ኢትዮጵያ በእውነት መነፅር – ዶ/ር ዘላለም እሸቴ

unnamed (2)

በዙሪያችን የምናያቸው ሁኔታዎች ኢትዮጵያ ትፈርሳለች ብሎ ስለሚያስተጋባ፥ ስጋታችን ለባለ አዕምሮ ሰው ትክክል ሊመስል ይችላል።  ይሁን እንጂ በዓይነ ሥጋ ከሚታየውና ከሚሆነው ትዕይንት ጀርባ ያለውን እውነት ለሚያስተውል ሰው፥ የኢትዮጵያ ትንቢት ፍፃሜ ዋዜማ ላይ እንደሆንን ፍንትው ብሎ ይገለጥለታል።

235315006 4702544726444033 8335973039341996430 n

ለመሆኑ ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች ሲባል ምን ጠብቀን ነበር?

ኢትዮጵያ እጆቿን የምትዘረጋበት አውድ ሁለት ምዕራፍ አለው።  አንደኛው ምዕራፍ በመጀመሪያ የሚሆን ሲሆን፥ ሁለተኛው ምዕራፍ ራሱ የመጀመሪያው ምዕራፍ የሚወልደው ነው።  ወደ እግዚአብሔር የመጀመሪያው እጅ መዘርጋት ምዕራፍ ለፈጣሪ መሸነፍንና በእርሱ መታመንን ያመለክታል።  ሰው ተንበርክኮ እጁን ወደ ፈጣሪ ሲዘረጋ፥ መማረኩንና ረድኤትን ከላይ መጠበቁን ያሳያል።  እጅ መዘርጋቱ፥ “ተስፋችን አንተ ነህ” ብሎ እርዳታ ከላይ እንደሚመጣለት ማወቁን ያመላክታል ።  የዚህ የመጀመሪያው የእጅ መዘርጋት ምዕራፍ፥ ገሀዱ ዕይታ የሚያመለክተው ምስኪንነትን ነው።  ፈተናችን ከአቅማችን በላይ ሆኖ ሲያንገዳግደን፥ እንዳንሻገር የሚከለክሉ ተግዳሮቶች በግራና ቀኝ ሲያይሉብን፥ የሚመለከተን ሁሉ በመፍረስ አፋፍ ላይ እንዳለን አድርጎ ሊቆጥረን ይችላል።  በዚህ አስቸጋሪ ሁኔታ እጆቻችንን ወደ ፈጣሪ ዘርግተን በእምነት እንደምንሻገር ስንናገር አንዳንዶች የማይገባቸው ለዚህ ነው። በዚህ ጊዜ መደገፊያችን እና ትምክዕታችን ፈጣሪን አድረገን አንገታችንን ቀና ስናደርግ፥ ከትእቢት ይልቅ ትህትና እንደሚያሸንፍ የምናውቀውና፥ በዚህ የመጀመሪያው የትንቢት ፍፃሜ ምዕራፍ ውስጥ የሚያለመልመን በፈጣሪ ላይ ያለን እምነት ሲሆን፥ ያም እምነት ጉልበት የሚሆነን በእውነት መነፅር ኢትዮጵያን ማየት ስንችል ብቻ ነው።

ይህን የጨለማ ጊዜ በመጀመሪያው እጃችንን የመዘርጋት ምዕራፍ በፈጣሪ ከተሻገርን በሁዋላ፥ ሁለተኛው እጅ የመዘርጋት ምዕራፍ ይወለዳል።  ያም እጆቻችንን ዘርግተን በረከቱን የምንቀበልበት የመታደስ ዘመን ነው።  በዚህ በሁለተኛው የእጅ መዘርጋት ምዕራፍ፥ ፈጣሪ ኢትዮጵያን እንደ ምልክት አድርጎ እንድታበራ የሚያደርግበት የጉብኝት ወቅት ነው። ፈተናችን ሊያጠራን እና ወደ ከፍታችን ሊያወጣን እንጂ ሊያጠፋን የማይችለው ምክንያት፥ ፈጣሪ ስላለና ስለሚረዳን ብቻ ነው። በዚህም ምክንያት ከመሬት ተነስተን፥ ማማ ላይ ስንታይ፥ ክብርን ለፈጣሪ እናመጣለን።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ውድ ወንድሞችና እህቶች - ሙሉጌታ በትረ ገብረማሪያም

እናት ምጥ ላይ ስትሆን በጭንቋ ተስፋ አትቆርጥም፥ ይልቁንም የሚወለደውን ሕፃን ለመታቀፍ ትናፍቃለች። እኛም ኢትዮጵያ ለአፍሪካ ኩራት እና ለዓለም ተስፋ ሆና ከወደቀችበት ቀና ብላ ቆማ እጆቿን ዘርግታ ልትሞሸር ያለችበት ወቅት በደጅ እንደሆነ የሚያረጋግጥልን፥ የዛሬው በስብራታችን እና በጨለማችን እጆቻችንን ወደ ኢትዮጵያ አምላክ መዘርጋታችን ነው።

ዛሬን ተሰብረን ባዶ እጃችንን ሆነን እጆቻችንን ዘርግተን እርዳን ብለን ስንጮህ፥ ፈጣሪ ወርዶና ፈርዶ የተዘረጉትን ባዶ እጆች በበረከቱ ነገ እንደሚሞላ ሁሉም ይወቀው።

ሦስት ሽህ ዓመታትን ያስቆጠረው የኢትዮጵያ ትንቢት ዛሬ በዓይናችን ፊት እየተፈፀመ እያየን፥ በድንዛዜ ሆነን ለምን እንጨነቃለን?  አይሁድ የክርስቶስን መምጣት ለዓመታት ሲጠብቁ ቆይተው፥ ጌታ ሲመጣ የገባቸውና የሰማይ ደስታን የተቋደሱት ጥቂት እረኞችና መንገደኞች ነበሩ።  ዛሬም ለዝንተ ዓለም ስንጠባበቀው የነበረው “ኢትዮጵያ እጆቿን ወደ እግዚአብሔር ትዘረጋለች” የሚለው ትንቢት ለመጀመሪያ ጊዜ በገሀድ መፈፀም እየጀመረ መሆኑን እያየን ስለሆነ፥ ኢትዮጵያ ልትፈርስ ነው ብለን በመጨነቅ ፈንታ፥ አዲሲቷ ኢትዮጵያ ልትወለድ ነው በሚል እምነት እንፅና።

ፈጣሪ ከመሬት ያነሳቸው የዘመናችን ታላላቅ ሀገሮች፥ ጀርባቸውን ለፈጣሪ በሰጡበት በአሁኑ ወቅት፥  የኢትዮጵያ ሕዝብ አማራ ትግራይ ኦሮሞ ጉራጌ ሶማሌ አፋር ወዘተ ሳይል ሁሉም፥ ግኡዙን ምድር ጨምሮ፥ የፈጣሪን ረድኤት በየዕለቱ በአደባባይ ሲማጠኑ ማየት ትልቅ ምስጢር ነው። የነገው ትልቅነት ዛሬን በፈጣሪ ተደግፎ ለቆመ ደካማ የተመደበ ሲሆን፥ የነገው ውርደት ደግሞ ዛሬን በትዕቢት ተነፍቶ ለቆመ ሃያል የተመደበ ነው። ይህን እውነት ለሚያስተውል፥ ወደ ብሩህ ተስፋችን እየተገፋን እንደሆነ ይታየዋል።

ዋናው ቁምነገር ትንቢቱ የመፈፀሚያው ጊዜ ደርሶ፥ ፈጣሪን በአደባባይና በየቤታችን፥ በየቤተ እምነታችንና በየባለስልጣናት ሰፈር፥ ሃይማኖት ሳይለይ፥ ትልቅ ትንሹ ፈጣሪን እየተጣራ መሆኑ ነው።  እኛ ከተሸነፍንለት፥ አምላክ እንደሚያሸንፍልን ለዘመናት የፀና እውነት ነው። እጆቻችንን መዘርጋት ላይ ስለደረስን፥ በዚህ ብቻ ደስ ይበለን።  አምላክ የሚታመኑትን አሳፍሮ አያውቅም። ከሁኔታዎቻችን ላይ ዓይናችንን አንስተን፥ ሰዓቱ ሞልቶ እጆቻችንን የመዘርጋት ምዕራፍ መጀመራችንን እያየን፥ የፈጣሪን ክብር ለማየት በመጠባበቅ በደስታ ወደ የሥራችን እንሰማራ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሮመዳን ዋዜማ እና ሮመዳን በሳውዲ አረቢያ! - ከነብዩ ሲራክ

ፍርሃቴ የመጎብኘት ዘመን አይመጣ ይሆናል የሚል ጥርጥር ሳይሆን፥ መጎብኘታችን የማይቀር የሚፈፀም የፈጣሪ ተስፋ እንደሆነ በማወቅ፥ እርግጠኝነት ላይ በመድረስ፥ ያኔ ስንጎበኝ እኛም በጊዜያችን ፈጣሪን እንዳንረሳ ነው። ለዚህም ይሆናል ምኞት አይከለከልምና የፈጣሪን ውለታ ማስታወሻ እኛ ደግሞ በሰንደቅ ዓላማችን ላይ የተዘረጉ እጆች እንዲያርፉበት እናደርጋለን ብዬ የምፀልየው። ኢትዮጵያ ታላቅ ስትሆን፥ ከመፍረስ ታድጎ ለታላቅነት ያበቃትን አምላክ ያኔ በክብር ታከብረዋለች።  አምላክ ምልክት አድርጎ ለአርአርያነት ሲያበቃት፥ ያኔ እኛም በፈጣሪ ስር እንዳለ አንድ ቤተሰብ ሆነን እንገለጣለን። በእውነት መነፅር ኢትዮጵያን ስንመለከት፥ ኢትዮጵያ ትፈርሳለች ብሎ ለመስጋት እንዴት ይሆንልናል?  እውነት፥ ለውርደት የምትፈርስ ኢትዮጵያን ሳይሆን ለክብር የምትወለድ ኢትዮጵያን ያሳያልና!

 

2 Comments

  1. ውድ ዶ/ር ዘላለም እሸቴ፣
    አገሩን እንደሚወድ አንድ ዜጋ ምኞትህን እጋራለሁ። ችግሩ ግን የጠቀስከው ጥቅስ ሁላችንም የምንመኘውን እንዲደግፍልን ካልሆነ በስተቀር ዐውዱን የተከተለ አይደለም። ለአገራችን መጸለይ አንችልም ማለት አይደለም፤ ብዙዎች እየጸለዩ ነው! ከዚሁ ጋራ ራሳችንን ልንጠይቅ የሚገባን ጥያቄ፣ በዚህ በቀውጢ ሰዓት ለአገሬ ምን እያደረግሁ ነው? የሚለውን ነው። ህወሓት ሠላሳ ዓመት የፈጸመው ወንጀል ሳያንስ የባእድ መንግሥታትን ተገን አድርጎ ራሱን እንደ ተበዳይ ሲያቀርብ ብዙሓን የሆንን ምን እያደረግን ነው?

  2. የሚገርም ነው። ምን ለማለት እንደፈለክ አይገባኝም። ህሳቤህ ሁሉ ያለ ስሌት በደመ ነፈስ ማጭድ በእጅ ይዞ ታንክ ላይ እንደሚወጣው የቀድሞ ተዋጊ ነው። ተሳፋሪ እንጂ ታንኩ በወገን ላይ በማድረስ ላይ ያለውን ጉዳት ለመግታት አቅም የለውምና። የፈጣሪና የኢትዮጵያ ፓለቲካ ጭራሽ ተገናኝተው አያውቁም። ኢትዮጵያዊያንም ወደ ሰማያት የሚዘረጉት ከቅጥፈት የጸዳ እጅ የላቸውም። ከትውልድ ወደ ትውልድ አንድ አንድን ሲጠልፍ፤ የቆመን ሲያፈርስ፤ ሰርቶና ጥሮ ያገኘውን ሲዘርፍ፤ በግፍ የዘረፈውን ለመሰሎቹ እንደፈቀደ ዘግኖ ሲበላና ሲያድል የኖረ ህዝብ ነው። ይህ ህዝብ የሚያስፈልገው የነቃ አዕምሮ፤ ከዘርና ከክልል ፓለቲካ አስተሳሰብ የነጠፈ ሰውን በሰውነቱ መዝኖ በሰውኛ ሰልፍ አብሮ ተሰልፎ የሚረዳዳ ህብረተሰብ እንጂ በማይኖርበት እምነት ፈጣሪን መጥራቱ ሃሳዊ መሆን ነው። አልፎ ተርፎም የማያዛልቅ ጸሎት ለቅስፈት ይሆናል እንዲሉ ነው የሚሆነው።
    ሰው የሚመዘነው በተግባሩ ነው። ዛሬ የጋምቤላ፤ የኦሮሞ፤ የቅማንት፤ የአማራ ገለ መሌ የሚሉን የነጻ አውጭ ጭራሮዎች ሁሉ የመከራ ክምሮች ናቸው። ቀን ሲከዳቸው ራሳቸው ጋይተው ሌላውን ሊያጋዪ። አሁን በትግራይ፤ በአፋር በአማራ ክልል የምናየው የዚህን እብደት ውጤት ነው። ግን ለዚህ ሁሉ ጥፋትና እብደት ተጠያቂው እኛ እንጂ ፈጣሪ ምንም አላረገም። በዚህም የተነሳ የሰማዪን አምላክ ና እኛን ምሰል ማለት ተገቢ አይመስለኝም። የምድራችን መፍትሄና ችግሩ እኛ ነን። እምነት የግል ነው። ሃገር ደግሞ የጋራ ነው። አሁን ግን ሃገር የክልል ብቻ እየሆነ ተቸግረናል።ማታለል፤ መዋሸት፤ መግደል፤ ማስገድል፤ ህጻናትን ለጦርነት ማግዶ መሸሸት፤ ባልተጠና መልኩ አካኪ ዘራፍ ብሎ እሳት ውስጥ ገብቶ መንደድ ሁሉ ወንጀል ነው። ሃበሻ የውሸት ቋት እንደሆነ ለማወቅ በሶሻል ሚዲያና በዪቱቭ የሚለጠፉ ሽርፍራፊ ሳንቲም ለቀማ በፈጠራ ወሬ ህዝባችን እንደሚያሳስቱ አይቶ መገንዘብ በቂ ነው። ጥያቄው ማን በሞተላት ሃገር ነው ማን የሚኖረው ነው?
    በእውነት መነጸር የአሁኗን ኢትዮጵያ ለተመለከተ በእርግጥም አፍራሽ ሃይሎች በውጭም በውስጥም ተሰልፈዋል። በሃገሪቱ ታሪክ ታይቶና ተሰምቶ በማይታወቅ ተግባር የራሷ ልጆች ሲኦል እናወርዳታለን፤ የምናወራርደው ሂሳብም አለን በማለት ለብቀላ ከትግራይ ምድር ተነስተው መከራን በመዝራት ላይ ይገኛሉ። ጠንጋራው የአሜሪካ የውጭ ጉዳይ ፓሊስም የወያኔን ኮቴ ተከትሎ እየተጓዘ ነው። አሜሪካ እብዶች በዋሉበት መዋሏ አሁን የተጀመረ አይደለም። የቆየ ራስ ጠቀም የሆነ ፓሊሲያቸው እንጂ። ወያኔንም የእነርሱ ጉዳይ አስፈጻሚና ተላላኪ ስለነበር አሁንም ተላላኪውን ወያኔን ወደ ስልጣን ለመመለስ በሱዳንና በግብጽ በኩል እየሰሩ ነው። አሁን በአፍጋኒስታን የምናየው የዚሁ የደንበር ገተር የውጭ ፓሊሲያቸው ያመጣውን ውጤት ነው። ውሃ ቢወቅቱት እንቦጭ እንዲሉ ከሃያ አመትና አንድ ትሪሊዮን ዶላር ብክነት በህዋላ ነገርየው ሁሉ ሩጫና ተመልሶ ያው ነው። የኢትዮጵያ ትንሳኤና ቀጣይነት የሚረጋገጠው ከዘር፤ ከቋንቋ፤ ከሃይማኖት፤ ከክልል ፓለቲካ በላይ ኢትዮጵያዊነትን ባስቀደሙ ሴትና ወንዶች ልጆቿ ደምና አጥንት እንጂ ሲፈለግ በማይገኝ የሃይማኖት መመጻደቅ አይደለም። በቃኝ!

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share