ፖለቲካ ማለት ለእኔ – ከማተቤ መለሰ ተሰማ

የዛሪ ሁለት አመት ገደማ ነው፡ በእለተ እሁድ ከቤተ ክርሰቲያን መልስ፡ ኢትዮጵያውያን ሰብሰብ ብለው ሻይ ቡና ወደሚሉበት አካባቢ ጎራ በማለት፡ ታድሜ ጥቂት እንደቆየሁ፡ ቀደም ብለው በመምጣት እዚያው ከነበሩት መካከል አንዱ፡ እኔ ፖለቲከኛ ሰው አልውድም፡ ሲል ሌሎች ጭራሽ ያዳመጡት አይመስልም ነበር፡ በበኩሌ ግን በገደምዳሜ እኔን ለመወረፍ እንደሆነ ባውቅም  እንዳልሰማሁ ማለፍን መረጥሁና ዝም አልኩት፡፡

 ግለሰቡ በሁላችንም፡ እንዳልተደመጠ በመገመቱ ያነኑ ቃል ሞቅ አድርጎ ደገመው፡ በዚህ ጊዜ ትግስቴ አለቀና፡ እኔደግሞ ከሃዲ ሰው ከምር ያስጠላኛል ስል ሁሉም ጆሮአቸውን አዋሱን፡ ለመሳሌ? በሚል ጠየቀኝ ለምሳሌማ እንዳንተ፡ የትናንት ተቃዋሚ የዛሪ መሃልሰፋሪ፡ ስለው ያዙኝልቀቁኝ ማለት ጀመረና ተለያየን፡ አሁንምድረስ የጎሪጥ እንተያያለን። በበኩሌ ከመነሻዎቹ አንዱ፡ ለፖለቲካ የምንሰጠው ትርጉም ልዩነት ይመስለኛል።

ፖለቲካ ማለት ለእኔ ሌላ ምንም ሳይሆን፡ ለመብላት፣ ለመጠጣት፣ ለመልበስ፣ መጠላያ ለማግኘት፣ ባጠቃላይ የሰው ልጅ በህይወት፡ ለመኖር የሚያስፈልጉትን ነገሮች ለማሟላት፡ የሚያደርገው ጥረት ነው።

ሰው ገና ከእናቱ ማህጸን ሲወጣ ጀምሮ ነው፡ ከፈጣሪው የተሰጠው መብት፡ ይከበርለት ዘነድ ጥያቄ ማቅረብ የሚጀምረው። ሲበረደው ያለቅሳል፣ ሲያለብሱት ዝም ይላል፣ ሲርበው ያለቅሳል ሲያበሉት ዝም ይላል፣ ሲታመም ያለቅሳል እክምና ሲያገኝና ሲፈወስ ዝም ይላል ወ.ዘ.ተ.እያለ ያድግና አካለ መጠን ሲደርስም፡ የሚጎድለው ነገር ሲኖር እንዲሟላለት፡ ቤተሰቡንም ሆነ መንግስትን ይጠይቅና፡ ቀና ምላሽ ካጣ መቃወም ይጀምራል። ለተቃውሞው ሰሚ ካጣ ደግሞ፡ ወደ አመጽ ይሸጋገርና ነፍጥ ወደማንሳቱ ይሄዳል።

እንግዴህ ለእኔ ፖለቲካ ማለት በቀላል አገላልጽ ሌላ ምንም ሳይሆን፡ መብትን መጠየቅ ነው፣ ፖለቲካ ማለት ለእኔ ልብላ፣ ልጠጣ፣ መጠለያ ላግኝ፣ የመናገር፣ የመጻፍ፣ የመሰብሰብ፣ መሪየን የመምረጥ መብቴ ይጠበቅልኝ፡ ማለት ነው።

አንዳንድ ሰዎች፡ እኔ ፖለቲከኛ አይደለሁም፣ የሀይማኖት ሰው እንጅ፡ ሲሉ ይደመጣሉ፡ እንደዚህ የሚሉ ሰዎች ለእኔ ከላይ የተዘረዘሩትና፣ ለሰው ልጆች ከፈጣሪ የተሰጡት መሰረታዌ መብቶች ለእኛ  አያስፈልጉንም፡ እያሉ ነው። እነዚህ ሰዎች ከሰውእነት ግብርም፣ ሆነ ከተፈጥሮ ህግ ውጭ ነን እያሉን እንደሆነ ነው የሚገባኝ፡

በጣም የሚገርመው ደግሞ ብዙወቹ፡ እኔ ፖለቲከኛ አይደለሁም የሚለውን ቃል ማስተጋባት የሚጀምሩት ሁኔታዎች ሲመቻቹላቸው መሆኑ ነው፡ በችግራቸው ወቅት የሀገርና የወገን በደል ያንገበገባቸው፡ መስለው በመቅረብ ለነጻነቱ ከምር ከሚታገለው ማህበረሰብ ጋር ተቀላቅለው፡ ሲንቀሳቁ ከቆዩ በሗላ ችግራቸው ሲቀረፍ ፊታቸውን ለማዞር ጊዜ አይወሰድባቸውም።

በስደት የሚኖረው፡ ኢተዮጰያዊ አብዛኛው ማለት ያስደፍራል፡ የሚኖርበት ሀገር መንግስት እንዲያስጠጋው፡ ሲጠይቅ፡ የሚያቀርበው ምክናያት፡ በሀገሪ ላይ የሰባዊና ዲሞክራሲያዊ መብቴ አልተከበረም፣ የህግ የበላይነትና መልካም አስተዳደር የለም፡ ወ.ዘ.ተ. በሎ እንጅ ሃይማኖት ላስተምራችሁ፡ ወይንም መዋለነዋየን አፍስሽ የልማት ስራ ላከናውንላችሁ ነው የመጣሁት ብሎ እንዳልሆነ ግልጽ ነው።

የመኖሪያ ፈቃዱን፣ ከዚያም የውጭ ሀገር ዜግነቱን፡ ሲይዝ ግን ሁሉንም በመተውና ትናንት የተናገረውን ቃል ብቻ ሳይሆን ሀገሩንና ወገኑንም በመካድ፡ ይሉኝታውን ሸጦ ሲያማውና  ሲያወግዘው የነበረውን፡ የወያኔን  ፍርፋሪ ለመልቀም ሲጣደፍ  የሚስተዋለው ሰው ብዛት የተየለሌነው። እዚህ ላይ እንዲታወቅልኝ የምሻው፡ ግን እያልሁያለሁት ሃገርቤት ደርሶ፡ የተመለሰውን ሁሉ ሳይሆን፡ሄዶ ከወያኔ ጉያ በመወተፍ፡ የመበታተን ግዳጅ ተቀብሎ የሚመለሰውን ብቻ መሆኑን ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  አቢቹ ፦ ነቄ ተብለሀል! (እውነቱ ቢሆን)

አንዳንዶቹ ሀገርና ሀይማኖት፣ ሀይማኖትና ፖለቲካ፤ ምንም አይነት መስተጋብር የሌላቸው፡ አስመስሎ በማቅረብ፡ የሀይማኖት ተቋማትን መደበቂያ ምሽግ ለማድረግ ሲሞክሩና ሰው ከፈጣሪው የታደለውን ነጻነቱን ታግሎ እንዳይቀናጅ፡ ጌታ ለሾመው አለመገዛት ሃጢያት ነው በማለት፡ ህዝብን እንደዲንጋይ ሲያፈዙት እንደበረዶ ሲያቀዘቀዙት ይስተዋላሉ።

አንዳንዶቹ ደግሞ፡ ለፖለቲካ ልዩና አስፈሪ ስህል በመስጠት፡ ለወገኑ የሚቆረቆረውን ሰው  ፖለቲከኛ ነውና አትቅረቡት በማለት፡ ሃገር ወዳዱ ኢትዮጵያዊ በማህበራዊ ህይወቱ የተገለለ እንዲሆን፡ ቀን እረፍት ሌት እንቅልፍ አጥተው በመስራት ላይ ተሰማርተዋል።

በጣም የሚገርመው ነገር ግን፡ የሚከተላቸው ወገናችን፡ በውጭ ሀገር እየኖረ፡ በሚኖርበት ሃገር በውል እያስተዋለው፡ ያለው ሃቅ፡ የፖለቲካ ሰው ማለት የሰው ልጆች ሰባዌና ዲሞክራሴያዊ መብቶች እንዲከበሩ፣ የህግ የበላይነትና መልካም አስተዳደር እንዲሰፍን፣ እረሀብ፣ እርዛት፣ ጉስቁልና፣ በሸታና ሞት፣ እስራት፣ ግርፋት፣ ስደትና ውርደት፡ ከምድረ ገጽ እንዲወገዱና፡ ሰው ሆኖ የተፈጠረ ሁሉ በነጻነትና በሰላም እንዲኖር፡ የሚታገሉ ሰዎች እንደሆኑ።

ፖለቲካ ማለት ደግሞ፡ የሰው ልጅ ከፈጣሪ የተሰጠው መብት እንዲከበርለት፡ የሚያቀርበው ጥያቄ መሆኑን ጠንቅቀው እያወቁ፡ አይናችሁን ጨፍኑና ላሞኛችሁ አይነት ትያትር ሲከውኑባቸው አሜን ብለው መቀበላቸው ነው።

ስለሀቅ  እውነተኛ የሀይማኖት ሰው የሆነ፡ ግለሰብ። ሰዎች ያለምንም ወንጀልና ሃጢያት በሰዎች ሰባዊና ዲሞክራሴያዊ መብታቸው ሲገፈፍ፣ ሲደበደቡ፣ ሲታሰሩ፣ ሲገደሉ ቢሆን መቃዎም፣ ካልሆነ ደገሞ ማዘን፣ ወደ እገዚያብሄር መጸለይ አይገባውም ነበርን? እውነተኛ የሀይማኖት ሰዎች የነበሩት እማ፡ ጥቁሩ አሜሪካዌ ማረቲን ሉተር፣ ደቡብ አፍሪካዊዩ ዴዝሞን ቱቱ፡ እድሜልካቸውን ለሰው ልጆች ነጻነት ሲታገሉ አይደለም እንዴ የኖሩት። የእኛወቹስ አቡነ ጴጥሮስ አዲስ አበባ ላይ፣ አቡነ ሚካኤል ጎሪ ላይ የህይወት ዋጋ የከፈሉት የሃይማኖት ሰዎች ባይሆኑ ነውን?

እራሳቸው በምክናያት ጫካውስጥ መመሸጋቸው አልበቃብሎ አጥንት፣ ደምና ስጋ የሆኑትን፡ ሀገርን፣ ሀይማኖትንና የመብት ጥያቄን ወይንም ፖለቲካን፡ እንደ ዶሮ ስጋ፡ በልተው በመለያየት፡ በስውር ለአምባገነኑ የወያኔ ስራት የእድሜ ማራዘሚያ ይሆን ዘንድ የሚጠቀሙበት ማደንዘዣ የመጽሀፍ ቅዱስን ቃል አጣመው በማቅረብ ቀኝህን ሲመታህ ግራህን ስጥ ብሏል እያሉ ነው፡፡

ለመሆኑ እግዚያብሄር የሰው ልጅ፡ በሰው ልጅ እንዲረገጥ ቢፈቅድ ኖሮ ዳዊይትን በጎሊያድ ላይ ያስነሳው ነበርን? ሙሴን በፈሮን ፊት ሞገስ  ይሰጠው ነበርን? ከሙሴ እልፈት በሗላ እስራኤላውያንን ወደተስፋየቱ ምድር የመራውን ኢያሱን፡ አይዞህ አትፍራ እኔ ከጎንህ ነኝና ደፍረህ ተዋጋ ይለው ነበርን? ሰውስ የራሱን ጥረት ሳያደርግ ሁሉን ነገር በፈጣሪ ላይ ጥሎ እንዲኖር፡ እግዚየብሄር አዝዟል የሚሉ ከሆነ፡ እነሱ ለራሳቸው ለምንድን ነው የሚሰሩት? ለምን እግዚያብሄር ሰረቶ ገነዘቡን እቤታቸው ድረስ እስኪያመጣላቸው ቁጭ ብለው አይጠብቁም ነበር፡፡

ለእራሳቸው የማያደርጉትን ለምን በሌላው ላይ ይጭናሉ?  ከላይ በዋቢእነት የተጠቀሱ የመጽሀፍ ቅዱስ ማስረጃዎችን በሀዲስ ኪዳን የተሻሩ የኦሪት ድርሳናት ናቸው፡ የሚል መከራከሪያ የሚያቀርቡ አይታጡ ይሆናል፡ ኦሪት በአዲስ ኪዳን አለመሻሩን፡ እየሱስ ክርስቶስ፡ በማቲዮስ ወንጌል ምዕራፍ 5 ላይ ሰለሙሴ ህግ በሚለው ስር፡ ሲናገር እኔ የሙሴን ህግና የነቢያትን ትምህርት ልሽር የመጣሁ አይምሰላችሁ፡ ፍጹም እንዲሆኑ ላደርጋቸው መጣሁእንጅ፡ ልሽራቸው አልመጣሁም፡፡ በማለት የተንኮል ድራቸውን በጥሶታል። እርግጥ ነው እግዚያብሄር ሃያል ነው፣ ሁሉ በእጁ ነው፡ ግን እኛም የበኩላችንን ጥረት ማድረግና የድርሻችንን መወጣት ተገቢ ብቻ ሳይሆን ግዴታም ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  “ ጆሮ ያለው ይሥማ ! የማይሰማ አይስማ ! “ መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ

እዚህ ላይ በዩሀንስ ወንጌል ምዕራፍ 11 ከሰፈረው መካከል አንድ ድርጊት በምሳሌነት ልጥቀስ፣ እየሱስ ክርስቶስ አላዛርን በሞተ በ4ቀኑ ነፍስ ዘርቶ ከሙታን ያስነሳው በመጀመሪያ ሰዎች የመቃብሩን ዲንጋይ እንዲያነሱለት ካደረገ በሗላ ነው፡ ግን አላዛር በእራሱ ሃይል ፈንቅሎ እንዲነሳ ማድረግ ለእየሱስ ክርስቶስን ተስኖት አይደለም፡ በእሱ ፈቃድ ውስጥ የእኛ የሰዎች ድርሻም መኖሩን ለማሳየት እንጅ፡፡

በአሁኑ ወቅት፡ ሰው ለነጻነቱ እንዳይታገል የሚሰብኩ፡ የወያኔ መልእክተኛ የሆኑ ግለሰቦችም ሆነ ቡድኖች፡ የሰዎችን መብት ብቻ ሳይሆን የእግዚያብሔርን ፈቃድም ነው እየተጻረሩ ያሉት፡ የማቲዎስ ወንጌል ምዕራፍ 4 እንዲህ ይለናል፡ዲያብሎስ እየሱስን በቤተመቅደስ ጣሪያ ጫፍ ላይ አውጥቶ አቆመውና አንተን እንዲጠብቁ  እግዚያብሄር መላዕክቱን ያዝልሃል፡ እግርህም በዲንጋ እንዳይሰናከል፡ በእጃቸው ይዘው የደግፉሀል ተብሎ ተጽፏል፡ ስለዚህ አንተ የእግዚያብሄር ልጅ ከሆነህ፡ እስኪ ከዚህ ወደታች ዘለህ ውረድ፡ ቢለው እየሱስም እግዚያብሄር አምላክህን አትፈታተነው ተብሎ ተጽፏል ሲል መለሰለት፡ በማለት ያስተምረናል፡፡እንግዴህ ሰው ለመብቱ እንዳይታገል የሚያኮላሹ፡ የሃይማኖት ሰዎችም ልክ እንደ ዲያብሎስ መምኑን በማሳሳት የድርሻቸውን ሳይወጣ ቁጭ ብሎ እግዚያብሄርንም እንዲፈታተን እያደረጉት ነው ያሉት።

ሰንቱ ወገናችን ነው፡ የመኖሪያ ፈቃዱን ለማግኘት አስፈላጊ ጥረቶችን በማድረግ ፋንታ፡ እግዚያብሄር ያመጣልሀልና ዝም ብለህ ጸልይ እየተባለ፡ የድርሻውን ሳይወጣ፡ ቁጭ ብሎ ምንም እንቅስቃሴ የለህም፡ ወይንም የለሸም እየተባለ ፈቃድ ተከልክሎ፡ በማልቀስ ላይ የሚገኘው፡፡ በኦሪት ዘሑልቁ ምዕራፍ 21 ደግሞ እስራኤላውያን፡ በከነአናውያን ላይ ድል ይቀናቸው ዘንድ፡ ለእግዚያብሄር ተስለው ውጊያ ገጠሙና ድል ነሱ፡ ይላል እንጅ እነሱ እንደሚሉት፡ ለእግዚያብሄር ነግረው ተቀመጡ አይደለም ያለው። በዚሁ እረስ በምዕራፍ 31 ላይ እግዚያብሄር ሙሴን በእስራኤል ህዝብ ላይ ስለፈጸሙት፡ በደል ምድያማውያንን ቅጣ ስላለው 12000 ሰራዊት አዝምቶ በመዋጋት ድል አደረጋቸው፡ ይላል እንጅ ቁጭ ብለው ሰለጸዩ አሸነፉ አላለም፡ ሁሉንም እያወቁ ነው ሰው የሀቅሙን ሳይሞክር መና ከሰማይ ይወርዳል ብሎ እንዲጠብቅ፡ በሃይማኖት ስም እያሽመደመዱት ያሉት።

ይህ ሁኔታ በሁሉም ኢትዮጵያዊ፡ የሃይማኖት ተቋማት የሚንጸባረቅ ቢሆንም፡ በተለይ ለኢትዮጵያ ስልጣኔ፣ አንድነትና ብልጽግና፣ ለእግዚያብሄር ክብር፡ የላቀ አስተዋጽኦ፡ያበረከተችውና ለልጆቿም *ሙሉ ትምህርት ከእነ ስጦታው *ፈጹም ቋንቋ ከእነ ፊደሉ *ስነጽሁፍ ከእነ ጠባዮና ከእነ ሙያው *ኪነጥበብ በእያይነቱ *ስነ ጥበብ በእየመልኩ *ጥንታዊ ቅርስ ከእነ ታሪኩ *እምነት ከእነ ፍልስፍናው *ነጻነት ከእነ ክብሩ *አንድነት ከእነ ጀግንነቱ *ሃገር ከእነድንበሩና ከእነፈቅሩ *ሰንደቅ ዓላማ ከእነ ትረጉሙ *የዘመን መቁጠሪያ ከእነ አገባቡ ወ.ዘ.ተ. ያቀናጀችንና የኢትዮጵያ ታሪክ በር የሆነችው ጥንታዊትና ሃዋርያዊቷ የኢትዮጵያ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖታችን ዛሪ መንገዷን ስታ። ወንበዴው ወያኔ በመነኮሳት ስም ያደራጃቸው አባላቱን በቤተ ክህነቱ የተለያዩ እርከኖች ላይ በማስቀመጥ ቤተ ክርስቲያናችን የክርስቶስ ሳይሆን የአንድ የፖለቲካ ፓርቲ ዓላማ ማስፈጸሚያ እንድትሆን ተደርጋለች። ወያኔ ካባ የለበሱ ካድሬዎቹን በማሰማራት ቤተ ክርስቲያኒቱን የመንግሥት ፖለቲካ መስበኪያና አገልጋይ እንድትሆን አድርጓታል። ዛሪ ቤተክርስቲያናችን፡ የአንድነትና የሰላም ፣የፍቅር መስበኪያ ሳትሆን፡ የንትርክና የብጥብጥ መድረክ ሆናለች። ታዲያ አንድ አናሳ ቡድን ይህነን ሁሉ አፍራሽ ተግባር ሲፈጽም “ሃይማኖቱን የሚወደው፣ ለእምነቱ ሟች የነበረው፣ ሕዝበ ክርስቲያን እንዴት ዝም አለ? ወያኔስ ይህነን ሃይል፡እንዴት  እንዲህ ሊንቀው ቻለ? የሚለው ጥያቄ ዘወትር የሚነሳና ወቅታዊይም ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ‹‹አብይ ማደሪያ የለው፣ ግንድ ይዞ ይዞራል!!!›› ዶሮ ማነቅያ!!! የሐገር ፍቀር!!! ቅርስህን አድን!!!

መልሱ አብዛኛው ክርስቲያን፡ የሀይማኖት አባቶቹን ይሰማል፣ ቃላቸውንም ይፈጽማል፡ ነገር ግን የዘመኑ አባት ተብዬ፡ ካባለባሽ የወያኔ ካድሪዎች፡ በስብከታቸው፡የጥንት ኦርቶዶክስ አባቶቹ እንዳደረጉት ለአገሩና ለእምነቱ፡ ሲታገል እንዲሞት ከመንገርና፣ ቀደምቶቹ ሃገር ሲወረር ድንበር ሲደፈር፡ ታቦቱን ይዘው በመዝመት እንደተዋጉ፣ ብዙዎቹ አበው ለአገራቸውና ለእምነታቸው ደማቸውን እንዳፈሰሱ፡ ኢትዮጵያ ከሶሰት ሺህ አመት በላይ ያሰቆጠረ የጀግንነት ታሪክ ያላት፡ የነጻነት ተምሳሌት የነበረች ሃገር መሆኗን፡ ከማስተማር ይልቅ፡ ይታደሏል እንጅ አይታገሉም፣ በሚል የፕሮፓ ጋንዳ ትምህርታዊ ዘይቤ፡ ፍጹም አደንዝዘው በመያዝ፡ እንደፍየል ቅጠል እያኜከ፡ ሰለቸልሲና ማንችስተር የባዕድ ሀገር የኳስ ቡድን የሚጮህና፡ ምንም ነገር ሳይሰራ እጁን አጣጥፈፎ በመቀመጥ ከሰማይ መና እንዲወርድለት የሚጠብቅ፡ ፈረንጅ አምላኪና ስደት ናፋቂ፡ ደካማ ፍጡር አድርገውታል ነው።

በአሁኑ ወቅት፡ በሀይማኖት አባትነት ስም የተሰማሩ፡ የወያኔ ካድሪዎች፡ ሕዝቡ መብቱን እንዳይጠይቅ፡ ከሚያደርጉበት አሳሳች ትምህርቶች መካከል “ሁሉንም ነገር ለእግዚአብሔር እንስጠው፣ “እግዚአብሔር ያውቃል፣ እኛ የእርሱን ጊዜ እንጠብቅ” የምትል የራስን ኃላፊነት ሳይወጡ በእግዚያብሄር የማላከክን ሰንፍና እንዲያዳብር የሚያቀርቡት ስብከት ተጠቃሸ ነው። አዎ!! እግዚአብሔርማ ሁሉን ያውቃል። ምን ጥርጥር አለው። ነገር ግን በዓለም ላይ የሚፈጸመውን ግፍና መከራ ሁሉ እንዲከወን እንደፈቀደ መቁጠር ደግሞ ከስህተቶች ሁሉ የላቀ ስህተት ነው!!!! የሰው ልጅ በነጻ ፈቃዱ የሚፈጽመው ወንጀል ነው እንጅ። ለዚህ ጥፋቱም በፈጣሪው ፊት ሲቀርብ ተገቢውን ቅጣት ያገኝበታል።

በህይወት ባለበት ወቅት ግን፡ አምላኩን ሳይረሳ፡ የራሱን ጥረት እያደረግ፡ ያለመው ይሳካለት ዘንድ፡ መማጸን ተገቢ ይመስለኛል። የማይስማማውን፡ መተውና ዓለምን እንድትመቸው፡ አርጎ መለወጥም ደግሞ የሰው ልጅ ድርሻ ይመስለኛል። ይህን ሃቅ ነው እንግዴህ፡ ታሪካቸውን ለሆዳቸው፣ስብናቸውን ለጥቅማቸው አሳልፈው የሸጡ የሀይማኖት ሰው ተብዬዎች፡ ሰርዶ እንዲለብስ እያደረጉ ያሉት፡ ይህንን ሃቅ ነው ካባለባሽ የወያኔ ፖለቲካ ካድሪዎች፡ የተሳሳተ አቅጣጫ እንዲይዝ እያደረጉ ያሉት። እናስ እስከመቸ ነው እያወቅን ሲቀለድብን የሚኖረው?? መቸ ነውስ በቃችሁ ብለን እውነተኛ አባቶቻችንን የምንፈልገው!!!!?????

መጋቢት ወር 2005

7 Comments

  1. መልካምና እውነታን የተከተለ ጽሁፍ ሆኖ አግኝቸዋለሁ ። በመሆኑም ለወያኔ በጥቅም የተገዙና ተነሳሽነት የጎደላቸው ሆድአደሮች ትልቅ ደወል ነው።

  2. በጣም ወቅታዊና ጠቃሚ ጽሁፍ ነው ፈጣሪ የሰጠንን መብት መጠየቅና መጠቀም ሰብአዊ ግዴታችንም ነው

  3. This article expose the reality in various religious groups., particularly in the Ethiopian Orthodox church. God bless you Matebe.

  4. የፅሑፉ ዓላማ ምንድን እንደሆነ በጭራሽ አልገባኝም። ስለ ፖለቲከኞች ነው ወይንስ ስለ ሐይማኖት አባቶች? ስለ መፅሐፍ ቅዱስ ነው ወይንስ ስለ ዳያስፖራዎች?

Comments are closed.

Share