እንግዲህ ድሮኗ ዳግም ስራ ጀምራለች – መሳይ መኮንን

ነገሮች እንደሚለዋወጡ የሚጠበቅ ነበር። አሁን የምናየውና የምሰማውም፣ የነበረው ተቀይሮ፣ በደመ ነፍስ የሚግተለተለው ሃይል፣ ተግትቶና የኋላ ማርሽ አስገብቶ ሲፈረጥጥ ነው። ካለፈው ሳምንት ወዲህ የህወሀት ቡድን ስካሩ በርዶለታል። አጉራ ዘለልነቱ ሉጋም ተበጅቶለታል። በድንገት ባልታሰበ አቅጣጫ፣ የሳሳ የመከላከያ መስመር ያለበትን አከባቢ ሰንጥቆ በመግባት የበቀል በትሩን ሲያሳርፍ ሰነበተ። በጊዜያዊና ፕሮፖጋንዳ በተጫነው ድል ተኩራርቶና ልቡ አብጦ ለደጋፊዎቹና ለምዕራባውያን ቀላቢዎቹ “አዲስ አበባ በሁለት ሳምንት እንገባለን፣ የፋሺስቱን አብይን መንግስት መንግለን እናስወግዳለን” የሚል ተስፋ ሲግት ቆየ።

240687702 3088844424728158 8585552962870239567 n

ለትግራይ ህዝብ ልጅህን ስጠኝና አዲስአበባ ገብቼ ውለታህን እመልሳለሁ እያለ ተሳለቀበት። 27 ዓመት አዲስ አበባን ተቆጣጥሮ፣ የኢትዮጵያን ሰማይና ምድር በመዳፉ ጨብጦ ለትግራይ ህዝብ ህይወት ትርጉም ያለው ለውጥ ያላመጣ ቡድን አከርካሪው ከተመታና መሪዎቹን በእስርና ሞት ካጣ በኋላ ምን ተዓምር ሊያመጣለት ከትግራይ ህዝብ የልጅ ግብር እንደሚጠይቅ የሚያውቁት እንግዲህ እነሱ ናቸው።

አሁን ነገሮች ተቀያይረዋል። እንደፈለጉ መገስገስ የለም። አዲስ አበባ የማይደረስባት መንግስት ሰማያት ሆናለች። የጅቡቲን መስመር ይዤ የኢትዮጵያውያንን ጉሮሮ እዘጋለሁ የሚለው ቅዠትም ውሃ በልቶታል። ካለፈው ሳምንት ጀምሮ በተለይም ከሀሙስ ወዲህ በህወሀት መንደር ርዕደ መሬት መከሰቱን የሚያሳዩ ምልክቶች እየወጡ ነው። ድሮኗ ስራ ጀምራለች። ከአርብ አንስቶ የተመረጡ ዒላማዎችን እየቀጠቀጠች ነው። ዘመቻውን ከሚመሩት አዛዦች የተገኘው መረጃ እንደሚያረጋግጠው ሰሞኑን በህወሀት ጀሌ ሰራዊት ላይ የተወሰደው እርምጃ ቡድኑን ዳግም ለማንሰራራት እንዳይችል የሚያደርገው ነው። ለአብነትም ከጋይንት እስከ ጋሸና ባለው መስመር በትንሹ 10ሺህ የሚሆን ጀሌ ከጥቅም ውጪ ሆኗል።

እስከእስታይሽ የተከማቸው የህወሀት ጀሌ አብዛኛው ተመትቷል። በክፍል ጦር ሂሳብ ከተሰላ ህወሓት አንድን ክፍለጦር ከ1600 እስከ 2000 ባለ የታጣቂ ቁጥር አደራጅቷል። ካለፈው ሀሙስ ምሽት አንስቶ በድሮን በታገዘ ጥቃት 9 የህወሀት ክፍለጦሮች ተደምስሰዋል። ኪሳራው በሰው ሃይል ከተሰላ በትንሹ ከ16ሺህ የሚልቅ ታጣቂ ተገድሏል። እንደሰማሁት የተረፈው ሃይል በላሊበላ አቅጣጫ ሸጡን ይዞ ወደትግራይ እየሸሸ ነው። ሆኖም ይህም ሃይል በህይወት ከትግራይ የሚደርስ አይመስልም። በየአከባቢው ህዝቡ እየጠበቀ እያስቀረው ነው። በእስታይሽና መርሳ ማዶ ስብሰባ የተቀመጠ የህወሀት አመራር ከህብረተሰቡ በተሰጠ ጥቆማ እዚያው ከስብሰባ እያለ በድሮን መመታቱም ታውቋል። ስለደረሰው ኪሳራ በሚቀጥሉት ቀናት የተሟላ መረጃ የሚደርሰን ይሆናል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሕገ-መንግስት ትርጉም ጥያቄ አስተያዬት - ኢሳያስ ሃይለማሪያም

በሌሎች ግንባሮችም ያለው ሁኔታ ተመሳሳይ ነው። የአፋሩ ግንባር እንደተለመደው ለህወሀት ሃይል መቅሰፍት የወረደ ያህል ሆኖ ቀጥሏል። ህወሓት በወልቃይት በኩል ሰብሮ የሱዳኑን ኮሪዶር ለማስከፈት ፈጽሞ የማይሞከር እንደሆነ ተረድቶተታል። ለዚህም በአፋር በኩል የጅቡቲን መስመር በመያዝ ላይ ሙሉ ትኩረቱን ለማድረግ የፈለገ ይመስላል። ከሁለት ወር በፊት በጭፍራ በኩል ሰብሮ ሚሌ ለመድረስ ያደረገው ሙከራ ከተጨናገፈበት በኋላ ሰሞኑን ነፍሰጡር ሴቶችን ሳይቀር አሰልፎ በአፋር በኩል አዲስ ጥቃት ከፍቶ ነበር። ከሀሙስ ጀምሮ እስከ ትላንት ቅዳሜ አራት ጊዜ ሞክሮ በከፍተኛ ኪሳራ ተመትቶ ተመልሷል። በአንድ የአፋር ግንባር ብቻ ከ1ሺህ በላይ ሙት ተመዝግቧል። የሰውን ህይወት እንዲህ በቁጥር ሲገልጹት ቀላል ይመስላል። በማይጠብሪ፣ አደርቃይ፣ በደባርቅ ቀበሌዎች የህወሓት ሃይል ላይ የደረሰበትን ኪሳራ ከጨመርን ትግራይ ምን ሰው ተረፋት ብለን አብዝተን እንድንጨነቅ የሚያደርገን ነው። ያሳዝናል። ለአንድ ጨርቁን ጥሎ ላበደ ቡድን ተብሎ ይህ ሁሉ የህይወትና የቁስ ኪሳራ ልብን ይሰብራል።

በህወሀት መንደር አሁንም ሽለላውና ፉከራው አልበረደም። አሁንም አዲስ አበባን ልንቆጣጠር ነው የሚለው ማደንዘዣ ዲስኩር ከትግራይ ህዝብ ጆሮ ላይ ይጮሃል። የምዕራቡ መንግስታት በእርግጥ አሁን ላይ የመሬቱን እውነት የተረዱት ይመስላል። ዝምታቸውን ሰብረው ስለ ድርድር የሚጮሁት ያለምክንያት አይደለም። በየሳምንቱ ከጉድጓድ እየወጣ ፊቱን በቅባት ወዛም እያደረገ በቴሌቪዥን መስኮት ብቅ እያለ ያዙኝ ልቀቁኝ የሚወራጨው ጌታቸው ረዳ በትዊተር ገጹ ላይ ሀተታ ዘ ፍርሃት ጽፎ አየሁት። ስለ ድርድር ጭንቅ ጥብብ ብሎታል። ድርድር ስለመኖሩ ሳናውቅ ስለአደራዳሪ ምርጫ ውስጥ ገብቶ ይፈተፍታል። ፍርሃት ሊሆን ቢችልም አብይን ልናስወግድ አንድ ሀሙስ ቀርቶናል፣ አዲስ አበባን ልንይዝ እንጦጦ አፋፍ ላይ ደርሰናል እያለ ለትግራይ ህዝብ ሲደሰኩር ቆይቶ ፍሬቻ ሳያበራ ድንገት ታጥፎ ስለ ድርድር ሲያወራ መስማት አስገራሚ ነው። ከዚህስ በኋላ የትግራይ ህዝብ ይህንን ቡድን ተከትሎ የገደል መንገዱን ይቀጥለው ይሆን?

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሤራና ግድያ ሀሤራና ግድያ ሀገርን ያፈርሳል እንጂ አይገነባም! - አሣምነው ጽጌ

ድርድር የሚባል የለም። ደብረጺዮን ለጉተሬዝ ደብዳቤ ጽፎ ድርድር እንፈልጋለን፣ አደራዳሪው ግን የአፍሪካ ህብረት መሆን የለበትም ሲል ተማጽኗል። ጌታቸውም በትዊተሩ ላይ የአፍሪካ ህብረትን ጥምብ እርኩስ እያወጣ የአደራዳሪ ምርጫ ዝርዝር ሲሰጥ ነበር። መብላቷን ሳታውቅ እጇን ታጠበች፣ ባል ሳታገኝ ለሰርጓ ተጨነቀች፣ ማን ሊስምሽ ታሞጠሙጪያለሽ። የህወሀት መሪዎችን ከድርድር ዲስኩራቸው አንጻር የሚገልጹ አባባሎች ይመስሉኛል። ድርድር ሳይኖር የአደራዳሪ ምርጫ ውስጥ የገባው ህወሓት መሬት ላይ በጥሩ መደቆሻ እየተደቆሰ ለመሆኑ ማረጋገጫ ነው። ቀደም ሲልም እንዳልኩት የህወሀት ጀምበር እየጠለቀች ነው። ከዚህ በኋላ ትንሳዔ የሌለው ሞት እንጂ እንደ ባለፈው አፈር ልሶ የመነሳት እድል አይኖርም። በነገራችን ላይ ድሮን ሲነሳ ሁሌም ከጆሮዬ ላይ የሚያቃጭልብኝ የሌ/ጄ ታደሰ ወረደ ቃለመጠይቅ ነው። ድሮን ምን ያህል እንደሚፈሩ በግልጽ የተናገረበት ነበር። ጀነራሉ በቁጭትና ንዴት ጥርሱን ነክሶ፣ ቡጢ ጨብጦ እንዲህ አለ “ድሮኗ ቀጠቀጠችን። መሳሪያዎቻችንን አነደደችብን። ያልጠበቅነው ነገር ነው”

እንግዲህ ድሮኗ ዳግም ስራ ጀምራለች።

1 Comment

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share