የኢትዮጵያ ህዝብ ትግል ለስርዓት ለውጥ እንጂ ለግብር ቅናሽ አይደለም – የኢትዮጵያ ሕዝብ የጋራ ትግል ሸንጎ (ሸንጎ)

ሐምሌ 13፣ 2009 (ጁላይ 20፣ 2017)

በተለያዩ ጊዜ የተለያዩ ችግሮችን እየፈጠረ እድሜውን ማርዘም የሚሞክረው አገር አጥፊ ወያኔ መራሹ ቡድን ከጥቂት ቀናት በፊት ህዝቡ ሊከፍል የማይችለውን የግብር ዕዳ ጥሎበት እያስጨነቀው ይገኛል።ይህንን በእብሪትና በግዴለሽነት የወጣ በጉልበት የማስገደድ ህግ የታገዘ የዘረፋ እቅድ  በሌላው መጠነ ብዙ ጸረህዝብ ውሳኔ ላይ ሲጨመርበት የእምቢ ባይነት ክብሪት ጭሮ በመላ አገሪቱ በመባል ደረጃ የህዝብ እምቢተኝነት እንደ ቋያ እሳት እየተቀጣጠለ በመሄድ ላይ ነው።

ህዝቡ ባለፉት ዓመታት ያሳየውን ትዕግስትና ቻይነት እንደሞኝነትና ፍርሃት የቆጠሩት ስልጣን ያወራቸው ባለስልጣኖች የህዝቡን ጥያቄ ከመመለስ ይልቅ በአገርና በወገን ላይ ሊፈጸም በማይችል መልኩ ያለ የሌለ ወታደራዊ አቅም በማፍሰስ ለመቆጣጠር ቢሞክሩም ሊሳካላቸው አልቻለም።የህዝቡን ትግል በጥልቀትም በብዛትም ከመሄድ አላገደውም።መስዋእትነቱ ቢበዛም የማታ ማታ በህዝቡ ድል እንደሚጠናቀቅ የታሪክ ማህደሮች ይመሰክራሉ።

ከዓመት በፊት በኦሮሞው ማህበረሰብ ተቀስቅሶ የነበረው ህዝባዊ ትግል በትግሉ ነጠላነትና ከሌላው ማህበረሰብ ጋር ባለመያያዙ  ለጊዜው ቢዳከምም ውስጥ ውስጡን እየተብላላ አሁን ዳግመኛ ለማገርሸት ምልክት እያሳየ ነው።በአምቦ፣በሆለታ፣ባሰበ ተፈሪና በሌሎቹም ቦታዎች የህዝብ እምቢተኛነት እያስተጋባ በመምጣት ላይ ነው።አልፎ ተርፎም አዲስ አበባን ዳር ዳሩን እየለበለባት ነው፤ወደ መሃል ከተማ ለመግባት የቀናት ጉዳይ ይመስላል።በሌሎቹም ከተማዎች እንዲሁ።በጎንደርና በጎጃም፣በሸዋና በወሎ የተቀጣጠለው ህዝባዊ አመጽ ምህዳሩን እያሰፋ ሌሎቹንም ክፍላተ ሃገራት እየሳበ አገር አቀፍ ትግል ወደ መሆኑ እየተሸጋገረ መጥቷል። ሁኔታው ዳግማዊ የካቲትን የሚወልድ ይመስላል።ያ ከሆነ ደግሞ እንደ የካቲቱ 1966 ትግሉ እንዳይጠለፍና የሌላ አምባገነን ቡድን መጠቀሚያ እንዳይሆን መጠንቀቅና ከዚያ አደጋ የሚከላከል ሃይል ማደራጀትና የትግሉን አቅጣጫ የሚቀይስ የጋራ አመራር መፍጠር ግድ ይላል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአሜሪካ በጥቅሟ ላይ የተመሰረተው የውጭ ፖሊሲ እና ከአፍሪካውያን አምባገነኖች ጋር ቀን እስኪጎድልባቸው የምትፈጥረው ወዳጅነት በቆዩት ዲፕሎማቶቿ ሪፖርት ውስጥ ሲፈተሽ

የህዝቡ ጥያቄ የወያኔን መንግስት ይህን አድርግልኝ ወይም ግብር ቀንስልኝ ሳይሆን ለሚገለኝ፣ለሚያስረኝ፣ለሚያሳድደኝ፣ለሚዘርፈኝ ለማይወክለኝ መንግስት ነኝ ባይ አገር አጥፊ  ዘረኛ ቡድን ግብር አልከፍልም የሚል ነው።የህዝቡ ትግል በጎሳ ኢትዮጵያን ለመበታተን የሚደረገውን ደባ በመቃወም ኢትዮጵያ ወይም ሞት ብሎ የአገሩን አንድነትና ክብር ለማስጠበቅ የተነሳ አገር አድን ትግል ነው። የህዝቡ ጥያቄ የእኔ፣በእኔ፣ለእኔ የሆነ  ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ይስፈን ነው።ከዚህ መለስ በሽርፍራፊ ጥቅም ተደልሎ እቤቱ ቢገባ የመከራው ዘመን እንደሚራዘም ያውቀዋል።ችግርና ስደት ዘረፋና ግድያ እንደማይቆምለት ተረድቶታል።

የህዝቡ ጥያቄ ይህ ሆኖ ሳለ በድርድርና በልመና የወያኔን መራሹን ቡድን እገራለሁ ወይም የህዝቡን ጥያቄ እንዲመልስ አደርጋለሁ ማለት ጅልነት ሲሆን  በህዝቡ ላይ አዲስ እግር ብረት እንዲቀየርለት መሞከርና መሻት ነው።ለለውጥ ቆመናል የሚሉ ድርጅቶች ምርጫቸው ሁለት ብቻ ነው።ከህዝቡ ትግል ጋር ደፍሮ መቀላቀልና አመራር መስጠት ወይም ከወያኔ ጋር አብሮ መጨፍለቅ። ወያኔ ጫካ ሲገባ ጀምሮ የነበረው ዓላማ ዘረኛና ኢትዮጵያ የምትባል አገር ፈራርሳ የራሴ ነው ብሎ የወሰነበትን አንዱን የኢትዮጵያ ክፍለሃገር መገንጠል  ነው። የህዝቡ ትግል ለውድቀቱ እንደሚዳርገው ካወቀ የመገንጠል ኦላማውን እውን ለማድረግ መሞከሩ አይቀርም፤ሌሎቹም ፈለጉን እንዲከተሉት ከማድረግ አይመለስም።ይህን አገር አፍራሽ አደገኛ አዝማሚያ ገና ከጧቱ ማጨናገፍ ይገባል፤የሚጨናገፈውም በኢትዮጵያ አንድነት የሚያምነው ትግሉን ሲያቀናጅና ሲተባበር ነው።የትግራይ ተወላጅም የዚህ አገር አድን ትግል አካል ሊሆን ይገባዋል። የትግራይ ክ/ሃገር የትግራዮች ብቻ ሳይሆን የመላ ኢትዮጵያዊ መሬት ነው፤ የሌላውም ክ/ሃገር መሬት እንዲሁ የትግራዩም ጭምር ነው።ትግራይ የኖረችው ከደቡብ፣ከምስራቅ፣ከምእራብና ሰሜን ተነስቶ ከሁሉም አቅጣጫ የዘመተ ኢትዮጵያዊ በከፈለው የህይወት ዋጋ እንጂ ወያኔ ከተፈጠረ በኻላ የተቆረቆረች አገር አይደለችም።የትግራይ ተወላጅ የወያኔን እኩይ ዓላማ ማጋለጥና መታገል አለበት። በጊዜያዊ ጥቅምና ወገንተኝነት ሊታለል አይገባም።ለትውልድ የሚያልፍ አገር አስረክቦ ማለፍ ከእለታዊ ጥቅምና ብልጭልጭ ኑሮ ይልቃል።በታሪክ የሚያፍሩበት ሳይሆን የሚኮሩበት ስራ ሰርቶ ማለፍ  ለራስ ቀርቶ ለልጅ ልጅ ኩራት ነው።ይህን ተርድቶ ከቀሪው የኢትዮጵያ ህዝብ ወገኑ ጎን ለመሰለፍ መወሰን አለበት።የነጻነት ትግሉ ለራሱም ጭምር መሆኑን ሊረዳው ይገባል።ከህዝባዊው ትግል ጎራ ካልተቀላቀለ የመከራው ሰለባ ይሆናል፤ ሊቋቋመው የማይችለው ጣጣ ውስጥ ይገባል።

ተጨማሪ ያንብቡ:  ዕድገት ወይስ ዉድመት? - ዶ/ር በቀለ ገሠሠ

ትግሉ ከዳር እንዲደርስና ግቡን እንዲመታ የሁሉም መተባበር አስፈላጊና ወሳኝ ነው።በግርግር የወያኔና መሰል ተገንጣዮች ዓላማ እንዳይሳካ ነቅቶና ተደራጅቶ መጠበቅ ተገቢ ነው።ግርግር ለሌባ ያመቻል እንዲሉ አገራችን ከባሰ አደጋ ውስጥ እንዳትገባ ህዝባዊ ትግሉ በተቀናጀ መልክ መመራት ይኖርበታል።የጠላቴ ጠላት ወዳጄ ነው በሚል አጉል ፍልስፍና አገርን ለበለጠ ቀውስ ከሚዳርግ የፖለቲካ ጭምብል ውስጥ ላለመግባት ጥንቃቄ ማድረግ ያስፈልጋል።

የኢትዮጵያ ህዝብ የጋራ ትግል ሸንጎ(ሸንጎ) አሁን በመቀጣጠል ላይ ያለውን ህዝባዊ አመጽና ትግል እየደገፈ ሌሎቹም እንዲደግፉት ጥሪ ያደርጋል።ለአገር አንድነትና ለስርዓት ለውጥ በሚደረገው ህዝባዊ ትግል  ውስጥ  ተሰልፎ የሚቻለውን ለማድረግ ከመቸውም ጊዜ በላይ ዝግጁነቱን ይገልጻል።

የህዝብ ትግል ያሸንፋል!

የህዝቡ ትግል ለመሰረታዊ ለውጥ እንጂ ለጥገና ለውጥ አይደለም!!

 

Share