ምልከታ (ክፍል-2) ሸንቁጤ – ከካናዳ

የቅዱስ  የሲኖዶስ  አቋም  እና ጥያቄ  ፖለቲካዊ?

መቼም  የኢትዮጵያን ታሪክ በወፍ በረር   እንኳ  ለቃኘ  መንግስት እና ቤ/ክ  የነበራቸውን  የከፋም የለማም ግንኙነት እና ተፅእኖ በቀላሉ መታዘብ እንደሚቻል  ግልፅ  ነው ::  መንግስት እና ሃይማኖት የተለያዩ መሆናቸው በህገ መንግስት  አንቀፅ ተቀርፆ በተደነገገባቸው አመታት እንኳ  ህጉ ከወረቀት  አልፎ  በተግባር  ተተርጉሟል ማለት ፍፁም አዳጋች ነው::   በተለይም የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤ/ክ ካላት የአማንያን ብዛት አንፃር ” ቤ/ክ መቆጣጠር አብዛኛውን ህዝብ መቆጣጠር”  ነው በሚል እሳቤ  መንግስታት በሊቀ ጳጳሳት ሹመት  እና  በቅዱስ ሲኖዶስ  ውሳኔዎች እንዲሁም  ሁለገብ የቤተክርስቲያን ጉዳዮች ቀጥተኛ ጣልቃ ገብነት ያደርጉ የነበረ መሆኑ  ጳጳሳቱም   መንግስትን  በመደገፍም ይሁን በመቃወም  ያሳዩት የነበረው ተሳትፎ በ አደባባይ ይደርግ የነበረ በመሆኑ ለክርክር የሚቀርብ  አይደለም:: በዚህም የተነሣ  ቤ/ክ ( ቅዱስ ሲኖዶስ) የሚወስዱት እያንዳንዱ  አቋም እና እንቅስቃሴ ከፖለቲካ ይዘት አንፃር  ከመመርመር(scrutinized ከመደረግ) ተርፎ  አይታወቅም:: የነ አቶ አካለወልድን የቤተክርስቲያኗን ቀኖና  ጥሰት ተከትሎ በቅዱስ ሲኖዶሱ  በአቶ አካለወልድ ቡድን እና  በመንግስት የተወሰዱ እርምጃዎችን እያነፃፀሩ መመርመር  በርግጥም  “ቅዱስ  ሲኖዶስ  ፖለቲካዊ  ተልእኮ  እና ሚና  ነበረው  ወይ ?”  ለሚለው ጥያቄ  አመክኖአዊ ምላሽ ለመበየን  ይረዳናል::

እነ አቶ አካለወልድ

– አቶ አካለወልድ  እና ጏደኞቻቸው  ለጳጳስነት  ያጯቸውን መነኮሳት ከ ቅዱስ ሲኖዶሱ መቀመጫ ጥቂት ራቅ  ብለው  በምዕራብ ሸዋ ወሊሶ በምትገኘው  ደብር በ ኦሮሞ ነፃነት ሰራዊት (OLA) እና  የ ኦሮሚያ ልዩ ሃይል  በጋራ  ባደረጉላቸው የፀጥታ ጥበቃ እና እጀባ  ባዕለ ሲመታቸውን እና “የኦሮሚያ ና  ብሄረስቦች ሲኖዶስ ” ምስረታቸውን  አበሰሩ

ቅዱስ ሲኖዶስ

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሚታደስ ቃል ኪዳን (ከጸጋዬ ገብረ መድኅን አርአያ)

የነ አቶ አካለወልድ  ቡድን የፈፀመው ተግባር ቀኖና ቤ/ክንን ያፈረሰ በመሆኑ ከድርጊታቸው እንዲታቀቡ  እና  በአስቸኳይ የቅዱስ ስኖዶስ ስብሰባ መጥራቱን አስታወቀ::

ከቀናት በሗላ በተካሄደው የቅዱስ ሲኖዶስ ጉባኤ  አቶ አካለወልድ እና ቡድናቸው ተወግዘው  በህገወጥ መንገድ እያደረጉት ያለውን የአብያተክርስቲያናት ወረራ መንግስት ጣልቃ በመግባት እንዲያስቆም እና ህግ እንዲያስከብር ጠየቁ

መንግስት

አብይ አህመድ  ታዳሚዎቻቸውን (audience)  በቆርጦ ቀጥል  ቪዲዮ ባሳዩበት የ36 ደቂቃ ሃተታ   “እኛ ጣልቃ አንገባም”  ቢሉም በገደምዳሜው ድጋፍቸውን ለአቶ አካለ ወልድ  እንደሆነ የሚያሳብቅ    ንግግር  ይልቁንም በፓትሪያርኩ እና ጳጳሳቱ መካከል ልዩነት  የምትፈጥር እሳት ጫር  አድርገው አለፉ::

ይህን ተከትሎ  ደጋፊዎቻቸው እና ተይህ ቀደም ” የነፍጠኞች ተላላኪ” በማለት አይንህ ላፈር ብለዋቸው የነበሩ  የነፃይቱ ኦሮሚያ ደጋፊዎች  ጀምበር  እንኳ ሳትጠልቅ  የ ” አብይ ወደፊት!” ከበሮአቸውን ይዘው ተነሱ::

አብይ  የነ አቶ አካለወልድ ጥያቄ  ፍትሃዊ የመብት እና  የህዝቡ ጥያቄ እንደሆነ ለመሳል ቢሞክሩም  የደጋፊዎቻቸው የ ትዊተር ጮቤ ረገጣ እና ዘመቻ  ግን ሌላ ነበር የሚያሳብቀው-” ኦርቶ- ማራ” አበቃ  , “ጠዋት ቀዳሽ  ማታ ተኳሽ” አማራ አበቃለት  ገና ጠርገን እናስወጣችሗለን   ፋኖ ጳጳሳት እና የመሳሰሉት እንደ ሰደድ ይስፋፉ የነበሩ መልዕክቶች በርግጥም  የ አቶ አካለወልድ  ቡድን እና የመንግሥት እውነተኛ  ግብ ምንድነው ብለን ደግመን እንድንጠይቅ የሚያደርግ ነበር

ቅዱስ ሲኖዶስ የአብይ አህመድን የ36 ደቂቃ  ቀረርቶና  ፉከራ  ተከትሎ በሰጠው የመልስ መግለጫ  ለፉከራ እና  ቀረርቶው ባለመጨነቅ እና የፖለቲካውን ወጥመድ  ወደ ጎን በመተው ; ሰውዬው ላነሳቸው እያንዳንዱ ነጥቦች ቤ/ክ  ምን እንደሰራች ና  እየሰራች እንደሆነ   ፍፁም በሃይማኖታዊ ህግ እና ስርዓት እና ቤ/ክ ስራዎች ላይ ብቻ ያተኮረ ምሉዕ የሆነ ምላሽ ሰጠ::

ተጨማሪ ያንብቡ:  አማራ፦ ህልውናህ ያለው በአንተው መዳፍ ውስጥ ነው (እውነቱ ቢሆን)

አቶ አካለወልድ እና ቡድናቸው  በመንግሥት እና ሌሎች ታጣቂ  ሃይሎች  እንዲሁም የኦርቶዶክስ ተዋህዶ  እምነት ተከታይ  በሆኑም  ባልሆኑም  ነገር ግን አጋጣሚውን እንደ አንድ ፖለቲካዊ ግብ  መዳረሻ በወሰዱ  ደጋፊዎቻቸው በመታገዝ የተለያዩ አብያተ ክርስቲያናትን መቆጣጠር መጀራቸው ይህንኑ ለመከላከል በሞከሩ ምዕምናን እና ቀሳውስት ላይ የታጠቁ የመንግስቱ ህገ አስከባሪ አካላት የወሰዱት አሰቃቂ ግድያ  ድብደባ እስር እና ወከባ በድጋሚ  በርግጥም  የመንግስትን  ፖለቲካዊ ድጋፍና ጣልቃ ገብነት  ያረጋገጠ ሆነ:: ይልቁንም እንደሻሸመኔ ባሉ ከተሞች  የመንግስት ታጣቂዎች  በደቦ  ከሚንቀሳቀሱ ቡድኖች ጋር በመሰናሰል  በምዕመናን ላይ  ያደረሱት ጅምላ ግድያ እና ድብደባ  ከጥያቄም   አልፎ ቁጣን የቀሰቀሰ ነበር::

ቅዱስ ሲኖዶሱ ይህን ተከትሎ በወሰደው አቋም የ ፀሎተ ምዕላ እና ሰላማዊ ሰልፍ መጥራቱ   ፖለቲካዊ አቅጣጫ ሊይዝ ይችላል የሚል ስጋት የነበረ ቢሆንም  አባቶች ግልፅ በሆነ ቋንቋ  በዝርዝር ለምዕመኑ ባስተላለፉት መመሪያዎች  የፀሎተ ምዕላውም ሆነ ሰላማዊ ሰልፉ የቤ/ክንን ህልውና በመታደግ ላይ ብቻ እንዲያተኩር አፅንዖት ሰጥተው ባስተላለፏቸው  መመሪያዎች  በብልሃት መንግስት ሲቋምጥለት የነበረውን የንቅናቄውን አቅጣጫ ለውጥ በማምከን ረገድ ከፍተኛ ሚና ነበረው:: ሲንተከተክ የነበረው የምዕመኑ ቁጣ ገንፍሎ ወደ አደባባይ እንዳይፈስ  ህዝቡን ፊቱን ወደ ቤ/ክ እና ፀሎቱ ብቻ እንዲያተኩር በማረቅ ሊከሰት ይችል የነበረውን አስከፊ ግጭት በብልሃት ለመቆጣጠር  ችለዋል:: በተለይም ደግሞ ከቤተ ክርስትያን በኩል ይሰጡ የነበሩ መረጃዎችን መግለጫዎችን እና መመሪያዎችን  በዋናነት መቆጣጠር መቻላቸው ምዕመኑም በ ቅዱስ  ሲኖዶሱ ላይ ባሳደረው ከፍተኛ እምነት ቅድሚያ ከአባቶች የሚመጡ ትዕዛዛትን ብቻ ለመቀበል መወሰኑ ሊከሰቱ ይችሉ ለነበሩ ውዥንብሮች ስንጥር  ቀዳዳ ሊሰጥ ባለመፍቀዱ  ምክንያት አብይ አስቦት የነበረው “መንግስቴን ሊገለብጡ ነበር” ትርክት መና ሊቀር ችሏል::

ተጨማሪ ያንብቡ:  አምናና ዘንድሮ - ነፃነት ዘለቀ

ውጥረቱ ን ለማርገብ በሽምግልና ወደ አብይ እና ሽመልስ ዘንድ ሄደዋል ከተባሉ ታዋቂ ግለሰቦች ተሰምቷል እንደተባለው ከሆነ  ከሁለቱ ግለሰቦች የተሰማው እብሪት እና ድንፋታ በርግጥም እነ አቶ አካለወልድ በፌድራል  እና ክልል መንግስታት አማካይነት የተሰጣቸውን ፖለቲካዊ አጀንዳ ለማስፈፀም የተንቀሳቀሱ ነበሩ ብሎ ለመደምደም ያስደፍራል::

በአንፃሩ  ቅዱስ ሲኖዶስ   የመረጃ ፍሰትን በአግባቡ በመቆጣጠር  አላስፈላጊ ውዥንብሮችን ማስቀረት መቻሉ የምዕምናኑን 100% አመኔታ በማግኘት ግልፅ እና ያልተምታታ የአመራር ሰጪነት ሚና መጫወቱ ከሲኖዶስ ያፈነገጠው ቡድን ያነገበው የፖለቲካ ተልእኮ በግላጭ እየታየ  እና  ከሀገሪቱ ከፍተኛ መንግስት አካላት ሙሉ ድጋፍ እየተቸረው እንኳ    በስሜት  ከሚነዳ አፀፋዊ የፖለቲካ ምላሽ በመቆጠብ በሁለቱ አካላት መካከል ያለውን የተልዕኮ ልዩነት  በጉልህ እንዲታይ በማድረጉ(የአቶ አካለ ወልድ እና  የመንግስትን ተልእኮ እርቃኑን አስጥቶታል ማለት ይቻላል) ፍፁም ሰላማዊ በሆነ መንገድ ለ3 ቀናት በተካሄደው  ፀሎተ ምህላ ለሃይማኖቱ ቀናኢ የሆነ ምን ያህል ምዕመን ከጀርባው እንዳሰለፈ በማሳየቱ   መንግስት ሊወስድ  ካሰበው ቤ/ክርስትያንን ” እንደገና ጠፍጥፎ ” ከመስራት ፕሮጀክቱ  ቆም ብሎ እንዲያስብ እና ወደ ” የጠፉትን በጎች ይዞ ወደ ብፁእ አባታችን መመለስን”  ለጊዜውም ቢሆን እንዲዞር ተደርጓል::

http://amharic-zehabesha.com/archives/179915

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share