ለአዲስ ዓመት ቅድመ ዝግጅት- በራሳችን ላይ እንዝመት፣- ይገረም አለሙ

የዘመን መለወጫ ግዜ እንደ የሀገራቱ ቢለያይም በሁሉም የሰው ልጆች ዘንድ አንድ ተመሳሳይ ስሜት ይኖራል፣ በሁሉም ረገድ ካለፈው ዓመት የተሻለ መመኘት፡፡ ለዚህ ይመስለኛል አንኳን አደረሳችሁ፣እንኳን ከዘመን ዘመን አሸጋገራችሁ መጪው ዘመን የደስታ የፍቅር፣ የሰላም የብልጽግና ወዘተ ይሁንላችሁ የሚባለው፡፡ በሀገራችን ባህልም በዋዜማው ምሽት ችቦ ከቤት ተለኩሶ ሲወጣ ከበሩ ግራና ቀኝ እየተተረኮሰ የጎመን ምንቸት ውጣ የገንፎ ምንቸት ግባ የሚባለው የአዲስ አመት ተስፋ   ተስፋ መገለጫ ነው፡፡ (ይህን እንኳን የአብዮታዊ ዴሞክራሲ ልጆች በተለይ ከሀገር ውጪ ያሉቱ እምብዝም የሚያውቁት አይመስለኝም፤) ነገር ግን አንዲህ እያልን እየተመኘን እየተናገርን ግና የተመኘነው ላይ ሳንደርስ የናፈቅነውን ሳናገኝ አመታት ተቆጠሩ፡፡ ዘመኑ የቁጥር ለውጥ ማድረጉን እኛም ምንም አዲስ ነገር የሌለውን አዲስ አመት ማለቱን ቀጥለንበታል፡፡

የናፈቀ ሰው ወይ እርሱ የናፈቀው ሰው ወዳለበት ጨክኖ የሚቻለውን ሁሉ አድርጎ መሄድ ካልቻለ፣ ወይንም ያኛው ተናፋቂው እርሱ ካልመጣ መናፈቅ/መነፋፈቅ  ብቻውን ሊያገናኝ አይችልም፡፡ምኞትም ቢሆን የተመኙትን ነገር ለማግኘት መደረግ ያለበትን ካላደረጉ እደው ዝም ብሎ በመመኘት የሚገኝ ነገር የለም ሊኖርም አይችልም፡፡

አመቱ የቁጥር ለውት ባደረገ ቁጥር ሰላምና  ፍቅር እንመኛለን፣  ዴሞክራሲያዊ ሥርዓት እንናፍቃለን፤ መጪው አመት የሰላም የፍቅር የብልጽግና ወዘተ ይንላችሁ እንባባላለን፡፡ ነገር ግን የናፈቅነው ጋ ለመድረስም ሆነ የተመኘውን ለማግኘት የሚያስፈልገውን መፈጸም ባለመቻላችን ከወያኔ አገዛዝ መገላገል ተስኖን ሰላም እንዳጣን አርስ በእርስ መቀራረበብ ተስኖነወ ፈወቅር እንደራቀን አለን እንዳለን፡፡ ዛሬም ባዶ ምኞትና ተስፋ የምንገልጽበት ተግባር አልባ ምኞት የምንለዋወጥበት የአመት ለውጥ ሁለት ወራቶች ቀርተውታል፡፡

ወያኔ ሥልጣነ ወንበሩን ለማደላደል ዙሪያ ገባውን በሚያጠናበትና የኢትዮጵያውያንን ምኞት፣የፖለቲካ ቅዝቃዜ ሙቀት   በሚለካበት የመጀመሪያዎቹ ዓመታት ለዚሁ ተግባ  ከተጠቀመባቸው ዘዴዎች አንዱ ሀሳብን የመግለጽ ነጻነት መፍቀድ ነበር፡፡ ይህ ቢያንስ በሁለት መንገድ ጠቅሞታል፤አንድም ሰውን ለማስተንፈስ፣ብሎም ለማናካስ፣ ሁለትም ብንለቀቅ ምን ያህል እንደምንሄድ፣የቱን ያህል ለሥልጣኑ ሥጋት እንደምንሆን  ለማወቅና ልጓም ለማዘጋጀት አስችሎታል፡፡ እናማ በዛን አጭር የቆይታ ግዜ ወር እየጠበቅን በጉጉት እናነባቸው ከነበሩ መጽሄቶች አንዷ በነበረችው ሙዳይ ላይ ይጽፉ የነበሩ አንድ ሰው ምን የሚል አለ ብለነው ብለነው፣ ሲያልቅብን ግዜና እየደገምነው ያሉት ሁሌ ይታወሰኛል፡፡ ዛሬ ከአስር አመት በኋላ እኚህ ሰው በህይወት ካሉ ምን ሊሉ እንደሚችሉ መገመት ይከብዳል፡፡ ያኔ ሁሉ ተነግሮ ተጽፎ መደገም ተጀምሮ ከሆነ ከዛን ወዲህ የተባለው የተጻፈው ሁሉ ድግግሞሽ ነው ማለት ነው፡፡ ግን እኮ ምን ያልተነገረ ምን ያልተጻፈ ነገር አለ? ያልተተገበረ እንጂ የሞላው፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ከማይቀር ታሪካዊ ስህተት እና ክህደት ራሳችን እና አገራችን እንታደግ !

ይህን ያልኩት ያንን ማስታወስ  ፈልጌ ሳይሆን ብዬ ነበር ማለት የማልወደው ሰውዬ  በሁኔታዎች አስገዳጅነት ምን አልባትም ጸሀፊው እንዳሉት የሚባል አዲስ ነገር ባለመኖሩ መለስ ብዬ ዛሬ ባነሳሁት ርዕሰ ጉዳይ ላይ በየአዲስ አመቱ ዋዜማ እንደ አቅሚቲ አንስቼአቸው የነበሩ ሰሚ ያላገኙ ሀሳቦችን በማስታወስ ለማጣቀሻነት ማቅረብ አስፈልጎኝ ነው፡፡

ልክ እንደ አሁኑ ከሶስት ዓመት በፊት በ2006 ዓም መግቢያ ዋዜማ ላይ በአዲስ አመት ብንለውጥ የሚል ከእኛ ከኢትዮጵያውያኑ በተለይም በፖለቲካው ምህዳር ላይ ከሚስተዋሉት ሰዎች ባህርይ አንጻር ሊፈጸም የማይችል ቅዠት  ውስጥ ገብቼ በጻፍኩት ጽሁፍ ውስጥ፣ መጪው ዓመት 2006 ሙሉ ቁጥር ነው፡፡ ለሙሉ ቁጥር ያለው አመለካከት ደግሞ በአብዛኛው አወንታዊ ነው፡፡ ታዲያ በዚህ የሙሉ ቁጥር የዘመን መለወጫ እለት የጥል ምንቸት ውጣ የፍቅር ምንቸት ግባ፣ የበቀል ምንቸት ውጣ የይቅርታ ምንቸት ግባ፣ የጥርጣሬ የሸፍጥና የሴራ ምንቸት ውጣ፣ የመተማመን የቀናነትና የግልጽነት ምንቸት ግባ ወዘተ ማለት ብንችል በማለት ይህችን መልእክት ጻፍሁ፡፡

ለሀገር ይበጃሉ የተባሉ ያልተነገሩ ያልተጻፉ ነሮች የሉም ተግባራዊነት የለም እንጂ፡፡ ሌላው ቀርቶ ፖለቲከኞቻችን እነርሱው ከተናገሩትና ከጻፉት ከፊሉን እንኳን ገቢራዊ ማድርግ ቢችሉ ሀገራችን ዛሬ ካለችበት በብዙ መልኩ የተለወጠች ለመሆን በቻለች ነበር፡፡ እናም ከላይ የገለጽኩትን ለማለት መድፈሩ የመጀመሪያ ርምጃ ሆኖ ያሉትን ለመፈጸም መቻል ደግሞ ዋናውና ወሳኙ ጉዳይ ይሆናል፡፡ የምንለውን ተፈጻሚ ለማድረግ ለቃል የመታምን፣ ለህሊና የመገዛትና ከራስ በላይ የማሳብ ቁርጠኝነቱ ካለ 2006ን ለአስተማማኝ ለውጥ የሚያበቃንን ጠንካራ መሰረት የምንጥልበት አመት ማድረግ ይቻላል፡፡ ይህን ማድረግ ቻልን ማለት ደግሞ ለምርጫ 2007 ምቹ ሁኔታ መፍጠርና ትውልድ ተሻጋሪ የዴሞክራሲ ሥርዓት ለመገንባት የሚያበቃንን ጥርጊያ ጎዳና ተያያዝነው ማለት ነበር፡፡ ከራስ በላይ ለሀገር፣ ከሥልጣን ይልቅ ለትውልድ ማሰብ ካለ ይህ የማይቻልም የሚገድም አይደለም፡፡ ይቻላል! የሚል ሀሳብ ነበረበት፡፡

ግን አንዱም አልሆነምና 2006 እንደቀደሞቹ ሁሉ ግዜውን ጠብቆ ቀናቱን ቆጥሮ አለፈ፤2007ም በዚሁ መልኩ እንደውም እርሱ በተለየ ሁኔታ ወያኔን ለመቶ በመቶ የፓርላማ ወንበር አሸናፊነት አብቅቶ ሊጠናቀቅ ሲል በዋዜማው ያው ቅዠቴ አለቅ ብሎኝ በዲስ ዓመት ፍቅር ብንመሰርት በሚል ርዕስ በጻፍኩት ጽሁፍ እንዲህ የሚል መልእክት ለማስተላለፍ ሞከርሁ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የተቸካዮች ምክር ቤት  - ከበእውቀቱ ሥዩም

የቱንም ያህል ስንቆፍር ውለን ስንቆፍር ብናድር የሚያለያዩን ጉዳዮች አንድ ከሚያደርጉን በዝተውም ልቀውም ሊገኙ አይችሉም፡፡ እንደውም በሀቅና በንጹህ ህሊና በንጽጽር ከተፈተሸ የሚያለያዩን ሚዛን የማይደፉ ናቸው ማለት ይቻላል፡፡ ነገር ግን እነዚህ ገነውና ጎልተው ማዶና ማዶ እንድንቆም ለማድረግ የሚያስችል አቅም ያገኙት ከእኔ በላይ የሚል አጋንንት ሰፍሮብን  የመነጋገር ፈቃደኝነት፣ የመወያየት ባህል፤ የመደማመጥ ትእግሰት ያሳጣን በመሆናችን ነው፡፡ እናም በዚህ አዲስ አመት ዋዜማ ይህን አጋንንት እናስወጣና  የፍቅርን አምላክ ወደ ውስጣችን እናስገባ፡፡

ነገር ግን ከጋኔኑ ተላቀን ወደ ፍቅር መቅረብ ሳንችል 2008 አለቀ 2009ኝም ሊሰናበትን ይሄው ዋዜማው ላይ እንገኛለን፡፡ ወደ ፍቅር ቀረብን ማለት አግዚአብሄር ፍቅር ነውና ወደ እግዚአብሄር ቀረብን ማለት ነበር፡፡ ወደ እግዚብሄር ስንቅርብ ደግሞ ሁሉን አንደ ፍቃዱ የሚያደርግ የማይሳነው አምላክ ነጻነት ካሳጣን ወያኔም ፍቅር ከነሳን ሰይጣንም ይገላግለን ነበር፡፡እኛ ግን መች …..!

ዛሬም እነሆ ምንም ለውጥ ማምጣት አይደለም ለመለወጥ ሀሳቡ እንኳን ሳይኖረን 2009 ባለንበት እንደተገተርን ጥሎን ሊለወጥ ነው፡፡ የማይቆጨን መስቃ የማይመረን ምን ጎዶች ነን፡፡ሌላውን ለመውቀስ፣ ለመክሰስ፣ ለማኮሰስ የምንደፍር ራሳችንን ለማየት ግን ቅንጣት ወኔ የሌለን፣በራሳችን አይን ውስጥ ግንድ ተጋድሞ በሌላው አይን ውስጥ ሰንጥር ፍለጋ የምንማስን ፣ የሚገዙንን የምንንቅ የምንሳደብ የምናናቅ ግን በእነርሱ መገዛታችን ውርደት ሆኖ የማይታየን፣  አረ ስንቱ የእኛ ጉድ ተዘርዝሮ ይዘለቃል፡፡

ሀይሉ ገብረ ዮሀንስ ገሞራው ለሽልማትም ለእስራትም ባበቀው በረከተ መርገም የሚል ርእስ በሰጠው ግጥሙ ውስጥ “ያሰብከው ምኞትህ አልሆን ብሎ ሲከሽፍ ሁኔታው ሲጠጥር፣ ጠጣሩ እንዲላላ የላላውን ወጥር፤” የሚል ዘመን አይሽሬ መለልእት አስፍሮ ነበር፡፡የተማረበት ቀርቶ በቅጡ የተረዳው መኖሩ ያጠራጥራል እንጂ፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  በጎጠኝነት የታጀበ ከፍተኛ የስልጣን ሽኩቻ በብአዴን መንደር አለ - መስከረም አበራ

ሀያ ስድስት ዓመት ሙሉ ከወያኔ ጋር ያለውን ገመድ ጉተታ ትተን እርስ በእርት እየተጓተትን ወጥረን ተወጣጥረን ወያኔ እየተንገዳገደም ወድቆ እየተነሳም እንዲገዛ አበቃነው፡፡ ይህ ሊቆጨን ሲገባ ፈጽሞ ስሜት አልሰጠንምና፡አሁንም  እዛው የዛሬ ምናምን አመት በቆምንብት ነን፡፡ እንደው እስቲ በእኛ በቀጥታ ባይደርስብንም በአብዛኛው ኢትዮጵያዊ ላይ የሚፈጸመው ሞት እስራት ስደት እንግልት ይታሰበንና የሀገሪቱ በጥቂቶች መቦጥቦጥ ይቁጨንና አዲሱ አመት ከመድረሱ አስቀድሞ ባሉት ሶስት ወራቶች የጠጠረውን ትተን የላላውን የምንወጥርበት፣ የትም ሊደርሰን ካልቻለው መንገድ ወጥተን አዲስ መንገድ ምንመርጥበት፣ የሰአስተሳሰብ ለውጥ አድርገን ከራስ በላይ ሀገር ለማለት የምንበቃበት፣ዙፋኑ አንድ ብቻ መሆኑንና እርሱም በህዝብ ፈቃድ መያዝ የሚገባው መሆኑን በማመን በየኪሳችን ያለውን ዘውድ ለመጣል ቢያሳሳንም በየቁም ሳጥናችን ውስጥ የምንቆልፍበት  ደረጃ ላይ ለመድረስ የሚያስችለን ዘመቻ በየራሳችን  ላይ ላይ እናውጅ፡፡

ብእረኛው ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድን በትያትሩም በሥነ- ግጥሙም ለመምከርም ለማነሳሳትም ብሎ ብሎ ሲያቅተው  ይመስለኛል በስተመጨረሻው ግድም ይድረስ ለእኛ ከእኛ የሚል ተከታታይ ግጥም በጦቢያ መጽሄት አስነብቦን ነበር፤ ያም አንባቢ እንጂ የሚገነዘብ፣ የሚመለከት እንጂ የሚያስተውል ለማግኘት አልበቃም  እንጂ፤ እሱ እንኳን ይህችን ዓለም ከተሰናበተ አስራ አምስት አመታት ተቆጠሩ፡ በህይወት ያለነው ግን ወደፊት የለ ወደ ኋላ የለ እንደ ተርኪስ ባቡር ተገትረሽ ቅሪ እንደተባለው አንድ ቦታ እንደተቸከልን አለን፡፡ እስቲ ታዲያ ዛሬ እንኳን ትንሽ በምንላቸው መገዛታችን፣ በምንንቃቸው መዘረፋችን ይቁጨንና፣ ምንም ማደርግ ባለማቻላችን ህሊናችን ይወቀሰንና፣ ለልጆቻችን ምን እያቆየን እንደሆነ ለአፍታ ይታሰበንና ወዘተ የሶስት ወር ዘመቻ በራሳችን ላ አውጀን እኛ በእኛ ብለን እንነሳ፡፡ ያጣነው ፍቅር ነው እንጂ፤የራቀን ከራስ በላይ ማሰብ ነው እንጂ፣ችግራችን የሥልጣን ጥም ሆኖ ነው እንጂ  ወያኔን አስገድድም ሆነ አንበርክኮ ኢትዮጵያን የዴሞክራሲ ካባ ማለበስ ለ90 ሚሊዮን ሕዝብ የሚገድም የሚከብድም አልነበረም፡፡( ቀሪው ወያኔ ቢሆን ማለቴ ነው)

ታዲያ እንግዲህ አንቺ ኢትዮጵያ እኛስ ልጆችሽ ምንድን ነን?                                                                               አመንኩሸ ማለት የማንችል ፍቅራችን የሚያስነውረን፣                                                                                        ዕድላችን የሚያስፎክረን                                                                                                                       ቅንነት የሚያሳፍረን ቂማችን የሚያስደስተን                                                                                                            አረ ምንድን ነን? ምንድን ነን?                                                                                                          አሜኬላ የሚያብብብን                                                                                                                                ፍግ የሚለመልምብን

ሎሬት ጸጋዬ ገብረመድህን

 

Share