ዓባይ እሳት ተፋ….!!!

ስሜን አላልተው ሲጠሩኝ
“አባይ” ነህ አያሉኝ፣
ከሃዲ  ዋሾ  ሲሉኝ
ሲሰድቡኝ ሲረግሙኝ
ግንድ ተሸካሚ ማደርያ ቢስ
ተንከራታች የብስ ለየብስ
እያሉ ሲወቅሱኝ
ለኖራችሁ ሁሉ፣ አሁንስ ምን ትሉኝ?
ጭስ አልባ እሳት አለኝ
እንዳትነኩኝ፣ ፍሩኝ
በሉ አክብሩኝ
ተምዘግዝጌ በሽቦ
ገባሁ በየቤቱ እንዲጋገር ዳቦ
ከእንግዲህ ስትጠሩኝ ጠበቅ አርጉኝ
“ዓባይ፣ ዓባይ”  በሉኝ
“አባይ” ዋሾ እንዳትሉኝ
“ዓባይ” የአገር ግርማ
ሆኛለሁ ለማማ
እርር ድብን ይበል ጠላት ይስማ
እንድኖር ለተስማማ
ስወቀስ  ስታማ
ከሀዲ የባንዳ ርዝራዥ
ሳይተኛ የሚቃዥ
ሟርት የሰፈረበት
አዶከብሬው  ሲነሳበት
ኡኡ!!!!! ውሃ አስጠሙ ጌቶቼን
ከማዶ ያሉትን
ቀብዲ ስተው ያኖሩኝን
ቃል በምድር በሰማይ፣ አፍርሳት ኢትዮጵያን
ብለው ያስማሉኝን
ከኑቡያ፣ እና ግብፅ ያሉ ወዳጆቼን
አለቆቼን፣ አሳዳሪዎቼን!!!!
እያለ የሚለፈልፈው
ምድረ ባንዳ
የአገር እዳ
እርሙን ያውጣ ይወቀው
“ዓባይ” ማደርያ አለው
ግንድ የለም ይዞት የሚዞርው
ከእንግዲህ ኬላ አለው
መርምሮ አጣርቶ እሚሰደው
የኢትዮጵያ ልጆች አብረው
ከውሃ እሳት ፈጥረው
በሽቦ ገመድ ወስደው
አረጉኝ መመኪያቸው
ቃል ገቡ ለጎረቤት
ትሩፋቱን ሊያሰራጩት
ለአፍሪካ እንዲሁም አውሮፖ አገራት
ይሄው ነው ውጤቱ የህብረት
የኢትዮጵያ አንድነት
እወቁት፣ ከገባችሁ ድንገት
የዳግማዊ አድዋ ብስራት
የድፍን ኢትዮጵያ መድሃኒት
ለባንዳ ግን የሆድ ቁርጠት!!!!!
የራስ ምታት!
የማይጠፋ ፀፀት!!!
ኢትዮጵያን ለናቁ፣ የውስጥ እግር እሳት!!!
“ዓባይ” እሳት ተፋት!!!
ነብስ ይማር ለሞቱት
ሀሳብ ላመነጩት
ምስጋና ለደከሙት፣ ለለፉት
ኢትዮጵያ ደማቅ ብርሃን ናት!!!!!
አትበገሬ ጠንካራ እናት
የሁላችንም ናት
ክብር ያላት!!!!

ተመባ የካቲት 13/ 2014

ተጨማሪ ያንብቡ:  "የእኔ ማነኝ ? " ጥያቄን ፤ ለምን በወጉ መመለስ አቃተን ? - መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share