June 6, 2022
5 mins read

በደቡብ ክልል ዘጠኝ ሰዎች በድንጋይና በዱላ ተወግረው ተገደሉ

286546426 5653506268015756 1477953705239891843 n

286546426 5653506268015756 1477953705239891843 n

በደቡብ ክልል ቡርጂ ልዩ ወረዳ ዘጠኝ ሰዎች በድንጋይና በዱላ ተወግረው ተገደሉ ፡፡ ግድያው ከትናንት በስቲያ ቅዳሜ የተፈጸመው በልዩ ወረዳው ሶያማ ከተማ በሚገኝ የገበያ ሥፍራ ላይ ነው ፡፡ የዶቼ ቬለ DW ታማኝ ምንጮች እንዳረጋገጡት ከሟቾቹ በተጨማሪ ሃያ አንድ ሰዎች ጉዳት ደርሶባቸዋል፡፡

ሟቾቹ ከኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ጉጂ ዞን በመነሳት ሶያማ ተብሎ በሚጠራው የደቡብ ክልል ቡርጂ ልዩ ወረዳው ከተማ ለገበያ የመጡ የኦሮሞ ጉጂ ብሄር ተወላጆች ናቸው ተብሏል፡፡ በሥፍራው ነበርን ያሉ የአይን እማኞች ለዶቼ ቬለ DW እንዳሉት ግድያው በሰዎቹ ላይ የተፈጸመው ራቅ ባለ የገጠር ቀበሌ አንድ የኦሮሞ ጉጂ ብሄር አባል የቡርጂን ሰው ገድሏል የሚል ወሬ በገበያው ውስጥ ከተሠራጨ በኋላ ነው፡፡

ከጥቃቱ ለጥቂት ማምለጡን የሚናገረው አንድ የአካባቢ ነዋሪ በሶያማው የገበያ ሥፍራ ተመለከትኩ ያለውን ለዶቼ ቬሌ DW ሲገልጽ ‹‹ በገበያ መሀል እያለን አንድ የቡርጂ ሰው በኦሮሞ ጉጂ ብሄር ተገለደ የሚል ወሬ በገበያ ውስጥ ተናፈሰ ፡፡ ወዲያውኑ በገበያው አካባቢ የነበሩ ወጣቶች በመሰባሰብ ‹‹ የእኛን ሰው እየገደላችሁ ከእናንተ ጋር እንገበያይም ›› በማለት የጀመሩት ረብሻ ወደ ግድያ ተሸጋገረ፡፡ በገበያ ውስጥ የተገደሉት ሱሮ ባርጉዳ ከሚባል የኦሮሚያ ወረዳ ዕቃ ለመሸጥና ለመግዛት የመጡ የኦሮሞ ጉጂ ብሄር ተወላጆች ናቸው ፡፡ የተገደሉትም በድንጋይ ተወግረው ፣ እንዲሁም በዱላና በሸንኮራ አገዳ ተቀጥቅጠው ነው ፡፡ አብዛኞቹ ወደ ፖሊስ ጣቢያ ግቢ ሸሽተው ባይጠለሉ ኖሮ ከዚህ የበለጠ ሰው ሊጎዳ ይችል ነበር ፡፡ እኛም ለጥቂት ነው ሮጠን ያመለጥነው ›› ብሏል፡፡

በደቡብ ክልል የቡርጂ ልዩ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪ አቶ ማሬ አለማየሁ በልዩ ወረዳው ጥቃት መፈጸሙን ለዶቼ ቬሌ DW አረጋግጠዋል፡፡ አንድ የኦሮሞ ጉጂ ብሄር አባል የቡርጂን ሰው ገሏል የሚለው ወሬ በገበያው መሀል መሠራጨቱ ለግድያው መነሻ ሰበብ መሆኑንም ዋና አስተዳዳሪው ተናግረዋል፡፡ በጥቃቱ ዘጠኝ ሰዎች ሲገደሉ ሌሎች ሃያ አንድ ሰዎች ተጎድተው እየታከሙ መሆኑን ዋና አስተዳዳሪው ገልጸዋል፡፡

በጥቃቱ የተገደሉት ሰዎች የኦሮሚያ ክልል ምዕራብ ጉጂ ዞን ሱሮ ባርጉዳ ከተባለው ወረዳ ወደ ደቡብ ክልል ቡርጂ ልዩ ወረዳ ለገበያ የሄዱ ሰዎች መሆናቸውን የሱሮ ባርጉዳ ወረዳ ሰላም ፀጥታ ጽህፈት ቤት አስታውቋል፡፡ የጽህፈት ቤቱ ሃላፊ አቶ ቡልቡላ ጅኦ በዕለቱ በአጎራባች የቡርጂ ልዩ ወረዳ ድንበር ላይ እሳቸው ሽፍታ ሲሉ የጠሩት የሸኔ ቡድን አንድ የቡርጂ ተወላጅን መግደሉን ለዶቼ ቬሌ DW ተናግረዋል፡፡ ይህም በሶያማ ከተማ በመገበያየት ላይ በነበሩ ሰዎች ላይ ያልተጠበቀ ጥቃት እንዲፈጸም ምክንያት ሆኗል ብለዋል፡፡

አሁን የደረሰው ጥቃት ተባብሶ እንዳይቀጥል በቅንጅት እየተሠራ ይገኛል ያሉት የቡርጂ ልዩ ወረዳ ዋና አስተዳዳሪው አቶ ማሬ አለማየሁ የድርጊቱን ፈጻሚዎች ለሕግ የማቅረብ ሥራዎች መጀመራቸውን ተናግረዋል፡፡ በአሁኑ ወቅት የጥቃቱ ቀንደኛ ታሳታፊ የሆኑ ሰዎች እየተለዩ መሆኑን የተናገሩት ዋና አስተዳዳሪው እስከአሁንም አሥር ተጠርጣሪዎች በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን ዋና አስተዳዳሪው መናገራቸውን ሸዋንግዛው ወጋየሁ ከሀዋሳ ዘግቧል።

DW

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Abiy Ahmed Liar
Previous Story

የተካደ ትውልድ (በእውቀቱ ስዩም)

285512406 600237591667500 4216980738470886439 n
Next Story

የፋኖ ም/ሻለቃ አዛዥ ሹመት አምባቸውን ጨምሮ ሁለት ሰላማዊ ነዋሪዎች በጎንደር ዙሪያ ተገደሉ!!

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop