ሁሉም ነገር ወደ አፋር ግንባር!! ኢትዮጵያን ከመፈራረስ ለመታደግ ህወሓትን መደምሰስ ያስፈልጋል – አክሎግ ቢራራ (ዶር)

አክሎግ ቢራራ (ዶር)

“ኢትዮጵያን ማንም አይረዳትም። ብቻዋን ናት። ሞሰለኒን ሃሳቡን እንደገና እንዲያይ የሩሲያ የማስፈራሪያ ቃል እንኳ አላቆመውም። ምን ያድርግ? ፈረንሳዮችና እንግሊዞች አይዞህ፤ ከእግዚአብሄር የተሰጠህ ቅዱስ መብትህ ነው ብለውታል። አሜሪካ እንኳ ሳትቀር በተዘዋዋሪ ደግፋዋለች። አርፈሽ ተቀመጭ፤ ይኼ ነጻነት፤ ነጻነት የምትይው ትግልና መፈራገጥ ለመላላጥ ነው ብላታለች። አይ ኢትዮጵያ!”

አዶልፍ ፓርለሳክ፤ ተጫነ ጆብሬ መኮነን (ተርጓሚ) የሃበሻ ጀብዱ

ክፍል አንድ

“የትግራይ ሕዝብ ዋና ጠላት አማራው ነው። በአማራው ህዝብ ላይ ሂሳብ እናወራርዳለን” ብሎ የፎከረውን ህወሓት/ትህነግን የሚደግፉና የሚያበረታቱ ብዙ የውጭና የውስጥ ኃይሎች መኖራቸው አያከራክርም። ይህንን የህልውና ጥቃት በመጀመሪያ ደረጃ መወጣት ያለበት በአሁኑ ወቅት ኢላማ የሆነው የአፋሩና የአማራው ሕዝብ ነው። ሕዝቡ ግዴታውን እየተወጣ ነው። ይህ ሕዝብ ከፍተኛ መስዋእት የከፈለውና የሚከፍለው ለራሱ ህልውና ብቻ ሳይሆን ለኢትዮጵያ ጭምር መሆኑን መረዳት አስፈላጊ ነው። ለኢትዮጵያ ነው የሚለውን ከተጋራን፤ የኢትዮጵያ ፌደራል መንግሥት ባለሥልጣናትና ኢትዮጵያዊያን በሙሉ “ሁሉም ነገር ወደ አፋር ግንባር” ብለው በአንድነት የመረባረብ ግዴታ አለባቸው። የአማራው ፋኖና ልዩ ኃይል ወደ ግንባሩ መሄዱን በአድናቆት እደግፋለሁ።

እኔን በጣም ያሳሰበኝ ግን፤ ህወሃት እንደገና ራሱን አጠናክሮ፤ ክተት ብሎ፤ ተጨማሪ የሰው ኃይል እየመለመ፤ በአፋር፤ በአላማጣ፤ በወልቃይትና በሌሎች አካባቢዎች አዲስና ከፍተኛ እልቂት፤ ውድመት በሚያካሂድበት ወቅት፤ የኢትዮጵያ ፌደራል መንግሥት መዘናጋት፤ ቸልተኛነትና አገራዊ ትኩረት ምን ላይ እንደሆነ ለኢትዮጵያና ለዓለም ህዝብ ግልጽ አለመሆኑ ነው። የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ ኔድ ፕራይስ ህወሃት “በአፋር አካባቢ የሚያካሂደው አዲስ ጦርነት አሳሳቢ” ነው ብሏል። ግጭቱ በሁሉም አካላት እንዲያቆም አሳስቧል። ይህ ማሳሰቢያ በተደጋጋሚ ተደርጓል። ሆኖም፤ ጦርነቱን በተለያየ ወቅትና ዘዴ የሚያካሂደውን ህወሃትን በሃላፊነት አልወቀሰም። ለእልቂቱና ለውድመቱ ህወሃት በሃላፊነት በሕግ ፊት እንደሚጠየቅ ፍንጭ አልሰጠም።

ይህንን ተደጋጋሚ ሁኔታ ስመለከት፤ የኢትዮጵያ ፌደራል መንግሥት የሚናገረውና በመሬት ላይ ያለው ሃቅ እርስ በእርሱ የሚጻረር ሆኖ አገኘዋለሁ። ለኢትዮጵያ ህልውና ዋና ጠንቅ ከሆነው ከህወሃት ጋር “ድርድር” እናደርጋለን ተብሎ የሚነገረው የኢትዮጵያ ፊደራል መንግሥት አቋም ለህወሃትና ለውጭ ደጋፊዎቹ ጡንቻ እየሰጠው ነው ብል የተሳሳትኩ አይመስለኝም። እንደ አመራር፤ እንደ ድርጅትና እንደ ርእዩተ ዓለም ህወሃት ሙሉ በሙሉ ካልተደመሰሰ በስተቀር ኢትዮጵያ እንደ ሃገር፤ ሕዝቧ እንደ ሰብአዊ ፍጥረት ሰላም፤ እርጋታ፤ ግዛታዊ አንድነት፤ ሉዐላዊነት፤ ሰብአዊ ክብር ወዘተ ስኬታማ የሚሆኑ አይመስለኝም። የተሰራው እየወደመ ልማት የሚቻል አይሆንም።

ህወሃት የሚካሂደው ጦርነት የአፋር ወይንም የአማራ ጦርነት አይደለም። የመላው ኢትዮጵያ የህልውና ጦርነት ነው። በተዛማጅ ስመለክተው ደግሞ፤ የአማራው ህልውና ከኢትዮጵያ ህልውና ጋር የተያያዘ ስለሆነ፤ በኢትዮጵያና በኢትዮጵያዊነት  የሚያምኑ አካላት ሁሉ ጦርነቱ በትግራይ ሕዝብና በአማራ ሕዝብ መካከል አለመሆኑን ተቀብለው ድጋፋቸውን ፊት ለፊት ከሃዲውን፤ ሽብርተኛውን፤ አውዳሚውን፤ ወንጀለኛውን ህወሕትን ላለፉት አስራ አምስት ወራት ሲዋጋ የቆየውን፤ አሁንም የሚዋጋውን የአፋሩንና የአማራውን ክፍል በማያመናታ ደረጃ የስንቅና ትጥቅ ድጋፍ በመስጠት ቁርጠኛነታቸውን ማሳየትና መቀጠል አለባቸው።

እስካሁን ድረስ የአፋሩና የአማራው ሕዝብ የከፈለው መስዋእትና የሚያሳየው ጀግንነት ዋና የኢትዮጵያዊያን ጀግንነትና ደፋርነት ተምሳሌት ሆኖ አገኘዋለሁ። ይህ ዋጋ ተከፍሎ የመጨረሻው ግብ ምን ይሆናል? የሚለው በግልጽ አልተመለሰም። የመጨረሻው ግብ ህወሃት እንዳያንሰራራ አቅሙን ሳያመናቱ ማማከን ከሆነ፤ ጦርነቱ “አልቋል” ለሚሉት የማሳስበው የአማራውን ሕዝብ ወደ ጎን ሊተውት ቢፈልጉም፤ የአፋርን እናቶችና አባቶት ማን ጠይቋቸው ነው እዚህ ድምዳሜ ላይ የደረሳችሁት? እላለሁ። አፋርን ትቶ ኢትዮጵያን ለማሰብ አይቻልም።

በአሁኑ ወቅት ኢትዮጵያ በመንታ መንገድ ላይ ያለች አገር ሆና ስለማያትና የፖሊሲ አቅጣጫዎች ለአንባቢው ግልጽ እንዲሆን በመመኘት ይህንን ዘገባ በድምዳሜ ለመጀመር እፈልጋለሁ።

  1. ጠብ ጫሪ፤ ከሃዲ፤ የመሬት ነጣቂና ተስፋፊ፤ አምካኝ ወዘተ ከሆነው ከህወሃት/ትህነግ ጋር የእርቅና የሰላም ውል ማድረግ አይቻልም። ህወሃት በአማራው፤ በቅርቡ ደግሞ በአፋሩ፤ ቀደም ሲል በአኟኩ፤ በሶማሌው፤ በኦሮሞው ህዝብ ላይ ያካሄደው ጭፍን እልቂት በሕግ ያስጠይቀዋል። ድርድር ግን አስፈላጊ ነው። ድርድር ስል፤ ህወሃት ጦርነቱን ሙሉ በሙሉ እንዲያቆምማስገደድ (Surrender)፤ የመጀመሪያው ግብ ነው። ህወሃት ለጨፈጨፋቸው ወገኖቻችን፤ ለወደመው ግዙፍ ኃብትና ጥሪት ካሳ እንዲከፍል ማሳወቅ ብልህነት ነው። የጦር መሳሪያዎቹን እንዲፈታና ለእልቂቱና ለውድመቱ በኃላፊነት የሚፈለጉትን መሪዎቹንና አባላቱን ለኢትዮጵያ መንግሥት እንዲያስረክብ ግልጽነት ያለው አቋም መውሰድ ወሳኝ እርምጃ ነው። ብዢታ እንዳይከሰት ለውጭ ወዳጅ አገሮች ማስታወቅ የፖሊሲ አካል ነው። ይህ መልእክት ለአሜሪካ መንግሥት ባለሥልጣናት እንዲነገር አሳስባለሁ። የኢትዮጵያን ዘላቂ ወዳጅነት ይፈልጋሉ የሚል እምነት ስላለኝ፤ ግልጽ ሆኖ ቢነገራቸው የተሻለ ውጤት ይኖራል፤ ኢትዮጵያም እንድትከበር ይረዳል።
ተጨማሪ ያንብቡ:  አንድነት፤ አንድነት ስንል አምሳ ዓመት ሊሆነን ነው - አክሎግ ቢራራ (ዶር)

 

  1. ህወሓት የአማራውን ሕዝብ “የትግራይ ሕዝብ የህልውና ጠላት ነው” ብሏል። ራሱ የቀሰቀሰው ጦርነት ከተጀመረ ወዲህ በትግራይ ውስጥ ለተከሰቱት እልቂቶች፤ ድፍረቶችና ውድመቶች ሁሉ ዋና ተጠያቂ አድርጎ የፈረደው በአማራው ሕዝብ ላይ ነው። “ሂሳብ እናወራርዳለን” ብሎ ባወጀው መርህ መሰረት በአማራው ድሃና ጥሮ ግሮ የሚኖርህዝብ ላይ—ገበሬውን፤ ነጋዴውን፤ የሱቅ በደረቴ ያለውን፤ ጠላና ምግብ ሽጠው የሚተዳደሩትን ወዘተ—ሳይለይ፣ በአማራነታቸው ብቻ ጨፍጭፏል፤ ህጻን፤ ወጣት፤ እናት፤ ባልቴት ሳይለይ በአማራነታቸው ብቻ ንጹህ ወገኖቻችን ደፍሯል። የሚተዳደሩበትን ንብረታቸውን፤ ቤታቸውን፤ በጋራ የሚጠቀሙበትን ተቋማቸውን ዘርፏል፤ አበላሽቷል ወይንም አውድሟል። ይህንን ምንም አይነት ርህራሄ የማያሳይ ግፍና በደል እንዲሁ “በይቅርታ” እንለፈው ብሎ መፍረድ ፍትሃዊ ሊሆን አይችልም። ድሃውንና ጥሮ ግሮ የሚኖረውን የአማራ ሕዝብ ወደ ባሰ ድህነት አውርዶታል። ለዚህ ነው፤ ህወሓት ካሳ የመክፈል ግዴታ አለበት የምለው። ይህንን ፕሮግራም የማስፈጸም ሃላፊነቱ የአማራውና የፌደራሉ መንግሥታት ባለሥልጣናት ነው። በተጨማሪ ግን፤  የአማራው ሕዝብ በመንደርተኛነት የሚታየውን ክፍፍል ክፍተት አጥብቦ፤ ራሱን ባለው አቅም አደራጅቶ፤ አካባቢውን ጠብቆ፤ ምርቱን እያሳደገ፤ እየተሳሰበና በአንድነት ሆኖ በመንግሥት ሃላፊዎች ላይ ተከታታይ ጫና ማድረግ አለበት።

 

  1. በእኔ ግምገማ፤ የአማራው ሕዝብ ገና ያልተጠቀማቸው በብዙ ሚሊየን የሚገመቱ ወዳጆች አሉት–በአፋር ክልል፤ በሶማሌ ክልል፤ በደቡብ፤ በአዲስ አበባ፤ በኦሮምያ ወዘተ እና በውጭ አገራት። “ድር ቢያብር” እንዲሉ ለአማራው ዋና መከታ ራስን ማደራጀት፤ ከተጠቂነት ስነልቦና መጥቆ መውጣት፤የማይቻለውን ይቻላል ብሎ ማሰብና መተግበር አስፈላጊ ነው። የፖለቲካና የኢኮኖሚ ተረኝነት በተለመደባት ኢትዮጵያ፤ የአማራውን አቅም ለማዳከም፤ መሪዎች እንዳይኖሩት ለማድረግ የሚደረገው ህወሃት የፈጠረው የከፋፍለህ ግዛው ዘዴ ወደፊትም እንደሚቀጥል ማሰብ ያስፈልጋል። ለምሳሌ ማህብረሰቡን በብዙ መንገዶች—-የስራ እድሎችን እየፈጠሩ ምርትን በማሳደግ፤ የተፈናቀለውን ሕዝብ መልሶ በማቋቋም፤ ነዋሪዎች በያሉበት ደህነታቸውን እዲታደጉና የኢትዮጵያን ብሄራዊ ጥቅም እንዲያስከብሩ በማድረግ፤ የወደሙትን ወይንም የተበላሹትን  ጤና ጣቢያዎች፤ ትምህርት ቤቶች፤ ድልድዮች፤ መንገዶች ወዘተ በመጠገን ወዘተ ከፍተኛ ሚና ሊጫወት እምቅ ችሎታ ያለውን ፋኖን መከፋፈል ወይንም እንዲከፋፈል ማድረግ ከፍተኛ ጉዳት አለው። ፋኖና ፋኖን የሚደግፉ አካላት ሁሉ ጨዋነትን፤ አብሮነትን፤ የሕግ የበላየንት አክባሪነትን፤ ለወገን ተቆርቋሪነትን፤ ታታሪነትን፤ ኢትዮጵያዊነትን የማስተጋባት ግዴታ አለባቸው። “ኢ-መደበኛ” ወታደራዊ አደረጃጀት አሳሳቢ ነው የሚለውን እኔም እጋራለሁ። ኢ-መደባዊነት እንዲነግስ ያደረገው ግን ህወሃት መሆኑን መዘንጋት አደገኛ ነው። በቃላት አጠቃቀም ላይ ጥንቃቄ ይደረግበት።

 

  1. በአፋሩ፤ በተለይ ሆነ ተብሎ በአማራው ላይ የሚካሄደው እጅግ በጣም አሳሳቢና ጭካኔ የተሞላበት ተከታታይ ግፍና በደልስርዓት ወለድና መዋቅራዊ መሰረት አለው። በአማራው ላይ የሚካሄደው መዋቅራዊ ጭካኔ፤ በኃይል የሚካሄድ ሁከት (Institutionally sanctioned and structural violence based on ethnic or religious affiliation) “በቃ (NO MORE) ከምንልበት ደረጃ ላይ ደርሰናል። በቃ ለፈረንጆች የበላይነትና ጣልቅ ገብነት እምቢተኛነት ብቻ ሊሆን አይችልም። በኢትዮጵያ ኢ-ስብአዊ እልቂት ይቁም ለማለት ካልደፈርን የውጭ አካላትን የመውቀስና የመተቸት የሞራል ብቃት ሊኖር አይችልም። ዝንጀሮ “መጀመሪያ መቀመጫየን” እንዳለችው ሁሉ፤ እስኪ ለሰብአዊ ክብር ቆመናል የምንለው ሁሉ “በአማራው ላይ የሚካሄደው ጭካኔ በቃ” ለማለት እንድፈር እላለሁ። ህወሓት ጭካኔ የተሞላበት ግድያ በኦሮሞ ሕዝብ ላይ ሲያካሂድ የጎንደር ወጣት “የኦሮሞ ደም ደማችን ነው” ካለው መፈክር የተለየ አይደለም።

 

  1. በአሁኑ ወቅት፤ ህወሃት ሌላ አጀንዳ አቅርቦልናል። በአፋርና በኤርትራ ግንባሮች ጦርነት ጀምሯል። በአፋር ግንባር የሚያካሂደው ግፍና በደል በፊት ከሆነው ጋር ተመሳሳይነት አለው። ምክንያቱን ሲገልጽ፤ ከአፋር የምንፈልጋቸውን መሬቶችቻችን ወደ “ታላቋ ትግራይ”ለማስመለስ ነው ይላል። ይህ መርህ፤ የህወሓትን እብሪተኛነት ከማሳየቱ ባሻገር፤ እስካሁን ድረስ በሰላም፤ በሕግ፤ በተቋቋመው የድንበር ኮሚሽን አማካይነት ያልተፈታውን፣ የወልቃይት፤ ጠገዴ፤ ጠለምት ራያን (National flash points) ሁኔታ ያስታውሰኛል።
ተጨማሪ ያንብቡ:  ህዝቡን የሴረኞቹ ሰለባ ማድረግ ወንጀል ነው (ኢትዮጵያውያን ተጋሩ የውይይት መድረክ)

 

  1. በቅርቡ ጠቅላይ ሚንስትር ዶር ዐብይ አሕመድ ሲናገሩ፤ “ወልቃይት በታሪክ የትግራይ አካል ሆኖ አያውቁም” ያሉት አግባብ ያለው አቋም ነው። የወልቃይት ጥያቄ የውጭ መንግሥታትንም የሚመለከት የኢትዮጵያ ጉዳይ ነው። ግብጽና ሱዳን የሚፈልጉት ወልቃይት የትግራይ አካል እንዲሆን ነው። ይህ ከሆነ፤ አካባቢው ለሁለቱ መንግሥታት ብሄራዊ ጥቅም ይረዳል። ለሱዳን የምትፈልጋቸውን ለም መሬቶች ለመያዝ ያስችላታል። ለግብጽ፤ የአባይን ወንዝ (ጥቁር አባይን) ለመቆጣጠርና የሕዳሴ ግድብእንዳይሳካ ለማድረግ ምቹ ሁኔታ ይፈጥርላታል። ይህ ኮሪዶር በቶሎው መፍትሄ ማግኘት አለበት። የኢትዮጵያ መንግሥት ይህንን በመሳሪያ ኃይል የተነጠቀ፤ ስትራተጂክ የሆነና  በብዙ መስዋእት ነጻ የሆነን መሬት ለአማራው ክልል መንግሥት የማስረከብ ግዴታ አለበት። የአማራ መንግሥት ደግሞ መሬቱን በፍጥነት ወደ ዘመናዊነት መቀየር አለበት። መሬት መያዝ ብቻውን ፋይዳ ቢስ ነው። በብዙ መቶ ሽህ የሚገመት ስራ ሊፈጥር የሚችል መሬት ስለሆነ እቅድ አውጥቶ ዘመናዊ ማድረግ አለበት። መሬቱ ከለማ አንድ፤ ስራ ይፈጥራል፤ ሁለት የምግብና ሌላ ፍላጎትን ያሟላል፤ ሶስት ለኢትዮጵያ የውጭ ምንዛሬም ያካብታል። በውጭ አገር የምንኖር ኢትዮጵያዊያን በዘመናዊ እርሽ ከፍተኛ ሚና ሊኖረን ይችላል፤ እድሉን እንጠቀምበት።

 

  1. በህወሃት አጀንዳ መመራትን እናቁም። ህወሃትበየቀኑ ልዩ ልዩ አጀንዳ የሚሰጠው ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ሙሉ በሙሉ አቅሙ ስላልመከነ ነው። ጦርነቱ አልቋል ለማለት የማልችለው ለዚህ ነው። የኢትዮጵያ መከላከያ ኃይል፤ በተለይ አየር ኃይሉ ድሮኖችን በመጠቀም፤ የአፋርን ክልልና ሕዝብ የመርዳት ሃላፊነት አለበት። ፋኖው ወደ አፋር መሄዱ ይመሰገናል። ኢትዮጵያ አንደ ሃገር፤ የራሷን ግዛታዊ አንድነት፤ ሉዐላዊነት፤ ዘላቂ ብሄራዊ ጥቅምና የዜጎቿን ደህንነት የመጠበቅ መብቷ በዓለም ደንቦችና በተባበሩት መንግሥታት ህግጋት የተደገፈ ነው። የአሜሪካ መንግሥት ጫና ይህንን ሃቅ ሊገታው ወይንም ሊዳኘው አይችልም። በዘላቂነት፤ የአሜሪካ መንግሥት ሊከራከር የሚችለው የራሱን ጥቅም ይጠቅማል ወይንስ ይጎዳል የሚል ስለሆነ፤ እኛ መከራከርና ማስተጋባት ያለብን፤ ጠንካራ፤ ብሄራዊ አንድነቷን ያረጋገጠች፤ ሁሉም ዜጎቿ ተከብርው በእኩልነት የሚኖሩባት፤ ከሁከት መጥቃ የወጣች፤ ድህነትን የቀረፈች ዲሞክራሳዊት ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ቀንድ ከፍተኛ ሚና እንደሚኖራት ማሳመን ነው። ህወሓት ይህንን ለማድረግ ፍላጎትም ሆነ ብቃት የሌለው አጥፊና አምካኒ ቡድን መሆኑን ማስረዳት አስፈላጊ ነው። የኢትዮጵያ መንግሥት በተደጋጋሚ የትግራይ ሕዝብ በረሃብ እንዳይሰቃይ በሚል የተቀደስ መንፈስ የምግብና ሌላ ቁሳቁስ ድጋፍ ወደ ትግራይ እንዲሄድ እያደረገ፤ ዋናው ማነቆ ህወሓት መሆኑን የማያምኑ የውጭ መንግሥታትና ድርጅቶችን ሳይሰለቹ ማስረዳትና ማሳመን ግድ ይላል። የዲፕሎማቶች ስራ ይኼው ነው። ህወሓት አንድ ሽህ ሶስት መቶ የማጓጓዣ መኪናዎችን ነጥቆ መልሶ ኢትዮጵያን ሲከስ በመሬት ላይ ያለውን ሃቅ እንዲገነዘቡት በኢትዮጵያ ያሉትን አምባሳደሮች የእርዳታ ሃላፊዎች ለምን ተሳታፊ ለማድረግ አልተቻለም?

 

  1. የኢትዮጵያዋና ተግዳሮት ድህነት መሆኑን አምናለሁ። ይህንን መዋቅራዊ ድህነት ለመቅረፍ የሚቻለው ግን አድሏዊ፤ ጎሳዊይና የተበታተነ ድህንትን የመቅረፍ ፍኖተካርታ፤ ፖሊሲና ፕሮግራም በመከተል አይደለም። ለማስታወስ፤ ህወሃት ኢትዮጵያን በበላይነት ሲገዛ፤ ትግራይ ልክ እንደ ነጻ አገር ከውጭ ለጋስ ድርጅቶችና ግለሰቦች ጋር ግንኙነት ነበራት። ለትግራይ ድጋፉ እንዲሰጥ የሚዋዋለውና በኢትዮጵያ ስም የሚፈርመት የህወሃት ፌደራል ባለሥልጣናት ነበሩ። የአሜሪካ መንግሥት ተራድኦ ድርጅት ለኦሮምያ ክልል ድጋፍ የሚሰጠው በፌደራል ባለሥልጣናት አማካይነት ነው። የአሜሪካ ድጋፍ ይፋ ከሆነ በኋላ ደግሞ በጤና አገልግሎት በኩል የጣሊያን መንግሥት ለኦሮምያ ከፍተኛና የተቀነባበረ ድጋፍ እንደሚሰጥ አስታውቋል። በዘመነ ህወሃት ለኢትዮጵያ ይሰጥ የነበረው ግዙፍ መዋለንዋይ ወደ ትግራይ ክልል የጎረፈበት ምክንያት ድህነትን ለመቅረፍ ነበር። ድህነት ግን ተቀርፏል ለማለት የሚያስችል መረጃ የለም። ክልሉ ራሱን አልቻለም። የአሜሪካ ተራደኦ ድርጅቶች፤ ዓለም ባንክና ሌሎች ትግራይን መልሶ ማቋቋም አስፈላጊ ነው የሚል መርህ እንደ ነበራቸው ዓለም ባንክ በነበርኩት ወቅት ስለ ትምህርትና ጤና አገልግልት ድጋፍ፤ አካባቢን ስለ መንከባከብ፤ መሰረተ ልማትን ስለማጠናከር ውይይትና ድጋፍ ይሰጥ ነበር። ዓለም ባንክ የደህንነት ፕሮግርም (Safety Net) የፈጠረው ድህነትን ለመቅረፍ ነበር። ያጠናከረው ግን በውጭ የምግብ እርዳታ መመካትን ነው። አብዛኛው የውጭ ምንዛሬ ተሰርቋል። በትግራይ ድህነትን መቅረፍ አስፈላጊ መሆኑ አያከራክርም። አከራካሪው በአንድ አገር ሁለት አይነት የልማት ፍኖተካርታ፤ ፖሊሲና ፕሮግራም መኖሩ ነው። አንዱ የፖለቲካ ሥልጣን የበላይነት ላለው የሚለገስ፤ ሌላው ድምጽና ኃይል ለሌለው የሚነፈግ። ይህ አካሄድ ወደፊት ግጭት እንደሚያከትል ማጤን አለብን።

 

  1. ሌሎች ችግሮች እንዳሉ ሆኖ፤ በአሁኑወቅት በጦርነቱ የደሙትና የወደሙት ክልሎች አፋርና አማራ ናቸው። የእለት ጉርሳቸው የወደመባቸው አፋሮችና አማራዎች እንዴት ከፍተኛ ትኩረት አልተሰጣቸውም? የአሜሪካ ተራድኦ ድርጅት ለሚቀጥሉት አምስት ዓመታት2 ቢሊየን ብር ፈሰስ በማድረግ ትኩረት የምንሰጠው ለኦሮምያ ክልል ነው ብሏል። ይህ ፕሮግራም (Productive Safety Net) መባሉ የሚመሰገን ሞዴል ነው። ምክንያትም፤ ከምርትማነት ላይ ትኩረት ስለሚያደርግ ነው። በዚህ ክልል የሚኖሩ ወጣቶችን፤ ሴቶችንና ሌሎች ነዋሪዎችን አቅምን በማጠናከር፤ ስልጠና በመስጠት፤ አካባቢን እንዲከባከቡ በማረግ ወዘተ 400,000 ዜጎችን ከድህነት አሮንቃ ነጻ ለማድረግ እንደሚቻል የአሜሪካ ኤምባሲ አስታውቋል። ይህ መሆኑ መልካም ነው። በተመሳሳይ ግን፤ ፍትሃዊ የሚሆነው፤ በአፋርና በአማራው ክልሎች ለሚዲደረገው ሰፊ መልሶ የማቋቋምና ድህነትን የመቅረፍ ስራ የአሜሪካ መንግሥት አስቸኳይ ፈሰስ  ቢያደርግ መልካም ነው እላለሁ። አለያ በትግራይ የሆነው ኢ-ፍትሃዊ ክስተት ይደገማል። በወደሙትና በተበደሉት ክልሎች መልሶ ማቋቋም ብቻ ሳይሆን፤ ዘላቂ የሆነ የስራ እድል ፈጠራና ምርታማነትን የማጎልመስ ስራዎች ቢደረጉ በአሜሪካ መንግሥት ላይ ያለውን እምነት ከፍ ያደርገዋል። እምነት እንዲኖር ደግሞ በአፋርና በአማራው ክልሎች የሕግ የበላይነት መከበር አለበት።
ተጨማሪ ያንብቡ:  “የሕዝብ ሰው/Public Figure” መሆን አንዳንዴ ሳያሰክር ይቀራል? - ብሥራት ደረሰ

 

  1. የአሜሪካመንግሥት ድጋፍ ሰጥቶናል በሚል ሰበብ ግን በቁርጥ ቀን ለኢትዮጵያ ድጋፍ የሰጡ ብዙ መንግሥታት እንዳሉ መዘንጋት የለብንም። ከእነዚህ መካከል የኤርትራ፤ የቻይና፤ የሩሲያ፤ የተርኪ፤ የሶማልያ፤ የኢራን፤ የኬንያ (በከፊል) ወዘተ. ከእነዚህ መንግሥታት ጋር ያለውን ግንኙነት በሁሉም ዘርፍ ማጠናከር ለኢዮጵያ ዘላቂ ጥቅም ይረዳል። ይህንን ግንኙነት የአሜሪካ መንግሥት ሊወስንልን አይችልም። አጀንዳውን መምራት ያለበት የኢትዮጵያ መንግሥት ነው። በተጨማሪ፤ የአሜሪካ መንግሥት ባለሥልጣናት ቀስ በቀስ፤ በኢትዮጵያ ላይ የሚሰጡትን የተሳሳተ አመለካከትና ገለጻዎች ስከን ብለው እያዩ፤ ሁኔታዎችን እያመዛዘኑ የሄዱ ይመስላል። የብሊንከንና የፌልትማን አይነት ጠብ ጫሪነት ገብ ብሏል። ይህንን እድል በተቻለ መጠን ማጠናከርና ለአሜሪካ ዘላቂ ጥቅም የሚበጀው በሕዝብ የተመረጠውን የኢትዮጵያን መንግሥት መደገፍ እንጅ ለሽብርተኛው ለህወሓት ድጋፍ መስጠት ሊሆን አይችልም ወደሚል ድምዳሜ ደርሰው ይሆን? መልሱን አላውቅም። የማውቀው ግን፤ የኢትዮጵያና የአሜሪካ የመቶ አስራ ስምንት ዓመታት ግንኙነት ቢታደስና ህያው ቢሆን አሜሪካ በአፍሪካ ቀንድ ብቻ ሳይሆን፤ በመላው አፍሪካ ተአመኔታን፤ ክብርን የምታገኝ መሆኑን ነው። እኛ በውጭ የምንኖረው ኢትዮጵያዊያን በአንድ ላይ ሆነን፤ ጥቅሟ ከኢትዮጵያ ብሄራዊና ዘላቂ ጥቅም ጋር ተጻራሪ ሊሆን አይችልም እያልን ጥብቅና የምናሳይበት ወቅት የደረሰ ይመስለኛል። ኮርፖሬት ሜድያው የሚከተለው ትርክት ከአመሪካ ባለሥልጣናት አቋም ጋር የተያያዘ ስለሆነ ሜድያውም አስተያየቱን የሚቀይርበት ጊዜ ረዢም ላይሆን ይችላል።

እነዚህን ለወቅቱ አግባብ አላቸው ብየ ካቀርብኩ በኋላ፤ ለዚህ ትንታኔ የተጠቀምኩትን ጥቅስ መሰረታዊ ምክንያት ላብራራ። ልክ በጣሊያን ወረራ ወቅት የታየው ጀብድ፤ መስዋእትና አገራዊ እንድነት ባለፉት አስራ አምስት የህወሓት ጦርነት ወቅት መከሰቱን ለማሳየት ነው። ኢትዮጵያን ከመፈራረስ የታደጋት ማንም ሊክደው የማይችለው አገር ወዳድነት፤ ጀግንነትና የውስጥ ብሄራዊ አንድነት ነው። አለያ ይህች የካፒታል እጥረት ያለባት አገር እንዴት ቻለችው? ኢትዮጵያ በጣሊያን ወረራ ጊዜ ብቻዋን ነበረች፤ አሁንም በአብዛኛው ብቻዋን ናት።

በቅርቡ የሚያሳዩት ረገብ ያለ አቋም እንዳለ ሆኖ፤ የአሜሪካ መንግሥት ባለሥልጣናት በተደጋጋሚ ከሽብርተኛው ከህወሓት ጋር ተደራደሩ፤ ታረቁ፤ የታሰሩትን “ሽብርተኖች” ፍቱ እያሉ ጫና ሲያደርጉ ታሪክ እየተደገመ መሆኑን መረዳት አስፈላጊ ነው። የአሜሪካ መንግሥት በጣሊያን ወረራ ጊዜ የተናገረውን “አርፈሽ ተቀመጭ” መሰል መርህ በረቀቀ ደረጃ ደግሞታል። ለነሱ ታዛዢ፤ አጎብዳጅና አገልጋይ የሆነውን ህወሓትን ከመደገፍ ወደኋላ ሳይሉ መቆየታቸው ሃቅ ነው። ሌላው አማራጫቸው በኢትዮጵያ መንግሥት ላይ ከፍተኛ ጫና በማድረግ ለነሱ ጂኦፖሊቲካና ስትራተጂክ ጥቅም ታዛዢና አገልጋይ የሆነ መንግሥት እንዲመሰረት ማድረግ ነው። ይህንን የሚያደርጉት፤ ልክ በሌሎች አገሮች እንዳደረጉት በእርዳታ ግብዓት ነው። ነጻ እርዳታ የሚባል ነገር የለም።

በተዳጋጋሚ እንዳሳሰብኩት፤ ኢትዮጵያን ለማዳከም፤ ቢቻል ለማፈራረስ ከሚሰሩት መካከል የግብጽ መንግሥት የመጀመሪያውን ደረጃ ሲይዝ፤ በሁለተኛ ደረጃ ህወሃትን በረቀቀ መንገድ በመደገፍና ድምጽ በመስጠት በአሜሪካ የሚመሩት የምእራብ አገሮች መሆናቸውን መርሳት የለብንም። የአሜሪካ መንግሥት ባለሥልጣናት የኢዮጵያ እውነተኛ ወዳጆች ናቸው ወይንስ አይደሉም? የሚለው ጥያቄ የተመለሰ ይመስለኛል። በተደጋጋሚ ያሳዩት ባህሪይና ተግባር የሚያመልከተው እሳክሁን ድረስ አለመሆናቸውን ነው። ውናው መስፈርት በህወሃት ላይ የማያሻማ አቋም መውሰድ ነው። በጣልያን ወረራ፤ የአጼ ኃይለ ሥላሴ መንግሥት እየደከመ በሄደበት ወቅትና በደርግ መንግሥት ተመሳሳይ ሁኔታ ታይቷል። በህወሓት የበላይነት የኢህአዴግ መንግሥት ሥልጣን ሲይዝ ግዙፍ ድጋፍ የሰጡበት ዋና ምክንያት ህወሓት ታማኝ ስለ ሆነና ለአሜሪካ የጸረ-ሽብርተኛ ትግል አጋር ለመሆን ቃል ስለገባ ነው። መለየት ያልቻሉት የኢትዮጵያን ሕዝብና በበላይ ሆኖ የሚገዛውን የህወሓትን መንግሥት ነው።

የአሜሪካ መንግሥት የሚከተለው መርህ “ዘላቂ ጥቅም እንጅ ዘላቂ ወዳጅ የለም” የሚል ነው። በቀዝቃዛው ጦርነት ወቅት፤ በመካከለኛው አሜሪካ ሆንዱራስ የተባለችውን ትንሽ አገር በብዙ ቢሊየን ዶላር ድጎማ ተጠቅመው የሶሻሊስት መንግሥት የነበራትን ኒካራጓን ለማዳከም ሞክረዋል። ሆንዱራስን እንደ ሃገርና እንደ ማህበረሰብ ዘመናዊ አገር ሊያደርጓት ግን አልቻሉም። በተመሳሳይ ኢትዮጵያን ከጎረቤት አገሮች ጋር ለማጋጨት ጥረት ይደረጋል አይደረግም? የሚል ጥያቄ አቀርባለሁ።

ስለዚህ “በሬ ሆይ በሬ ሆይ” የሚለው ብሂል አንርሳ እላለሁ። ሆንዱራስ በሙስና ተዘፍቃ ድህነትን ለመቅረፍ አልቻለችም። የአሜሪካ መንግሥት በአፍጋኒስታን፤ በሶርያ፤ በኢራክ፤ በሊብያና በሌሎች አገሮች ጣልቃ ገብቶ ያዘመነውና ዲሞክራሳዊ ስርዓት የመሰረተበት አገር የለም። በዩክሬን የሆነውም እስካሁን ድረስ አወዛጋቢ ነው። ምን አልባት በዩክሬንና በሩሲያ ይካሄድ ይሆናል ተብሎ ሰሞኑን የሚወራው የጦርነት ውዝግብ ለኢትዮጵያ ፋታ ይሰጥ ይሆን ወይ? በሱዳንስ ያለው ውጥረት? ብየ ራሴን እጠይቃለሁ። እድል ሲኖር እድሉን መጠቀም የመሪዎች ሚና ነው።

ይህን ካልኩ በኋላ፤ ለኢዮጵያ መንግሥት ባለሥልጣናት የማሳስበው በቀውጢ ቀን የደረሱልንን መንግሥታት እንዳናሸሽ የሚል መልእክት ነው። “ያልጠረጠረ ተመነጠረ” እንዳይሆን።

ክፍል ሁለት የኢትዮጵያን ስርዓታዊና መዋቅራዊ ተግዳሮቶች ይተነትናል፤ መፍትሄዎችን ይጠቁማል

January 27, 2022

dr aklog birara 2
Dr. Aklog Birara former Sr. Advisor at World Bank,, Commentator at Center for Inclusive Development (ABRAW) and a regular contributor to Zehabesha.com

 

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share