የኮሮና ወረርሽኝ – የምርጫ ዘምቻ የጀርመን ልምድ እና አስተያየት በሕገ-መንግስት ላይ-ክፍል 6 – ፀጋዬ ደግነህ (ዶ/ር)

/

ለተከበራቹህ ወገኖች

  1. የኮሮና ወረርሽኝ እና ምርጫ

በኮሮና ወረርሽኝ ምክንያት የኢትዮጵያ ምርጫ መራዘሙን በተመለከተ ስለጀርመን ምርጫ ልምድ ለመግለፅ በአጭሩ እሞክራልሁ። የኢትዮጵያ ምርጫ ለመራዘሙ ምክንያት ተደርጎ የሚሰማው በወረርሽኙ የተነሳ የበለጠ ሊያጋልጥ የሚችለው ወይም አስቸጋሪው የምረጡኝ ቅሰቀሳ ዘመቻ፣ የምርጫው ሂደት እና በምርጫው ቀን ለማስፈፀም እንደማይቻል ነው። የጀርመንን ልምድ ከወሰድን ምርጫ በየ4 ዓመቱ ሲደረግ ይህም ከፍተኛ በሆነ፣ ለወራት በሚቆይ በሚሊዮን የሚቆጠር ህዝብን ባሳተፍ የምርጫ ዘምቻ የሚካሄድ ነው። የምርጫ ዘመቻ የፖለቲካ ግንኙነትን ከህዝብ ጋር ማጠናከሪያ እና ማሳተፊያ ተድርጎ ይወሰዳል። ከምርጫው በፊት በስልጣን ላይ ያለ ፓርቲም ሆነ ተፎካካሪ ወገኖች ሁኔታውን ለመመርመር እና የወደፊቱ እቅዶቻቸውን  የሚያስተዋውቁበት እድል የሚፈጠርበት ነው፡፡ ተምራጮችም የመመርጥ ድምፅን  ለማብዛት (Vote-maximizing) ለማድረግ እና ካለፈው ምርጫ በኋላም የተዳከመውን የፓርቲ እና ህዝብ ግንኙነቶች ለማደስ የሚሄዱበት መንገድም ነው። ይህም ለከፍተኛ አገርን ለመምራት የሚሰየሙትን የፖለቲካ እጩ ተወዳዳሪዎቻቸው ላይ የህዝቡን እምነት ሊለካ የሚቻለበት፣ የሚመረመርበት፣ እርስ በእርሳቸው በተለያዩ መድረኮች በሚያቀርቡት ሃሳቦች የሚፎካከሩበት እና የሚመዘኑበትም ነው። በምርጫ ዘመቻ ትልቁ አላማም ማሱን ማነቃነቅ እና ደጋፊዎችን ማደራጀትም ነው።

በጀርመንም፣ በሌላ አገሮችም ሆነ ኢትዮጵያ በምርጭ 97 እንደሚታወቀው በቀጥተኛ የምርጫ ዘመቻ በአደባባይ የሚደርጉ ስብሰባዎች፣ በየመንገድ ላይ የሚደርጉ የምርጫ ዘመቻዎች፣ በየመኖሪያ ቤቶች አካባቢ ከመራጩ ሕዝብ ጋር የሚካሄዱ ውይይቶች፣ ትርዕቶች እና ዝግጅቶችን የያዘ ነው፡፡ በተጫማሪም ቀጥተኛ ባልሆነ መልኩ በመገናኛ ብዙኃንን፣ በማስታወቂያ፣ በሶሻል ሚዴያ፣ በራሪ ወረቀቶችን፣ የምርጫ ፖስተሮችን፣ የምርጫ ጋዜጣዎችን እና እትሞችን፣ ፕሮግራሞችን በፖስታ በየቤቱ በመላክ ወዘተ የሚካሄድ ነው። ይህን እድል ፓርቲዎቹ እና ህዝቡ ፍትሃዊ ምርጫ እንዲደርግ የሚያስችል የመተዋወቅ እና የመርጃ ፍሰት በተቻለ መጠን እኩል እንዲዳርስ ያደርጋል። ምርጫ ተደርጓል ለማለት ብቻ የሚደርግ ኢፍትሃዊ ይስሙላን ያስቀራል። ምርጫ ለሁሉም ነገር መፍትሄ ባይሆንም የዲሞክራሲ አንዱ መግለጫ ነውና ይህንን መገለጫውን በተገቢው መልኩ ለማስፈፀም ይረዳል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በውኑ ድብኝት ይታጠባልን? በገለታው ዘለቀ

ትኩሱ የምረጡኝ ቅስቀሳ ዘመቻ („heiße Phase“ / the hot phase of the campaign) ሲቃረብ ወይም የምርጫው ቀን ከ2 ወር በታች ሲቀረው በየመንገዱ የምረጡኝ ማስታወቂዎች እና ፖስተሮች በየቦታው መለጠፍ ይጀምራሉ። 709 ለሚሆነው የጀርመን ፓርላማ መቀመጫ እና  በዛኑ ቀን የሚደረጉ (ሁሉም ባይሆን) የሪጅናል ስቴት፣ የወረዳዎች፣ የከንቲባነት ምርጫ የሚወዳደሩ በሺ የሚቆጠሩ ሰዎች የምረጡኝ ዘምቻ ያደርጋሉ። የጀርመን ፓርላማ ወንበር ብዛትም በየጊዜው ማስተካከያ ይደርግበታል። በተለምዶ እንድሚታወቀው ከፕሪዝዴንታዊ ምርጫ ይልቅ ፓርላማዊ ምርጫ ብዙ ሰዎችን ያሳትፋል። በ2017 በአጠቃላይ ለጀርመን ፓርላማ መቀመጫ ብቻ 4828 ተወዳዳሪዎች ሲሳተፉ፣ የአምስት ፐርሰንት መስመር ግድበትን በማለፍ ፓርላማ የገቡት 6 ፓርቲዎች ናቸው።  ቻንስለር ሜርክል በየቀኑ ማለት ይቻላል በአገሪቱ ውስጥ በተለያዩ አካባቢዎች እስከ ሁለት ዘመቻዎችን እና በተጨማሪም ከየዕለቱ ጋዜጦች እና የቴሌቪዥን ጣቢያዎች ጋር ቃለ መጠይቆችን ያደርጉ ነበር። እንዲሁም ከዋናው ተፎካካሪ መሪ ጋር የቴሌቪዥን ክርክሮችን አድርገዋል። የተለያዩ የፖለቲካ ፓርቲ መሪዎች እና ዕጩዎችም እንደዚሁ አድርገዋል። በአጠቃላይ ሲታይ በብዙሺ በሚቆጠር ቦታዎች ላይ በሚሊየን የሚቆጠሩ ሰዎችን በማሰባሰብ ያለማቋረጥ የምረጡኝ ዘምቻ ተደርጓል። ግማሽ ሚሊዩን የሚቆጠሩ አስመራጮች፣ ታዛቢዎች እና ረጂዎች ሰልጥነው ከ90ሺ በላይ በሚቆጠሩ የምርጫ ጣቢያዎች ውስጥ ሲሳተፉ ከ61 ሚሊዮን በላይ የሆኑ እድሜያቸው ከ 18 ዓመት በላይ የሆነ የጀርመን ዜጎች ድምፅ ሰጥተዋል። በአካል ለመምርጥ ያልተመቻቸውም አስቀድመው በደብዳቤ ድምፅ ይሰጣሉ።

ይህ ገልፃ ምን ያህል ብዜታዊ የሰዎች እንቅስቃሴ በምርጫ ዘምቻ እና በምርጫ ወቅት በከፍተኛ ደርጃ እንደሚጨምር ለማሳየት ሲሆን በተጨማሪም መራጩ ህዝብም ለመምርጥ በቂ ጊዜ፣ የመርጃ ማግኘት እና ማመዛዘኛ መብቱ መጠብቅ እንዳለብት ሲያሳይ በሌላ በኩልም የፖለቲካ ድርጅቶችም ያለገደብ ተዘዋውረው፣ ፕሮግራማቸውን አስተዋውቀው ተከራክረው፣ ለህዝብ ጥያቄ መልስ የሚሰጡበትን፣ የሚመዘኑበት የዲሞክራሲያዊ ሂደትንም ይገልፃል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  “አላዋቂ ሳሚ ንፍጥ ይለቀልቃል!” (ከ የአርአያ ጌታቸው)

ይህንን ግንዛቤ ከወሰድን በኋለ ወደ ኮሮና ወረርሽኝ እና በተጓዳኝ የደረሰውን ከፍተኛ ኢኮኖሚያዊ ድቀት፣ ማህበራዊ ግድበት እና የባህሪ ለውጥን ስንወስድ በላይ በተጠቀሰው መልኩ ምርጫን ለማድርግ የሚያስችል ሁኔታ በአሁኑ ወቅት እንደሌለ የሚያሳይ ነው። ሌላው ቢቀር እንኳን አንዳንድ አገሮች በኢንተርኔት የተመረኮዘ የምርጫ ዘመቻ የሚያስቡት አገሩ እና ህዝቡ ከደርሰበት የኢንተርኔት ስርጭት ብቃት፣ በየቤቱ ካለው ገደብ የለሽ እርካሽ ኢንተርኔት አገልግሉት፣ የመጠቀሚያ መሳሪያዎች መዳረስ እና የህዝቡ የአጠቃቀም ባህልም የሚወሰንም ነው። ስለ ከተሜው ጐልቶ የሚነገርበትን ኢትዮጵያን ከወሰድን እንኳን ከ80% በላይ የሚሆነው በገጠር የሚኖረው ማህበረሰብ ቀርቶ በከተማ ለሚኖረው በኢንተርኔት የተደገፈ ቅስቀሳ ለማድረግ በንፅፅሩ በቂ አቅምም፣ ኢንፍራሰትራክቸር እና  የመጠቀሚያ ዲቫይሶች የሉም። ወደ ግማሽ በላይ የሚቆጠረው ህዝብ የመብራት ኃይል በብቃት አይዳረሰውም። የጀርመን ጥምር መንግስት እንደኮሮና ወረርሽኝ መሳይ አደጋ ከተከሰት ድምፅ መስጠትን በደብዳቤ ብቻ ለማድረግ የሚያስችል እቅድ ላይ ተነጋግረውበታል። ይህ ሊሰራ የሚችለው በእርግጥ ከገጠር እስከከተማ የእያንዳንዱን ቤት የሚያዳርስ የፖስታ አገልግሎትና የአድራሻ ስረዓት ሲኖር ነው።

  1. የህግ ትርጉም እና ሕገ-መንግስት

ህጎች በጀርመን ውስጥ ኑሮን እና አብሮ መኖርን ያስከብራሉ፣ ይቆጣጠራሉ ይባላል። የመንግስት ውሳኔን በጀርመን ፍርድቤቶች ማስቆም ወይም መቀየር የሚቻልበት ሁኔታ ብዙ ነው። የሚወጡትን ውሳኔዎች፣ እርምጃዎችን እና ህጎችንም ጭምር በግለሰብ ደርጃ እንኳ ለፍርድ ቤት አቤት በማለት ወይም ክስ በመመስረት የማስቀየር እና ውሳኔ የማግኘት መብት እና ባህልም አለ።  የኮሮና ወረርሽኝ እና ተጓዳኝ ጉዳቱ መሰረታዊ መብቶችና ነፃነቶችን፣ ህጎችን አግዷል። በጣልያን እና በስፒይንም የጦርነት አዋጅ (martial law) በሚመስል መልኩ ከፍተኛ ገደቦችን የጣለ ነበር። መንግስት በጣለው ግድበቶች ላይ በፍርድ ቤት በግል በመክሰስ ውሳኔን ያስነሱ እንዳሉ ሁሉ፣ የመንግስት ግድበት ትክክለኛ መሆኑን የወሰኑ እና የፍርድ ቤት አቤቱታን ወይም ክስን ውድቅ ያደርጉ አሉ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ወንጭፍና ድራጉኖፍ

የጀርመን የሕገ-መንግስት ፍርድቤት እንደ አሜሪካው ሱፕሪም ኮርት የመጨርሻ ፍርድ ሰጪው ነው።  እ.ኢ.አ. በ2000 የአሜሪካ ፕሪዜዳንትነት ምርጫ የአልጎር እና የጆርጅ ቡሽን በድምፅ ቆጠራ ላይ የመጨረሻውን ውሳኔ የሰጠው ሱፕሪም ፍርድቤቱ እንደሆነ አይረሳም። ኢትዮጵያም የሕገ-መንግስት ፍርድቤት ባይኖርም  በፌዴርሽን ምክር ቤት፣ የሕገ-መንግስት አጠሪ ጉባኤ ከኮሮና ጋር በተያያዘ መልኩ ምርጫን ለማራዘም ሕገ-መንግስታዊ ትርጉም በማሰጠት የተደርገው ሂደት እና ውሳኔ  አዲስ ልምድ እና ለወደፊት በተለያዩ  የህግ ክፍተቶች ላይ እና የመጨርሻ ውሳኔ በሚያሻቸው ጉዳዮች ላይ ተሞክሮ እንደሚሆን ተስፋ አለኝ።

ከመፅሃፍ ቅዱስ፣ ከቅዱስ ቁርአን ውስጥ የተለያዩ የክርስትና እና የእስልምና ሃይማኖቶች እንደወጡና እንደተተረጎሙ ሁሉ ህጎችም በተለያየ አቅጣጫ የሚተርጎሙ ናቸው በየጊዜው ካልተሻሻሉ። ወደ ዋናው ነጥብ ስመለስ ህጎች በተለያየ መልኩ እንዳይተርጎሙ፣ እንዳያሻሙ፣ እንዳያንጠባጥቡ እና ክፍተት እንዳይኖርባቸው ተደርገው በተቻለ መልኩ ተቀርፀው እና በየጊዜውም ተሻሽለው መቅርብ እንዳላችው የጀርመን ልምድ ያሳያል። ጀርመን ባለፉት 70 አመታት ውስጥ 54 ጊዜ ያህል ሕገ-መንግስቱን አሻሽሏል። ለምሳሌ እስከ ዛሬ ከተሻሻሉትም ትልቁ የማስትሪሽን ስምምነት ለማፅደቅ የሕገ-መንግስት መሠረት መፈጠር እንዲስችል፣ የፌደራል ጀርመን በአውሮፓ ህብረት ውህደት እንዲሳተፍ የሚያደርግ 7 ንዑስ አንቀፆች ያሉት አዲስ አንቀፅ ነው።

የኢትዮጵያ ሕገ-መንግስት የተሻሻለ አንቀፅ አለው ሲባለ ተሰምቷል። ይህም ከሆነም ባለፉት ዓመታት ምን ያህል እንደሆኑ ሊታወቁ ሲገባ ሕገ-መንግስቱም በየጊዜው እንደ ብዙ አገሮች ሁሉ የመሻሻል ሂደት እንዲኖረው ማበረታታት ያስፈልጋል።

———

ከመልካም የጤንነት ሰላምታ ጋር

ፀጋዬ ደግነህ (ዶ/ር)

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share