ሮፍናን በዚህ ፈታኝ ወቅት – መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ

ሮፍናን በዚህ ፈታኝ ወቅት ፣ በሰውነት ተፋቅረን ዳግማዊ አደዋን እንድንሰራ ወቅታዊ ጥሪ ያሥተላለፈልን ጀግናችን ነው ።

ለሁሉም ጌዜ አለው

የእኛን ሰው ፣ አዋከቡት
ዘር ጭነውበት
ሰውነቱንም አሥረሱት
በቋንቋ ከፋፍለውት ።
ሰው የተሰኘውን የወል ስሙን
የደም፣ የሥጋና አጥንት አንድነቱን
የቆዳውን ፣ የጭቅላቱን ና የፊት ቅርፁን ።
የቁመናውን ተመሳሳይነት
ሰረዙት ሰውነቱን ፣ የቋንቋ ሥም በመሥጠት ።
የሰው ፍጥረቱ ሲመረመር
ሰው በሳይንሥ ሆነ በኃይማኖት
ከሰው በሥተቀር ሌላ ሥም ሳይወጣለት
በእኛ አገር ግን ለሙከራ
ሰው ተፈረደበት በቋንቋው እንዲጠራ ።
ይባስ ተብሎ የእገሌ ቋንቋ እየተባለ ፣አገር ተከለለ
ዜግነት ረክሶ የፖለቲከኞቹ ቋንቋ
ሰማይ አከለ።
በህዝብ መካከልም የባቢሎን
ግንበኞች ታሪክ ተደገመ
አንዱ የዳቦ ያለህ ብሎ ሲጮኽ ፤
ሌላው አፈር አሥቃመ ።
ለሠላሣ ዓመት ግተው አሠከሩት
እንዲሆን ድንብርብር
እንዲወላገድ መያዣ መጨበጫ በሌለው ፣ በአበደ የፖለቲካ ዛር ።
ዛሬ ግን ያ ሰውነቱን የረሳው ፣ ተርታው ሰው
ሰውነቱን በኢትዮጵያ ጠላቶች ሴራ ተረዳው ።
የዘር ፖለቲካ ሴራ ምን እንደሆነ አወቀ
በውሥጥ እና በውጪ ጅቦች ሴራም ተደነቀ ።

ግንቦት 11/2013 ዓ/ም
የግጥሙ ባለቤት መኮንን ሻውል ወልደጊዮርጊስ

ይህንን ግጥም እንድፅፍ ያነሳሳኝ የሮፍ ናን ( የኑሪ ሙዘይን )” ሠከላ “የተሰኘ አዲስ ዘፈን ነው ። የዘፈኑ ግጥም ፣ ኮርኳሪ ና አንቂ ነው ። ከታሪክ አንፃርም በታሪካችን እንድንኮራ የሚያደርግ ከመሆኑም በላይ ጥቂት ጀግኖቻችንን በማውሳት ፣ የእነዚህ ሥመ ጥር ጀግና የአፍሪካ ኩራት የሆኑ ጀግኖች ልጆች መሆናችንን በማሥታወሥ ፤ ሰው መሆናችንን ተገንዝበን ፣ ለፍቅርና ለይቅርታ ልባችንን እንድንከፍት የሚመክር ፣ ወቅታዊ መልክት ያለው ጥበባዊ ስራ ነው ፡፡

ሮፍ ናንን በግሌ በጣም አደንቀዋለሁ ። በእርግጥ ማንም ልቡ ለኪነት የቀረበ ይወደዋል ። በበኩሌ ግን የራሱ የሆነ ፣ ልዩ የሆነ የሙዚቃ ፈጠራና የአገጣጠም ሥልት ያለው ፣ የዘመናችን ሊቀ ኪነት ያሬድ ብዬዋለሁ ።

ሮፍ ናን ሙዚቃ የመፍጠር ና የማቀናበር ችሎታው ምጡቅ ነው ። ሮፍ ናን ለእኔ ከሙዚቃ አንፃር ፣ ምጡቅ ና ሰማያዊ የሆነ ምናብ ያለው የጥበብ ሰው ነው ። እንደ ኢትዮጵያዊው የዜማ ሊቅ ያሬድ እሱም አዲስ ሙዚቄ ፣ አዲስ ኢትዮጵያዊ ሥልትን ፈጣሪ በመሆኑም ዓለም ያደንቀዋል ። ነፍሱ የሰውን ተላላነት ጠልቃ የምትገነዘብ በመሆኗም ግጥሞቹ ጠንካራ መልዕክት ያላቸው ናቸውና ኢትዮጵያዊያን በአገራቸው ልጅ የጥበብ መልክት ከእንቅልፋቸው ነቅተዋል ፡ ። ትላንትም እንደዛሬው ፣ ሰው ተላላነቱን ተገንዝቦ ሲያበቃ “እውነትም ይህ እውነት ፣ ጠፍቶን ነበር ! ” በማለት ፣ ሰው ማንነቱን አውቆ ፣ እንዲባንን የሚያደርጉ ግጥሞቹ ናቸው ከእንቅልፉ ያስነሱትና ፣ ሰው መሆኑን በቅጡ እነዲገነዘብ ያደረጉት ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  እኛ “ትውልደ-ኢትዮጵያውያን “ የውጭ አገር ዜጎች  በሚል አርዕስት በባይሳ ዋቅ-ወያ በተጻፈና በዘሃበሻ ላይ ስለተለጠፈው ጽሁፍ  የተሰጠ ትችታዊ ሀተታ!

ሮፍ ናን ፣ በውብ ዜማ ና በተለየ የኤሌክትሮኒክሥ ሙዚቃ ቅንብር ፣ህሊናንን ኮርኩሮ በማንቃት ፣ ወደ ህይወት ውብ መንገድ ፣ ዝንጉ ሰዎችን አባኖ ንቁ የሚደርግ ምስጉን ሊቀ ጥበብ ነው ። ከ 2 ዓመት በፊት እንሆ ያለንን ነፀብራቅን መለሥ ብላችሁ ሥታዳምጡ ይህ እውነት እንደሆነ ለመመሥከር ትገደዳላችሁ ።

ሥለአገር ፣ ሥለፍቅር ፣ ሥለባህላችን ፣ ሥለማህበራዊ ኑሮ ትሥሥር እንዴትነት የሚገልፁ ፤ የሚያነቁና ወደማሥተዋል መንገድ የሚመሩ ዜማዎችን ትላንት በማዜም ኢትዮጵያዊያንን አንቅቷል። ” እውር አሞራን ማነው ያበለው…እውነት፣ እውነት ? ” ብሎ በመጠየቅ እንድናስብ አስገድዶናል ።

የረሳችሁትን ላሥታውሳችሁ ና የሎሬት ፀጋዬ ገ/መድህን ” እሳት ወይ አበባ ” ግጥምንም በዘፈኑ ውሥጥ አካቶ በመጫወት ከፍቅርና ከእውነት ፈርሃት እንድንወጣም አስገድዶናል ። ፀገሽ ፍርሃትን ለማሸነፍ ፣ ሁሌም ተጋፋጭ ጠንካራ መንፈሥ ያለው ፣ ለእውነት ፣ ሥለ እውነት የኖረ በለቅኔ ና ከተውኔት አንፃርም ከሼክስፒር እኩል የሚታይ የትያትር ፀሐፊ ነው ። ከባለቅኔነት አንፃርም ራሱን እንደ ፑሽኪን ነበር ፀጋዬ የሚቆጥረው (በነገራችን ላይ ፣ በሀሁ ፐፑ ትያትር ውዝግብ ወቅት ፣ ሥለ ትያትሩ ግምገማ ላይ መቅረብ አውሥቶ ፀግሽ በቁጭት” ፑሽኪንን ማነው የገመገመው ? ” በማለት በአንድ መፅሔት ላይ መልሥ ሲሰጥ እንዳነበብኩ አሥታውሣለሁ ። እናም ሮፍ ናንን ከፀግሽ ግጥም ቀንጭቦ በተሸለመበት አንድ መድረክ ላይ ከሁለት ዓመት በፊት ተጫውቶት ነበር ። )

ዛሬም ሮፍ ናን ፣ ” የአገር ልጅ ሥምሽን አገኘሽ ወይ ? ሲል በመጠየቅ ፣ ሰው ነህ ፣ ሰው ነኝ ፣ ሰው ነን ፣… የሰው ልጅ ከፍጥረቱ ጀምሮ ከሰማይ የተሰጠው ሥም ” ሰው” ነው ። በማለት ፣ ማንም ለማንም የተለያየ የጎሳ ሥም በመሥጠት ሰውን ከሰውነቱ ሊያወጣው ና ሊፍቀው ከቶም አይችልም ። በማለት መልዕክቱን አሥተላልፏል ።

ሮፍናን ፣ ሰውነትን እና እኛ ኢትዮጵያዊያን የተለየ ባህላዊ ና ተፈጥሯዊ ቅርሰ እና ማንነት እንዳለን ” ሰከላ ” በተሰኘ የዘፈን ግጥሙ በማንጎራጎር ፣ በማንነታችን እንድንኮራ ከማድረጉም በላይ በፈጣሪ ከተሰጠን የተፈጥሮ ፀጋ ጋራ ያለንን ቁርኝት መለሥ ብለን በመቃኘት ወደ ቀልባችን እንድንመለሥ መክሮናል ።

ሮፍ ናን ፣ በውብ ዜማው እያዋዛ ሥለ ኢትዮጵያዊነት ና ሥለ ሰውነት ፣ ሥለፍቅርና ሥለ ሰው አፈርነት ነግሮናል ። ትውልድ በቅብብሎሽ ሲጓዝ አኩሪ ታሪኩን እንዳይዘነጋ አሳስቧል ። ኢትዮጵያዊውው የዓለም አካል ነው ። ሰው የተባለ ፍጥረት ነው ። የሰውነት እና የኢትዮጵያዊነቱን ጉዞ የጀመረውም ከ3000 ዓመት በፊት ነው ።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የሽብርተኛ አዋጅ ደንግጎ ሽብርተኛን መፍታት ሊያመጣ የሚችለው ክስተት ምን ይሆናል?

ኢትዮጵያ የኃይማኖትም አገር ናት ። ኃይማኖት ሰው ሁሉ እኩል እና የአዳምና የሄዋን ዘር እንደሆነ የሚሰብክ ነው ። ኃይማኖት አባቶችም አለቃ ፈጣሪ መሆኑ ይታወቃል ። ( በእኛ አገር ግን አንዳንዶች ፣ አለቃቸው ገንዘብ እንደሆነ በድርጊታቸው እያረጋገጡልን ነው ። ፈጣሪ ይቅር ይበላቸው ። ) እንደምታውቁት በተረጋገጠ ታሪክ በ34 ኛው ዓ/ም ነው ኢትዮጵያ ፣ በኢትዮጵያዊው ጀንደረባ አማካኝነት ክርሥትናንን የተቀበለችው ። ( በ325 ዓ/ም ከኒቂያ ጉባኤ በኋላ ነው የሚሉ አሉ ። አሥገዳጁን የግብፅ ኮፕቲክ ኦርቶዶክስ ተፅዕኖ እና እሥከ1955 ድረሥ ፓትርያርክ ሆነው የሚሾሙት ግብፆች እነደነበሩም አስታውሱ ። አትዘንጉ ። በአፄ ኀይለሥላሴ ዘመን ነው ። አቡነ ባሲለስ የመጀመሪያው ኢትዮጵያዊ ፓትርያርክ ሆነው በግብፅ ኦርቶዶክስ ቤተክርስቴን በዓለ ሢመታቸው የተከናወነው፡፡ በወቅቱ ግርናዊነታቸው ታድመዋል ።

የእሥልምና ኃይማኖት ወደኢትዮጵያ የገባው በአረብ አገራት እሥልምና ሳይሥፋፋ በፊት ፣ እንደሆነም ይታወቃል ። ( በነገራችን ላይ ፣ በኃይማኖቱ ብቻ ሣይሆን የአሜሪካም ሆነ የአውሮፖ መንግሥታት ሳይፈጠሩ ኢትዮጵያ በለሰፊ ግዛት አገር ነበረች ። ቀይ ባህርም የኢትይጵያ ግዛት ነበር ። ኤርትራ የሚባል ስምም የ17 ኛውመ ክ/ዘ ታሪክ ነው ። እሥከ 19 ኛው ክ/ዘ ኤርትራ የሚባል ሥያሜ አልነበረም ። ቀይ ባህር በባህረ ነጋሾች የሚመራ የኢትዮጵያ ግዛት ነበር ። የባህር ንጉሶችን የሚሾሙትም የኢትዮጵያ ነገሥታት ነበሩ ። የመጨረሻው የባህረ ነጋሽ አሥተዳዳሪ ራሥ አሉላ አባነጋ ነበሩ ።

ዛሬ ወያኔ የዘራውን ሰውነትን የሚያሥረሳ የግብዝነት ፍሬ እየበሉ ያደጉ ሰው ጠል በመሆናቸው ፣ በቋንቋ እያመካኙ እጃቸውን ታጥበው መብላቱ እንዳይቀርባቸው የፖለቲካ ነጋዴዎቹ ፣ ዛሬም የኢትዮጵያ ብልፅግና እንቅፋቶች ሆነው ተገኝተዋል ።
በዚህ ወቅት ነው ሮፍ ናን የግብዞችን ናላ የሚያዞር ፣ ብዙሃኑንን ኢትዮጵያዊ ልቡን በሃሴት የሚሞላ ፣በደስታም የሚያፍነክንክ ፣” ሠከላ ” ብሎ ታላቅ መልዕክት እንሆ ኢትዮጵያዊያን ያለን ። ታላቅነታችንን አብሳሪ ፣ የአያቶቻችንን ና ቅድማያቶቻችንን ህብረት ና ፍቅር መሥካሪ የሆነውን የዘፈን ውብ ግጥሙን እንሆ !

ሠከላ
ሠከላ አባይን ወለደ
እናቴም እኔን !
ኢትዮጵያኖች እንደምንአላችሁ
የአንዲት እናት ልጆች በአድ የሌላችሁ
እሯ እላለሁ
እሯ በልዬ
የዛ ጀግና ልጅ
የዛ ሰውዬ ።
እሯ በል አንተ
እሯ በልዬ
የዛ ጀግና ልጅ
የዛ ሰውዬ
ግባልኝ !
ይህ ይድረሰው ለዛ ሰው
ወራሪውን ለመለሰው
የነፃነት ተምሳሌት አድርጎ
ሥሜን ክብር ላወረሰው
ያደረክልኝ ብዙ ነው ከፍዬም አልጨርሰው
ያረክልኝ ሁሌም አዲስ ነው
በሄድኩበት የምለብሰው ።
ብጠራው ሥምህን ዓመት መች ይበቃል
በዓለም ያለ ጥቁር ፣ ከትውልድ ትውልድ አንተን ያመሰግናል
እሯ በል አንተ
ምንም እንኳን ከአንተ ባያምርብኝ
ዛሬ ላይ የምፅፈው ፣ የእኔ የሚሆን ታሪክ ፣ ጭለማ ቢመሥልብኝም
ተሥፋ አለመቁረጥ ከአንተ ተምሬለሁ ፣ አደራህም አለብኝ !
እሯ ልበል እንደአንተ ምንም እንኳን ከአንተ ባያምርብኝ !
ሠከላ አባይን ወለደች
እናቴም እኔን ።
ቅድሚያ ሰው ! ደግመው ግን ማነህ ቢሉኝ ?
ኢትዮጵያ ነው ሥሜ ።
አልወድቅም ለመድረሥ ፣ እጄ ቢያጥርም
……..ከበላይ ባልዘልቅም ።
ባይመሥልም ፣ አንዴ አያቅተኝም
እንደ ቴዎድሮስ ባልደግምም ።
አዝማች ……..
እሯ በል !
እሯ በልልኝ !
የዚያ ጀግና ልጅ …
ግባልኝ !
አሀሀይ ጉማ !
ጦቢያው ለይቅርታ ቅደም
ቀድመህ እንድትተው ድገም ።
ድገም ቢያሥቀድምህ መልሥ
የአባትክን አደራ መልሥ
ያኔ በላይ ይዘልቃል
ያንጊዜም ቴዎድሮስ ይደገማል
ያንጊዜም አሉላ ራሥ ነው
ምኒልክ ዛሬም ንጉሥ ነው ።
በልልኝ አንተ ሰው
በልልኝ አንተው
ራሥህ ላይ
ይቀርባል አንተ ሰው ።
እሯ በልበት ጥላቻ ላይ
የአደዋ ዘማቹ የልጅ ልጅ ።
እኔ እና አንተ አይደለን
ሮፍ ናንን ዘእምነገደ ጦቢያው
የአንተም እንድያ አይደለም
ሠከላ አባይን ወለደች
አባቴም እኔን ።
ቅዲሚያ ሰው ደግመው ግን ማነህ ሲሉኝ
ኢትዮጵያ ነው ሥሜ !
ከቶ አልቀርም ለመድረሥ ፣ እግሬ ቢያጥርም
አብዲሳን ባልቀድምም ።
ሲይጨልም ሳይመሽ
ለይቅርታ ላዝግም ።
ጣይቱን አልሰጥም ።
እሯ እላለሁ
የልብ አድርሥ
የዛ ጀግና ልጅ
የዮሐንስ !
እሯ በል አንተ
እሯ በልልኝ
የጃጋማ ልጅ
ግባልኝ !
………አዝማች
ሁሉም ትውልድ አደዋ አለው
የእኔም አድዋ ልቤ ላይ ነው ።
ቢገኝ ፍቅር ማሳያ
በይቅር ልቆ መገኛ ።
ያንጊዜ አብዲሳ ይደርሳል
በልቤም ባልቻ ይነፍሳል
ዮሐንስ ደሙ ወርቅ ነው
ላልከዳው ጴጥሮሥ መልሥ ነው ።
ጠበቁኝ በደም እርሰው
የጥፋት ጉድጓድን ምሰው
በሰባራቸው አፍሰው ።
ሰባራ ሰንደቅን ይዘው ።
እንግዲህማ እኔ ልሻል
መርዙን በይቅርታ ልሻር ።
ከአባቶቼም በይሆንልኝ
ከአያቶቼ አንድነትን ልማር ።
እሯ ልበል የዛሬ ሰው
ፍቅር ፈሰሰብኝ ልፈሰው ።
ልንተባተብ ጀግንነቱን
ከልቤ ላግኝ ምህረቱን ።
አሹ !

ተጨማሪ ያንብቡ:  እንደ ዘበት ያለፉት ነፍሶች - (እውነተኛ የወንጀል ታሪክ)

 

2 Comments

  1. ዋው! ሰሚ ቢገኝ ጥሩ ምክር ነው። ዘመኑ በዳይ ተበዳይ ነኝ የሚልበት ጊዜ ሆነና ነው እንጂ ይቅር ማለት ተገቢ ነበር። ጠ/ሚ አቢይ ወያኔን ይቅር ቢላቸውም እነሱ ግን በእኛ ይባስ ብለው አሁን ያለንበት መቀመቅ ውስጥ ከተቱን። እንግዲህ የዚህ አይነቱን ጉዳይ በዚያው በተለመደው አረመኒያዊ ትንቅንቅ መፍታት ነው ሌላ ምን አማራጭ አለ?

Leave a Reply

Your email address will not be published.

Share