ለሴረኞች እየመሸ ይመስለኛል በኢትዮጵያ እየሆነ ያለው  ሁሉ ይገለጥ ዘንድ ነው – ሰርፀ ደስታ

በአይናችን የምናየውን እውነት እየካድን ሕሊናችንን ሸጠን በሚስኪኖች ሞትና ሥቃይ ላይ ኑሮአችንን እየገነባን ይሄን ሁሉ የሚያይ አምላክ የለም በሚል ብዙዎች በሰው ፊት ቅዱስ መስለው የታዩባቸውን ሁኔታዎች ሳስብ እጅግ አዝናለሁ፡፡ ዛሬ በኢትዮጵያ እየሆነ ያለውን ነብይ መሆን ሳያስፈልግ አንዳዶቻችን ቀድመን መተንበይ ችለን ነበር፡፡ ታላቁ ፈላስፋ እንዳለው እግዚአብሔርን (እውነትን) ለማወቅ ባልፈለጉት መጥን የማይገባውን ያደርጉ ዘንድ ለማይረባ አእምሮ አሳልፎ ሰጣቸው ይለናል፡፡ በአለፈው አራት ዓመት የተጠጋ ዘመን የሆነውና አሁንም እየሆነ ያለውን በጥልቀት ላስተዋለው እጅግ አስፈሪ ዘመን ላይ መድረሳችንን ያሳየናል፡፡

ዛሬ ላይ አንዳንዶች ጥቂት የገባቸው ካሉ አላውቅም፡፡ አሁንም ቢሆን የማየው ነገር ገራሚ ነው፡፡ ብዙዎች በኢትዮጵያዊነታቸው ብዙ ሲዘፈንላቸው የነበሩ ዛሬ ማንነታቸው ፍንተው ብሎ ወጥቷል፡፡ ከወያኔ በከፋ አረመኔያዊ ሴራ የመጣውን አደገኛ ቡድን ትተው ዛሬም እየሆነ ያለውን የወያኔ ሴራ በሚል ግፍንና አረመኔነትን ለማስቀጠል ተባባሪ የሆኑ ኢትዮጵያዊ ነን የሚሉ ብዙ ናቸው፡፡ ዛሬ ወያኔ እያደረገች ላለቸው ነገርስ አቅሟ ማን ነው ብሎ መጠየቅ ይቅርና ወያኔ ዝር ባላለችበት ከተሞች ሲቃጠሉ እንደ ምንም ከወያኔ ጋር ሊያይዙት ሞክረዋል፡፡ ዘር ማንዘሩ ኦርቶዶክስ እምነት ተከታይ የሆነው ሐጫሉ ሁንዴሳ በሴራ መገደሉ ሳያንስ ሐጫሉ ተወልዶ ያደገበት አምቦ ከልጃቸው ሞት አስከፊነት ሐዘን ውጭ አንዳች ሳይል ኦሮሞ ነኝ በሚል ሽፋን ከሞጆ እስከ ባሌ የኦርቶዶክስ ተከታዮች (ኦሮሞ፣ አማራ፣ ትግሬ ወይም ሌላ ሳይል በኦርቶዶክስነት ብቻ)  ሲገደሉና ንብረታቸው ሲወድም ዛሬ መንግስት ነኝ የሚለው መዋቅር ዋና እንደነበር ግልጽ ሆኖ እያለ ብዙዎች አድበስብሰውት አለፈ፡፡ የሐጫሉ ዘመዶች ሻሸመኔ ላይ በኦርቶዶክስነታቸው ንብረታቸው እየወደመ በሴራ ሐጫሉን የገደሉት ተመልሰው በሐጫሉ አስከሬን ሌላ ድራማ ቀጠሉልን፡፡ ኮንቪንስ ወይም ኮንቪንስ መሆኑ ነው፡፡

ብዙ ብዙ ሆኗል፡፡ አጣዬ፣ በይፋ ክቡር የሆነው የሰውን ልጅ በግሬደር መቅበር፣ ከቀን አንድ ጀምሮ በቀን በመቶዎች ከዛም በላይ በጅምላ መጨፍጨፍ የእለት ከእለት ዜናችን ሁኖ ደንዝዘናል፡፡  ወያኔ በጦርነት ያደረገቸውንና ከዛ ጋር ያለውን ሌላ ሴራ ትቼ ማለት ነው፡፡ ይሄ ሁሉ እንዲሆን ግድ ነው፡፡ ምክነያቱም ይሄን ሁሉ ግፍ የሚፈጽሙትን ቅዱስ እግዚአብሔር ግፋቸውን በራሳቸው ላይ ሞልቶ እስኪውጣቸው ቀን ቆርጦላቸዋልና፡፡ የሚግርም ነው፡፡ ያዳቆነ ሰይጣ ሆነና ነገሩ በወያኔ 27 ዓመት አይተንው እርም ያልንውን በወያኔ ማደጎዎች ከዛም በከፋ ሲመጣ ዛሬም የወያኔን ዘመን እየኮነንን በአይናችን እየሆነ ያለውን አረመኔነት ክደን ለአረመኔዎች ከለላ ሆነናል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  "እውነትም ከእናታችን ሆድ ውሀ ሆነን በቀረን" ላለማለት ምን ይጠበቅብናል? * ቹቹ አለባቸው

ብዙዎች እውነት እነደዛሬው ጥርት በላ ባልወጣችበት ዘመን በኢትዮጵያዊነት ትልቅ ዝናን ያገኙ ዛሬ ማንነታቸው ተጋልጦ ተመልሰው ኢትዮጵያዊ ከእኛ በላይ ለማለት ሲንፈራገጡ እያየን ነው፡፡ በቃ እንዲህ ነው መንገዱ፡፡ ምን ለጊዜው ማጭበርበር ቢችሉም ሁሉም ገሐድ መውጣቱ አይቀርም፡፡ ሕልናቸውን ክደው በብዞዎች ስቃይና ሞት ነግደዋልና፡፡ የኦሮሞ ፖለቲካ ከወያኔ የከፋ አካሄድ እየሄደ እንደነበር በይፋ ቀድመን ያስጠነቀቅን ጥቂቶች ብንኖርም ትርፋችን የስድብ ውርጅብኝ ነበር፡፡ ምን አልባት ጥቂቶች የምንለውን ሰምተውናል፡፡

የኦሮሞን ፖለቲካ ከኦሮሞነት ጋር እያያዝኩት አደለም፡፡ ከሐጫሉ በላይ ለኦሮሞ ሕዝብ  የታገለ የለም፡፡ ሆኖም የሐጫሉ ኦሮሞነት ከኢትዮጵያዊነት ጋር የተነካካ ስለነበር ሐጫሉ መወገድ ነበረበት፡፡ በኢትዮጵያዊነት ማን ከእኛ በላይ ከሚሉት እንደነታማኝ ካሉ ጎንደሬዎች ይልቅ የወለጋው ታምራት ነገራ ዛሬ ለኢትዮጵያዊነት  ያለውን መታምንን አይተናል፡፡ እስኪ ዛሬ ስለታምራት የሚያውራ ኢትዮጵያዊ ነኝ የሚል ማን ነው? ሚዲያዎች በሙሉ በወያኔ ማደጎዎች ብልጽግና በሚባል ቡድን ተገዝተው ታዝበናል፡፡ ታምራት በሚዲያ ስለሚታወቅ ነው፡፡ ሌሎችም ስለ ኢትዮጵያዊነት እየተጋደሉ ያሉ የሚገርመው ከዛው ከወለጋ የሆኑን አውቃለሁ፡፡ የእነሱን ኢትዮጵያዊነት ሳይ ከመጽናናትም በላይ ነው፡፡ ምክነያቱም ሊሞቱለት የቆረጡለት ማንነት እንደሆነ ታዝቤያለሁና፡፡ ይሄን የምለው ነገር ለማሳመር አደለም በአካል ጭምር የማውቀው እውነት ስላለ ነው፡፡

ዛሬ መንግስት ነኝ የሚለው የወያኔ ማደጎ ከአሳዳጊው ከኮረጃቸው ስልት ሌላ እንኳን ፈጠራ ስለማይችል አሁን እየሆነ ያለውን እያየን ነው፡፡ የኦነግ/ኦህዴያውያን የወያኔን መንበር ሲወርሱ በአዴን የተባለው ቀድሞ የነበረው ቦታው ተጠብቆለት በዋናነት በአማራ ላይ ግፍ እያስፈጸመ ነው፡፡ አሳዛኙ ነገር ግን አገርን በሴራ አቅዶ ለመምራት ምን ዋጋ እንደሚያስከፍል ከአሳዳጊያቸው ወያኔ ሳይማሩ ከወያኔ በከፋ ሴራ እንወጣዋለን ብለው ይሄው ወደ እማይቀሬው ውርደትና ሞታቸው እየሄዱ እንደሆነ አሁንም ከወዲሁ አሳስባለሁ፡፡

የተንኮልን ጉድጓድ አታርቁ ቢባሉም አሁንም እንኳን ሴራ ከመቆፈር ቆም ብለው ለማስተዋል አልቻሉም፡፡ አብይ አህመድ ኢትዮጵያን ወያኔ ካመጣቸው የዜር ፖለቲካ በተጨማሪ በሐይማኖት ፖለቲካ ቁማር በይፋ በማኒፌስቶ ጽፎ መጥቶ ለምን ያለው አልነበረም፡፡ አሁን በያዙት አያይዛቸው ግን እድሜያቸው የት እድሚደርስ አላውቅም ግን በጣም ቅርብ ይመስላል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ዐማራነት የግል ጉዳይ አይደለም - አንዱ ዓለም ተፈራ

አዳነች አቤቤ የተባለቸው ግለሰብ  በኦርቶዶክስ ተከታዮች ላይ እያሳየቸው ያለው ትቢት ይገርማል፡፡  ይህች ግለሰብ በየትኛው ስልጣንና መብቷ እያደረገች ያለቸውን እንደምታደርግ አይገባኝም፡፡ ለነገሩ የአዲስ አበባ ከንቲባ ተብላ ጂግጂጋና ጎንደር የምትዘልበት መክነያቱ ምን ነበር? የአንድ ከተማ ከንቲባ ከከተማው ውጭ በምን አይነት መለኪያ በሌሎ ቦታ ሥልጣን እንዳለው የሚሄደው? ሰሞኑን ድግሞ ከኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቅዱስ ሲኖዶስ ጋር ድፍረቷን ቀጥላለች፡፡ ይች ሰው መካሪ ቢኖራት ጥሩ ነበር፡፡  ባለፈው መስቀል አደባባይ ላይ ይሄ አደባባይ ከተማው ግብር ከፋይ እንዲህ አምሮ የተሰራ እያለች ስትደነፋ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያ አንድ አደለም በአመት 10 እሷ ያለቸውን ወጪ አውጥቶ የሚያስገነባ ገቢ ለአገር እንደምታስገባ ቆም ብላ ብታስተውል ማን በነገራት፡፡

ዓለም ወደኢትዮጵያ ለጉብኝት ከመጣ የመስቀልን አከባባርን ራሱን ጨምሮ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ሰርታ የቆየቻቸውን ድንቃደንቅ አሻራዎችና ታሪክ ለማየት ነው፡፡ ምን አልባት ጥቂት የተፈጥሮ ቦታዎችንም ሊያውም በአብዛኛው እግረመንገድ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቅርሶችንና ሥርዓቶች ለማየት የመጣው ያይ ይሆናል፡፡  ከዚህ በኋላ የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቲያን እነዚህን ሁሉ ቅርሶች ሙሉ በሙሉ በራሷ ቁጥጥር ሥር ማድረግ አለባት፡፡ አዳነች አቤቤ የደነፋችበትን የመስቀል አደባባይ እድሳት አደለም ትልልቅ የአውሮፕላን ማረፊያ የተሰሩት ከየት በተገኘ ገቢ ነው? መንግስት አክሱምና ላሊበላ አውሮፐላን ማረፊያ የሚያሰራው የራሱ ገቢ እንዳይነጥፍበት ነው፡፡ ሌላ ቀርቶ የአንዳንድ አድባራት ክብረ በዓላት ራሳቸው ምን ያህል ገቢ እንደሚያስገኙ ስንቶቻችሁ ታውቃላችሁ? እንደው እንደምሳሌ የቁሉቢ ገብርኤል፡፡  መስቀል አደባባይን ለማደስ ገንዘቡ ከየት ነው የመጣው? እውነት ከአዳነች አቤቤ ግብር ከፋዮች ነው? አትቀልዱ፡፡  የመስቀል አደባባይን አክብረው ሁሉም የነበረውን ሥርዓት እንደ አገር ቅርስነት ማቆየት ሲገባ ዛሬ እንወርሳለን የሚሉ በዝተዋል፡፡ ሲጀምር ሙስሊሙም ይሁኑ ፕሮቲስታንቱ በሕግ የራሳቸው ቦታ ጠይቀው በማልማት የራሳቸውን አሻራ ለታሪክ ማኖር ሲገባቸው የነበረውን ለማጥፋት ይሄን ያህል ምቀኝነት ሐይማኖታዊ አደለም፡፡ በየትኛውም ዓለም ብትሄዱ ለሆነ አሰራሩ ይሄ ነው፡፡ ኢሬቻ እንኳን ዛሬ ድንገት መጥቶ የቦታ ባለቤት ሆኗል፡፡ ሊያውም በኢትዮጵያውያን ገነዘብ የተሰራን ቦታ፡፡  ኢሬቻ በክርስቲያኑም ይሁን በሙስሊሙ የባዕድ አምልኮ ነው፡፡ መስቀል አደባባይ ሳይሆን የኢሬቻ የአምልኮ ቦታ የተሰራው ግን በሕዝብ ገንዘብ ነው፡፡ መስቀል አደባባይ ከእነስያሜው የመስቀል ማክበሪያ ቦታ ነው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሰማያዊ ፓርቲ የሚታገለው ማንን ነው ? (ግርማ ካሳ)

ለማንኛውም አማራን የትኛውም እምነት ይኑረው ኦርቶዶክስ የትኛውም ዘር ይሁን ለማጥቃት የአብይ አህመድና  ሴራ እየሄደበት ያለው ሂደት ሳይውል ሳያድር ሴራው ወደዚሁ ቡድን እየተመለሰ ይመስላል፡፡  ጥቂት ጊዜ ስለቀረ እንደኖህ ዘመን መጨፈሩን የያዛቸው ግድ ስለሚላቸው ይቀጥላሉ፡፡ እኔ ግን እላለሁ ሁሉም ያስተውል፡፡ ሰሞኑን የደቡብ ክልል ምክትል የተባለ ጉራጌ ነው አሉ ጉራጌን በኦሮሞ ሴራ ተሳታፊ ለማደረግ እንዴት መሰራት እንዳለበት ሲመክር የነበረውን ሰምቻለሁ፡፡ ግን ሰዎች ከእነጭርሱ የዚህን ያህል አብደዋል? በሰውዬው ሐሳብ የተስማማችሁ ጉራጌዎች ሞክሩት፡፡ የኦሮሞ ፖለቲካ ሴራ በፍጥነት ሊያጠፋው ከፍተኛ አደጋ ከተጋረጠበት ሕዝብ ውስጥ ጉራጌ ዋነኛው ነው፡፡ ለዛ ግን አማራውን ማዳከም ግድ ስለሚለው ነው ዛሬ በአለ በሌለ ኃይሉ አማራ ላይ የዘመተው፡፡ጉራጌ አደገኛ ቀለበት ውስጥ ነው፡፡ ሶማሌ ሌላው ነው፡፡ ጋምቤላም እንደዛው፡፡ ለጊዜው ከጉሙዝ ጋር የተወሰነ ስምምነት አለ፡፡ ሆኖም የኦሮሞ አረመኔ ፖለቲከኞች ምኞት ሁሉንም ማጥፋት ወይም ወደ ኦሮሞነት መቀየር ነው፡፡ ይሄን እናሳካለን ብለው ነው አብይ ከመጣበት ቀን እንድ ጀምሮ በኮንፊውዝ ነደ ኮንቪንስ ባለው ፐረሮጄክት እያስኬደ ያለው፡፡ አፋርን አሁንም ከአማራው ቀጥሎ ሰለባ የሆነ ነው፡፡ ቃል የተገባለት ሲዳማም አይቀርለት፡፡ ቀሪ የደቡብ ትንንሽ ሕዝቦች ዛሬም የሚናገርላቸው ሳይኖር እያለቁ ነው፡፡ በሌሎዎች እነ ባእዴን የሚደገፈው የኦሮሞ አደገኛው ከወያኔ የከፋው ሴራ ይሄ ነው፡፡ ይሄ ሁሉ አረመኔያዊ እብደት ግን በፍጥነት ሴረኞቹን ሊውጣቸው ወደእነሱ እየተንደረደረ ነው፡፡ እንደ ፈርኦን ሰራዊት በላያቸው ማዕበሉ ሊከደን ጥቂት የቀረው ይመስላል፡፡ ሁሉም ዛሬ ለራሱ ሲል ይጠንቀቅ፡፡ አሁን ነገሮች ገሐድ እየወጡ ነው፡፡

ቅዱስ እግዚአብሔር ኢትዮጵያንና ሕዝቧን ይጠብቅ፡፡

አሜን!

ሰርፀ ደስታ

በቄለም ወለጋ ዞን የጊዳሚ ወረዳ በአሸባሪው ሸኔ 87 ንጹሐን በጅምላ በአንድ ቦታ ተገድለው ተገኝተዋል ሲል የዞኑ አስተዳደር ገለጸ

 

2 Comments

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share