ሰር አሌክስ ፈርጉሰን በቁጥሮች

ከይርጋ አበበ

26 : 38 በስታዲየሙ የተሰቀለው የውጤት ማሳያ ኤሌክትሮኒክስ ሰሌዳ የፈርጉሰንን ከኦልድ ትራፎርድ መለዬት በማስመልከት ያስነበበው ጽሑፍ ነው ።ለዚህ ጽሑፌ ርዕስ ያደረኩት ይህ ቁጥር አሰልጣኙ በክለቡ የቆዩባቸውን ዓመታት እና ያገኟቸውን ዋንጫዎች ብዛት ለመግለፅ የተጠቀሙበት ገለፃ ነው።
በሃያ ስድስት ዓመታት የተገኙ ሰላሳ ስምንት ዋንጫዎችን ወደ ክለቡ የዋንጫ መደርደሪያ ማምጣት የቻሉት ሰር አሌክስ ፣ከጨዋታው በኋላ በስታዲየሙ ለታደሙት የክለቡ ደጋፊዎች እና ተጫዋቾች ንግግር አድርገዋል ። በንግግራቸውም እስካሁን በክለቡ ለነበራቸው ቆይታ የተደረገላቸውን እንክብካቤ አድንቀዋል ፤ለክለቡ ውጤት ቀጣይነት ሲባል ለሳቸው የተደረገው ለተተኪው አሰልጣኝም እንዲደረግላቸው ደጋፊዎቹን ተማጽነዋል። ተጫዋቾቹም ለለበሱት ማሊያ ፍቅር እንዲኖራቸው እና ለክለባቸው ውጤት ማማር ጠንክረው እንዲሰሩ አሳስበዋል።
  ህዳር ወር መጨረሻ ላይ ማሰልጠን የጀመሩትን ክለብ ለመሰናበት ጫፍ ላይ የደረሱት አሰልጣኝ ሰር አሌክስ ፈርጉሰን በማንቸስተር የመጨረሻ ዓመት ቆይታቸው የመጨረሻ ዋንጫቸውን በኦልድ ትራፎርድ ያደረጉትን የመጨረሻ ጨዋታ የዌልሱን ክለብ ሁለት ለባዶ በማሸነፍ መጨረሻቸውን አሳምረው ለመውጣት በቅተዋል።  በታላቁ ኦልድ ትራፎርድ ስታዲየም በልዩ ትዕይንት የተጀመረውና ከሰባ ሺ በላይ ቀያይ ባንዲራዎች አሸብርቆ በከፍተኛ ድጋፍ የታጀበው የእሁድ ምሽቱ ጨዋታ ከሰር አሌክስ በተጨማሪ አንጋፋውን ፖል ስኮልስንም ለሁለተኛ ጊዜ ለመሸኘት የተመቸ አጋጣሚ ነበር።  የሰቀለውን ጫማ በሰር አሌክስ ልመና አውርዶ በማጥለቅ ለቀያይ ሰይጣኖቹ ከፍተኛ አገልግሎትን መስጠት የቻለው ፖል ስኮልስ ከአሰልጣኙ ጋር በክብር ለመሸኘት ችሏል።
  ሰር አሌክስ ፈርጉሰን በቁጥሮች
2ፈርጊ ከማንቸስተር ዩናይትድ ጋር ማግኘት የቻሉት የአውሮፓ ሻምፒዮንስ ሊግ ዋንጫ ብዛት
5 በፈርጉሰን የሰለጠኑቡድኖች ብዛት ሲሆን፡ ኢስት ስቲርሊንግ፣ ሴይንት ሜሪ፣ አበርዲን፣ የስኮትላንድ ብሄራዊ ቡድን እና ማንቸስተር ዩናይትድ
6 በተጫዋችነት ዘመናቸው ሰር አሌክ የተጫወቱባቸው ክለቦች፡ ኩይን ፓርክ፣ ሴይንት ጆንስተን፣ ደንፈርምሊን፣ ፋልክሪክ እና አይር የተባሉ የስኮትላንድ ክለቦች
9 የሰባ አንድ ዓመቱ የቀድሞ የማንቸስተር ዩናይትድ አሰልጣኝ ያገኟቸው የኤፍ ኤ ካፕ ዋንጫዎች ቁጥር አምስቱን በማን ዩናይትድ አራቱን በአበርዲን
26 ስኮትላንዳዊው አዛውንት በኦልድ ትራፎርዱ ክለብ የነበራቸው ቆይታ በዓመት፡- ይህንን ያህል ዓመት ማንቸስተር ዩናይትድን ያሰለጠነ አሰልጣኝ የለም።
38 የእንግሊዙ ክለብ ባለፉት ሃያ ስድስት ዓመታት በሰር አሌክስ ፈርጉሰን አሰልጣኝነት ያገኛቸው ዋንጫዎች ብዛት፡- ይህንን ያህል የዋንጫ ብዛት መደርደሪያው ላይ የሰቀለ አሰልጣኝ ሲቪው ላይ የተፃፈለት አሰልጣኝ ከሰር አሌክስ ውጪ ማንም የለም።
104 ሰር አሌክስ በሃያ ስድስት ዓመታት ቀዩን ማሊያ ለማልበስ ወደ ክለባቸው ያስመጧቸው ተጫዋቾች፡- ለመጨረሻ ጊዜ ያስፈረሙት ትውልደ አይቮሪኮስታዊው ክሪስቶፎር ዛሃ ሲሆን ባለፈው ጃንዋሪ ወር በተከፈተው የተጫዋቾች ዝውውር በ15ሚሊዮን ፓውንድ ገዝተው ለአሳዳጊ ክለቡ በውሰት ሰጥተውታል። በፈርጊ ተገዝቶ ለፈርጉሰን ቡድን መጫወት ያልቻለ ተጫዋች።
170 ውጤታማው አሰልጣኝ በተጫዋችነት ዘመኑ ለተሰለፈባቸው ክለቦች ያስቆጠሩት ግብ ድምር፡-  ፈርጊ ላለፉት ሃያ ስድስት ዓመታት ወደ ማንቸስተር ካዘዋወሯቸው 104 ተጫዋቾች ውስጥ የሚበዛውን ቁጥር የሚይዙት አጥቂዎች መሆናቸው አሰልጣኙ ውጤታማ የአጥቂ መስመር ተጫዋች እንደነበሩ ማሳያ ነው ሲሉ የሚያውቋቸው ይናገራሉ።
370 ቁምጣና ማሊያ ለብሰው ወደ ሜዳ የገቡበት የጨዋታ ብዛት፡- ለስድስት ክለቦች በአጠቃላይ መሰለፍ የቻሉት የጨዋታ ብዛት 370 ብቻ ሲሆን በነዚህ ጨዋታዎች 170 ግቦችን ማስቆጠር መቻላቸው እውነተኛ የጎል ማሽን ነበሩ ያስብላል።
1499 ማንቸስተር ዩናይትድን እየመሩ ወደሜዳ የገቡባቸው ጨዋታዎች፡- ከሳምንት በኋላ 1500ኛ ጨዋታቸውን የሚያደርጉ ሲሆን፡- እስካሁን ግን 1499 ጨዋታዎችን አድርገው 895ቱን ማሸነፍ ችለዋል።
የፈርጉሰን ምርጥ አስራ አንድ
የእንግሊዙ ዘ ኢንዲፔንደንት ጋዜጣ የሃያ ስድስት ዓመት የሰር አሌክስ ፈርጉሰንን ምርጥ 11 ፈራሚዎች እንዲመረጡ በበተነው መጠይቅ መሰረት የአብላጫውን ድምፅ ያገኙትን አስራ አንድ ተጫዋቾች እንዲህ እናቀርባቸዋለን።
1. ፒተር ሺማይክል ምርጡ የፈርጊ ግብ ጠባቂ
2. ጋሪ ኔቭል ዝምተኛው ጀግና
3. ፓትሪስ ኢቭራ የፈርጉሰንን ክፍተት የደፈነ ምርጥ የኋላ መስመር ተጫዋች
4. ያፕ ስታም ደፋር እና አይደክሜ ሆላንዳዊ
አማካይ መስመር
5 . ክርስቲያኖ ሮናልዶ የዓለማችን ውዱ ተጫዋች የፈርጊ ምርጥ ፖርቹጋላዊ ፈራሚ
6 . ሪያን ጊግስ የአንድ ክለብ ማሊያ ብቻ ገላው የለመደው ዌልሳዊ ምርጥ ባለ ግራ እግር
7 . ሮይ ኪን አየርላንዳዊው ጉልበተኛ በማንቸስተር አሻራው የማይተካ ሚና ነበረው
8. ፖል ስኮልስ ምርጡ እንግሊዛዊ ለፈርጉሰን ቡድን ያልከፈለው አልነበረም
የአጥቂ መስመር
10. ዋይኒ ማርክ ሩኒ በማንቸስተር ያለው ቆይታ ያልተረጋገጠው የኤቨርተን አካዳሚ ፍሬ ከምርጦቹ የፈርጊ ፈራሚዎች አንዱ ለመሆን ጊዜ አለፈጀበትም
11. ኤሪክ ካንቶና የአንድ ሚሊዮን ፓውንድ ወጪ የሆነበት ፈረንሳዊ አመለ ብልሹ ከ1995-98 የማንቸስተር ዩናይትድ ውጤት ግምባር ቀደም ተጠቃሽ ነበር።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሽሬ ትግራይ ወጣቶች መከላከያውን ይቅርታ ጠየቁ
Share