማንነቱ እየተጠቃበት ያለውን ሁኔታ በምክር ቤት የተመሰከረ ጉዳይ ነው።
የአዲስ አበባ ምክር ቤት አባሉ ዶክተር ካሳ ተሻገር ከመታሰሩ በፊት በነበረ የምክር ቤት ስብሰባ በአስር ሺህ የሚቆጠሩ አማራዎች በገፍ መታሰራቸውን በምክር ቤት ተናግሯል።
በተመሳሳይ አቶ ገዱ አንዳርጋቸው በፓርላማ ባደረገው ንግግር የኦሮሞን ህዝብ በአማራ ህዝብ ላይ የማነሳሳት ተግባር እየተፈፀመ መሆኑን ተናግሯል።
በመንግስት የሚተዳደረውን የኢትዮጵያ ሰብአዊ መብት ኮምሽን ጨምሮ የአገር ውስጥና የውጭ የሰብአዊ መብት ተቋማት የአማራ ተወላጆች በጅምላ እየታሰሩ መሆናቸውን አሳውቀዋል።
ጦርነቱ አማራ ክልል ላይ ሆኖ እያለ አስቸኳይ ጊዜያዊ አዋጁ ከአማራ ክልል ውጭ እንዲተገበር ተደንግጓል። ይህን ተከትሎም ቀደም ብሎ ከነበረው በከፋ የፓርላማ አባላትን የመከሰስ መብታቸው ሳይነሳ፣ ምስኪን ሰርቶ አደሮችን በማያውቁት ጉዳይ እያፈሱ ማጎሪያ ውስጥ አስገብተዋቸዋል። በርካታ የአማራ ተወላጆች ኦሮሚያ፣ በአዲስ አበባ፣ ደቡብ፣ ሲዲማ፣ አፋር ክልል ሰብአዊ ክብርን በሚነካ ሁኔታ ታስረው ይገኛሉ። ለምሳሌ ያህል ዛሬ በተቆርቋሪዎች በኩል ወጥቶ ማህበራዊ መዲያ ላይ እየተዘዋወረ የሚገኝ ምስል ገላን አካባቢ የሚገኝ ካምፕ በጅምላ የታሰሩ አማራ ተወላጆችን ሁኔታ የሚያሳይ ነው። የገላን ካምፕ አሰቃቂ ምስል ወጣ እንጅ ሌሎች ከዚህም የከፉ መኖራቸው ተሰምቷል።
የአማራ ተወላጆች በሌሎች ክልሎች ብቻ ሳይሆን ከተለያዩ የአማራ ክልል አካባቢዎች ታፍሰው በብር ሸለቆ፣ በሸዋ ሮቢት እንዲሁም በየወረዳውና በየከተማው በሚገኙ ጣቢያዎች ታስረው መከራ እየተቀበሉ ይገኛሉ። ይደበደባሉ፥ ምግብ አያገኙም።
“ማንም አይደርስልህም፤ ፋኖ ያስፈታህ፤ 4 ኪሎ ሲያምርህ ይቀራል” ወዘተ… እየተባሉ ይሰደባሉ። በምርመራ ወቅት ከፍተኛ ድብደባ ይፈጸምባቸዋል።
በሌላ በኩል የአማራ ባለሀብቶችን ገንዘብ ክፍሉና ትፈታላችሁ በማለት ገንዘብ እየተቀበሉ ነገር ግን እንኳን ሊፈቷቸው ፍርድ ቤትም አያቀርቧቸውም።
እስሩ በተጠቀሱት ቦታዎች ብቻ ሳይሆን በሐዋሳና በሌሎች የደቡብ ኢትዮጵያ አካባቢዎች እንዲሁም በቤንሻንጉል እና በአፋርም ጭምር የተከናወነ ነው።
ይህ የጅምላ እስርና ማሰቃያ ዜጎች በማንነታቸው ተለይተው የተጠቁበት፣ ነገ በማንም ላይ የሚደርስ፣ በንፁሃን ላይ እየተፈፀመ ያለን የጭካኔ ወንጀል ማንኛውም ኢትዮጵያዊ ሊታገለው የሚገባው ነው።