የሙስናው አዙሪትና ማረበሎቹ – ከ ሙሉጌታ ገዛኸኝ

 

ባለፉት ሁለት አስርት ዓመታት ሙስና በአገራችን የተለመደ ባህል እንጅ ፈፅሞ አነጋጋሪ ቀይ ስህተት ሊባል አልተቻለም፡፡

ጥናቶች እንደሚጠቁሙት ሙስና መንስዔው ዓይነተ-ብዙ ገፅታ የተላበሰና  አደገኛ ውስብስብ ረጋ ሰራሽ የኅብረተሰብ ጠላቶች ከሚባሉት ቀዳሚውን ድርሻ ይይዛል፡፡ የማኅበራዊ ጠንቅና ግብረ ገብነት መጓደል፣ የልማት በላየሰብ፣ ተጠያቂነትና ግልፀኝነት የጎደለው አሰራር ያለመኖር እንዲሁም የሕግ የበላይነት ያለመስፈን ዓይነተኛ ማሳያ ነው፡፡

ቀደም ባሉት ዘመናት ጉቦ፤ መተያያ፤ እጅ መንሻ፤ ወዘተርፈ በሚባሉ መጠሪያዎች ይታወቅ የነበረ ቢሆንም ኢሕአዴግ መራሹ ድርጅት በትረ ስልጣን ከተረከበ ወዲህ በወል ስያሜ ሙስና የሚል የዳቦ ስም ሰጥቶታል፡፡ ስያሜውም ህጋዊ ሰውነት ኖሮት እነሆ ዛሬም ጥቅም ላይ ውሏል፡፡ ግለኛና ቋንጃ ቆራጭ ሹመኞች ከድሀው ሕዝብ ጉሮሮ ይመነድባሉ፡፡ አድራጎቱ ከጨቅላ ሕፃን ጡጦ ነጥቆ ከመጥባት በምን ይለያል፡፡ ሙስና፣ ሌብነት፣ የዋጋ ንረትና ኑሮ ውድነት ሕዝቡን ጥሪት አልባ ማድረጉ አይቀርም ቢባል አልተጋነነም፡፡ በብልሹ ጎጣዊ አሰራር እንዲሁ አበሳውን የሚቆጥረው ሕዝብ ገዥ ፓርቲውን አምርሮ መጥላቱና ለውጥ መሻቱ ምንስ ቅር ያሰኛል?፡፡ በዘመነ መሣፍንት በየጁ ባላባቶች መካከል በተፈጠረ የስልጣንና የጥቅም ሽኩቻ የታዘበው አዝማሪ ስንኝ ሲቋጥር እንዲህም ተብሎ ነበር አሉ፡፡ ‘ማንም ያሻውን ቢል ያም ሌላ ያም ሌላ፤ አንዱን የእናትህ ልጅ ብሩን ይዘህ ብላ’ ፡፡  በአሁኑ ዘመን በሙስና ቅሌት የተጠረጠሩ የመንግስት ሹመኞችና የምዝበራው ተባባሪ ግለሰቦች የመያዛቸው ዜና በሕዝብ ዘንድ የተሰለቸ እንጂ ሰበር ዜና ተብሎ መቅረቡ ብቻ ነው የሚያስገርመው፡፡

መንግስት ሙስናን በቁርጠኝነት እየተዋጋ እንደሆነ የዜና ማሰራጫዎች ዘወትር ይለፍፋሉ፡፡ አልፎ አልፎም ሕዝቡ በሰላማዊ ሠልፍ ሙስናን እንዲያወግዝ ጥሪ የሚያደርጉ አስተዳደር አካባቢዎች እንዳሉ እንሰማለን፡፡ ግን ሙስናን ለመከላከል ሀቀኛ መላው እንዲህ የታጣለት ካቅም በላይ ሆኖ ይሆን ጥያቄ ያጭራል? ራሳቸውን ካበለፀጉ በኋላ ሲገመገሙ በሹም ሽር ወደ ሌላ ሃላፊነት ቦታ ይታጫሉ፤ ይፈነጫሉ፡፡ ባልበለፀገ ሉቃሳም ሲተካኩ እንዲህ ሠርግና ምላሽ ሆኖላቸው ይፈነጫሉ፡፡ ጌታዋን የተማመነች በግ ላቷን እደጅ ታሳድራለች ነውና የተማመኑበትን የፖለቲካ ድርጅት እንደ መዥገር ተጣብቀው ደም እየመጠጡ ያሻቸውን ይፈፅሉ፡፡ ከአፄው ዘመን ጀምሮ ፓለቲካዊ ጋብቻና አምቻ ልማድ ትስስሩ  ለጥፋት ማቅለያ ያህል በደጅ ጠኝነት ሸንቆጥ ተደርጎ ይታለፋል፡፡ በአሁኑ መንግስትም ይኸው ነው የሚስተዋለው፡፡ የፖለቲካ ድርጅቱን ቁርባነ ምስጢር ጨብጦ እዚያው ደጅ ጠኝ መሆንን ይጠይቃል፤ ጋብቻና አምቻውም አዋጭ ስለሆነ ከአንዱ የሥራ ሃላፊነት ወደ ሌላ ቢጠናም አምባሳደርነቱን ማን ይከለክላል፡፡ ጃንሆይ አሉ እንደሚባለው «ተዉት ክፉ ሰው ለክፉ ቀን ይጠቅማል» ይሆን ነገሩ፡፡   እርግማን አይሉት ያለመታደል የሹማምንት አባዜ የታሪካችን ውርስ ሆኖ እንደኮሶ ተጣብቶን ዛሬም መፍትሄው አልተገኘም፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ጀግንነት የሁለት ፊደላት ፍጥረት ነው ። ሥራ!

ሙስና ከአገር ክህደት ተለይቶ መታየት የማይገባው ስለሆነ በጊዜው ነውረኞቹን ወደ ምፅኣት ፍርድ ማድረሱ የማይቀር ነው፡፡ ሙስና በአሁኑ ዘመን እጅግ ስር ሰዶ የሥርዓቱ ልዩ መለያ ሆኖ በቀላሉ መከላከል ያልተቻለበት ዋናው ምክንያት በፖለቲካ ወገንተኝነት ላይ በተፈጠረ ምቹ አጋጣሚ መሆኑን በርካቶች ይስማሙበታል፡፡ የሞራል ልዕልና ብቃት የሌላቸው ነገር ግን ተዋፅዖን ለማመጣጠን በሰበባሰበቡ ወደ መንግስታዊ ሃላፊነት ይጋበዛሉ፡፡ ብቃትን ግምት ውስጥ ያለማስገባቱ ግለሰቦች አጋጣሚውን ለብልሹ አሰራር ወይም ንቅዘት ይዳርጉታል፡፡ ይህ በጥንታዊ ግሪኮች ሰፍኖ ከነበረው የኦሊጋርኪ አገዛዝ መሰል አደጋው በአገርና በሕዝብ ህልውና ላይ ከባድ ሆናል፡፡

በቀዳማዊ ኃይለ ሥላሴ ዘመነ መንግሥት በሕዝብ ላይ አስተዳደራዊ በደል ያደረሱና በምግባረ ብልሹነት ጉቦ መተያያ በመቀበል ያስመረሩ ባለስልጣናትና ሹማምንት ጉዳያቸው በገለልተኛ መርማመሪ ኮሚሽን እንዲጣራ በፓርላማ እውቅና የተሰጠው ኮሚሲዮን ተቋቁሞ ነበር፡፡ በተፈጠረለት አብዮታዊ ግርግር የደርግ ወታደራዊ ጁንታ ስልጣን በመንጠቁ የምርመራ ኮሚሽኑ ተግባር ተሰናከለ፤ የህግ የበላይነትን አፈር ድሜ አበላው፡፡ የበታች ወታደሮችና መኰንኖች ፍላጎት ብቻ እነዚያ የአገር ባለውለታ ሰዎች ሰብዓዊ መብታቸው ተገፎ በአሰቃቂ ሁኔታ ተረሸኑ፡፡ ከዚያም በኋላ ወታደራዊው ደርግ በሚወስደው የጭካኔ እርምጃ መደናገጥ በመፈጠሩ የዲሞክራሲዊ ጥያቄ በውይይት መሆኑ ቀርቶ መልኩን ቀየረ፡፡ በዘመነ ደርግ ለተወሰነ ጊዜያት የጉቦ በሊታነትና ብልሹ አሰራር አባዜ እየቀነሰ መምጣቱ አይዘነጋም፡፡ ነገር ግን በአስተሳሰብ ለውጥ ሳይሆን በግድያ እርምጃ ላይ ብቻ መመርኮዙ ከዘላቂ መፍትሄው ይልቅ ከማስተንፈሻነት አልዘለለም፡፡

በአሁኑ ዘመን የሚፈፀመው የሙስና ባሕሪ ደግሞ ከበፊቱ ምን ይለየዋል ስንል? አፈፃፀሙ ረቀቅ ያለና በተደራጀ መልክ የገንዘብ ስወራው በውጭ ባንኮች በተለይም ለዓለም የገንዘብ ድርጅት(አይ.ኤም.ኤፍ) ቁጥጥር አሻፈረን በሚሉ የሩቅ ምስራቅ አገሮች ይቀመጣል፡፡ በአገር ውስጥ ደግሞ በተለያዩ ዘመዳ ዘመዶቻቸው ወይም ሽርክና ባላቸው የንግድ አጋሮቻቸው ስም ገንዘቡና ድርጅቱ ይንቀሳቀሳል፡፡ አሁን ፋሽኑ እያለፈበት መጣ እንጂ ሎተሪ ከደረሰው ግለሰብ ላይ እጣውን በመግዛት የሀብት ምንጩ ሎተሪ እንደሆነ ወሬው ይነዛል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሰልፋችሁን ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር አድርጉ - ከይኄይስ እውነቱ

የሙስና ችግር እየተጠናከረ በመሄዱ ያሳስበኛል ያለው መንግስት የፀረ- ሙስናና የሕዝብ እንባ ጠባቂ የሚባል ተቋም በአዋጅ እንዲመሰረት ቢደረግም የተፈለገውን ለውጥ እምብዛም አላስገኘም፡፡ በሥነ ዜጋወ ሥነ ምግባር ትምህርት ውስጥ ተካቶ ስለ አገር ወዳድነት እና የሙስና አስከፊነት ትምህርቱ ለወጣት ተማሪዎች የሚሰጥ ቢሆንም ሙስናን አስመልክቶ በብዙሀን መገናኛ(ሚዲዎች) የሚቀርቡ ማስታዉቂያዎችም እንዴት እንደሚሞሰን ትምህርት ይቀስምበታል፡፡

የሕዝብ ቁጣ ሲያይል ደግሞ የመንግስት ሹምና ባለስልጣን በነፍስ ወከፍ ያፈራውን ሀብት ማስመዝገብ አለበት የምትል ብልጭ ብላ ጥፍት የምትል እንቅስቃሴ አለች፡፡ ታዲያ ምን ያህል ተመዘገበ? ምን ያህል ትርፍስ አካበቱ? ምን ያህሉስ ወደ ሕዝብ ተመላሽ ተደረገ? እግዜር ይወቀው፡፡ አንዳንዱ ከነበረበት ቦታ ሲመጣ ምንም ያለነበረው በአጭር ጊዜ ውስጥ ወደ ሚሊየነርነት ይቀየራል፡፡ የአራትና አምስት ሰማይ ጠቀስ ፎቆች ባለቤት ሆኖ ያከራያል፤ ይሸጣል ይለውጣል፡፡ ስልጣንን ያለአግባብ በመጠቀም የሚገኝ ሀብት መሆኑን ሕዝቡ ጠንቅቆ ያውቃል፡፡  በቅርብ ጊዜ ደግሞ ፀረ- ሙስና ኮሚሽን በጠቅላይ አቃቤ ሕግ ስር ሆኖ የፀረ ሙስና ትግሉን አመቺ ያደርገዋልም ተብሏል፡፡ «ዲሞክራሲን እናጠናክር፣ ድሀ ተኮር ፖሊሲ፣..» ወዘተርፈ ምኞት ብቻ ሳይሆን ኮሚሽኑ በተግባር ራሱን ችሎ ተጠናክሮ የሚያከናውንበት አቅም መፍጠሩ ላይ ነው ቁም ነገሩ፡፡

የድሀው ኅብረተሰብ በደም መጣጭ ሙሰኞች ህይዎቱ በቀቢፀ ተስፋ ከዛሬ ነገ ኑሮዬ ይሻሻልኛል ለሚያስበው ሁላ እጣ ፋንታው መራቆትና የዕለት ተዕለት ሰቀቀን መግፋትን ይገደዳል፡፡ አወይ ሙስና! ሙስና አሏት ስሟን አሳምረው!

ትራንፓረንሲ ኢንተርናሽናል የተባለው ዓለም አቀፉ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት እ.ኤ.አ በ2005 ይፋ ባደረገው የዳሰሳ ጥናት ሪፖርት ሙስና በማደግ ላይ ባሉ አገሮች በተለይም ከሰሀራ በታች ባሉ አገሮች ምቹ የሆነ የሀብት ማግበስበሻና ወደ ውጭ አገራት ባንኮች በህገወጥ መንገድ የገንዘብ ፍሰት ይካሄድበታል፡፡ አብዛኛው ገንዘብ በብድርና እርዳታ የሚገኝ ሲሆን ለልዩ ልዩ የልማት ፕሮዤዎች ማካሄጃ ይውላል የሚታሰብ እንደነበር የዳሰሳ ጥናቱ ይጠቁማል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ኮለኔል ጎሹ ወልዴ እና ዶር ታዬ ወ/ሰማያት ወዴት ገቡ?

አፍሪካ በአደጉ አገራት እርዳታና ብድር ቋሚ ጥገኛ እንድትሆንና የተቆለለባትን እዳ ባለመክፈል ለእጅ አዙር ቅኝ ግዛት እንደሚያጋልጣት ይገለፃል፡፡ በተለይም እንደ ኢትዮጵያ ከድህነት ወለል በታች ያሉ አገራት ሕዝባቸውን በቅጡ መመገብ የተሳናቸው የቀጣዩ ትውልድ የተደቀነበትን ከባድ የህልውና ቀውስ እንዴት ሊታደጉት ይችላሉ? መፍትሄውስ ከወዴት ይሆን? አሳሳቢ ነው፡፡

አብዛኞቹ ጥናቶች ከሙስና አዙሪት ለመውጣት የዲሞክራሲን ባሕል ማዳበርና ማስረፅ ለአሳሳቢው ችግር መፍትሄው በቂ ነው ብለው ቢያስቀምጡም ፍቱን አልሆነም፡፡ ሌሎች  እንደሚሉት ደግሞ በንግድ ኩባንያዎች እና በመንግስታዊ ፓርቲ መዋቅር ያለው ትስስር ማላቀቅ፣ የፖለቲካ ሥርዓቱ ሙስናና የልኂቃን ምቹ አጋጣሚውን መጠቀም እሳቤን ማስቀረት፣ ግልፀኝነትን ተጠያቂነትን፣ የመንግስ ስልጣን ሕዝብን ማገልገያ ታሪካዊ እድል እንጅ ራስን ማንደላቀቂያና ማበልፀጊያ ዓነተኛ መሳሪያ እንዳልሆነ መገንዘብ የቻሉ ቁርጠኛ አገር ወዳድ ዜጎችን ያአንዳች ቅድመ መስፈርት የሃላፊነት ቦታዎችን መስጠት፣ ለብልሹ አሰራር ምቹ ሁኔታን የሚፈጥሩ መንግስታዊ የአሰራር መዋቅሮችን በሚገባ ማጤን፣ ማንም ሰው ለህግ የበለካነት መገዛትን በተግባር ለማስመስከር ውስን የበታች አመራሮችን ብቻ ማሳደድ ሳይሆን ችግሩ የሚመለከታቸው ከፍተኛ ሹማምንትም በተጠያቂነት ለፍርድ መቅረብ የመሳሰሉት ሀሳቦችን በዓይነተኛ መፍትሄነት ይሰነዝራሉ፡፡ የሙስና ነገር ብዙ የሚያነጋግር ነውና በዚህች መጣጥፍ ሊቋጭ አይችልም፡፡ ልብ ብሎ ያዳመጠው የለም እንጅ የጥንቱ አራዳ ገበያ አዝማሪ ስንኙን ሲቋጥር እንዲህ ብሎም ነበር፡፡ «የአንገቷ ንቅሳት የጥርሷ ሙስና እሮብ ያስገድፋል እንኳን ሀሙስና፡፡» አንድ ወጣት ጡረተኛ(ጥሮተኛ) ወዳጄ ምን እያደረክ ነው አለኝ አይ የሙስናው አስከፊነት ስላሳሰበኝ እኔም የበኩሌን ትንሽ ልጫጭር ብዬ ነው አልኩት፤ እሱም… ኪ፤ ኪ፤ ኪ፤ኪ…አይ አንተ! እልቅስ በክረምቱ ዝናብ የአዲስ አበባ ጎዳናዎች ያለጀልባ አናሻግርም ወይፍንክች ሆኗል አሉ ታዲያ በተፈጠረው የሥራ እድል ምንአሰብክ? በአርምሞ ተለያየን…  ቸር ግጠመን!!!

 

 

Share