ኢትዮጵያ የዕንቆቅልሽ ምድር – ዳግማዊ ጉዱ ካሣ

ሐምሌ 21 ቀን 2013ዓ.ም፡፡

ያለንበት ወቅት “አላልኩህም? ምን ብዬህ ነበር? ያልኩት መሬት ጠብ አላለም! ወዘተ.” የሚባልበት እንዳልሆነ አውቃለሁ፡፡ ያ ጊዜ ትንሽ ይቀረዋል፤ ከአንድ ዓመት ብዙም የሚበልጥ ግን አይመስልም፡፡ ምክንያቱም  ሁሉም ነገር እያቀጣጨ ያለው ያን የነጻነት ዘመን ለማብሰር ይመስላል፡፡ “ይህን ያህል ሰው ሞተ፤ ይህን ያህል ሰው ተገደለ፤ ወያኔ ነፍስ ዘርታ ወደማጥቃት እንድትዞር እነአቢይ በሁሉም ረገድ ካገዟት በኋላ ‹እያጠቃች መጥታ› እዚህ ደረሰች፤ ያንን ሥፍራ ያዘች…” የመሰለውን የእውነትም ሆነ የውሸት ወሬ ተውት፡፡ መሆን ስላለበት ይሆናል፡፡ እንኳንስ ይሄኛው ያኛውም እንዲህ ሆኗል፡፡ ይሄኛውማ ወትሮስ ምን ሊያጣ? ያልነበረህን አታጣም፡፡ በጥቂት ዓመታት ውስጥ በተዘረፈ ሀብት ንብረት ፓሪስንና ሎንዶንን መስሎ የነበረው ቦታ እንኳን ጃርት የበላው ዱባ መስሏል፤ ያሳዝናል፡፡ የወደመው የኛው ነውና ጉዳቱ የጋራችን ነው፡፡ ቢሆንም ያለ ነው፡፡ ሳትለፋ በቀላሉ አገር ዘርፈህ የራስህን አበባ ብታስመስል መቅሰፍት ይታዘዝበታል፡፡ ሰው የማይገባው ይሄ ነው፡፡ የወዲህኛውማ ዱሮውንም አንዳችም ልማት እንዳይሠራበት በሻጥር ተቆልፎ ቁጥቋጦ ብቻ ሆኖ ቀርቷል፡፡ አንዲት ሪፈራል ሆስፒታል ትሠራ ተብሎ መዋጮ ቢጀመር አይደለም እንዴ እርሷም ቁም ነገር ሆና የተከለከለችው?  የነዚያ የገልቱዎቹ ቦታም ምንም እንኳን በትራክተር ቢርመሰመስም እሱም የተዘረፈና በሸርና በሸፍጥ የተከማቸ በመሆኑ ከነዚያኞቹ የዘለለ ዕድል የለውም፡፡ ሰው ግን አንዱ ከአንዱ እንዴት መማር አይችልም? ዕውቀትና ጥበብ፣ ማስተዋልና ብልኅነት እንጂ ድንቁርና እንዴት ይወረሳል? የሰው ልጅ ወዴት እየሄደ ነው? አንጎል ኢትዮጵያ ውስጥ ሲገባ እንዲህ ይግማማል ማለት ነው? እስኪ አስቡት….

አሁን ጊዜው ጭፍና ነው፡፡ በኔ የአካባቢ ዘዬ “ጭፍና” ማለት ጨፈነ ከሚለው ቃል የተወሰደና ዙሪያ ገባው በጉምና በጭጋግ ወይም በደመናና ካፊያ ለዕይታ የሚያስቸግር ሲሆን የምንጠቀምበት ቃል ነው፡፡ የአሁኑ ጊዜም በሁለት መንገድ ጭፍና ነው፡፡ አንደኛው ክረምት በመሆኑ በተፈጥሮ ሳቢያ ጭፍና ነው፡፡ ሁለተኛው የአህመድ አቢይ ሤራ የፈጠረው ሀገራዊ መጥፎ ድባብ ነው፡፡ የኑሮ ውድነቱም ከጭፍና ፈጣሪዎቹ አንዱ ነው፡፡ ጭፍና ብቻ!

ተጨማሪ ያንብቡ:  ያልመከተ ተፈነከተ፤ ያልተደራጀ ተፈጀ። - ጌታቸው ኃይሌ

አቢይ አህመድ ማለት – አሁን በደምብ መናገር ይቻላል – ከወርቃማው የኢትዮጵያ ዘመን መባቻ በፊት ለሦስት ዓመታት ገደማ ኢትዮጵያን እንደብረት ቀጥቅጦ እንደሰም አቅልጦ ይገዛታል የተባለው ሃይማኖት የለሽ ሰው ነው፡፡ የርሱን ዐረመኔያዊ ጭካኔና ሃይማኖት የለሽነት እዚህ ላይ መዘርዘር ለቀባሪ እንደማርዳት ነው፡፡ አውቆ ያልደነቆረና ያልታወረ ያውቀዋል፡፡ በዚያ ላይ አለማየሁ ገ/ማርያምን የመሰሉ ደንገጡሮቹም ይቀየሙኛል፤ ጋንኤል ክብረትን የመሰሉ አማካሪዎቹም ይረግሙኛል፡፡ ጥሎብን የርሱ ስም በክፉ ሲነሳ የሚያለቅሱና ማቅ የሚለብሱ ብዙ ናቸው! ምን ቢያዞርባቸው ይሆን ግን? ይሄ የምዕራብ አፍሪካ የነኢዩ ጩፋና እስራኤል ዳንሳ የመተት ፓኬጅ ጉድ አፈላብን አይደል?

“ደግነቱ የዘመኑ ማጠር በጄ እንጂ” ይላል ቀዳሚው ትንቢተ አበው ስለዚህ ሰውዬ ሲናገር፡፡ “ደግነቱ የዘመኑ ማጠር በጄ እንጂ እንደርሱ ፍላጎትና ምኞት አንድም አማራ በሕይወት እንዲተርፍ አይፈለግም፡፡ የተረገዘ የአማራ ሕጻን ሳይቀረው ልክ እንደሄሮድስ የእናቶቻቸውን ሆድ በሠይፍና በጎራዴ እያስቀደደ ያስፈጃቸዋል፡፡ ጥቂት ጊዜ ቢያገኝ ቆሞ የሚሄድ አማራ አይቀረውም፡፡ አማራን ለማስፈጀት የማይፈነቅለው ድንጋይና የማይበጥሰው ቅጠል አይኖርም፡፡ ትግሬንና አማራን በሤራ ካጨራረሰ በኋላ የራሱን የጉግ ማንጉግ መንግሥት ለመመሥረት ከላኩት ዓለም አቀፍ ጉግ ማንጉጎች ጋር ይመሳጠራል፡፡ ይሁንና ብዙም ሳይቆይ ይነቃበታል፡፡ የተታለሉትም ወደሕዝብ ተመልሰው የራሱን መቃብር ይቆፍሩለታል፡፡ በመጨረሻም አይሞቱ ሞት ሞቶ ከነምኞቱና ከነጓደኞቹ ግብኣ መሬቱ ይፈጸማል፡፡….” ይላል፡፡ መጽሐፉን ፈልግና አንብበው፡፡ ቃላት ቢለዋወጡብህ አትገረም፡፡ እንኳን ቃላት ሰውም ይለዋወጣልና፡፡

አይገርምም? አማራን አማራ ነው ያጠፋው፡፡ አማራ ያጠፋውን አማራ ደግሞ ካለ አማራ አያድነውም፡፡ ስለዚህ የአማራ መጥፊያም ሆነ መዳኛ አማራው ነው፡፡ ሌላው እንዲሁ አጃቢና አጫፋሪ ነው፡፡ ከፈለግህ ልንገርህ፡-

ተጨማሪ ያንብቡ:  የመብት ረገጣውንና የከፋፋዮችን ሤራ በጋራ እናስወግድ! (ሸንጎ)

አማራው ዋለልኝ መኮንን – ለአማራው ሞት የመሠረት ድጋይ ጣለና ለነሻዕቢያና ትህነግ መመሥረት አንዱ ሰበብ ሆነ፡፡ በምሥረታው ረገድ አንዳንዶች ቢቀድሙትም በዕብድ ገላጋይነት እሱም ድንጋይ አቀባይ ነበር፡፡

በአያቱም በሚስቱም አማራ የነበረው መለስ ዜናዊ የአማራን መቃብር አምቦርቅቆ ከፍቶ እርሱና ጓደኞቹ የቻሉትን ያህል አማራን ገድለው ቀበሩበት፤ የተከፈተው ጉድጓድ አሁንም አማራን እየሰለቀጠ አለ፡፡ አንድ ቀን ግን ይዘጋል፡፡

አማራው ክፍሌ ወዳጆ ፀረ አማራውን ህገ መንግሥት አርቅቆ በወያኔ ፓርላማ እንዲጸድቅ አደረገና ሞተ፡፡

አማራው ሙሉጌታ አሥራተ ካሣ የሕወሓት ተላላኪና አሸርጋጅ ሆኖ ታሪክ ሠራ፤ አሁንም አለ መሰለኝ፡፡

አማራዋ ገነት ዘውዴ ለአማራ ጨፍጫፊው መለስ ዜናዊ መንታ መንታ ስታለቅስና ኢትዮጵያን ድራሹዋን ስታጠፋ አይተን ጉድ ብለናል፡፡ እሷና ብዙ ዘመዶቿ የወያኔ አገልጋይ ነበሩ፡፡ አሁንም እጅግ ብዙ አማሮች ከኦህዲድና ከኦነግ ሥር ተወትፈው ለአማራው ዕልቂት የበኩላቸውን አስተዋፅዖ እያደረጉ ያሉ አሉ፡፡

አማራው ብአዴን በግማሽም ይሁን በሩብ ጎናቸው የአማራ ነገድ ተወላጅ በሆኑ አባላቱ ከሌሎች ጠላቶች ጋር በማበር አማራን እያስጨረሰ ኢትዮጵያንም እየገዘገዘ አሁን ድረስ አለ፡፡ አማራ ያልነበሩት ግን አማራን ለማስፈጀት በወያኔ አማራ ተደርገው ለአማራው የተሾሙት እነአዲሱ ለገሠ፣ ታምራት ላይኔ፣ ተፈራ ዋሉዋ፣ በረከት ስምዖን፣ ታደሰ ካሣ፣ ኅላዌ ዮሴፍ፣ … እነዚህና ሌሎቹም በአማራው ነፍሰ ሥጋ ተጫወቱበት፡፡ እነታምራት ላይ የጥንቱ አልበቃቸው ብሎ አሁንም ሊጫወቱበት እየተሰባሰቡ እንደሆነ እየሰማን ነው፡፡ ልክም ናቸው፡፡ ከእኛ ሰው ሲጠፋ እነሱ ምን ያድርጉ?!

በአያት ቅድመ አያቶቹ ጎንደሬ መሆኑ የሚነገርለት ኢሳይያስ አፈወርቂ በጫካ ትግል ወቅት ወታደሮቹን የዒላማ ተኩስ የሚያለማምደው ከደርግ በማረካቸው የአማራ ወታደሮች እንደነበር ይነገራል፡፡ ገብሩ አሥራትን ጨምሮ ከቱባ ቱባ የወያኔ አመራሮች ውስጥ ብዙዎቹ ከአማራ የሚዋለዱ ሆነው ሳለ አማራን ሲያስጨርሱ ኖረዋል፡፡ ወይ የአማራ ዕድል!

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከነመላኩ ፈንታ በኋላ የቆመ መርከብ የሆነው ፀረ - ሙስና ኮሚሽን

በእናት በአባቱም፣ በሚስትና ልጆቹም አማራ የሆነው አቢይ አህመድ ይሄንኑ የወጣበትን ነገድ ካላስጨረስኩ ብሎ ከትግራይ እስከሸዋ በዘረጋው ወጥመድ አስገብቶ በኦሮሞ ሻጥረኛ የጦር አዛዦችና በወያኔ ጀሌ እያስፈጀው ይገኛል፡፡ ጌቾ ምላሱም አማራ ሆኖ ሲያበቃ አፉም ሆነ ሁለ ነገሩ የሚነቃው አማራ ላይ ነው፡፡ ያ በእናቱ አማራ በአባቱ ዐረብ የሆነና ኦሮሞነት ሲያልፍም የማይነካው ጃዋር መሀመድ እንኳን የአፍ ጥይት ተኩስ የሚለማመደው በአማራ ላይ ነው፡፡

ማን ማንን እያስገደለ እንደሆነ ልብ አላችሁ አይደል? አማራን ለመግደል ካሰፈሰፈና በግምባር ከተሰለፈ ኃይል- ፈረንጆችን ሳይጨምር- በሰውነቱ የአማራ ደም የሌለበት ፈልጋችሁ ማግኘት ከቻላችሁ ወንድ ናችሁ፡፡

የሚያጽናናው ግን አማራው የዘመቱበትን አማሮች ሁሉ የሚያንበረክክበትና እናት ሀገሩን ከአማሮች ሤራ የሚታደግበት ወርቃማ ዘመን ሊብት በጣም አጭር ጊዜ የቀረ መሆኑ ነው፡፡ ይህ ሁሉ ግርግርና ትርምስ ያልፋል፡፡ አልፎም ታሪክ ይሆናል፡፡ ቢሆንም እስኪያልፍ ማልፋቱ ያለ ነውና ብዙ አበሳ አለብን፡፡ ምዕራፍ ሁለት የዕልቂት ዘመቻ ለመጀመር የሽመልስ አብዲሣንና የአቢይ አህመድን ቀጭን ትዕዛዝ የሚጠብቅ በአዲስ አበባ ዙሪያ አሰፍስፎ ስለሚጠብቀው የኦነግ ሸኔ ጦር እንዳልነግራችሁ ትደነግጡብኛላችሁና ልተወው፡፡ እግዚአብሔር እንኳን ከፎከረ ከወረወረም ያድናል፡፡ ትልቁ መፍትሔ የሚገኘው ከፈጣሪ ነውና ወደ ፈጣሪያችን አጥብቀን እንጸልይ፡፡

ኢትዮጵያ የዕንቆቅልሽ ምድር፡፡

 

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share