የኢትዮጵያ ሕዝብ በተለይም አማራ ሆይ ከዳግም ክህደት ተጠንቀቅ! – አገሬ አዲስ

ህዳር 24ቀን 2014ዓም(03-12-2021)

በአለፉት ዓመታት ጠቅላላ የኢትዮጵያ ሕዝብ የአማራው ማህበረሰብ በተለይ የመንግሥት ሥልጣኑን በተቆጣጠሩት ሃይሎች ሲከዳ፣ሲፈነገል መቆዬቱ አይካድም።በስሙ እዬማሉ እዬተገዘቱ የሰቆቃ ሰለባ እንዳደረጉት አይዘነጋም።አንዱ ወርዶ ሌላው በተተካ ቁጥር የሚደርስበት ግፍና በደል ብሎም ክህደት የበዛ እንጂ ያነሰ አልሆነም።ያንን ክህደት በፕሮፓጋንዳ ዘመቻ፣ባድር ባይ ጋዜጠኞችና አውደልዳዬች ሽፋን እንዳይታወቅ እርብርቦሽ ሲደረግ ታዝበናል።የግፉ ሰለባ የሆነው ግን  በሚገባ ያውቀዋል።

አጎንብሶ ቢሄድ ሞኝ አይደለም በጉ፣

ነገርን ካልተውት ናቅ እያደረጉ።

ለአገሩ ሰላምና አንድነት ሲል መከራውን ችሎ መታገሱ ግን ከጅልነት እዬተቆጠረበት ፣ይሉኝታቢስ መሪዎቹና አጨብጫቢዎቹ በለመዱት የሃሰት መንገድ መንጎዳቸውን አላቆሙም።ዛሬም እንደ ትናንቱ ሕዝቡን በመናቅ ለሥርዓቱ ተገዥና መሪዎቹን አማኝ እንዲሆን የግለሰብ ጣኦት እዬገነቡለት ነው።የሩቅ ጊዜውን ትተን ከዓመት በፊት ወያኔ በመከላከያ ጦር አባላት ላይ የፈጸመውን ታሪክ ይቅር የማይለው ሸፍጥ፣ክህደትና ወንጀል ተከትሎ በወያኔ ቁጥጥር ስር የነበሩትን የመከላከያ አባላትን ህይወቱን ገብሮ ፣በቦምብ ላይ  እዬተራመደ፣ደረቱን ለጥይት ገብሮ  ነጻ ያደረገውን  የአማራ ፋኖና ፣ሚሊሽያ እንዲሁም ልዩ ሃይል  የጀብዱ ሥራ  እግሬ አውጭኝ ብለው ለሸሹት  የመከላከያ አመራሮች ጠቅልሎ በመስጠት ባለውለታዎችን እንዳልነበሩ የማድረግ ክህደት መፈጸሙ አይረሳም።ይህ  ቁጥር አንድ ክህደት ሆኖም ይመዘገባል።በጊዜው የኦሕዴድ/ብልጽግና መሪ አብይ አህመድም ሳይቀር ያሞገሰው ተጋድሎ ነበር።እነባጫ ደበሌም እንዲህ አይነት ጀግንነት ታይቶም ተሰምቶም አይታወቅም በማለት አድንቀውት ነበር።ታዲያ ምን ያደርጋል ሳይውል ሳያድር የአማራ  ፋኖን፣ ሚሊሽያንና ልዩ ሃይሉን ባመሰገኑበትና ባደነቁበት አፋቸው የድሉን ባለቤትነት ለድል ቁርሱ፣ለአፈንፋኙና ለሳተናው ለሚባሉት የሽሽት ፊታውራሪ ጀነራሎች ጠቅልለው ሰጡት።

ወርቅ ላበደረ ድንጋይ ሆነና አማራው ለዋለው ውለታ ምላሹ ወያኔ አንሰራርቶ ከገባበት ጉድጓድ ወጥቶ ጦርነትና ወረራውን በአማራውና በአፋሩ  መሬት ላይ እንዲያደርግ ዕድል ተሰጠው፤ዕድልም ብቻ ሳይሆን ትጥቅና መሣሪያውንም አስረክበውት ለአንድ ዓመት የዘለቀ መከራና ግፍ እንዲቀበል አደረጉት።

ያ ዱቄት ሆኗል፣እንኳንስ በወታደራዊ ጠንካራ አቋም ይቅርና በአንድ ጋንታ (ዘጠኝ ሰው)ደረጃም ለመሰባሰብ ከማይችልበት ደረጃ ላይ ነው ያሉት የወያኔ የጥፋት ሃይል ለዳግመኛ ጦርነት እንዲበቃ አደረጉት።ይህም ብቻ አይደለም የምዕራባውያን ወያኔን ደግፎ ተቃውሞና ጫጫታ ሲበዛ የችግሩ ተጠያቂ አማራው እንደሆነና አብይ አህመድ የሚመራው መንግሥት ለድርድር ፈቃደኛ እንደሆነ ለማሳዬት ዳር ዳር ማለት ጀመረ።እምቢተኞቹና ያስቸገሩኝ ሌሎች ናቸው በማለት ጣቱን ወደ አማራው ላይ ጠቆመ።ይህም ቁጥር ሁለት ክህደት ነው።

እብሪት የነፋው ወያኔ ግን ከአራት ኪሎ ቤተመንግሥት ባለቤትነት ውጭ የምቀበለው ድርድር የለም በማለቱ ፣የደጋፊዎቹን ጫጫታ በመተማመን ጥቃቱን በአማራውና በአፋሩ  ላይ እያስፋፋው በመሄድ ለአብይ መንግሥት አደገኛ ሁኔታ ለመፍጠር ጫፍ ላይ ደረሰ።የአማራውና የአፋሩ  ማህበረሰብ ልጆች፣ፋኖና ሚሊሽያ እንዲሁም የልዩ ሃይል አባላት ለጥቃቱ ሳይንበረከኩ ትግላቸውን ቀጠሉ።ትንሽ የማይባሉ የመከላከያው የጦር መሪዎች ለወያኔ አጋር በመሆን መረጃ ከማቀበል አልፈው የአማራውን ታጋይ ከጀርባ ወጉት፣አሶጉት። አፈግፍግ፣ተመለስ፣አትተኩስ፣አትከላከል በሚል ፈሊጥ አዳክመው ሕዝቡም በሃሰት የሽብር ወሬ ቦታውን እዬለቀቀ እንዲሰደድ አደረጉት።ወያኔም በተለቀቁት ቦታዎች ለመንሰራፋትና ለመግደል ንብረትም ለመዝረፍና ለማውደም በሩ ተከፈተለት።ክህደት ሶስት ተብሎ ይመዝገብ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ፍቅራችን የት ገባ? - ከተማ ዋቅጅራ

በራሱ ስንቅና ትጥቅ የሚታገለው የአማራውና የአፋር ልዩ ሃይል፣ ፋኖና ሚሊሽያ ያለ የሌለ አቅሙን ሰብስቦ ወያኔን  ከያዘበት መሬት ጠራርጎ ለማውጣት ፍልሚያውን በመቀጠል ብዙ መስዋዕት ከፈለ።የወያኔ ጦር ከከሃዲ የመከላከያ አባላትና ከቀሩት ጸረ ኢትዮጵያ ከሆኑት ሃይሎች ጋር በማበር የወረራ ጉዟቸውን ወደ አዲስ አበባ ሲቀጥሉ ከዙፋኑ የመውረዱን ስጋት ተከትሎ ሊደርስበት የሚችለው ውርደት አሳስቦት በመሸ ሰዓት የአማራ ፋኖና ሚሊሽያ ባደረገው ተጋድሎ በተፈጠረው የድል ዋዜማ አብይ አህመድ ጦር ሜዳ ሄዶ የድሉ ባለቤት ሆኖ ብቅ አለ።አጃቢዎቹና አጨብጫቢዎቹም እሱን ተከትለው ማዘጥዘጥ ጀመሩ።በድል አጥቢያ አርበኝነት መሬትና ሰማዩን በጫጫታ ሸፈኑት። አብይ አህመድ የጦሩ ገበሬ ፣የድሉ ባለቤት፣ሶስተኛው ሚኒሊክ፣ ናፖሊዮንወዘተ እያሉ የማይገባውን ስምና ዝና አሸከሙት።እርግጥ ነው አብይ የጦር ሃይሉ አዛዥ እንደመሆኑ ባይዋጋም በጦር ሜዳው መገኘቱ ለመከላከያ ወታደሩ ሞራል አስተዋጽኦ አድርጓል፤ለፋኖና ለሚሊሽያ እንዲሁም ለልዩ ሃይል አባላት ግን የጨመረው ጀግንነት የለም።ከመዝመቱም በፊት ሆነ በዃላ በትግላቸው ላይ ለውጥ አላመጣም።የነሱ የትግል ሞተር የአገር ፍቅር እንጂ  የኦህዴድ  መሪ የአብይ አህመድ ፍቅርና መዝመት አይደለም።ይህንን እውነት የሚገልጹትን አንደበታቸውን እያፈኑ በሃሰት ውንጀላ ለማሸማቀቅ ተሞክሯል፣እዬተሞከረም ነው።ከዛም አልፎ የግንኙነት መረባቸው እንዲበጠስ ተደርጓል።ለማወናበድ ነጻ ሜዳ ያገኙት እበላ ባይ ቅጥረኞቹ ብቻ ናቸው።እንደፈለጉ ይገባሉ ይወጣሉ።የፈለጉትን ይቀባጥራሉ።

ትናንት የሚኒልክን ስም ለማንሳት የሚጠሉት በምኒሊክ ስም ዘማቾች ነን ብለው አረፉ። ትናንት አማራ የለም ይሉ የነበሩት በአማራው መሬት የሚገኙትን ሆቴሎች አጣበቧቸው።እንዲያ ነው ዘመቻ ማለት! ያንን ተከትሎ ተከፋይ ጋዜጠኛ እንደ ቆርቆሮ መጮህ፣እንደ ገደል ማሚቶ ማስተጋባት ያዘ።የአማራና የአፋር ልዩ ሃይል፣ ሚሊሽያ ና ፋኖ ስም ላለመጥራት ምሎ ተገዘተ።ሌላው ቀርቶ አማራውን እንወክላለን ብለው ሲቀባጥሩ የነበሩት የፖለቲካ ድርጅቶች ሁሉ የፋኖንና የሚሊሽያውን ተጋድሎ ጠቅልለው ለአብይ አህመድና ለመከላከያ አሸከሙት።የአማራውን ተጋድሎ፣የፋኖንና የሚሊሽያውን ተሳትፎ መኖሩንም እረሱት።እንዲያ ነው አድር ባይነት! ክህደት አራት

እዚህ ላይ አንድ የማይካድ ነገር ቢኖር በመከላከያ ውስጥ ከሃዲና ባንዳዎች እንዳሉ ሁሉ አገር ወዳዶችና ለተገኘው የድል ጅማሮ ከፍተኛ አስተዋጽኦና ድርሻ ያላቸው መኖራቸውን መካድ አይገባም።በነዚህና በአማራውና በአፋሩ ፋኖና ሚሊሽያ ብሎም በአገር ወዳዱ ኢትዮጵያዊ እርብርቦሽ የተገኘ የድል ምዕራፍ  ነው።የድል ምዕራፍ ሲባልም ጦርነቱ ገና ያላበቃ መሆኑ እንዲታወቅና ሙሉ ለሙሉ ድሉ የሚጠናቀቀው ግን ወያኔ ሞቶ ሲቀበር፣ በአገራችን የረጨው መርዛማ አስተሳሰቡና አጋሮቹ ሁሉ አብረውት ድባቅ ሲመቱ ነው።የጥፋት መመሪያ ሰነድ የሆነው ሕገመንግሥቱ ተቀዳዶ ሲጣል ነው።ያ ካልሆነ ችግሩ በሌላ መልክና በሌላ ቦታ ሊያንሰራራ የሚችልበት ዕድሉ ከፍተኛ ነው።አሁን ወያኔ ተሸነፈ ተብሎ  የድል ነጋሪት እዬጎሸሙ ለኦነግና ለመሰሎቹ ጸረ ኢትዮጵያ ሃይሎች ጊዜና ቦታ መስጠት አይገባም።የወያኔን ጥላ ተከትለው ተመሳሳይ አገር አጥፊ ፣በተለይም አማራውን ከምድረገጽ ለማጥፋት የተሰለፉት ሃይሎች አቅማቸውን እንዲገነቡ ድጋፍ የቸራቸው መንግሥት የዚያው የጥፋት ሃይሉ  አካል መሆኑን ማመንና አደጋውን ለመቋቋም የሚያስችል አቅም መገንባት ለነገ የማይሉት ተግባር ነው።መንግሥት ለነዚህ የጥፋት ሃይሎች አጋር ነው ሲባል ውሸት አለመሆኑ የሚረጋገጠው በኦሮሚያ በሚባለው ክልል ውስጥ እንደልቡ የአማራውን ማህበረሰብ እያረደና እያፈናቀለ፣እየዘረፈ የሚገኘውን ቡድን በዝምታ ማለፉ፣ኦሮሞን ኦሮሞ አይገለውም በሚል ሽፋን የሌላውን መገደል እውቅና በመስጠት፣በክልሉ ሚሊሽያ ስም በመቶ ሽህ የሚቆጠር ጦር ከነሙሉ ትጥቁ እንዲደራጅ መፍቀዱና ማገዙ፣አማራው ጥቂት የሚሊሽያ ጦር አሰለጠነ ተብሎ የሚወርድበት ጫናና ዘመቻ፣የፋኖ መሪዎች ናቸው የሚባሉትን በድብቅና በገሃድ ማሳደዱ፣መግደሉ፣በመከላከያ ስር ይሁኑ በሚል ስበብ ትጥቅ ማስፈታቱ፣ለአማራው የሚቆረቆሩ የጦር አዛዦች መታፈናቸው፣ ይህ ሁሉ የወደፊቱን የተረኞች የጥፋት ጉዞ፣የኦህዴድንና የኦነግን የዳግማዊ ወያኔ የመሆን ሂደት ቁልጭ አድርጎ ያሳያል።ልዩነታቸው በሥልጣኑ መከፋፈል እንጂ በዘር ፖለቲካ ኢትዮጵያን በመበታተኑ ዘላቂ ዓላማ አይደለም።ያማ ባይሆን ኖሮ ኦነግ ሸኔ በተባለ የዳቦ ስም የሚንቀሳቀሰውን ትንሽ ቡድን በመቶ ሽዎች የሚቆጠረው የኦህዴድ ስልጡን ሚሊሽያና ልዩ ሃይል በቀናት ሳይሆን በሰዓታት ውስጥ እንዳልነበረ ባደረገው ነበር።ለዚያም ነው የኦነጉ መሪ ዳውድ ኢብሳ ማን ማንን ይነካል፣ማን ማንን ትጥቅ ያስፈታል ሲል በእብሪት የተናገረው።ይህንን አልሰማሁም አላዬሁም የሚል ካለ አንድም በጥቅምና በፍርሃት ህሊናውን የሸጠ አለያም የቡድኖቹ ተባባሪና ደጋፊ የሆነ ብቻ ነው።     

ተጨማሪ ያንብቡ:  መክሸፍ እንደ ወያኔ! ህብረት ህብረት የሚያውድ ሰልፍ ተወጣልሽ።ኢትዮጵያ ደስ ይበልሽ! - ቢላል አበጋዝ

ሊከሰት የሚችለው ሌላው ክህደት

ወያኔ ተበታትኖ ተምቤን ሸለቆ ውስጥ በሚርመሰመስበት ጊዜ ዱቄት ሆኗል ያለው ባጫ ደበሌ አሁን ደግሞ ተደብቆ ከከረመበት ዋሻ ብቅ ብሎ ወያኔ ከእንግዲህ አደጋና ስጋት አይሆንም የሚል መልእክት ሲቀባጥር ተሰምቷል። አብይ አህመድም ጦርነቱ ተጠናቋል የሚል ትጥቅ የማስፈታት ዲስኩር አሰምቷል። ይህንን ይዘን የድሉ ባለቤት አብይ አህመድ ነው የሚለውን ቱሪናፋ ስብከት ስንጨምርበት የአማራው ፋኖና ሚሊሽያ የታገለለት የማንነት፣የራያና አዘቦ ፣የወልቃይትና ጠገዴ ጥያቄ ምን መልስ ሊሰጠው ይችላል ወደሚለው ጥያቄ ብናመራ የሚከተሉት ሊሆኑ እንደሚችሉ መገመት አያቅትም።

አብይ አህመድ በምዕራባውያን የተወነጀለበት የጀኖሳይድ ክስ እንዳይመሰረትበት፣ ለመንግሥቱ ዕውቅና ለማግኘትና የነፈጉት  ዕርዳታ እንዲቀጥል የአማራውን ጥያቄ አሳልፎ እንደሚሰጥ ጥርጥር የለውም።ይህንንም ደግሞ ደጋግሞ በሕገመንግሥቱ መሰረት ይታያል በሚለው አቋሙ ገልጾታል። ጦርነቱ ውስጥ የገባነው ወያኔ በወረራ ከያዘው መሬት እንዲወጣና የእኔን መንግሥት ዕውቅና እንዲሰጥ ነው በሚል ሽፋን አሁን በድል አድራጊነት የሚገሰግሰውን ሕዝባዊ ጦር ባለበት ቦታ ላይ እንዲቆም፣ተከዜን አልፎ ሄዶ ወያኔን እስከመጨረሻው ድባቅ መትቶ የትግራይንም ሕዝብ ከዚህ አውሬ ቡድን መዳፍ እንዳያላቅቀው በመሰንከል፣ ለወያኔ የክልሉ ባለቤትነትን እውቅና ሰጥቶ ድርድር ከማድረግ እንደማይመለስ ያለፉት ታሪኮቹ አመላካቾች ናቸው። ከማድረግም አይመለስም።የዘፈን ዳር ዳሩ እስክስታ ነው እንደሚባለው የጦርነቱ ተጠናቀቀ ወሬ ያንኑ ያመላክታል።

የኢትዮጵያ በተለይም የአማራ ሕዝብ ሆይ

በስከ ጀርባ የሚሰራብህን ቁማርና ደባ አጢነው።በሥልጣን ላይ ያለውን ጎሰኛና ተረኛ የኦሕዴድ /ኦነግ ቡድን በሥልጣኑ ላይ ለረጅም ጊዜ ለማቆዬት መሪውን ከአምላክ እኩል አድርገው ፣እንደጣኦት የሚያመልኩትን፣አድርባዮች አትስማቸው።አሁን በሥልጣን ላይ ያሉት ላለፉት ሰላሳ ዓመታት በተለይም  ላለፉት ሦስት ዓመታት ለገፋኸው አስከፊ ኑሮ ተጠያቂዎች መሆናቸውን አትርሳ። የሚመሩት ስርዓት በክልል ላይ ክልል እዬጨመረ የልዮነት ግንብ ገንቢ መሆኑን አትዘንጋ።ነገ ደግሞ ክልል የራሱን ዕድል በራሱ ይወስን ይልህና ያችኑ አንቀጽ ሰላሳ ዘጠኝ መዞ አገረ ቢስ ያደርግሃል።ሕገመንግሥቱ ወይም ሞት የሚለው ያለ ምክንያት አይደለም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የወያኔን የጥፋት ድግስ እናምክን!

በዓላማ ሳይሆን በሥልጣን ሽኩቻ ተቃርነው በውጭና በውስጥ ያሉትን ጠላቶችህን  አትዘንጋ፤በምዕራባዊያን ድጋፍ አገርህን ለመበታተን ሴራ የጎነጎኑት የባዕዳን ፈረሶች እንዳይጋልቡህ ከወዲሁ ሰንክላቸው። በተሻለ ቁመናና አደረጃጀት ሃይልህን ገንባ።ሃይል መገንባት ጦረኛ መሆን ሳይሆን ከጦረኞች ተከላክሎ ለመዳን መሆኑን አስብ፤ጠላቶችህ መታጠቅ የሰላም ጸር መሆን ነው የሚሉትን ማዘናጊያ አትቀበል።ሕግ ያላስከበረውን መብት ሃይል ያስከብረዋል የሚለውን ምክር አስታውስ።በእርዳታ ስም የምዕራባውያን በማር የተለወሰ መርዝ  ተግተህ እንዳታልቅ በራስህ ተማመን።ሆዱ የሞላ ባሪያ ከመሆን የተራበ ነጻ ደሃ መሆን ይሻላል፤ምክንያቱም የህልውና ነጻነት ከሁሉም በላይ ነውና።የጊዜውን ድህነትህን በነጻነት አገር ሠርተህ ትሻገረዋለህ። የጊዜውን የርሃብ አደጋ ለማሶገድ በለምለሙ መሬትህ ላይ ብትዘራ በሶስት ወር ውስጥ የተትረፈረፈ ምርት ታገኛለህ። በበረዶና በአሸዋ የተዋጠ መሬት ያላቸው አገር ሕዝቦች ሳይራቡ፣ከራሳቸው ተርፈው ለአንተም እረጂ ሲሆኑ ማዬቱ ልብ ይሰብራል።ከዚያ የበታችነት ለመውጣት ፍላጎቱ ካለህ ቀላል ነው።

ለድህነት የዳረገህ የባዕዳን ባሪያና አገልጋይ የሆነ መብትህን የማያስከብር  ዘርፎ የሚያዘርፍ መንግሥትና ስርዓት በመስፈኑ ነው።የአንተ በነጻነት መኖር ለሌላው አፍሪካዊ ምልክትና ፋና ወጊ ነው።እምቢ ለባዕዳን አገዛዝ ማለት የቆዬ ልማድህ ነውና ዛሬም ሆነ ወደፊት አትበርዘው፤ሊበርዙ የሚነሱትን ፊት ንሳቸው።ለጊዜያዊ ምቾትና ጥቅም ህይወትህን አትበክለው፤መጭውን ትውልድም የባዕዳን እስረኛ አታድርገው።በራስህ ባሕል፣ በራስህ እምነት ኩራ።በራስህ ምርት ተጠቅመህ የአገርህን ኤኮኖሚ ገንባ፤ኑሮህን አሻሽል።ለባዕዳን እምነትና መጥፎ ልማድ እጅህን አትስጥ።ታሪክህን የሚያበላሹትን ጥረታቸውን አበላሽ።ለባርነት እራሳቸውን ያጩትን ከተቻለ ወደ ቀልባቸው እንዲመለሱ አድርግ።ኢትዮጵያዊ ማንነቱን የሚክደውን ለኢትዮጵያ ባለቤትነት አትፍቀድለት። በአሜሪካ መራሹ የምዕራባውያን ሴራ ገመድ ውስጥ ተብትበው ሊጥሉህ የሚቅበዘበዙትን ሃይሎች በዝምታ አትለፍ።ለዳግም ባርነትና ቅኝ ግዛት ቀንበር  በተዘዋዋሪ መንገድ ሊጭኑብህ በዴሞክራሲና በሰብአዊ መብት ሰበብ የሚያሴሩትን የምዕራባውያንን ተንኮል  መክትና አክሽፍ። አሁንም በጎረቤት አገሮች ድንበር በኩል የጥፋት ሃይሎችን አሰርጎ ለማስገባት ደፋ ቀና እያሉ ነውና አትዘናጋ፣ጎረቤቶቼ አያስጠቁኝም ብለህ ሙሉ ለሙሉ አትተማመን።እነሱም በቋፍ ላይ ስለሆኑ የምዕራቡን ድጋፍ ለማግኘት ኢትዮጵያን የመስቀል በግ ከማድረግ እንደማይመለሱ አውቀህ  በንቃት ተከታተል።እምነትህ በራስህና በፈጣሪህ ላይ ብቻ ይሁን።  

በዬቦታው በስምህ እርዳታ የሚሰበስቡትን ለመቆጣጠር አንድ የእርዳታ አሰባሳቢ ማእከል ይኑርህ፣ትግልህንም በእቅድና በስልት የሚመራ የጋራ አመራር ያለው ማእከል ፍጠር።የተበታተነውን ሃይልህን ሰብስብ።በጎጥና በመንደር ህሳቤ እንዳትበከል ተጠንቀቅ፤ከሰርጎ ገቦችም እራስህን ተከላከል።

የአማራው ትግል ኢትዮጵያንና ኢትዮጵያዊነትን ብሎም አፍሪካዊነትን  ለማስከበር ነው!

ድል ለኢትዮጵያ ሕዝብ!

አገሬ አዲስ

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share