December 24, 2017
8 mins read

የህወኣት እሪያ ሊሆን የሚፈቅድ ማነዉ? – መኮንን ሀብተጊዮርጊስ ብሩ (ዶ/ር)

 

መኮንን ሀብተጊዮርጊስ ብሩ (ዶ/ር)

የታሰበበት ሕልምና ድርጊት በተናጠልም ይሁን በጋራ ከመልካም ወይም ከክፉ መንፈስ ነዉ። መልካም መስሎ ክፉ፤ አልያም ክፉ መስሎ መልካም የሆነ ተግባር ሊኖር ቢችልም ምንም ይሁን ምን ሁሉም ነገር በጊዜ ዉስጥ እየጠራና እየተገለፅ መሄዱ አይቀርም። ወንጌላዊዉ ማቴዎስ ክፉዎችንና ሰዉ አሳዳጆች አጋንንት ያደረባቸዉ ናቸዉ ሲል ይገልፃቸዋል። ማንስ ቢሆን የተቀደሰ መንፈስ ተላብሶ የራሱን አምሳያና ወገን ክፉና አሳዳጅ ሊሆን ይቻለዋል?። ለጊዜዉም ቢሆን የአጋንንት መኖሪያ ደግሞ የእሪያ መንጋ እንደሆነ ወንጌል ያስተምረናል (የማቴዎስ ወንጌል 8:30) ። ስለዚህ አሁን በትግልና በፀሎት ዉስጥ አያለን የምንጠይቀዉ የህወኣት እሪያ ሊሆን የሚፈቅድ ወይም የሚያልም ማን ነዉ የሚል ነዉ።

ህወኣት በደደቢት በርሃ በቅድስቲታ ሀገር ላይ ክፋትንና መለያየትን መርጦ መንቀሳቀስ ሲጀምር ፈቅዶም ይሁን ሳይፈቅድ ያኔ የአጋንንት ማደሪያና መፈንጫ እሪያ መሆን መርጧል። ላለፉት አርባ ዓመታት የእርኩስ መንፈስ የእሪያ መንጋ ሆኖ በዋለና ባደረበት ሁሉ ወንድምን ከወንድሙ፣ ልጅን ከአባት እናቱ፣ ትዉልድ ከትዉልድ፣ አንዱን ወገን ከሌላዉ ወገን እያናቆረና እያለያየ እስካሁን ቢቆይም ተገፍተዉ ተገፍተዉ እመቃብር አፋፍ የደረሱት የቅድስቲቷ ምድር ሰዎች ግን በቃን ብለዋል። አዎን በቃ!! የበቃን ግን ህወኣት ብቻ ሳይሆን በእነሱ በእሪያዎቹ ላይ ያለዉም መንፈስ ነዉ።

‘መልካም ሰዉ ከልቡ መልካም መዝገብ መልካም ነገርን ያወጣል። ክፉ ሰዉም ከክፉ መዝገብ ክፉ ነገርን ያወጣል’ ይላል የአምላክ ቃል (የማቴዎስ ወንጌል 12 :33)። ክፉት ደግሞ ከጎምዛዛ ፍሬዋ ትታወቃለች። ለቀባሪው ማርዳት ቢሆንብኝም የህወኣትን ጎምዛዛ ፍሬ በርካታ ሚሊዮን ኦሮሞች፣ አማሮች፣ ጉራጌዎች፣ በጥቅሉ ኢትዮጲያዊያን ሳይወዱ በግድ እንዲዉጡ ተደርገዋል። በርካቶች ከአያት ከቅድመ አያታቸዉ ሲወርድ ሲዋረድ ከመጣ መኖሪና እርሻቸዉ ላይ ተፈናቅለዉ አባወራ ተብለዉና ተከብረዉ እንዳልኖሩ በስተርጅና የሴት ልጅ ገላ የሚቸረቸርበት ዳንስ ቤት የበር ዘበኛ መሆን ዕጣቸዉ ሲሆኑ ታዝበናል። ከቀበሌዋ ርቃ ተጉዛ የማታዉቅ ታዳጊ ወጣት እንደ አበባና ሰሊጥ እየተጫነች ለስቃይና በደል በየ አረብ አገራቱ ስትጣል፤ ከዚያም ጨርቋን ጥላ ስታብድ አይተናል። በቀን አንዴ በልቶ ማደር አልችል ብለዉ እራሳቸዉም ቤተሰባቸዉም በጠኔ ከመት የባሕር ውሃ አልያም የምድር እባብ ይግደለኝ ብለዉ ወጥተዉ መቅረታቸዉን ሰምተናል። አሁን በዚህች ሰዓት ሴት ወንዱ፤ ሼህ ባህታዊዉ፤ ሽማግሌ ወጣቱ፣ ኦሮሞና አማራዉ ወገንና ተቆርቋሪ እንደሌለዉ እትብቱ በተቀበረበት የራሱ ሀገር ላይ በግዞት ሆኖ፤ እርኩስ መንፈስ በተሸከሙ እሪያዎች የቁም ስቃይ እያየ መሆናቸዉን እናዉቃለን። ይህ ሁሉ ስቃይ፣ ይህ ሁሉ ስደት፣ ይህ ሁሉ ግዞት በእሪያዎቹ ተጭኖ የመጣ እርኩስ መንፈስ ዉጤት በመሆኑ ለአንዴና ለመጨረሻ ጊዜ ከምድራችን ሊወገድ የሚችለዉ እሪያ ላለመሆን በፈቀደ ሕዝብና መሪዎች ብቻ ነዉ።

ሴይጣን ክርስቶስን ሊፈታትን ወደ ከፍታ ቦታ ወስዶ ዝቅ ብለህ ብትሰግድልኝ ይህን ሁሉ እሰጥሃለዉ ሲል የዓለምን ፈጣሪ በቁሳቁስ ሊመዝነዉ እንደሞከረ ያህል በኢትዮጲያ ምድር ያሉ እሪያዎችም የኢትዮጲያን ሕዝብ ጥያቄ አሳንሰዉ እንደበፊቱ ብትንበረከኩልን ጥቂት ስልጣን እንሰጣችኋለን፣ ስንፈልግ ያሰርናቸዉን ጥቂት ንፁዓን እንፈታላችኋለን፣ ሌላም ሌላም ዕቃ ዕቃ እንጨምርላችኋለን በማለት ለአርባ ዓመታት የተሸከሙትን ጋኔን ሌላዉ ላይ ጭነዉ ሊያራክሱ መሞከራውቸዉ እንደታረደ ከብት መንፈራገጣቸው መሆኑ የገባቸዉ መሪዎች እንዳሉ ሁሉ ሊሳሳቱና ከእርያዉ ጋር እሪያ ሊሆኑ የፈቀዱ መኖራቸዉን ታዝበናል። ተወደደም ተጠላም ጥያቄዉ የነፃነትና የመከባበር ነዉ። ጥያቄዉ በዛች ምድር ላይ ሁሉም በሕግ ፊት እኩል ሆኖ የመኖር መብት ነዉ። ጥያቄው አዳማሞ ይሁን መቀሌ፣ ባሕር ዳርም ይሁን ድሬደዋ በዚያች ምድር ላይ የተወለደ ሕፃን እኩል ተጠቃሚም ተጎጂም ይሆን ዘንድ ነዉ። ጥያቄዉ ዕቃቃ ልመና አይደለም፣ ይልቁንም በርካቶች ደማቸዉን ባፈሰሱላትና አጥንታቸዉን በከሰከሱላት ምድር የተወለድን ሁሉ ሀገራችን ብለን ደስታና ሐዘኑን በጋራና በእኩልነት መቋደስ የምንችልበትን ምድርን ከእሪያዎች መረከብ ነዉ። ስለዚህ ከነፃነት ያነሰ ጥያቄ ሊኖር አይገባም። ለጊዜው ጥቂቶች ይሁዳን ሊሆኑና ሕዝባቸዉን ሊያሞኙ ቢመርጡ ሊመጣ ያለዉን ትንሳኤ ግን ፈፅሞ ሊያስቀሩ አይችሉም፤ ምክንያቱም በታሪክ በየትኛዉ ቦታና ጊዜ አንድ የሆነ ሕዝብ ተሸንፎ አያዉቅምና።

የሀገሬ ሰዉ ሊሞት ያለ ከብት ይፈራገጣል ይላል። ቅዱስ መፅሐፉም እርኩስ የተሸከሙት እሪያዎች ከአፋፍ ወደ ገደል ከዛም ወደ ባሕር ተወረወሩ ይላል። ስለዚህ ጥያቄዉ በዚህ ትንሳኤ በቀረበ ሰሞን የህወኣት እርኩስ መንፈስ እሪያ ሊሆን የሚፈቅድና አብሮ ወደ ባሕር ለመወርወር የሚከጅል ተላላ አለ ወይ? ነዉ።

አምላክ ሆይ ከክፉ ሐሳብና ተግባር ሕዝብህን ጠብቅ። አሜን።

 

2 Comments

  1. መኮንን ሀብተጊዮርጊስ ብሩ (ዶ/ር)፣ ህወሓት ኣመራሩን በባንዳዎች ተጠልፎ በታኝ እንደሆነ ኣቃለሁ። ኣንተ ግን ትክክለኛው ታሪክ እየደበቅ ውሸት ፈጠራ ግዜህን ከምታባክን ትታረም ዘንድ እመክርሃለሁ። “የህወኣት እሪያ ሊሆን የሚፈቅድ ወይም የሚያልም ማን ነዉ የሚል ነዉ፤” የደርግ ጨካኝነትና የናንተ የስልጣን ጥማት፣ ስልጣን ከያዙ በሓላም እንዴት ትግሬ ስልጣን ይይዛሉ ብላቹሁ መንቀሳቀሳቹሁ፣ ህወሓት በከፈተው የዘር/መንደር ክፍፍል እናንተም እንደዛው መሰበሰባቹሁ ወዘተ ናቸው። መወነጃጀሉ ይቅር ምክንያቱም ፍርድ የሚሰጥ የለም መጀመርያ ተባብረን ሕግ የመላይነት ስርዓት እንመስርት ከዛ ወንጀለኞች በሕግ ይጠየቃሉ ኣለበለዝያ እናንተ ከምን ጸድታቹሁ ነውና ሁሉም ወደ ወያኔ የምትለጥፉት።

Comments are closed.

Previous Story

We got a right to pick a little fight, Bonanza

Next Story

ይብላኝ ለህወኣትና ለተክላይ – መኮንን ሀብተጊዮርጊስ ብሩ (ዶ/ር)

Latest from Blog

አስቸኳይ ህዝባዊ ጥሪ

July 24, 2024 ዓለማቀፍ ትብብር ለኢትዮጵያዊያን መብት Global alliance for the Rights of Ethiopians (GARE) በደቡብ ኢትዮጵያ ክልል ገዜ ጎፋ ወረዳ ኬንቾ ሳቻ ጎዝዲ ቀበሌ በደረሰው የመሬት መንሸራተት የብዙ ወገኖቻችንን ህይዎት ማለፉን
Go toTop