እራስ ሳይጠና ጉተና! – አገሬ አዲስ

ህዳር 8 ቀን 2014 ዓም(17-11-2021) ከአገሬ አዲስ

ገና አራስ ቤት ባለ፣ባልጠነከረ በህጻን ጭንቅላት ላይ ሹርባ እጎነጉናለሁ ወይም ጎፈሬ አበጥራለሁ አይባልም።ቢታሰብ እንኳን የጅል ምኞት እንጂ ተግባራዊ አይሆንም።በህጻኑ አናት ላይ የሚፈልጉትን የጸጉር አሠራር ለማዬት ልጁ ማደግና መጠንከር ጸጉሩም መብዛትና መደንደን አለበት።ለዚያም ነው እራስ ሳይጠና ጉተና የሚባለው።

ይህንን አባባል እንደምሳሌ ወስደን በሌላውም ቦታ ብንተረጉመው ለምናስበውና ለምንመኘው ሁሉ መዳረሻ የግድ ብቃትና ጥንካሬ መኖሩ ቅድመሁኔታ ይሆናል።በቅጡ አስበውና ተሰናድተው ያልጀመሩት ጉዞ ወይም ተግባር ገና ከጥዋቱ ሳይጀምሩት ይሰናከላል።እንደህጻኑ ጉተና ምኞት ብቻ ሆኖ ይቀራል።

በዚህ እርዕስ ስር ይህንን ጽሑፍ ለማዘጋጀት ያነሳሳኝ የአማራው ማህበረሰብና ያለበት አስከፊ ሁኔታ ስላሳሰበኝ ሲሆን ከገጠመው አደጋና የህልውና ጥያቄ አኳያ፣ከሚከፍለው መስዋእትነት አንጻር የጎደለው ነገር ቢኖር እንዲሟላ የበኩሌን አስተያዬት ለመሰንዘር ነው።እውነቱን ሳይደብቁና ሳይሳሱ፣ብሎም ሳይፈሩ መግለጽ ለተነሱበት ዓላማ ሊኖር የሚገባውን ክብር ከማሳያቱም በላይ ለስኬቱ ያለን ፍላጎት የማሳያ እርምጃ ነው።ስለሆነም ከነቀፋና ከአጉል ትችትና እንዲሁም ከዘለፋ እንዳይቆጠር ከወዲሁ ማሳሰብ እወዳለሁ።ባያሳስበኝ ኖሮ ብዕሬንም አላነሳም ነበር።

እንደሚታወቀው የአማራው ማህበረሰብ ለራሱ ሳይኖር ኢትዮጵያንና ሌሎቹን ወገኖቹን በነጻነትና የትልቅ አገር ባለቤት ሆነው እንዲኖሩ መስዋዕት የከፈለ ጀግናና ደግ ማህበረሰብ ነው።ከጎጥና የጎሳ አመለካከት ተሻግሮ በሃገራዊ አመለካከት የዳበረ የታሪክ፣ የባህል የቋንቋ፣የስነልቦና ባለቤት የሆነ ማህበረሰብ ነው።በኢትዮጵያዊነቱ የማይደራደርና ከማንኛውም ጎሳ ጋር በፍቅር፣በጋብቻ፣በብዙ ማህበረሰባዊ ግንኙነቶች ሕብረብሔራዊ አገር የገነባ ለመሆኑ እንኳንስ ወዳጆቹ ጠላቶቹም ጠንቅቀው ያውቃሉ።ይህም በመሆኑ ነው ኢትዮጵያን ለማፍረስ የሚሹ የውጭና የውስጥ ጠላቶቹ ተረባርበው በዬጊዜው ሊያጠፉት የሚነሱት።ከኢትዮጵያ አልፎ ለአፍሪካ ብቻ ሳይሆን ለጥቁር ሕዝብ ነጻነት የከፈለው መስዋዕትነት በታሪክ ጎልቶ ይታያል። ያም በወራሪዎችና ቅኝ ገዢዎች መንጋጋ አስገብቶት ኖሯል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ወያኔ በ«ዐማራ ክልል» ለኤች. አይ. ቪ. ኤድስ በሽታ መከላከያ ብሎየሚያሠራጨው መድኃኒት በሽታውን የማይከላከል መሆኑ ተገለጠ

ከሃምሳ ዓመታት ወዲህ በአማራው ማህበረሰብ ላይ የሚደርሰው በደልና የማጥፋት ዘመቻ ከሰላሳ ዓመት ወዲህ በተለይም ባለፉት ሦስት ዓመታት ተጠናክሮ በሞትና የሽረት ጫፍ ላይ አድርሶታል።ከማንኛውም ጊዜ የበለጠ የተቀናጀ ዘመቻ ተከፍቶበት አገሬ ብሎ ከተቀመጠበትና ለዘመናት ከኖረበት ቦታ እዬተፈናቀለ፣እዬተገደለ፣ንብረቱ እዬወደመና እዬተዘረፈ በbg,ዛ ሃገሩ ስደተኛ ሆኖ አሰቃቂ ደረጃ ላይ ደርሷል።ይህንን ፀረሰው የሆነ ድርጊት ለመቃወም የግድ አማራ መሆን አያስፈልግም፤ እንደሰው የሚያስብ የዬትኛውም አገር ዜጋና ጎሳ ሊያወግዘውና ከተጠቂው የአማራ ማህበረሰብ ጎን ሊሰለፍ ይገባዋል።ወቅቱ ለሰብአዊነት የመቆምና ያለመቆም ፈተና የሚቀርቡትና የሚያልፉበት ወይም የሚወድቁበት ጊዜ ነው።ከአማራው ጎን መሰለፍ ማለት ለአማራው ብቻ ሳይሆን ነግ በኔ ብሎ ከሚመጣው አደጋ እራስንም ጭምር ለማዳን መሆኑን መረዳት ተገቢ ነው።ኢሰብአዊነትና ጎሰኝነት ድንበር የለውም።በተመቸው ጊዜ ሁሉንም ያዳርሳል፤ይበክላል።ያጠቃል።

አማራው እዬደረሰ ካለበት ግፍና መከራ ብሎም የህልውና አደጋ ለመገላገል አሁን አንገቱን ቀና በማድረግ ላይ ይገኛል።ምንም እንኳን የዘገዬ ቢመስልም ጭራሹን ከመቅረት ይሻላል።በዚህ የመነሳሳት ጅማሮ ላይ ሌላ ተጨማሪ ሃላፊነትና ግዳጅ ሊሸከም አይገባውም።መጀመሪያ እራሱን ማጠናከርና ከአደጋው መትረፍ የመጀመሪያው ግዳጁ ሊሆን ይገባዋል።ያንን ስኬታማ ለማድረግ እራሱን አደራጅቶ፣በአንድ አመራር ሥር ሆኖ አቅሙን ገንብቶ መገኘት አለበት።ጠላቶቹ የያዙትን የመሳሪያ፣የገንዘብ፣የመረጃ አቅም መያዝ ይኖርበታል።በተበታተነና ባልተቀናጀ መልኩ የሚያደርገው መከላከል ከጥቅሙ ጉዳቱ ያመዝናል።በሌሎቹ አጋር ሃይሎች ጉያ ከመሸጎጥና ከመተማመን በራሱ አቅም መተማመንና በሁለት እግሩ መቆም ይኖርበታል።በየአቅጣጫው የሚታዬው እምቢ ባይነት ስሜትና ወኔ በበሰለ አመራርና ስልት ካልታገዘ ለጠላቶቹ የተመቼ ዒላማ ይሆናል።

ኢትዮጵያን የሚያድነው እራሱ ሲድን ነው።ሌሎቹም ሊኮሩና ሊያከብሩት ብሎም ከጎኑ ሊሰለፉ የሚችሉት ጠንካራና አስተማማኝ ሃይል ሲኖረው ነው።ደካማና ደሃን ልጅ እናቱም አትወደውም እንደሚባለው አማራው ደካማና ልፍስፍስ ከሆነ ለደቃቆቹ ፣ከሱ በቁጥር ለሚያንሱትም መጫወቻና መቀለጃ ይሆናል።ታሪኩን ማደስ የሚችለው ጠንክሮ ሲወጣ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሉባ ገዳ፡  የጨፍጫፊወች ዕድር

አማራው በራሱ መተማመን አለበት።ሰፊ ለም መሬት፣በቂ ውሃ፣ብዙ ህዝብ፣ልዩልዩ ማዕድን ያለው ከባቢ ባለቤት ነው።ከራሱ አልፎ ለሌላው ይተርፋል።ስደትንና ልመናን ሊጠዬፍ ይገባዋል።ብዙ የተማሩ ልጆች ስላሉትም ከዘመኑ እድገትና ስልጣኔ ዃላ ቀር አይሆንም።የሚቀረው ይህንን ተገንዝቦ አንገቱን ቀና አድርጎ መሄዱ ብቻ ነው።ጭንቅላቱን የማይሸከም አንገት የለም!

አማራውን ማገዝና መደገፍ ማለት ጎሰኝነትን ማራመድ አይደለም።የሰብአዊነት ግዴታ እንጂ።በተጨማሪም የኢትዮጵያን ትንሳኤ ለማረጋገጥ የግድ ለኢትዮጵያ ዋልታና ማገር የሆነውን የአማራ ማህበረሰብ እንዲኖር ማገዝንና መርዳትን ይጠይቃል።በታሪኩ አማራ ጸረ ኢትዮጵያዊነትና ጠባብነት የለውም።አሁንም አማራ ነኝ ብሎ ለመነሳት ያስገደደው አማራ ነህ ተብሎ የሚደርስበት ግፍና በደል ነው።

ሁሉን ነገር ችሎ የተኛውን በሬ፣

ነካክተው ነካክተው አደረጉት አውሬ።

ኢትዮጵያን ለማስከበር የግድ አማራው እራሱን ማስከበር ይኖርበታል። በመካከሉ የሚረጨውን የጎጥ መርዝ ደፍቶ በአማራነት መሰባሰብ የግድ ይላል። አለበለዚያ

እምብዛም ሞኝነት ለበግም አልበጃት፣

አስራ ሁለት ሆና አንድ ተኩላ ፈጃት።እንደሚሉት ይሆናል።ብዙ ሆኖ በጥቂቶች፣መንገላታት፣መደፈርና መከራ ማዬት አግባብ አይደለም።ያሳፍራልም!

የአማራው እራሱን ማስከበር ማለት ኢትዮጵያንና ሌላውን የአፍሪካ ሕዝብ ማስከበር ማለት ነው።የእጅ አዙር ቅኝ ገዢዎች ዳግም አፍሪካን ለመውረር ቤተሙከራ ያደረጉት ኢትዮጵያን ነው።በውስጥ ተባባሪዎቻቸው የሚያካሂዱት ወረራና አገር አፍራሽ ጦርነት ካላቸው አፍሪካን የመቀራመት ስልት ተነጥሎ ሊታዬ አይገባውም።

በዬቦታው የተቋቋሙት የአማራው ማህበረሰብ የድጋፍ ስብስቦች በአንድ ጣራ ስር ሆነው በተቀናጀ መልኩ ሊሠሩ ይገባል።በወታደራዊ፣በፖለቲካ ፣በመረጃ፣(ሚድያ)በገንዘብወዘተ ዘርፎች ማዕከላዊነት መኖር አለበት።ከሰርጎ ገቦችና ከጩልሌዎች መትረፍ የሚቻለው ጠንካራ ድርጅታዊ አመራርና ማዕከል ሲኖር ነው።በትግሉ ሰፊ ሚናና ተመክሮ ያላቸው እንደሞረሽ አማራ ድርጅት ያለውን ቢያጠናክሩት አዲስ ቤት ለመሥራት የሚወስደውን ጊዜና ጉልበት ይቆጥባል።ድርጅቱ ድክመት ቢኖርበት ደካማ ጎኑን አርቆ እንዲሄድ ማድረጉ እንደሚሻል መናገር ከወገንተኝነት አያስቆጥርም።የተሻለም ካለ ፊትለፊት ብቅ ይበልና የትግል ተመክሮውን ያካፍል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  በማተብዋ ልዳኝ - ወድቃ የተነሳችው - (ከስንሻው ተገኘ)

አገሬ ጠንክራ ካረገጠች እርካብ፣

ነገራችን ሁሉ የእምቧይ ካብ የእምቧይ ካብ። ከእውቁ ጋዜጠኛ ይፍታሂ ንጉሤ

አንድ አማራ ለሁሉም አማራ፣ሁሉም አማራ እንደአንድ አማራ!

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share