የጁነዲን ሳዶ ባለቤት ወ/ሮ ሀቢባ መሐመድን ጨምሮ የ32ቱ ሰዎች ክስ ለሕዝብ ክፍት እንዲሆን ጠበቆቹ ጠየቁ

በዘሪሁን ሙሉጌታ

.ዐቃቤ ሕግ 197 የሰው ምስክር ለማቅረብ ጠይቆ 89 ምስክሮችን ብቻ አሰማ

በ1996 ዓ.ም የወጣውን የኢፌድሪ የወንጀል ሕግ አንቀፅ 32(1)(ሀ)(ለ)፣ 38(1) እና የፀረ ሽብርተኝነት አዋጅ ቁጥር 652 /2001 አንቀፅ 3(1) (4) (6) እና 4 ስር የተመለከቱትን ድንጋጌዎች በመተላለፍ የተከሰሱትን የቀድሞ የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትር የነበሩት የአቶ ጁነዲን ሳዶ ባለቤት ወ/ሮ ሀቢባ መሐመድን ጨምሮ ሌሎች 32 ሰዎች ክስ ለሕዝብ ክፍት እንዲሆን ጠበቆቹ ጠየቁ።
ቀደም ሲል ዐቃቤ ሕግ በተጠርጣሪዎቹ ላይ የሰው ምስክር በሚያሰማበት ወቅት ለምስክሮቹ ደህንነት ሲባል ችሎቱ በዝግ እንዲካሄድ ፍርድ ቤቱ በመወሰኑ ችሎቱ በዝግ ሲካሄድ ቆይቷል። ዐቃቤ ሕግ ለክሱ ዝርዝር ያስረዱልኛል ያላቸውን 197 የሰው ምስክሮች እንደሚያሰማ አስቀድሞ ለፍርድ ቤቱ ያመለከተ ቢሆንም 89 ምስክሮችን ካሰማ በኋላ ማጠናቀቁን ተከትሎ የፍርድ ሂደቱ ለጋዜጠኞችና ለዲፕሎማቶች እንዲሁም ጠበቆቹ ለተጠርጣሪዎቹ ዘመድ ወዳጆች ክፍት እንዲሆን ጠይቀዋል።
ከተጠርጣሪዎቹ ጠበቆች አንዱ የሆኑት ጠበቃ ተማም አባቡልጉ በተለይ ለሰንደቅ ጋዜጣ እንደገለፁት፤ በመጪው ሐሙስ ሰኔ 13 ቀን 2005 ዓ.ም የሚሰየመው ችሎት ለሁሉም የኅብረተሰብ ክፍል ክፍት እንዲሆንና በቀጣይ በተከሳሾቹ ላይ ዐቃቤ ሕግ አቀርበዋለሁ ያለው የኦዲዮና ቪዲዮ ቅጂ ለጠበቆች ቅድሚያ ሊደርስ ይገባል ብለዋል።
በአሁኑ ወቅት የተጠርጣሪዎቹ ጉዳይ እየታየ ያለው የቀድሞ ቅንጅቶች ጉዳይ ይታይበት በነበረው በቃሊቲ ወረዳ 8 አዳራሽ ውስጥ ሲሆን፤ ጉዳዩ እየታየ ያለው በፌዴራል አራተኛ ወንጀል ችሎት ነው።
በሌላ በኩል ከዚህ በፊት በፌዴራል ከፍተኛ ፍርድ ቤት “ጅሃዳዊ ሀራካት” በሚል የቀረበው ዘጋቢ ፊልም በአሁኑ ወቅት ጉዳያቸው እየታዩ ካሉ 12ቱ ተጠርጣሪዎች አለአግባብ ስማቸው መጥፋቱን በመግለፅ፤ በጠበቆቻቸው አማካኝነት በፕሬስ ሕጉ አንቀፅ 43 መሠረት ፎቶና ምስሎችን አለአግባብ ታይቷል በሚል 8 ሚሊዮን ብር የካሳ ክስ አቅርበው እንደነበር ጠበቃ ተማም ገልፀዋል። ነገር ግን የዳኝነት 83 ሺህ ብር ከፍለው ክሱን በፌዴራል ከፍተኛ ፍ/ቤት ለመክፈት ሲሞክሩ፤ ሬጅስትራሩ የክስ ፎርማሊቲ አልተሟላም በማለት ለዳኛ ሳይመራ፣ አቤቱታ አቅራቢዎች ሳይከራከሩ፣ ተከራካሪ ወገኖች መጥሪያ ሳይሰጣቸው አላግባብ በመዘጋቱ ለፌዴራል ጠቅላይ ፍ/ቤት ይግባኝ አቤቱታ ሰሞኑን እንደሚያቀርቡ አያይዘው ገልፀዋል።
በተጨማሪም የመጅሊስ ምርጫውን በተመለከተ መጅሊሱ የተመረጠበት አካሄድ ሕገ-መንግስቱን፣ የኢትዮጵያ ፍትሐብሔር ሕግን እና የመጅሊስ ሕገ-ደንብን የጣሰ ነው በሚል ያቀረቡትን ክስ የሥር ፍርድ ቤቶች ውድቅ ቢያደርጉም፤ ጉዳዩ ሰበር ሰሚ መድረሱንና ለሰኔ 27 ቀን 2005 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ መሰጠቱንም ጨምረው ገልፀዋል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኮለኔል አያናው መስፍን ቤተመንግስት ከሄዱት የወታደሮች ጀርባ አሉበት ተብለው ተጠርጥረው ታሰሩ

ምንጭ ሰንደቅ ጋዜጣ

1 Comment

  1. junedin sado how do you feel now? skank cadre, hopefully by now you can understand why the ETHIOPIAN people love to exile rather than to be abused by weyanes

Comments are closed.

Share