የመጨረሻዎቹ እርምጃዎች! አንገብጋቢ መረጃ!! – ቴዎድሮስ ጌታቸው

ውድ አንባቢያን አንድ ጊዜ! ጥንቃቄ!!

ይህ ፅሑፍ የተዘጋጀው ነገር ለመደጋገም አይደለም፤ አሁናዊ ነገሮችን ይዘን የተዘነጉ ነገሮችን በማካተትና አንጥሮ በማውጣት፤ ተጨባጭ ስዕልና ተጨባጭ ግንዛቤ በመፍጠር፤ ሁሉም እንደየአቅሙ ተረድቶ፤ የጋራ ውሳኔ ላይ እንዲደርስ ለማስቻል ነው፡፡ አስደነገጥካችሁ? ይቅርታ፤ አሁን ወደጉዳዩ እንግባ፡፡

ነባራዊው የቀጠናችን ሁኔታ ሲሰላ!

አሁን በተጨባጭ መሬት ላይ ያለው እውነታ፤ ግብፅና ሱዳን በጋራ ያሰማሩት በታንክና በከባድ መሣሪያ የታጀበው የጦር ሠራዊት፤ በኢትዮጵያ ድንበር አቅራቢያ የሚያንዣብብበት፤ ሀገራዊና ቀጠናዊ የጦርነት ስጋት የደቀነበት፤ የኢትዮጵያና የወዳጅ ጎረቤት ጦርም በተጠንቀቅ የሚገኝበት ነው፡፡ በመሆኑም ይህ የሱዳንና ግብፅ ተግባር ለምን? ብለን ለመጠየቅ እንገደዳለን!! ለዚህ ጥያቄ ምላሽ ለመስጠትና ተገቢ መላምት ላይ ለመድረስ፤ ለንፅፅር የሚውሉ መረጃዎችን በግብአትነት መጠቀም ያስፈልጋል፡፡

ያደጉና ጦረኛ የሆኑ ሀገራት፤ አልፎ አልፎ ጦርነት የሚመስል ጦርነት /Phoney War/ ይፈበርካሉ፤ ይህ ስልት ተግባር ላይ የሚውለው ለጋራ ጥቅምና ደህንነት ሲባል ነው፤ ለምሣሌ በ2ኛው የዓለም ጦርነት በ1940 እንግሊዝና ፈረንሳይ Anglo-French በተሰኘው የጦር ጥምረት፤ የተጠቀሙት የጦር ስልት ተጠቃሽ ነው፡፡ በዚህ የጦር ስልት የጀርመንን የወረራ ግስጋሴ ለመግታት፤ ኖርዌይን በመውረር የጀርመን ኃይል የኢኮኖሚ ማጠናከሪያውና ጉልበት ማግኛው የሆነውን ‹የብረት አረር› ለመቆጣጠር ሙከራ የተደረገበት ነው፡፡ እንግሊዝና ፈረንሳይ የተከተሉት ይህ የ Phoney War ስልት ውጤታማ ቢሆንም የዘገየ ነበር፡፡

tplfአንድ ሌላ ማነፃፀሪያ

ጨምር፤ ለዚህ እሩቅ ዘመንና ሀገር አንሄድም፤ ማነፃፀሪያውን በቅርቡና አዚሁ ሀገራችን ኢትዮጵያ እናገኘዋለን፤ የኢትዮጵያ መንግስት በሰኔ 2013 ያወጀው የተኩስ አቁም አዋጅ፤ እንደምንጠብቀው ‹‹የጥሞና ጊዜ›› እና ለትግራይ ክልል ገበሬ ‹‹የእርሻ ጊዜ እድል ለመስጠት›› ብቻ አይደለም፤ ዘርፈ ብዙ ዓላማዎችን ያነገበ ነበር፤ ከዛ ውስጥ አንዱ ወታደራዊ ኃይልን እና የጦር ትጥቅን፤ በምዕራብ አቅጣጫ /በሱዳን አዋሳኝ ግዛት አካባቢ/ ማዛወር ወይም ማስፈር ነበር፤ ለምን? ካልን በሱዳን የመሬት ወረራ እንደተፈፀመብን አይዘነጋም የሚል ነው፡፡ የዚህ የኢትዮጵያ ወታደራዊ ኃይል በምዕራብ አቅጣጫ በብዛት እንዲሰፍር የተደረገው፤ ሱዳን በወቅቱ እንደተረዳችው ኢትዮጵያ ራስን የመከላከል እርምጃ ልትወስድባት ሳይሆን፤ ኢትዮጵያ ሁለተኛው ዙር የህዳሴ ግድብ የውሃ ሙሌት በስኬት ማጠናቀቋን ስታበስር፤ ችግር እንዳይፈጠር ወታደራዊ ኃይሏን በተጠንቀቅ ለማቆም ነበር፡፡ ራሷን ከወረራ የመከላከል መብቱ ያላት ኢትዮጵያ! ማንም በማይጠብቀው መንገድ ይህን የ Self Defense Pretext ስልት! 2ኛውን ዙር የውሃ ሙሌት አጠናቃ፤ ለግብፅ፣ ለሱዳንና ለዓለም ይፋ አድርጋበታለች!!

እነዚህን ሁለት ንፅፅሮችን በሚገባ ከተመለከትን፤ ግብፅና ሱዳን በጋራ ሆነው በኢትዮጵያ ድንበር አቅራቢያ ጦር የሚያሰፍሩበት ምክንያት /ሰበብ/ ምን ሊሆን ይችላል? ዓላማና ግቡስ ምንድን ነው? በሚል ለሚነሳው ጥያቄ ወደመልሱ የሚያቃርቡን ይሆናል፡፡ እነሆ፤

በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ!

‹‹በአንድ ድንጋይ ሁለት ወፍ›› የሚለው በሀገራችን የተለመደ አባባል ነው፤ ነገር ግን ይህን አባባል ወደግብፅ እና ሱዳን ሀሳብና የትግበራ አካሄድ ስናመጣው፤ በጣም አደገኛና የሚያስከትለው ውድመትም ሲታሰብ እጅግ ሰቅጣጭና ለህሊና የሚከብድ ያደርገዋል፡፡ ምን ማለት ነው! የሁለቱ ሀገራት በኢትዮጵያ ድንበር ላይ የጦር ኃይላቸውን ማስፈር፤ ከላይ ለንፅፅር እንዳቀረብናቸው! ጦርነት የሚመስል ጦርነት /Phoney War/ ስልት አይደለም! ወይም ኢትዮጵያ የተጠቀመችበት ‹‹ራስን የመከላከል ሰበብ›› /Self Defense Pretext/ ስልት አይነት አይደለም፡፡ የግብፅና ሱዳን የድንበር ላይ ወታደራዊ ዝግጅት ታዲያ ምን ሊሆን ይችላል?

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአብይ አህመድ ውሸቶች (2018-2020) ክፈል 1 - ሊባኖስ ዮሃንስ

ይህ! የሱዳንና ግብፅ የከበባ ስልት! ሁለቱ ሀገራት ጦር ባሰፈሩበት አካባቢ የኢትዮጵያ ጦር በከፍተኛ ቁጥር እንዲሰለፍ በማድረግ፤

  1. ሀገራችን ውስጥ ባሉት አሸባሪዎች ተጠቅሞ የታላቁ ህዳሴ ግድብን ማስመታት፤ እንዲሁም በአፋር በኩል የሚገኘውን የኢትዮጵያ ወጪና ገቢ መተላለፊያን ማዘጋት፤

  2. ግብፅና ሱዳን ጦር ባሰፈሩበት አካባቢ የሚገኘው የኢትዮጵያ ጦር ሲሳሳ /ኃይሉ ሲከፋፈል/፤ በቀላል ማጥቃት ለሱዳን ተጨማሪ መሬት ማስገኘት ሆኖ ይታያል፤

ይህን መላምት በተጨባጭ ማስረጃ እናስደግፈው! ይህን ማስረጃ የምናገኘው! በግብፅ ብሄርተኛነታቸውና በመንግስት ሚስጥር አዋቂነታቸው ምክንያት! መረጃቸው ከሚታመንላቸው ግብፃዊው ፖለቲከኛ ሸሪፍ አልሲርና ግብፃዊው ጋዜጠኛ አህመድ ሙሳ፤ በያዝነው መስከረም ወር 2014 ካስተላለፉት መልዕክት ነው!! ሸሪፍ የግብፅ መንግስት የደረሰበትን አቋም በተመለከተ ‹‹የትግራይ ኃይል /አሸባሪው ማለት ነው/ የህዳሴ ግድቡን በተሳካ ኢላማ ያጠቃል›› ሲል ይፋ አድርጓል፤ የሸሪፍ ይህን ሚስጥር መዘርገፍ! በግብፃውያን ጋዜጠኞች ዘንድ፤ ‹‹ሸሪፍ ሚስጥሩን ማውጣት አልነበረበትም›› በሚል ቁጣን መቀስቀሱ ይታወቃ

፡፡ ጋዜጠኛ አህመድ ሙሳ በበኩሉ ‹‹የትግራይ ኃይል ከአፋር ክልል ለቆ መውጣቱ የጦር ኪሣራ ነው፤ ይህ መሆን አልነበረበትም›› ሲል ተጨማሪ መረጃዎችን ይፋ አድርጓል፡፡ ይህ ማስረጃ ብቻውን ግን በቂ አይደለም!! ምክንያቱም የግብፆቹን ወቅታዊ ማስረጃ (መረጃ) ከአሸባሪው ህ.... ቀደምት ስትራቴጂ ጋር ማመሳከር ይኖርብናል፡፡

አሸባሪው የህ.... ቡድን! የሽብር እንቅስቃሴው ከግብ እንዲደርስ ሊከተል የሚገባውን ስትራቴጂ ለመወሰን፤ በሰኔ 2013 /3 ወር በፊት/ ባደረገው የዙም ውይይት ወቅት፤ የሚከተሉትን የውሳኔ ሀሳቦች አካቷቸው ነበር፡

  1. ለትግራይ ሀገር መሆን ከአራት ሀገሮች ጋር ጥብቅ ዝምድና ያስፈልጋል፤ እነሱም ግብፅ፣ እሥራኤል፣ እንግሊዝና አሜሪካን ናቸው፤…ለግብፅ በአባይ ጉዳይ መወያየት፤ ሀገረትግራይ እንድትመሠረት የምትደግፍ ከሆነ፤ አባይ በወታደራዊ ስሪት በትግሬዎች አቅም እንዲፈርስ መደረግ እንደሚቻል የውሳኔ ሀሳብ ማቅረብ

  2. በሱማሌና አፋር መካከል የተፈጠረውን ግጭት በማባባስ፤ የአፋር ብሄረሰብ ላይ በትግራይ በኩል ጦርነት እንደሚከፈት በማድረግ Existencial Threat እንዲሰማው ማድረግ፤ይህንን ስልት በማፍጠን ከአፋር ጋር የመሬት ጥያቄ በማንሳት ወደቀጣዩ ውጊያ መግባት/ለመረጃዎቹ Zehabesha Youtube Channelን አመሰግናለሁ/

እነዚህ መረጃዎች ከላይ ላስቀመጥነው መላምት፤ የተሟላ ስዕል የሚያላብሱና ማረጋገጫ የሚሆኑ ናቸው፡፡ ይህን ማረጋገጫ ከያዝን! ግብፅና ሱዳን ወታደራዊ ኃይላቸውን ወደኢትዮጵያ ድንበር የማስጠጋት እንቅስቀሴን ምንነት ለመረዳት አስቸጋሪ አይሆንም፡፡ ያም ማለት! በኢትዮጵያ ላይ ‹‹የውስጥ ከፍተኛ ውድመት ማድረስ እና በወረራ መሬት የማግበስበስ እቅድ›› /The Plan of Internal Mass Destruction & Invasion of Land Grab/ አካል ሆኖ እናገኘዋለን፡፡ በዚሁ መንገዳችን ተጉዘን የግብፅን ፍላጎት ብናሰላው በሚገባ ግልፅ ይሆንልናል! የግብፅ ፍላጎት! ከጦርነት በዃላ በምትፈራርሰውና በምትንኮታኮተው ሱዳን! የሱዳናውያን ታዳጊና ጠባቂ መስላ! በሙሉ ወታደራዊ ኃይሏ በመግባት! ሱዳን ላይ ራሷን ማደላደል ነው!! አሁን በዐይናችን ሥር እየተከናወነ ያለው የአሸባሪ ቡድኖች እንቅስቃሴም፤ ለግብፅና ሱዳን ወታደራዊ ድርጊት የሰጠነውን ስያሜ፤ በተግባር እያረጋገጠልን ይገኛል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ያረጋገጥነው የምግብ ኢዋስትናን (ዋስትና አላልኩም) ነው።

የመፍትሄ ሀሳብ!

ለመጨረሻ ጊዜ የሚሞከር የመጀመሪያ እርምጃ!

ከዚህ አማራጭ ከሌለው፣ ከአይቀሬውና ከአስገዳጁ ‹‹አውዳሚ ጦርነት›› በፊት፤ ለመጨረሻ ጊዜ የሚሞከር የመጀመሪያ እርምጃ አለ፤ ያም ኢትዮጵያ እና ሱዳን ‹‹ከጨዋታው ሜዳ›› ማለትም ‹‹ከተቀናበረላቸውና ከውጤት አልባው የእልቂት ሜዳ››፤ አዎ ‹‹ከጨዋታው ሜዳ በጋራ ውሳኔ አለመገኘት›› ነው!! ወደዚህ ተገቢ እርምጃ ለመድረስ፤ ሱዳን! ግብፅ የአረባዊነት መርፌ ተጠቅማ ከወጋጃት ማደንዘዣ መንቃት ይኖርባታል፤ ብታምኑም ባታምኑም የግብፅን ማደንዘዣ የሚያረክሰውና ሱዳንን የሚያነቃው ጠቃሚ ክትባት! እናት ሀገር ኢትዮጵያ እጅ ይገኛል!!

  1. ሱዳን! በአረብ ሊግ የተቀመረባትን አደገኛ ቀመር መርምራ እንድትደርስበት ማድረግ፤

  2. ሱዳን! ግብፅ ከሱዳን ጀርባ እያራመደች የሚገኘው፤ ‹‹የ1860 የለንደን ቀመር ግልባጭ›› መሆኑን! ተጨባጭ መረጃና ማሳያ እንድታገኝ ማድረግ፤

  3. ሱዳን! በአፍሪካ ቀንድ ከሚነደው ‹‹ከብርቱ ጥፋት እሳት›› የሚገኘውን ውጤት ደጋግማ እንድታስብበት ማድረግ፤

  4. ሱዳን ከጎረቤቶቿ ማለትም ከኢትዮጵያ፣ ከኤርትራ፣ ከደቡብ ሱዳን፣ ከሴንትራል አፍሪካ ሪፐብሊክ እና ከቻድ ጋር ያላትን፤ አሁናዊ እንዲሁም የወደፊት የጋራ ጥቅሞቿን፤ በጥንቃቁ እንድታሰላስል ማድረግ፤

እነዚህ ተቀዳሚና ተገቢ እርምጃዎችን ከግብ ማድረስ! ሱዳን ከተወጋችው የግብፅ ማደንዘዣ ፈጥና እንድታገግም የሚያስችላት ሲሆን፤ ለዚህ ተፈፃሚነት ሱዳንን ፈጥኖ ወደህክምና ማዕከሉ በማስገባት /ሱዳንን ለንግግር ዝግጁ በማድረግ/ ረገድ፤ ከኢትዮጵያ ብርቱ ጥረት ማድግን የሚጠይቅ ነው፡፡ እዚህ ላይ! የምዕራብ አፍሪካ አመራሮችን ጨምሮ ሌሎች የፓንአፍሪካኒዝም አቀንቃኝ አመራሮች፤ የሚያበረክቱት አስተዋፅኦ ተጠባቂ ይሆናል፡፡ ይህ ብርቱ ጥረት ውጤት የማይገኝበት ከሆነ ግን! ‹‹የመጨረሻውን አርምጃ መውሰድ›› አስገዳጅ ያደርገዋል!!

እነሆ! የመጨረሻው እርምጃ!

በግብፅ ዓላማ ላይ የተመሠረተው፤ ይህ የኢትዮሱዳን ጦርነት አይቀሬ ከሆነ! ጦርነቱ በሱዳንና ኢትዮጵያ ተጀምሮ የሚቋጭ ሳይሆን! ወደጎረቤት ሀገራት ማለትም ወደኤርትራ፣ ደቡብ ሱዳንና ወደተቀሩት ሀገራት የመገስገሱ ነገር አይቀሬ መሆኑን ያመላክተናል!! ምክንያቱም የአሸባሪው ህ.... ስትራቴጂ፤ የግብፅና የምዕራባውያን ስትራቴጂ አካል መሆኑ በሚገባ ተረጋግጧል፤ የአሸባሪው ቡድን ስትራቴጂ ደግሞ ‹‹ትግራይን እንደሀገር ለመመስረት፤ የአራት ሀገራት ቅርፅ መለወጥ አለበት›› የሚል ነው፤ እነዚህንም ሀገራት ኢትዮጵያ፣ ኤርትራ፣ ሶማሊያና ጂቡቲ ብሎ በየሥማቸው በመጥራት፤ የጥቃቱ አካል አድርጎ አካቷቸዋል፡፡ በመሆኑም ጦርነቱ ወደጎረቤት ሀገሮች ገስጋሽነቱ አያጠራጥርም ማለት ነው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  " ፍርደ ገምድሉ የኢትዮጵያ ፖለቲካ !!" - በአቻምየለህ ታምሩ

ደቡብ ሱዳንም ብትሆን ያለኢትዮጵያ ጠንካራ ቁመና፤ በአፍሪካ ቀንድ ጥቅሞቻን ለማስጠበቅ፤ በአቢዬ ግዛት ከሱዳን ጋር የገባችበትንም የይገባኛል ውዝግብ በድል ማጠናቀቅ የሚቻላት አይሆንም፤ ጂቡቲንና ኬንያንም ካየን ምዕራባውያኑ አፍሪካ ቀንድን የጥቅማቸው ማስጠበቂያ ለማድረግ የሚከተሉት ስትራቴጂ! ‹‹በቅድሚያ አፍሪካ ቀንድን ለአሸባሪ ቡድኖች አሳልፎ መስጠት›› በመሆኑ፤ ‹‹ታላቋ ሶማሊያ›› በሚል ቅዠት ውስጥ ከሚገኘውና ከሶማሊያ በሚነሳው የሽብር ቡድን መናጣቸው አይቀርላቸውም፡፡

ይህን የአፍሪካ ቀንድ ሀገራቱን የተናጥል አጣብቂኝ ውስጥ መውደቅ፤ ትኩረት ሰጥተን ስንመለከተው! ጊዜ ጠብቆ አንድበአንድ መበላትን የሚያስከትል፤ አደገኛ አደጋ በያንዳንዱ ሀገራት ፊት መደቀኑን እናስተውላለን!! ያለውም አማራጭ በአፍሪካ ቀንድ ሀገራቱ የትብብር ጥላ ሥር በአንድነት መቆም መሆኑን እንደርስበታለን፡፡ እንደአንድ የፖለቲካ ተመልካች ትኩረት ሰጥቼ ስመለከት፤ የአፍሪካ ቀንድ ሀገራቱን ይህ ‹‹አማራጭ አልባ አማራጭ›› በመርህ ደረጃ የሚያግባባቸው ከሆነ! እያንዳንዱ ሀገር ራሱንና ቀጠናውን ለመታደግ፤ ሁለት መልክ ያለው አሰላለፍ የሚከተሉ መስሎ ይታየኛል፡፡

አንደኛው ሶማሊያ፣ ጂቡቲና ኬንያ ያንዣበበባቸውን አደጋ ለመቀልበስ በጋራ የሚቆሙበት ሲሆን፤ ሁለተኛው ኢትዮጵያ በውስጥና በውጭ የገጠሟትን የህልውና አደጋዎች! ኤርትራና ደቡብ ሱዳን ከደጃቸው የሚገኘውን፤ ነገር ግን ገስጋሽና ደራሽ የሆነውን የህልውና አደጋ ከእንጭጩ ለመቅጨት! በጋራ የሚቆሙበት! አንድ አይነት ዓላማና ግብ ያለው ተጠባቂ የአሰላለፍ ስልት ነው፡፡

ይህን የመሰለው የአፍሪካ ቀንድ ሀገራቱ አሰላለፍ! ለአፍሪካ ቀንድ ሀገራቱ ጥቅምና ህልውና መጠበቅ ሲባል! ለአፍሪካ ቀንድ ሀገራቱ ሠላምና ደህንነት ሲባል! አፍሪካ ቀንድን ለመታደግ ሲባል! በተባበረ ክንድ!! በሶማሊያና በኢትዮጵያ የሚገኙትን ሽብርተኛ ቡድኖችን፤ የግብፅን እኩይ ዓላማ ለመተባበር የተሰለፈውን የሱዳን ጦርና የተቀላቀለውን የግብፅ ጦር በአንድ ላይ መሠዋት! ‹‹የመጨረሻው እርምጃ›› አካል ይሆናል!!

አሁን የምንገኝበት ጊዜ! የዘመኑ የአፍሪካ ቀንድ ቆራጥ አመራሮች የሚለዩበት! የዘመኑ የአፍሪካ ቀንድ ጀግና አመራሮች እንደወርቅ ተፈትነው የሚወጡበት! ራሳቸውንና ትውልዳቸውን በዘላለማዊና ክብር ባለው የታሪክ መዝገብ የሚያፅፉበት! በመላው ዓለምም አንፀባርቀው የሚታዩበት! ቀጠናቸውን እና አፍሪካን የሚያስከብሩበት! ወርቃማውን እድል ይዞ የመጣበት ጊዜ ላይ እንገኛለን!!

በመሆኑም የኢትዮጵያ እና የተቀሩት የአፍሪካ ቀንድ ሀገራት ሕዝቦች! በቀጠናቸው አሁን ያለውን ‹‹ወታደራዊ እና ፖለቲካዊ›› የሤራ አጣብቂኝ በመረዳት! እንዲሁም ሤራውን ለማክሸፍና በድል አድራጊነት ለመወጣት! የአፍሪካ ቀንድ ሀገራቱ እያደረጉ ያለውን ከፍተኛ ዝግጅት በሚገባ በመገንዘብ! በውስጣቸው የሰረፀውን አፍሪካዊ ሥነልቦና እንደስንቅ ተጠቅመው! አፍሪካ ቀንድን ለመታደግ ለቆረጡ መሪዎቻቸው እገዛ ማድረግ እና በፅናት መቆም ይጠበቅባቸዋል!! ጤና ይስጥልኝ፡፡

ሠላም ለኢትዮጵያ ሠላም ለአፍሪካ

ማስታወሻይህ ፅሁፍ የደራሲው የመጨረሻ የአፍሪካ ቀንድ ትኩረቱ አይደለም፤ በያዝነው ወር (በቅርብ ቀናት) በሚያሳትመው መጽሐፍ፤ ዝርዝር ጉዳዩን ለሕዝብ ይፋ ያደርጋል፡፡

tewedros
ቴዎድሮስ ጌታቸው /ደራሲና የፖለቲካ ተመልካች/

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share