ከደጋጎቹ ጠበቆች መካከል አንዱ


[ ስመጥር የሆኑት ጠበቃ ተማም አባቡልጉ ! አግባብ ያልሆነው የ1ዓመት ከ7 ወር የእግድ ጊዜያቸው አብቅቶ፤ ፍርድ ቤቶች በክረምት ሊዘጉ ከቀናት በፊት የጥብቅና ፍቃዳቸውን ለማግኝት ችሏል ]

ጠበቃ ተማም አባቡልጉ


የጥብቅና ሙያ በታማኝነት፣በቅንነትና በታታሪነት የሚከናወን የሕግ የሙያ ሥራ ነው።ሙያው የራሱ የሆነ መብትና ግዴታ ያለው ሲሆን ይህንኑ ግዴታና መብት ያለመወጣት ደግሞ ምግባረ ብልሹነት ሲሆን ይሄም በራሱ ተጠያቂነትን ያስከትላል ፡፡ የጠበቆች ምዝገባና ፍቃድ አሰጣጥ አዋጅ ቁጥር 199/92 እንዲሁም፣ የጠበቆች የሥነ ምግባር ደንብ ቁጥር 57/92 እና ሌሎች የሕግ ደንጋጌዎች ይህንኑ ግንዛቤ ውስጥ በማስገባት ተጠያቂነት መቼ እና እንዴት ሊከተል እንደሚችል በግልጽ የሚያሳዩ የሕግ ድንጋጌዎች ናቸዉ ።

እነኚህን ድንጋጌዎችን ጠንቅቆ በማወቅ በሙያው አንቱታን ካተረፉት መካከል ስመጥር የሆኑት ጠበቃ ተማም አባቡልጉ አንዱ ናቸዉ ። ቀደም ብሎ በዳኝነት ሙያ የረጅም ጊዜ አገልግሎት የሰጡ ሲሆን፣አሁን ላይ ደግሞ በጥብቅና ሙያ አገልግሎት እየሰጡ ይገኛሉ ። ጠበቃ ተማም አባቡልጉ ከሕግ ሙያው ባሻገር የስነጽሑፍ ችሎታቸው ቀላል የሚባል አይደለም ።በተለያዩ ጋዜጦች እና መፅሔቶች ላይ የተለያዩ ርእሰ -ጉዳዮችን በማንሳት ለአንባቢያን ሃሳባቸውን በጽሑፍ በቀላል የመግለጽ ተሰጥኦ ጭምር ያላቸው ጠበቃ ናቸዉ ።

የጥብቅና ሙያ ለሕግ የበላይነት መከበር የሚኖረው አስተዋፅኦ ከፍተኛ እንደመሆኑ መጠን፤ጠበቃ ተማም አባቡልጉ በሙያቸው የሕግ የበላይነት እንዲከበር የበኩላቸውን አስተዋፅኦ ከማድረግ ወደኋላ እንደማይል የሥሯቸውን በጎ ሥራዎች በመመልከት ምስክርነት መስጠት ይቻላል ።ከነዚህም መካከል በአገራችን ኢትዮጵያ የሕግ የበላይነት እንዲከበር የሚጠይቁ የሰብዓዊ እና የዴሞክራሲ መብት ተሟጋቾች እንዲሁም ፖለቲከኞች የሚያደርጉትን ህጋዊ እንቅስቃሴ እግር-በእግር በመከተል በሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት የሚወስዳቸው የተለያዩ እርምጃዎች ዓለም የሚያውቀው የአደባባይ ምስጢር ነው። ሆኖም ግን ጠበቃ ተማማ አባቡልጉ እነኚህ የመብት ተሟጋቾች ለሕግ የበላይነት እንዲከበር በሚንቀሳቀሱበት ወቅት ለእስር እና እንግልት ሲዳረጉ ሙያዊ የሕግ ድጋፍ እንዲሰጡ ሲጠየቅ ሳያመነቱ በጎ ምላሻቸውን ሁሌም እንደሰጡ ነው ።

የፖለቲካ እና የህሊና እስረኞች በአገዛዙ ሥርዓት የሚደርስባቸው በደል እና እንግልት እንደተጠበቀ ሆኖ፤ ሌላው እና አስቸጋሪው ነገር የሕግ አማካሪ እና ጠበቃ ማግኘት ነው። አብዛኛዎቹ ጠበቆች የፖለቲካ ጉዳዮ ጥብቅና እንዲይዙ ሲጠየቁ በሚታወቀው እና በማይታወቅ ምክንያቶች ፍቃደኛ አይሆንም ። ሆኖም ግን ጠበቃ ተማም አባቡልጉ የሙስሊም ህብረተሰብ የመፍትኄ አፈላላጊ ኮሚቴ አባላት”የእነ-ኡስታዝ
አቡበከር አህመድ” ፣ በእነ ዘላለም ወርቃገኘሁ የክስ መዝገብ በፌደራል አቃቤ ህግ የሽብር ክስ የተመሰረተባቸው አራቱ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች አመራሮች እና ጋዜጠኞች፣ እንዲሁም ሌሎች በተመሳሳይ የሽብር ክስ የተከሰ የህሊና የፖለቲካ እስረኞች እና ተከሳሾች ጥብቅና ቆመዉ ለተከሳሾች የሕግ አገልግሎት ሰጥቷል ። ለሰጡትም አገልግሎት በአብዛኛው በነፃ ሲሆን የተወሰኑት በአነስተኛ ዋጋ ነው። (ይህን ሃቅ የፖለቲካ እና የህሊና እስረኞች የሚመሰክሩት ጭምር ነው።)

ይሁን እንጂ በሙያቸው አንቱታን ካተረፉት መካከል አንዱ የሆኑት ጠበቃ ተማም “በሥነ- ምግባር ጉድለት” በማለት በመጀመሪያ አንድ ዓመት ፤ ቀጥሎም ምክንያቱ በግልጽ ባልተቀመጠበት ሁኔታ በድጋሚ ለሰባት ወራትን በአጠቃላይ አንድ አመት ከሰባት ወር ከሙያው እንዲታገድ ተደርጓል ። ለእግድ ያበቋቸው ምክንያቶች የጠበቆች ምዝገባና ፍቃድ አሰጣጥ አዋጅ ፣ የጠበቆች የሥነ ምግባር ደንብ እና ሌሎች የሕግ ደንጋጌዎች ተላልፈው በመገኘታቸው ሳይሆን ፤ከዚህ ቀደም ለሎሚ መጽሄት በሰጠው አስተያየት ሲሆን፣ ሰማያዊ ፓርቲ የሽብረተኞች መጠቀሚያ ሆኗል በሚል በኢትዮጵያ ቴሌቪዥን የቀረበውን ዘገባ በመተቸታቸው እንዲሁም በኢትዮጵያ የጸረ ሽብር ህግ ላይ ነፃ አስተያየት በመስጠታቸው ነው። በተጨማሪ የኢትዮጵያ ቴሌቪዥንንና የጸረ ሽብር ህጉን ታዓማኒነት እንዳይኖረው አድርገዋል የሚል አቤቱታ ቀርቦባቸው አንድ አመት ከሰባት ወር ከጥብቅና ሙያ እንዲታገዱ ምክንያት የሆነዉ ።ሆኖም ግን በታማኝነት ፣ በቅንነትቱ እና በታታሪነት የሚታወቁት ስመጥር የሆኑት ጠበቃ ፤ አግባብነት የሌለው ፍትሃዊ ያልሆነው የእግድ ጊዜያቸው አብቅቶ ፍርድ ቤቶች በክረምት ሊዘጉ ከቀናት በፊት፤ ለ1 አመት ከሰባት ወር ታግዶ የነበረው የጥብቅና ፍቃዳቸውን ለማግኘት የቻሉት ።

(ይድነቃቸው ከበደ)

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሶቪየት ኅብረት ከናዚ ጀርመን ጭፍጨፋ አስጥላቸው ኔቶ ሥር የተሸጎጡ የባልቲክ አገሮች *ከጎርባቾቭ ውሳኔ መዘዝ፤ - ከጌታቸው ወልዩ (ሜክሲኮ ባህረ-ሰላጤ)
Share