ለይቶና አቅዶ የገጨንን ዘር ጨፍጫፊ ሾፌር ለቀው ተሽከርካሪውን (የነጂውን) እንዴት እንክሰሰው? – ወንድእጥር መኮነን 

ለክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር

ማሳሰቢያ- ጽሁፍ ከምሰራው ስራም ከመስሪያቤቴ አቋም ጋርም አይያያዝም!! – ወንድእጥር መኮነን

የሰሜን እዝ ጭዳነት ዝንጋኤ ይገባዋልን? ሞረሽ ለሃገሬ ብለው ለተሰዉት ጀግኖች አጽም ፍትሃት እንጂ ዳግማዊ ግፉዕነት ልኬታቸው ነውን? በአሸባሪዎች ሴሰኝነትና ወራዳነት ብቻ ሳይሆን ማህጸናቸው በቢለዋቸውም ጭምር የተደፈረ ሴቶች (ህጻናትና መነኩሴዎች) ፍትህ እንጂ ሃፍረት ይፈረድላቸዋልን? በዘራቸው ምክኒያት መታዎቂያ እየታየ የተጨፈጨፉ ንጹሃን ደም አሁንም በራማ ሲጮህ ጆሮ ይነሳዋልን አይሰማዎት ይሆን? ሽብርተኞቹን ከአይጥ ጎሪያቸው ፈልፍለው ሲያወጡ የተሰውት ሃገር ጠባቂዎች ጠበቃ ይነፈጋቸዋልን? ከሁሉም በላይ ሃገር ከድተው ብቻ ሳይሆን ወግተው ያደሙ የዘር አጥፊ ሾተላዮችን ማርን የሚሉት የትኛውን ያልደማ የኢትዮጵያ መሬት እየረገጡ እንዲራመዱበት ነው? በእውኑ አይደለም ነጻነት የማረሚያቤት ቅጥርና አፈር እንኳን አይጠየፋቸውምን?

እነዚህን የገዛ ሃገራቸውንና ህዝባቸውን ወግተው የሚያስወጉ #የእፉኝት_ልጆች ምህረት ከተገባቸው የእስር ቤት ቅጥሮች ውስጥ ማን ሊታጠር ፍትህም ርትዕም ይሆናል? የንጹሃንን ህልውና በደም የለዎሱ አሸባሪዎች ይቅርታ ከተገባቸውና፣ ይህ ፍትህ ሆኖም ህላዌያቸው በጥፋት ሞተረኞቹ ቅርቃር ውስጥ የገባባቸው ህዝቦችና ሃገርን ህልውና የማስከበር ቁልፍ #በባለስልጣን_ፊርማ ከተዋጀ እርስዎ ፈተው የለቀቋቸው ሊቀ-ሽብራን በዘር ጥላቻቸው አስክረው እየነዱ ያመጧቸውን ሽብር የተቀለቡ ተሽከርካሪዎች በጦር ሜዳ አውዶች መደምሰሳችን እንዴት የፍትህና የርትእ ሚዛን እንደ ተከሳሽ እንጂ እንደ ባለድል ሊሰፍረን ይችላል?

በየአትሮኑሱ የሚያንቆለጳጵሷትን ንጽሂት ኢትዮጵያን ከባንዳዎችና ከአሸባሪዎች የጭካኔ ድርና ሸማ ገፈው ያዳኑ ጀግና የነጻነት ቀንዲሎች አንጸባራቂ ኢትዮጵያዊነት አይንዎትን አይቆጠቁጥዎትም ወይ?

ክቡር ጠቅላይ ሚኒስትር፥ ይህንን ጽሁፍ ከመጻፌ በፊት ልቤን ከሰበረው የትናንትና ሰበር ዜናዎት ውጪ የየትኛውንም ሚዲያም ማህበራዊ አንቂም ጽሁፍ አላነበብኩም ነገር ግን #ጥፋት_በጥፋት_አይጸዳም_ይብስ_ይበሰብስ_እንጂ የሚለውን ያሳደገኝ ኩሩ ህዝብ ብሂል ልዕልና በጥያቄ እንድጻረር ሰቅዞ ይዞኛል! በመንበርዎት ይዜዎታለሁ ይህን ይመልሱልኝ? #የእባብ_መርዙ ከ*ጡ መሆኑን ሳይዘነጉ የሽብር ቡድኑን ከኋላ የሚዘውሩ ያሏቸውንና ለሃገርጠባቂ እርድ ያዘዙ የዘርማጥፋትና የስይጥንና ሊቃውንቱን ደብረ ጽዮን፥ ጌታቸው ረዳን፥ ጻድቃን የሚለው ግብር ፍጹም የማይገባውን #ሃጣኢ እንዲሁም ከታዳሽነት ይልቅ #ወራዳነቱ የጎላውን ወዲ ወረደና ሌሎችን በኢትዮጵያዊነት ስንይዝስ ፍትህ እንደሚቀጣቸው ምን ዋስ አለን?

ተጨማሪ ያንብቡ:  አንድ ነጥብ ስለመንግሥትና የሲቪል ማሕበረሰብ ድርጅቶች - አንድነት ይበልጣል ከሐዋሳ

ይህን የተውት እሺ የነሱ የጥፋት ተሽከርካሪ የነበሩትና የአማራ ክልል አዲስ መዋቅር ገና ከመሰሪዎቹ ጉምቱ የሴራ ትብትብ እንኳ ሊፎካከር ሳይችል፣ የበደሉት ኢትዮጵያን ሆኖ ሳለ እርስዎ ዝም በማለትዎ የአማራ ክልል በ2010 ለሰሩት ወንጀል የህግ ሚዛኑን ጠብቆ በእስር የቀጣቸው አነ #በረከስት_ስምዖን የነ ስብሃት ጨፍጫፊነት ደቀ መዝሙር ቢሆኑም እንኳን ስብሃት ተፈቶ ደቀ መዝሙሮቹ የእስር ቤት ቅጥር ላይ ሊቆዩ ይገባልን? #አህያውን_ፈቶ_ዳውላውን_ማሰር አይደለም ይላሉ? ልክ ሹፌሩን ለቆ ተዘዋሪውን የካቴና ሲሳይ እንደማድረግ? በህወሃት ዘዋሪነት ንጹሃንን የሶማሌ ወንድምና እህቶቻችንን ከመግደል አልፎ ከጅብ እባብ አይጥና ጉንዳን ጋር ያሰረው አብዲ ኢሌ ግፍ ከነአቦይ ስብሃት አራጅነት ይስተካከላል የሚሉ ከሆነ ልኬታዎት የሚዛን ልምሻ ላይ አልጣለዎትምን?

በዘር ማጥፋት የተከሰሱ የደም ቁማርተኞችን ይቅር ማለት ፍትህ ቢመስልዎ ህዝብን እንደ ህዝብ ኢትዮጵያን እንደ ባዕድ ያደሙ የጥላቻ ጣሪያ ላይ የሚቆምሩ አሸባሪዎች ፈትቶ ራስዎት “ኮሎኔል መንግስቱ በ1983 በውጪ ሴራን ተንኮል እንጂ ፈልገው ከሃገር እንዳልዎጡ ገባኝ” ያሉላቸውን ሰው በዘር ማጥፋት ያውም እርስዎ በተደጋጋሚ ባመኑት በወያኔ ስንኩል ህግ ተፈርዶባቸው (እዚህ ላይ የደርግን አገዛዝ ግፎች ዘንግቼ ሳይሆን ከዎያኔ ልዕለ ጭካኔ ስይጥንናና ገዳይነት ቢያንስንጂ አይበልጥም ብየ ስለምምን መሆኑን ተረዱኝ )ይቅር ማለትና ምህረት ማድረግ እንዴት እነ ስብሃትን ማርኩ ከሚለው በኔ እምነት #ጥዩፍ_እሳቤ ሚዛን አጣብዎት?

በሂዎቴ ከሰራኋቸው ስራዎች የንጹሃንን ጭፍጨፋ ማጋለጤና ሲገድሉ ሁሉ ቪዲዮ እየቀረጹ አማራውን ገድለው አማራው ጨፈጨፈን ለማለት ሲሰናዱ በቦታውና ከነ ማስረጃው ማጋለጤ ቢሆንም አሁን የዚህ ሴራ ማሃንዲሶች ይቅር ተባሉ ወይም ተማሩ ስባል ምነው የነዛ ንጹህ አማራዎችን አንደበት #ምጽዓት_በሰበር_መጥቶ በከፈተልኝና ድምጻቸው በተሰማ የሚል የተፈጥሮ ጥርሰትን እመኛለሁ። (ይህ ውስጠ ሙግቴ በሶማሌም በአፋርም በአዲስ አበባ በኦሮሚያም በደቡብም በቤኒሻንጉልም በሃረሪም በሲዳማም በጋምቤላም በአሸባሪዎች ክፋት በንጽህነት #ደመከልብ_የሆኑትንም_ማለቴ_ነው )

ተጨማሪ ያንብቡ:  ይድረስ ለኢሳት፣ ለኦኤምኤን እና ለሕወሓት በያላችሁበት – ምሕረቱ ዘገዬ (አዲስ አበባ)

ጥያቄየ ባያልቅም በዚህች ተምሳሌት ልቋጭ፤

በአንድ የመዲናችን መጠጥ ቤት ተስተናጋጆች “ኢትዮጵያ ትፈርሳለች አትፈርስም?” የሚል ጉንጭ አልፋ መሸታ ላይ እያሉ የከተማ ደንብ አስከባሪዎች በድንገት የጨዋታው አንገት ላይ ደርሰው “የግንባታ ፈቃድ ካላት አትፈርስም ፈቃድ ከሌላት አይቀርላትም!!” ብለው ሳቅ የሚያጭር ቁም ነገር ጣሉ አሉ። እናም እልዎታለሁ የኢትዮጵያ መሰረት ህዝቦቿ ከፍትህና ርትዕ የሚጻረር የትኛውንም ምድራዊ ሃይል አሜን ብለው ስለማይቀበሉና ለዚህም በደስታ እየተሰዉ ሃገርን ሰላጸኑና መንግስታቸውን ስለሚያከብሩ እንጂ የመሪዎች ስህተትም ጥፋትም ስለማይታያቸው አይደለም።”

ሰ.ይ.ፍ ያሏቸው #ሰላም #ይቅርታና #ፍቅርስ “እኔ ከቤቴ እንዴት ቢባል ከውጪ ንብረቴ?” የሚል ስጋት እንዳለው ነጋዴ ሁሉ  #ንጹሃንን ቀብሬ ግፈኛ ገዳዮችን ምንሲሆን ምሬ? የሚል የህልውና ጥያቄ ከግፉዓን እንዳጎነቆለ ይዘነጉት ይሆን?

አመሰግናለሁ

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share