ፋሽስቱ አብይ አህመድ በጎጃም መራዊ ከተማ በሚኖሩ አማሮች ላይ የፈፀመውን የዘር ማጥፋት ጭፍጨፋ አስመልክቶ ከዓለም አቀፍ የአማራ ህብረት የተሰጠ መግለጫ

 የካቲት 13 ቀን 2024 ዓ.ም.

የአብይ አህመድ  የመራዊ ጭፍጨፋ: ዳግማዊ ማይካድራ

ጥር 20 ቀን 2016 ዓ.ም. የፋሽስቱ የአቢይ አህመድ ወራሪ ሰራዊት  ጎጃም በምትገኘው በመራዊ ከተማ በሚኖሩ ከ 200 በማያንሱ ንፁሀን አማራወች ላይ የፈፀመውን አረመኔያዊ የዘር ማጥፋት ጭፍጨፋ (genocide) ዓለም አቀፍ የአማራ ህብረት  በፅኑ ያወግዛል። የፋሺስቱ ወራሪ ሰራዊት ቤት ለቤት በመግባት ያገኛቸውን ሁሉ በፍፁም አረመኔያዊነትና ያለምንም ርህራሄ ሕፃናትን፣ ነፍሰ ጡሮችን ፣ አዛውንትን፣ ወጣቶችን በጦርነቱ ምንም ተሳትፎ የሌላቸውን ንፁሃን ዜጎች ጨፍጭፏል። የቀይ ሽብርን ዘመን በሚመስል መልኩ ከተረሸኑት በተጨማሪ ብዙዎች ለከፋ አካል ጉዳት እንዲሁም እና አእምሮ በሽታ ተዳርገዋል። ይህ አሰቃቂ ጭፍጨፋ የዘር ማጥፋት ብቻ ሳይሆን በጦር ወንጀልም የሚያስጠይቅ ዘግናኝና አረመኔያዊ ድርጊት ነው። በዚህ አማራውን ለማጥፋት ታልሞ በተፈፀመው የዘር ማጥፋት ጭፍጨፋ ከተረሸኑት ውስጥ የ15 ዓመት ወጣቶች፣ የ95 ዓመት አዛውንት መነኩሴ እና የሃይማኖት አባቶች ይገኙበታል። በተጨማሪም ሁለት አብያተ ክርስቲያናት እና መጠነ ሰፊ የዜጎች ንብረት ውድመት እና ዘረፋ ተፈጽሟል እንዲሁም ወደ ፳ የሚደርሱ ተሽከርካሪዎች ተቃጥለዋል።  ዓለም አቀፍ የአማራ ህብረት ይህን አሰቃቂና ዘግናኝ ጭፍጨፋ በድጋሜ እያወገዘ ሁሉም ኢትዮጵያውያን ብሎም ዓለም አቀፉ ማህበረሰብ እንዲያወግዘውና ጭፍጨፋው እንዲፈፀም ያዘዙት እና የፈፀሙት ለፍርድ እንዲቀርቡ ግፊት እንዲደረግ በአፅንዖት ይጠይቃል።

ላለፉት ዘጠኝ ወራት የአማራ ክልልን የወረረው እና በውጊያ ሜዳ ሽንፈት የገጠመው የአቢይ አህመድ እና የብርሃኑ ጁላ ጦር ሽንፈት ሲገጥመው ሰላማዊ ዜጎችን በድሮን፣ በታንክ፣ በመድፍና በዙ ሀያ ሶስት እየጨፈጨፈ ይገኛል። በደብረ ኤልያስ ከ570 በላይ መነኮሳትን፣ በደብረ ማርቆስ ቤት ለቤት በመግባት ከ100 በላይ ንፁሀንን ረሽኗል፣  በፍኖተ ሰላም፣ ደምበጫ፣ አማራ ሳይንት፣ በእስቴ፣ እና በሰሜን ሸዋ በድሮን በብዙ መቶ የሚቆጠሩ ንፁሀንን ጨፍጭፏል። እነዚህ እንደማሳያ ጠቀስናቸው እንጅ ከ100 ጊዜ በላይ የድሮን ጥቃት እንዳደረስና በሺህ የሚቆጠሩ ንፁሀንን መጨፍጨፉ የሚታወቅ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በአርባ ምንጭ የባልደራስ አመራሮች እገታን በተመለከተ የፓርቲው ድርጅታዊ መግለጫ

እንዲሁም ላለፉት አምስት አመታት  ይህ ጨካኝ የአብይ አህመድ  ፋሽስታዊ አገዛዝ ያለማቋረጥ በአማራው ላይ የዘር ማጥፋት ጭፍጨፋ በወለጋ፣ ቤንሻንጉል ጉምዝና በአዲስ አበባ ዙሪያ ባሉ ከተሞች  ሲፈጽም መቆየቱ እና በሽህ የሚቆጠሩ አማራወችን ማፈናቀሉ  ይታወቃል። በሸገር ከተማ ከ113 ሺህ ቤቶችን በዶዘር በማፍረስ ወደ 700 ሺህ ዜጎች በዋናነት አማራወች ቤት አልባ ማድረጉና ማፈናቀሉ የሚረሳ አይደለም።

በአሁኑ ወቅትም ከመቶ ሺ በላይ የሚደርሱ አማራወች በየእስር ቤቱ በተለይም አዋሽ አርባን በመሰለ የማጎሪያ ስፍራ በማሰር ከፍተኛ ስቃይ እያደረሰባቸው ይገኛል። በዚህ አስከፊ ስርዓት የተፈናቀሉት አማሮች ቁጥር ወደ 5 ሚሊዮን እንደደረሰ ይገመታል። በጠቅላላው ኢትዮጲያ ውስጥ ወደ 30 ሚሊዮን የሚደርሱ ዜጎች ለረሃብ እንደተጋለጡ እየተዘገበ ይገኛል፣ ከጭፍጨፋው የተረፈውን አማራ በረሃብ ለመጨረስ በማቀድ  የአማራው ገበሬ ማዳበርያ እንዳይደርሰው በመደረጉና በጦርነቱ ምክንያት ከ50% በላይ የሆነዉ መሬት ባለመታረሱ ከራሱ አልፎ ቀሪው የኢትዮጲያን ህዝብ በመመገብ የሚታወቀው አማራው ለከፋ ረሃብ ተጋልጦ ይገኛል።

ይሁንና ከማንኛውም ችግር በላይ አማራውን የሚያሳስበው ነገር የህልውናው ጉዳይ ነው። ጠላቶቹ ከምንጊዜውም በላይ አማራውን እንደ ህዝብ ሊያጠፉት ተነስተዋል። ጎጃም በምትገኘው  በመራዊ ከተማ ነዋሪወች ላይ የደረሰው የጅምላ ጭፍጨፋ የዚህ ሴራ አካል ነው። ይህ በመራዊ የደረሰው እልቂት በደቡብአፍሪካ አፓርታይድ አገዛዝ መጋቢት 21 ቀን 1960 ዓ.ም.  በሻርፕቪል በጥቁር አፍሪካውያን ላይ ከደረሰው እልቂት የከፋ ነው። በአጠቃላይ አገዛዙ በጎንደር፣ በጎጃም፣ በሸዋ፣ በወሎ እና በወለጋ በሌሎችም የኦሮሚያ ክልል አካባቢዎችተመሳሳይ ጭፍጨፋና ግፍ በአማራው ላይ ፈጽሟል። በሁለተኛው የዓለምጦርነት ወቅት በንጹሃን ዜጎች ላይ ተመሳሳይ ወንጀል የፈፀሙት በጀርመን ሂትለር እና በጣሊያን የፋሽስቱ ሙሶለኒ አገዛዞች እንደነበሩ ታሪክ መዝግቦታል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከአማራ ኢትዮዽያውያን ማህበር በስዊዘርላንድ የተሰጠ የአቋም መግለጫ

ሕዝብ እብሪተኛ አገዛዝ ስር ሲወድቅ መብቱን ሲነፈግ፣ የሃይማኖት ነፃነቱን ሲያጣ የሀገሩ ክብርና አንድነት ሲደፈር፣ በሰላም ሠርቶ ማደር ሲሳነው፣ በኑሮ ውድነትና በሥራ አጥነት ሲቸገር፣ ጭራሽ የመኖር ተስፋው ሲጨልም ከትዕግሥትና ከመንፈሳዊው የትግል ዘዴ ወጥቶ በአደባባይ በሚገለጽ ተቃውሞ ውስጥ ለመሳተፍ ወይም ነፍጥ አንስቶ ለመፋለም ይገደዳል። የአማራ ፋኖ ተገዶ የገባበት ትግልም በመርሆ ላይ የተመሰረተ እና በህዝብ ድጋፍ የተሰጠው ትግል ሲሆን ለአማራ ህዝብ ህልውና ብሎም ለመላው የኢትዮጲያ ህዝብ ነፃነቱና መብቱ ተከብሮ ያለ ስጋት ፍትሃዊ በሆነ ስርዓት መተዳደር እንዲችል ለማድረግ የሚደረግ ተጋድሎ ነው።

አብይ አህመድና አገዛዙ በመራዊና በሌሎች ቦታወች በአማራው ላይ ላደረሱት የዘር ማጥፋት ጭፍጨፋ በማያሻማ መልኩ ተጠያቂ እንደሚሆኑ ጥርጥር የለውም። ዓለም አቀፉ  ማህበረሰብ በተለይም ይህንን አረመኔያዊ አገዛዝ በተለያየ መንገድ እያገዙ ያሉ መንግሥታት ይህን አገዛዝ ለመርዳት የቀረፁትን ፓሊሲያቸውን እንዲፈትሹና ተገቢውን ማስተካከያ እንዲያደርጉ እንጠይቃለን። የአሜሪካን መንግሥት የመራዊዉን ጭፍጨፋ አስመልክቶ ያወጣው መግለጫ በጎ ጅምር ነው። ሌሎችም መንግሥታት ተመሳሳይ አቋም፣ መግለጫወችና ተግባራዊ እርምጃወች በአገዛዙ ላይ እንዲወስዱ ጥሪ እናደርጋለን።

የአብይ አህመድ አገዛዝ በእብሪት በአማራው ላይ የጀመረውን ጦርነትና ጭፍጨፋ ለመቀጠል የሚያስቸለውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ስድስት ወሩን ጨርሶ ለአራት ወር ማራዘሙን እናወግዛለን። እንደዚሁም አገዛዙ የኢትዮጵያ እርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያንን ለማዳከምና ለማጥፋት እያደረገ ያለውን ሴራ ዓለም አቀፍ የአማራ ህብረት በፅኑ ያወግዛል። ከሰሞኑ የቅዱስ ሲኖዶስ ዋና ፀሀፊ የሆኑትን አቡነ ጴጥሮስን ወደ ሃገራቸው እንዳይገቡ መከልከሉ በቤተክርስትያኒቱ ላይ ያለውን ጥላቻ የሚያሳይና ከ60 ሚሊዮን በላይ ለሚሆኑት ኦርቶዶክሳውያን የእምነቱ ተከታዮች ያለውን ፍፁም ንቀት የሚያሳይ  ነው። ምዕመናን ለሃይማኖት ነፃነታቸው መከበር ፀንተው እንዲታገሉ ጥሪ እናቀርባለን። በሌሎች እምነት ውስጥ ያሉ ኢትዮጵያውያን በሙሉ ይህን የአብይ አህመድን የዕብሪት አካሄድ በማውገዝ ነግ በእኔ ነውና ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ጎን እንዲቆሙ እንጠይቃለን።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በሱማሌ ክልል በ‹‹ቦምባስ›› ከተማ በተፈጠረው ግጭት አፋጣኝ ፍትህ እንዲሰጥ (ኢዜማ)

የፋሽስቱ አገዛዝ በአማራው ላይ የሚያደርሰው መጠነ ሰፊ ጭፍጨፋና ሰቆቃ እንዲያበቃ የሚከተሉት በአስቸኳይ እንዲተገበሩ እንጠይቃለን።

  1. የአብይአህመድ አገዛዝ ለአራት ወራት ያራዘመውን የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በአስቸኳይ በማቆም ወራሪ ሰራዊቱን ከአማራ ክልል እንዲያስወጣ፣
  2. በመራዊከተማ በአማራ ወገኖቻችን ላይ የተፈጸመውን የዘር ማጥፋት ጭፍጨፋ የሚያጣራ ገለልተኛ የዓለም አቀፍ መርማሪ ቡድን እንዲሰማራ እና የዘር ማጥፋት ላይ የተሳተፉትን በዓለም አቀፍ ፍርድ ቤት እንዲቀርቡ ማድረግ፣
  3. በግፍየተጨፈጨፉ ቤተሰቦች የደም ካሳ አንዲያገኙ፣
  4. የህሊናእስረኞች ያለ መንም ቅድመ ሁኔታ እንዲፈቱ፣
  5. የተፈናቀሉትናበረሃብ የተጠቁት ወገኖች ተገቢውን እርዳታ እንዲያገኙ፣
  6. የአብይአህመድ አገዛዝ በኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን ላይ እየፈፀመ ያለውን ተንኮልና ሴራ በአስቸኳይ እንዲያቆም እና አቡነ ጴጥሮስን፣ ቅዱስ ሲኖዶስን፣ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ቤተክርስቲያን ምዕመናንን እንዲሁም ቀሪውን የኢትዮጵያ ህዝብ በሙሉ ይቅርታ በመጠየቅ ሊቀጳጳሱ በአስቸኳይ ወደ ሃገራቸው እንዲመለሱ እና ሃላፊነታቸውን እንዲወጡ እንዲያደርግ እየጠየቅን፣
  7. ኢትዮጵያውያንይህን የንጹሃንን ጭፍጨፋ እንዲያወግዙና የአማራውን የህልውና ትግል በመደገፍ አገርን ከዚህ አስከፊ ስርዓት ለማላቀቅ ለሚደረገው ትግል አካል እንዲሆኑ ጥሪ እናቀርባለን።

አማራ የህልውና ትግሉን በአሸናፊነት በማጥናቀቅ በኢትዮጵያ ፍትሃዊ ስርዓት ይዘረጋል!!

ዓለም አቀፍ የአማራ ህብረት

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share