ዝግጅት! ለማን? – ቴዎድሮስ ጌታቸው

ባለፈው የፅሁፍ መረጃ ልውውጣቸን ወቅት፤ ‹‹ትጥቅ የማስፈታት ድርድር›› በሚል ርዕስ፤ ዋናውን አሸባሪ የህ.ወ.ሓ.ት. ቡድን እና አንበጣውን ትጥቅ ከማስፈታት ውጪ፤ ሌሎች አማራጮች የሌሉ መሆኑን ተጨዋውተናል፡፡ ይህ የመረጃ ልውውጣችን ተጨባጭ ሆኖ እና መሬት ቆንጥጦ ይዞ ለመታየት! ጥቂት እርምጃዎችን ብቻ እየተጠባበቀ ይገኛል፡፡ ለዚህ ማረጋገጫ የሚሆነን! የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ጠቅላይ ሚኒስትር የህልውና ዘመቻውን በሚመሩበት ግንባር ተገኝተው፤ በሰራዊቱ ፊት የተናገሩት ንግግር ነው፡፡ ጠቅላይ ሚኒስትሩ ‹‹ጁንታው ድብደባውን አልቻልኩም እያለ ነው›› ሲሉ! የአሸባሪውን ‹‹ትጥቅ የመፍታት አይቀሬነት›› አመላክተዋል፡፡

በጠቅላይ ሚኒስትሩ የጦር ግንባር ዘማችነት እየተከናወነ ያለውን /አሁን ጽ/ቤታቸው ተመልሰዋል/፤ የተሟላ የህልውና ዘመቻ ተከትሎ፤ ሰሞኑን በሱዳን ወታደራዊ መንግስት ‹‹ጥቃት ተፈፀመብኝ›› የሚል እንጉርጉሮ መደመጥ ጀምሯል! ይህን የሱዳን ‹‹የትንኮሳ መንደርደሪያ›› ትኩረት ሰጥተን ስናጤነው! ‹‹በወረራ ተጨማሪ መሬት የመያዝ ዝንባሌ›› መስሎ ይታያል፡፡ እንዲህ ያለው ‹‹የሱዳን ዝንባሌ›› በድንገት የተከሰተ ወይም ከኢ.ፌ.ዴ.ሪ. መንግስት የመረዳት አቅም በላይ የሆነ አይደለም፡፡ ምን ማለት ነው?

የጄነራሎቹ ዝግጅት!

የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. መንግስት ሰኔ 2013 ‹‹የተናጥል ተኩስ አቁም›› ካወጀ በዃላ፤ ጠቀሜታ ያላቸው ተግባራትን አከናውኗል፤ ከነዚህ ውስጥ፡-

2ኛውን ዙር የህዳሴ ግድብ መሙላት! ይህንንም ተከትሎ የሚመጣን የውጭ ጥቃት ለመመከት! ወታደሩን በተጠንቀቅ ማቆም፤

‹‹የሩቅ ግብ ያለው ወታደራዊ ዝግጅት›› ማድረግ ነበር፡፡

ከላይ የተጠቀሰው ተራ ቁጥር 2! ማለትም ‹‹የሩቅ ግብ ያለው ወታደራዊ ዝግጅት›› በተግባር ብቻ ሳይሆን! በሀገራችን ኢትዮጵያ ጄነራሎች ንግግር የተደገፈ ጭምር ሆኖ ይገኛል፡፡ የጦር ኃይሎች ጠቅላይ ኤታማዦር ሹም ጄነራል ብርሃኑ ጁላ! ‹‹አኛ በዋናነት የምንፈልገው ጁንታውን ሳይሆን እነሱን እንደፈረስ የሚጋልቧቸውን ነው›› ሲሉ፤ ብርጋዴል ጄነራል ባጫ! ‹‹የኛ ዝግጅት ለጁንታው ሳይሆን ጁንታውን ለሚጋልቡት ነው›› በማለት የመከላከያ ሰራዊቱን የዝግጅት ምንነት! ቀደም ሲል ጀምሮ ግልፅ ሲያደርጉ ቆይተዋል፡፡ በተጨማሪም! ጠቅላይ ሚኒስትር ዐቢይ አህመድ! የመከላከያ ሰራዊቱ አካል ስለሆነው ‹‹የኮማንዶ ዝግጅት›› ሲገልፁ፤ ‹‹ጁንታው መለማመጃችን ነው›› በማለት! ስለቀጣዩ ዘመቻ ጥቆማ ሰጥተው ነበር፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ድምጻዊያን አምና በዳላስ ዘንድሮ በሜሪላንድ

ይህም ሆኖ! የጄነራሎቹን ተደጋጋሚ ገለፃዎችና የጠቅላይ ሚኒሰትሩን ጥቆማ፤ መላው የኢትዮጵያ ሕዝብ ተረድቶታል ማለት አይቻልም፡፡ ለዚሀ ማረጋገጫ የሚሆነን! አሸባሪው ህ.ወ.ሓ.ት. ሽብር በፈፀመባቸው አካባቢዎች የተፈጠረውን ችግር መነሻ በማድረግ፤ ‹‹እንዲህ እስኪሆን ድረስ መከላከያ ሰራዊቱ ምን እየሠራ ነበር›› የሚል ‹‹ቅሬታ የማቅረብ ዝንባሌ›› በመኖሩ ነው፡፡

‹‹አውነትና ንጋት እያደር ይጠራል›› እንደሚባለው፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በቅርቡ ከአሸባሪው የህ.ወ.ሓ.ት. ቡድን ጋር በተደረገው ውጊያ! ‹‹የውጭ ኃይላት›› እንደነበሩበት ይፋ ማድረጋቸው፤ በማሕበረሰቡ ውስጥ የነበረውን ብዥታ፤ በከፊል ገፎታል ማለት ይቻላል፡፡ ያም ማለት! በጦርነቱ ውስጥ የተሳተፉ ‹‹የውጭ ኃይላት›› መጋለጥ፤ በአንድ በኩል! የመከላከያ ሰራዊቱን ‹‹የሩቅ ግብ ያለው ዝግጅት›› እና የጄነራሎቹን ንግግሮች፤ የኢትዮጵያ ሕዝብ በሚገባ እንዲረዳው ያስቻለ ሲሆን፤ በሌላ በኩል! ማሕበረሰቡ ‹‹የጥፋት ፈረሱን እና ጋላቢውን›› በጠራ ምስል እንዲመለከተው አግዞታል፡፡ ይህ ኩነትም! በሂደት ሕዝቡን ‹‹የተሟላ ምስል›› የሚያስጨብጠው ይሆናል!!

የተሟላ ምስል ፍለጋ!

የተሟላ ምስል ፍለጋችን ውስጥ አሜሪካንና አጋሮቿ ‹‹እንደምንም ብለን›› የሚለውን፤ በኢትዮጰያ ላይ የሰነዘሩትን ‹‹አደገኛ የውሳኔ ሀሳብ›› ወይም ‹‹ዛቻ›› እናገኛለን፤ ይህ የምዕራባውያን ‹‹እንደምንም ብለን›› የተሰኘው ንግግር በቅጡ ሲፈተሸ! የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. መንግስትን ‹‹በኢትዮጵያ ሕዝብ ቅቡልነት›› ከያዘው ሥልጣን የማውረድ ውሳኔ ሆኖ ይገኛል፡፡ ቀጥሎም! የሽግግር መንግስት መመስረት በማለት አደገኛ የውሳኔ ሀሳባቸውን ይቋጫሉ!!

ልብ እንበል! ምዕራባውያኑ ይህን አደገኛ የውሳኔ ሀሳባቸውን ያሳለፉት፤ በአስፈፃሚነት /በተጋላቢነት/ የተመኩበት የህ.ወ.ሓ.ት. አሸባሪ ቡድን፤ ሕዝብ ከማሸበር! ንብረት ከማውደም! የሚጠላውን ማሕበረሰብ ከመጨፍጨፍ ውጪ! ውጤት ማምጣት ተስኖት አጣብቂኝ ውሰጥ በወደቀበት! ምዕራባውያኑም በቡድኑ ላይ የነበራቸው ተስፋ በተሟጠጠበት፤ በህዳር/2014 ነው፡፡

በመሆኑም የምዕራባውያኑ ‹‹እንደምንም ብለን የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. መንግስትን ከኢትዮጵያ ሥልጣኑ እናውርደው›› የሚለው አደገኛ ውሳኔ፤ ከአሸባሪው ህ.ወ.ሓ.ት. የተሻለ አስፈፃሚ /ተጋላቢ/ እንዳላቸው የሚጠቁም፤ ወይም ሌላ ‹‹ተጋላቢ ፈረስ›› ለማዘጋጀት! ቁርጥ ውሳኔ ላይ መድረሳቸውን ያመላከተ ነው፡፡ ስለዚህ ከወዲሁ ‹‹ቀጣዩ ተጋላቢ›› ማን ሊሆን ይችላል? ብለን መጠየቅና በሚገባ መለየት ይኖርብናል!!

ተጨማሪ ያንብቡ:  በመደብ ትግል የሚያምኑ በመደብ ትግል ይደመሰሳሉ - ሸንቁጥ አየለ

ቀጣዩ ተጋላቢ!

ሱዳን! የአሸባሪውን ህ.ወ.ሓ.ት. ጥቃት አድራሽና ወኪሎችን በሀገሯ ስታስጠልል፣ ስታስታጥቅ፣ አሸባሪው የሁመራን መግቢያ መውጫ ለማስከፈት ጥረት ሲያደርግ፤ ተባባሪ ስትሆን፤ እንዲሁም በኢትዮጵያ ምዕራባዊ ክፍል በሽብር ተግባር የሚንቀሳቀሰውን፤ የቤ.ሕ.ነ.ን. ታጣቂ ቡድንን እያስታጠቀች ስትልክ፤ ሱዳን! ‹‹የጋላቢነት ሚና›› ያላት መስሎን ቆይቷል፡፡ ግን ስህተት ነበር! ይህን ላስታውሳችሁ!!

ሱዳን! ከአሸባሪነት ጥቁር መዝገብ ማለትም! State Sponsor Terrorism List በአሜሪካን መልካም ፈቃድ ስትሰረዝ፤ ኢትዮጵያ ‹‹እንኳን ደስ ያለሽ›› ብላት ነበር፡፡ አሜሪካን ‹‹በህዳሴው ግድብ ስትደራደሩ በአይኔ በብረቱ መመልከት እፈልጋለሁ›› ስትል! ኢትዮጵያ፣ ሱዳንና ግብፅ ‹‹እሺ›› አሉ፤ ዋሽንግቶን ከሄዱ በዃላ አሜሪካን ሀሳቧን በመለወጥ! ‹‹ኸረ እንደውም የውሳኔ ሀሳብ ባቀርብላችሁ ማን ይከለክለኛል›› ስትል! ሱዳን ተሸቆጥቁጣ ‹‹እሺ›› ካለች በዃላ ግን! ኢትዮጵያ በሱዳን ላይ የጥርጣሬ አይኗን ልትጥልባት ችላለች፡፡

ሱዳን በዚህ አላበቃችም! አሜሪካን ‹‹የገንዘብሽን ፖሊሲ እኔ በምፈልገው መልኩ አራምጂ›› ስትላት! ሱዳን ተግባዊ ለማድረግ መፍጠኗ፤ ኢትዮጵያ በሱዳን ላይ ከጥርጣሬ ያለፈ! የመርማሪ ዐይኗን እንድትተክልባት አሰገደደ፡፡ ከግብፅ ጋር ወታደራዊ ልምምድና ወታደራዊ የጦር ትብብር ማድረጓ! እንዲሁም ሱዳን ከምዕራባውያንና ከግብፅ ጋር ስር-የሰደደ ግንኙነት ስታደርግ መቆየቷ ሲታከልበት! ምዕራባውያን በቅርቡ ‹‹እንደምንም ብለን›› ሲሉ በኢትዮጵያ ላይ ለሰነዘሩት ዛቻ! ቀጣይ አስፈፃሚ /ተጋላቢ/ በግብፅ ተባባሪነት ‹‹ጎረቤት ሱዳን›› እንደምትሆን አመላክቷል፡፡

ስለዚህ! ኢትዮጵያ ከቀጣዩ ተጋላቢ ጋር ፊት-ለፊት እስክትፋጠጥ! አስክትገጥም እና እስክታንበረክከው ድረስ! ጦርነት እንደማይቋጭ! ማንኛውም በኢትዮጵያ ውስጥና በውጭ የሚገኙ ኢትዮጵያዊያንና አፍሪካውያን! እንዲሁም የኢትዮጵያ ወዳጅ ሀገራት አመራሮችና ሕዝቦች! ጠንቅቀው ሊያውቁት ይገባል!!

የኢ.ፌ.ዴ.ሪ. ጠቅላይ ሚኒስትሩ፤ ከግንባር ዘመቻ ወደጽ/ቤታቸው የመመለሳቸው ምክንያትም! ከዚሁ ጋር የተያያዘ እንደሆነ፤ ማለትም! ቀጣዩን ተጋላቢ ከነግብረ-አበሮቹ ‹‹የማንበርከክ እቅድ›› ለመንደፍ እና ጅማሬውንም ለማብሰር እንደሆነ ይታመናል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሰሜን ኮሪያና ወጣቱ ዝንጀሮ

ቀጭን መጠቅለያ!

ይህ ወቀት! ‹‹አንገብጋቢ ወቀት›› ነው!! በዚህ አንገብጋቢ ወቅት እኛ ኢትዮጵያውያን አሸባሪውን ህ.ወ.ሓ.ት. ትጥቅ ከማስፈታት ባሻገር! ቀጣይ ለሆነ ዘመቻ ራሳችንን እንድናዘጋጅ የሚመከርበት ወቅት ነው፡፡ በዚህ አንገብጋቢ ወቅት! መሰላቸት፣ መልፈስፈስ፣ ማጉረምረም እና መዘናጋት! ቦታ አይኖራቸውም፡፡ ምክንያቱም! እንዲህ ያለው አደገኛ አካሄድ ‹‹ስውር ተጋላቢ›› መሆንን ያስከትላል!!

ልብ እንበል! ‹‹ስወሩ ተጋላቢ›› ከሌላ ቦታ የሚመጣ አይደለም፤ ‹‹ስውሮቹ ተጋላቢዎች›› በዚህ የኢትዮጵያ እና የአፍሪካ ቀንድን ህልውና የመታደግ ጦርነት ውስጥ፤ መሰላቸትንና መዳከምን ከሚያሳዩ! እንዲሁም ባለ-ፅኑ አቋምተኞችን ከሚያዳክሙ! ከኛው ወንድምና እህቶች ውስጥ የሚፈልቁ ናቸው፡፡

ይህ ‹‹አንቂ የፅሑፍ መረጃ›› ያስፈለገው ድል እንዲገኝ ለመርዳት ብቻ አይደለም! በጥቃቅን ስህተት ችግር ከመፈጠሩ እና ‹‹የነበር ቁጭት›› ውስጥ ከመውደቃችን በፊት! የሚዋደዱ፣ በኢትዮጵያ ምድር ለኢትዮጵያና ለአፍሪካ ቀንድ ህልውና በአንድነት የሚዋደቁ! እህትና ወንድሞች መሀል! ዃላ የሚመጣውን የእርስ-በርስ ‹‹መራር መወቃቀስ›› ለማስቀረት ጭምር ነው፡፡

ሠላም ለኢትዮጵያ ሠላም ለአፍሪካ

ቴዎድሮስ ጌታቸው

/ደራሲና የፖለቲካ ተመልካች/

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share