ፈረስ ተቀይሯል!! ጋላቢው ማን ይሆን? – ጌድዮን በቀለ

ወያኔ አምጦ-አምጦ ሲንቆራጠጥና ሲወራጭ ከርሞ ፈረስ ቀይሯል፤ ልጓሙም ፤ኮርቻውም፤ ለኮውም ያው የቀድሞው ወያኔ ነው። ከህዝቡ ጋር እልህ የተጋባ ይመስል ለፈረሱ እቃ ማለዘቢያ ቅባት እንኳን አልቀባባውም። የወያኔ ስማበለው ሽፈራው ሸንቁጤ እንቅጩን ነግረውናል፤ ማንም ይሁን ማን “የኢሃዴግ ሊቀመንበር ዋና ተልኮው የፓርቲውን አላማ ማስፈጽም ነው!” ተወደደም ተጠላ ”አብዮታዊ ዲሞክራሲ ዛሬም ባሸናፊነት ወጥቷል!!”ምን ትሆኑ! አይነት።

ባለሙሉ ተስፈኞች፤የቢሆን ቅን አሳቢዎችና አትድከሙ ባዮች ባንድ ላይ በየራሳቸው ምክንያት ከወራት በላይ ላስቆጠረው የወያኔ ዱለታ ጆራቸውን ቀስረው እኩል ተወጥረው ከርመዋል።እንደልብ አንጠልጣይ ድራማ ህዝብን በማይወክል አምባገነንና ፋሽስታዊ ቡድን ድራማዊ ሽኩቻ አጋ ለይተው ተከራክረዋል፤የክርክሩን ይዘት አንዳንዶች ከባብ እንቁላል እርግብ የመጠበቅ ያህል ቢቆጥሩትም ሌሎች ደግሞ ላለፉት ሶስትና አራት ዓመታት በሁሉም የኢትዮጵያ ክልሎች በተለይም በኦሮሚያና አማራ ክልሎች የተካሂያዱ ህዝባዊ ቁጣዎች የተነሳ የተወለደው “የለማ ቲም”ና “የገዱ አንዳርጋቸው” ቡድን የሚባል ስያሜ የሚታውቀው ለውጥ-ለውጥ የሸተተው ወገን ባሳየው ህዝባዊ ወገንተኛነት አዝማሚያዎች ከድቅድቅ ጨለማ መሃል እንደምትታይ የብርሃን ጭላንጭል ለተስፋ ጠባቂዎች ተስፋ ሆኖ መታየቱ  አያስገርምም።

ተስፋው ወደ አምልኮ ተቀይሮ ውጤታማ እየሆነ በሄደው ትግል ላይ ቀዝቃዛ ውሃ ካልቸለሰበት በስተቀር። ከታሪክ እንዳየነው ህዝብ መሪነቱን ከእጁ አውጥቶ ለቡድኖችና በቡድን ስም ለሚመጡ ግለሰቦች አሳልፎ በመስጠት ድሉን ያስነጠቀበት አሳዛኝ ገጠመኝ የቅርብ ጊዜ አስከፊ ትዝታ ነው።

ያሁኑ የህዝብ ተሰፋና ጉጉት ተቀያሪው ፈረስ እንደ አቶ ሐይለማርያም የዎያኔን “አብዮታዊ ዲሞክራሲ” ተሸክሞ በወገኖቹ አስክሬን ላይ ይረማመዳል? ወይስ በልጃቸው አስከሬን ላይ እንዲቀመጡ የተገደዱትን እናት፤ ባንድ ቀን ሶስት ለጆቻቸውን ያጡትን አባት፡ ብዙ ሽህ ኢትዮጵያውያን ለሞት የታደርጉበትን ፤ ከቀያቸው ተፈናቅለው ለስደት የተዳረጉበትን፤ በስር የሚማቅቁበትን “የዎያኔ አስከፊ ስርአት” የሚያበቃበትን መደላድል ለማበጀት ፊቱን አዙሮ ይጋልባል? የፈሰስውን እምባ ለማበስ ወይንስ ጨምሮ ለማስለቀስ ይተጋል? በሚሉት ገልጽና ግልጽ በሆኑ መጠይቆች የተሞላ ነው።

ተጨማሪ ያንብቡ:  አቶ ገለታው ዘለቀ በኢትዮ 360 ላይ ተጋብዞ ስርዓታዊ ሽብር በሚለው አርዕስት ላይ በኤርምያስ ለገሰ ለቀረቡለት ጥያቄዎች ለሰጣቸው መልሶች ትችታዊ አስተያየት!

ለሁሉም በመጭው ሰኞ አዲሱ ጠቅላይ ሚንስትር በበዓለ-ሲመታቸው በሚያደርጉት ዲስኩር የማን ፈረስ እንደሆኑ ወይም በየትኛው እርካብ ለመቆንጠጥ እንደተዘጋጁ የሚያመላክቱ ፍንጮች እናገኛለን። ዶክተር አብይ የትኛውን አይነት ፈረስ ለመሆን እንደሚመርጡ እሳቸው ያውቃሉ። እየሞተ ያለውን ጉድጓዱ የተማሰለትን ወያኔንና ፤ እሳቸውንና ጓደኞቻቸውን ጨምሮ በባርነትና ሎሌነት ለሃያሰባት ዓመት  ሲነዳቸው የኖረውን የበሰበሰ ስርአት አዝለው ወደመቃብር መውረድ ወይስ እየጎመራ የሄደውን እሳቸውንና ድርጅታቸውን ጭምር ነጻነት የሚያጎናጽፋቸውን የህዝብ ትግል በመቀላቀል ደንገላሳ መርገጥ።

ብዙዎች እንደሚሉትና እንደተስማሙበት አዲሱ ፈረስ በመንታ መንገድ ላይ መቆማቸውን እኔም እስማማለሁ። ለኔ  ግን የማስተዋል ልቡናውን ላልተቀማና በህሊናውና በአይምሮው ለሚመራ ባለብዙ ተስፋ ወጣት በስመ መንታ መንገድ እንደዚህ ባለ ቀላልና ግልጽ ምርጫ ይደናገራል ብየ አላስብም።

የሚያስፈልገው ጎንበስ ብሎ የቆመበትን መሬት ማየት ብቻ በቂው ነው። ጎንበስ ሲሉ የቆሙበት መሬት ላይ ገና ያልደረቀ እልፍ ኢትዮጵያውያን እምቦቃቅላ ህጻናት ደም መጫሚያቸውን እንዳጨቀየው ያስተውላሉ። ያለ አበሳቸው ኦሮሞ በመሆናቸው በቻ በባዶ እጃቸው እንዲበረከኩ ተገደው በጥይት የተደበደቡት ወጣቶች ደም ይከረፋቸዋል። አማርኛ በመናገራቸው ብቻ ወልደው ከብደው ባፈሩበትና በኖሩበት ቀዬ በቆንጨራና ባካፋ የተጨፈጨፉ እናቶችና ህጻናት አጽም ይጎረብጣቸዋል። ይሄኔ ታድያ የትኛውን ጎዳና መምረጥ እንደሚገባቸው ለቅጽበት አይጠራጠሩም። ቀና ሲሉ ትናንት እሳቸውና ወንበዴዎቹ ለወንበር ሲራኮቱ ከጎናቸው የነበሩት የስራ ባልደረቦቻቸው እንደጥጃ ተጠፍረው ወህኒ መወርወራቸውን ማስተዋል አይሳነቸውም።

በገዛ ቤታቸው ለምን ትስቃላችሁ፤ለምን ያን ሁሉ በደል ፈጽመንባችሁ አገር ጥላችሁ አልፈረጠጣችሁም እንደማለት “ አምባሻ” የሌለው ባንዲራ በታችሁ ወሰጥ ሰቅላቸኋል በሚል አሳበው ዳግም በገፍ ለስር የዳረጓቸውን ጋዜጠኞችና የፖለቲካ መሪዎች እጣ ሲስሙ ነገ ለሳቸውም እንደማይቀር ማሰብ ያቅታቸዋል በሚል አልጠረጥራቸውም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ወያኔ ቅዠት እንጂ ራዕይ የለውም! በመቅደስ አበራ (ከጀርመን)

ስለዚሀም ነው ከዶክተሩ ፊት የተደቀነው ምርጫ እንደኔ አተያይ ከነጻነትና ባርነት ከታሪክ ሰሪነትና የታሪክ አተላነት የትኛውን ትመርጣለህ? የማለት ያህል የቀለለ የሚሆነው። ነጻነትን መርጠው ቢሞቱም ክብር ቢያሸንፉም ድርብ-ድርብርብ ድል ነው። ከመንታ መንገድ ይልቅ ታሪክ ለዶ/ር አብይ ማንም የኢትዮጵያ መሪ ያላገኘውን በብዙ ገጽታው የተመቻቸና የተደላደል እድል ስጥታቸዋለች።

አንደኛውና የመጀመሪያው ገና በትረመንግስቱን በስርአት መያዙ ላልተረጋገጠ እጩ መሪ  ዳር እስከዳር ደጋፊና ተቃዋሚ ህዝብ ባንድ ላይ ሊባል በሚችል ደረጃ እንደነጻነት አሻጋሪ ተስፋ ማሳደሩ በራሱ ካለፉት የቅርብ ጊዜ መሪዎች የተለየ መልካም እድል መሆኑ ሊታወቅ ይገባል። ይህ ብቻውን ዶክተሩ ወዴት ማዘንበል እንዳለባቸው ዋነኛ አመላካች ነው።

ኢትዮጵያውያን ከንግዲህ ወዲያ ያለነጻነት ከመኖር ሞት ይሻለናል ማለታቸውን ግንባራቸውን ላልሞ ተኳሽ ወያኔ ገዳይ ቡድን ያለፍርሃት እየሰጡ ወደፊት መገስገሳቸውና በዚሁ የተነሳ  በወያኔ ስፈር ውስጥ የተፈጠረው ትርምስና መፍረክረክ ሁለተኛው የ ዶክተሩ ጉልበት ምንጭ ነው።

ሶስተኛው ለ27 አመት ጉልበትም ወረትም አንደበትም በመሆን ዎያኔን እሽክብ-እሽክብ ሲያደርጉት የነበሩት አሜሪካንና የአውሮፓ መንግስታት 180 ድግሪ ፊታቸውን መዞራቸው ፤ እንደደቡብ ሱዳን ያሉ ሙጥቅላ አገሮችን ጨምሮ ሌሎች ጎረቤት ያፍሪካ አገሮች  ሳይቀሩ ያላገጡበት የዎያኔ ቡድን ባሳፋሪ ሁኔታ ጥርሱ መወላለቁን ለመረዳት ከአብይ የቀረበ የማወቅ እድል ያለው ሊኖር አይችለም።

ዶክተሩ ሩቅ ሳይሄዱ ቆሜለታለሁ የሚሉት የኦሮሞ ህዝብ በወጣት ልጆቹ አማካኝነት ባቀጣጠለው ትግል ተገፍቶና ተበራቶ ጆሮውን ለህዝብ መስጠት የጀመረው ድርጅታቸው በዚህ አጭር ጊዜ ባገኘው ህዝባዊ ድጋፍ ብቻ የወያኔን ሰፈር እንዳርበተበተው ማስተዋል ከቻሉ የትኛው ጎዳና መከተል ቀና መሆኑን መለካት አይሳናቸውም።

ተጨማሪ ያንብቡ:  “መነሻችን እዚህ መዳረሻችን እዚያ” የሚለው የዲያስፖራ ከንቱ አታካራ!

እነዚህና ሌሎች ያልጠቅስኳቸው በርካታ መልካም እድሎች ከዝብ ጎን በመሰለፍ በዎያኔና አጃቢዎቹ ዙሪያ ተንጠልጥሎ የቀረውን ያብዮታዊ ዲሞክራሲ በትርና ማስፈራሪያ የሆነውን “ዲሞክራሲያዊ ማእከላዊነትን” ጥሰው ለመውጣት የሚያስችል ጉልበት እንደሚያስገኙላቸው በማሰብ ዶክተሩ በዘመን አንድ ጊዜ የሚገኝ ታላቅ ስራ ሰርተው ዘመን ተሻጋሪ ሰም ክብርና ዝና የሚጎናጸፉበት እድል ወለል በሎ ተከፍቶላቸዋል ባይ ነኝ።

እንግዲህ አዲሱ ፈረስ በዘመን አንድ ጊዜ ተመቻችቶ የቀረበላቸውን መልካም እድል ተገን አርገው ሊጫንባቸው የተዝጋጀውን ኮርቻ አሽቅንጥረው በማእክላዊነት ስም ከተለጎሙበት ልጓምና ድርጅታዊ ዲሲፕሊን አለንጋ ለመላቀቅ በድፍረት ተጋፍጠው ለዝና ወዳበቃቸው ህዝብ ለመቀላቀል ይጋልባሉ ወይስ ያበቃለትን ይወያኔ ስራት ለማስቀጠል ያብዮታዊ ዲሞክራሲ ፈረስ ሆነው በህዝቡ አስከሬንና አጽም ላይ ጉግስ ይጫወታሉ?

ለሁሉም የኢትዮጵያ ህዝብ ለወራት በተካሂያደ ምጥ  ለአቅመ ጠቅላይ ሚንስትር የበቁትን ዶክተር በተስፋና በጥርጣሬ  ስሜት እንደ ንስር አይኑን አፍጦ እንደ ውሻ ባፍንጫው እያነፈነፈ ጆሮውን ቀስሮ እየተጠባበቀ ነው። ማንን እንደሚመርጡ የበአል ሲመታቸው ዕለት ይገልጡልናል በማለት ተስፋ እናድርግ።

ጌድዮን በቀለ – gedionbe56@yahoo.com

 

1 Comment

  1. voice of desperation and defeat !

    Nothing comes out of a dark mind born and raised in suspicion and misery !

Comments are closed.

Share