ለብአዴን ጉባኤ የተሰጠ ምክራዊ አስተያየት – በደሳለኝ ቢራራ

ጁላይ 20 በተካሄደ የብአዴን ስብሰባ ውስጥ ተቀረጸ የተባለውን ድምጽ ሰማሁት። እንደተለመደው ብአዴን ማቀዝቀዣ አጀንዳውን ይዞ ብቅ ብሏል። ከሁሉም ነገር አስቀድሜ ማንሳት የምፈልገው የብአዴንን ህልውና ሊያስቀጥሉ የሚችሉ ማምታቻ አጀንዳዎች ሁሉ ማለቃቸውን ነው። ከዚህ በኋላ ብአዴን የሚተርፍበት ምንም እድል የለውም። ብአዴን (የአማራ ብልጽግና) እንኳን እንደ ቡድን ስልጣን ይዞ ሊቀጥል ይቅርና፡ አመራሮቹና አባላቱም እንደ ግለሰብ የሚጋፈጡት መራር ጽዋ ከፊታችን እየመጣ ነው። ስለሆነም ባልታወቁ ታጣቂዎች በየቤታቸው ተለቅመው ከማለቃቸው በፊት፡ ቢያንስ የግለሰቦችን ህይወት ማትረፍ እንዲችሉ የመስተዳድሩን መዋቅር ለህዝባዊ ኃይሎቹ አስረክቦ ክልሉን ለቀው መጥፋት ቢችሉ መልካም ነው። ህዝባዊ ሰራዊቱ መስተዳድሩን ከተረከበ የህዝቡን ሰላም የመመለስ እና የማረጋጋት ስራ ይሰራል እንጅ ብአዴኖችን እና ቤተሰባቸውን የማሳደድ እና የመግደል ፍላጎትና ተልእኮ አይኖረውም ብየ አምናለሁ። ይህንን መነሻ ተረድተው ብአዴኖች እራሳቸውንና ቤተሰባቸውን ስለማትረፍ ሲሉ ክልሉን ለቀው ቢወጡ ይመከራል።

ከዛ ውጭ ህዝብ ይቀበላቸዋል፤ ተሰሚነት አላቸው ወይም ግማሽ ፋኖ ናቸው ተብለው ይታሰባሉ ብሎ ያመኑባቸውን ግለሰቦች፡ ስሜት ኮርኳሪ ንግግሮችንና የህዝብ ጥያቄዎችን ለምክር ቤቱ እንዲያነሱ በማድረግ፡ የፋኖውን የህልውና ትግል ለማቀዝቀዝ መሰማራት ውጤት አያመጣም። በመሰረቱ የአማራን ጥያቄዎችና በደሎቹን ለምክር ቤቱ ማቅረብ ወይም መጠየቅ ጀግንነት አይደለም። የአማራን ጥያቄዎች ለመመለስ እና ለማስፈጸም በህዝብ ምርጫ ውክልና እና ስልጣን የተሰጠው ሰው ጥያቄ ስላቀረበ የተለዬ ነገር እንዳደረ የሚታሰብ የመሰላቸው ሌሎቹ ተመራጮች በህዝቡ ላይ የሚፈጽሙትን ደባ እና ክህደት እንደ መደበኛ አሰራር ስለቆጠሩት ነው። ባይሆን ኖሮ መደበኛ የህዝብ ተወካይ ማንጸባረቅ የሚጠበቅበትን የህዝብ ነባራዊ ሁኔታ ያቀረበ ሰው እንደ ጀግና ይታያል ተብሎ አይታሰብም ነበር።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የብልጽግና ፓርቲ በገሃነም ደጃፍ ላይ እየጨፈረ ያለ ይመስላል። ይልቁንም የአስተዳደር አቋሙን ለማሻሻል አሁንም አልረፈደበትም

የሆነው ሁኖ ብአዴን የድርድር ጥሪ ለፋኖው ለማቅረብ ያኮበኮበ ይመስላል። ብቻ እንደምንም ተንጠላጥሎ ከአማራ አናት ላይ ለመቆየት የምታስችለውን አንዲት ቅንጭ ጠጉርም ብትሆን ለመጨበጥ ያለ የሌለ እየቧጠጠ ነው። ብአዴን በአማራ ህዝብ ላይ የፈጸመው እልፍ አእላፍ ክህደትና ጭፍጨፋ የተዘነጋ መስሎት ጭራሽ እራሱን የአማራ ህዝብ ተቆርቋሪ አድርጎ ተከስቷል። በራሱ ፍላጎትና ውሳኔ ሲፈጀው የኖረውን ህዝብ፡ በሌሎች የፖለቲካ አጋሮቹ ለማሳበብ “ለህዝብ ተቆርቋሪ ነን፡ በፖለቲካ አጋሮቻችን ተከድተን ነው እንጅ” የሚል ድምጸት ተንጸባርቋል። በግልጽ ቃል “ለሴራ ፖለቲካ ተጋልጠናል፡ ተከድተናል” ተብሏል። ማን እመኑልን አላቸው? የፖለቲካ እንጅ የሐይማኖት መሪ ለመሆን አልመረጥናቸው! መከዳትን ምን አመጣው? በፖለቲካ እንደአዋጭነቱ እንኳን መክዳት፡ መግደልም አገልግሎት ላይ የሚውል ስልት ነው። ሴራ፥ አሻጥር፥ ድለላ፥ ማጭበርበር፥ መዋሸት፥ መካድ፥ ማፈን፥ ማስፈራራት፥ ማማለል፥ . . . ሁሉንም መጠቀም ይቻላል። ታዲያ ፖለቲከኛ እንዴት ተከዳሁ ይላል? “ተከዳሁ” የሚባል ነገር የሚመጣው ቅድመ ሁኔታው “ማመን” ሲሆን ነው። በፖለቲካ ደግሞ ፈጽሞ ማመን የሚባል ቃል አይታወቅም። ጥናትና ክትትል፥ ምርመራ፥ እቅድ፥ ግምገማ፥ ስሌት፥ ድርድር፥ ሰጥቶ መቀበል፥ ወዘተ ናቸው የፖለቲካ መንገዶች።

ማመን የሚባል ነገር የሐይማኖት መንገድ ነው። ማመን ግቡም ጽድቅ ነው። ፖለቲከኛ ተልእኮው ስልጣን መያዝ እና በስልጣን ዘመኑ ለመፈጸም ቃል የገባቸውን ተግባራት መፈጸምና ማስፈጸም ነው። ታዲያ የብአዴኖች አላማ ‘ብጹዕ አባታችን’ መባል ነበር እንዴ? ስሌት የሚባል ነገር አያውቁም? ለነገሩ መደንዘዝ እንኳን ስሌት ስሜትም ያሳጣል። ለዚህም ነበር የአማራ ጅምላ መጨፍጨፍ ከወለጋ እስከ ማይካድራ ሲፈጸም የሀዘን መግለጫ ለመስጠት እንኳ ያላነሳሳቸው፤ ምንም ጉዳያቸው ያልነበረው። ስሜትም ስሌትም የሌላቸው በድኖች በመሆናቸውም ነው በጦርነት የወደመውን ክልል መልሶ ለማደራጀት ወደ 26 ቢሊዮን ዶላር ያስፈልጋል እየተባሉ ባለበት ወቅት የፌደራል መንግስቱ የበጀት ድልድል ሲያደርግ እንኳ ጥያቄ ለማቅረብም ወኔ ያልነበራቸው። በተቃራኒው ግን ከዛችውም ኩርማን በጀት ላይ የፌደራል መንግስቱ በትግራይ ላይ ላደረሰው ውድመት አማራ ክልል ከተሰጠው በጀት ላይ ቀንሶ ካሳ እንዲከፍል ሲጠየቁ ለመወያየት የሚቀመጡ ልፍስፍስና አድርባይ ድኩማን ናቸው። ስሜትም ስሌትም ማጣት እንደዚህ ያደርጋልና። እነዚሁ ድንዙዛን ግን የአማራውን የህልውና ትግል ስለመቀልበስ ሲዶልቱ የሚኖራቸው ብርታት የሚገርም ነው። በእርግጥ ለረጅም ዘመናት በጥናት የታወቀ እና ተለይቶ የተያዘ አማራውን ማጥቃት እና ማጥፋት የሚቻልበት ቋሚ ስትራቴጅ ስላለ ያንን መደጋገም ነው የያዙት።

ተጨማሪ ያንብቡ:  እነሆ በሀገራችን አዲስ ጎሳ መፈጠሩ ተሰማ - 'ፌስዳቢ' | ከዲ/ን ዳንኤል ክብረት

ህዝባችን ማጤንና ማረም የሚገባው እሳቤዎቸ፥ አተያዮችና መሰረታዊ የአስተሳሰብ ሽግግሮች አሉ። “ንግስና እና ቅድስና በአንድ መስመር የሚከወኑ የማህበራዊ ፖለቲካ ኑባሮዎች ናቸው” ብሎ ለሽህ ዓመታት የተቀበለና የተገበረ ህዝብ ስለሆነ፡ ከፖለቲካና ሐይማኖት መስመሮች መለያየት አልፎ መቃረናቸውንና፡ ፖለቲካው የሐይማኖት ጸር ሁኖ የበላይነትን የተጎናጸፈበትን እጥፋት እንደ ጠቃሚ የታሪክ ዱካ መከተል አለመቻል አሁን ለሚደርስበት ሰለባነት ተጋላጭ አድርጎታል።  አሁንም ህዝቡ እንደ ቀድሞው ዘመን ሁሉ ውብ ንግግር ይማርከዋል። ንግግር ሁሉ ከልብ ይመስለዋል። አንድን አካል “መሪየ” ብሎ ከተቀበለ በኋላ ይደልለኛል፥ ያጭበረብረኛል፥ ይከዳኛል ብሎ አይጨነቅም። ከመጠራጠር ይልቅ “ከመሪው በላይ ማን ለእኔ የሚያስብልኝ ሰው አለ?” ብሎ እራሱን ይሞግታል። ሐይማኖታዊ አስተምህሮውም “መጠራጠር የሰይጣን ተጽእኖ” እንደሆነ እየደጋገመ ስለሚነግረው ተጠራጣሪ ሁኖ ከሚጠቀም ይልቅ አምኖ ጉዳቱን ቢጋፈጥ የተሻለ ጽድቅና ሰማእትነት እንደሚሆን አምኖ እና ወስኖ ዝም ይላል። በዚህ ሁኔታ ህዝቡ በንግግር ውበት በደሉን ይረሳል፤ ቂሙን ይሽራል፤ ጥቅሙንም አሳልፎ ይሰጣል። ውብ ንግግርን መውደድ ብቻ አይደለም የህዝባችን ድክመት፡ ያምናልም። የማህበራዊ ህይወቱ መሰረት ሐይማኖት በመሆኑ ብዙውን ማህበራዊ መስተጋብር የሚያስኼደው ንግግርን በማመን ነው። በባህላዊ ማህበራዊ ህይወቱ ለሚከውናቸው ሁሉም መስተጋብሮች ቀጣይነት ሲል መተማመንን መሰረታዊ እሴት አድርጎ ቆይቷል። በተለይ በግብይት ላይ በየትኛውም የአማራ አካባቢ ከፍተኛ መተማመን ስላለ ደረሰኝና ሶስተኛ ወገን ወይም ዋስትና እና ተያዥ ሳያስፈልግ ነው ግዥ፥ ልውውጥ፥ እርክክብ፥ የሚከናወነው። ይህንን እሴት ወደ ፖለቲካው ማስገባት ግን ለተከታታይ ጉዳት ተጋላጭ አድርጎት ኖሯል። ዘመን ከተቆጠረ ህይወት ከተጀመረ ጀምሮ በአማራ ላይ የተፈጸሙ በደሎች በሙሉ ምክንያታቸው ንግግርን ማመን ነው። በዚህ ርዕስ ላይ እራሱን የቻለ ጥልቅ ጥናት ስላለ በቅርቡ ለንባብ ይበቃል ብዬ ተስፋ አደርጋለሁ። ሆኖም ግን የብአዴን መከዳዳት አጀንዳ ጋር ሊቆራኝና የብአዴን ከተጠያቂነት ማምለጫ ሊደረግ እንደማይችል አበክሬ ማሳሰብ እወዳለሁ። የዛሬውን የምቋጨው፡ “ብአዴን ሆይ ይልቅስ አምልጥ!” በማለት ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከብልጠት ወደ ብልህነት - እውነቱ ደሳልኝ

በደሳለኝ ቢራራ 23 ጁላይ 2023

 

https://youtu.be/uOTeRkhulQ8

1 Comment

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share