የዳዊት ጠጠር! (መብራቱ ከስቶክሆልም)

ሰዉ በሀገሩ እንደ ዜጋ እኩል ተወዳድሮ ለመኖር ከአንድ ብሔር መወለድ ወይንም በጥብቅ መዛመድ የቅድሚያ መመዘኛ ሲሆንበት፤ ወዶ ያላመጣዉ፣ ፈቅዶ ያልተዛመደዉ ብሄሩ የተፈጥሮ ዉበቱ ሳይሆን እርግማን ሲሆንበት፤ ተምሮ ማወቅ አዉቆ መጠየቁ፣ ለሀገሩ መቆርቆሩ በቅን ሳይታይለት ቀርቶ መጨረሻዉ እድለኛ ከሆነ ማዕከላዊ አለያም ቅሊንጦ መግባትና ሰዉሰራሽ ሲኦልን ማየት ማሳረግያዉ ሲሆን በለስ ያልቀናዉ ደግሞ በዚች ምድር የመኖርያ ቀኑ በአንባገነኑ ስርዓት ሲወሰንለት፤ አፈር ገፍቶ ለፍቶ ግሮ ጥሮ ሳይማር ያስተማረዉን ማህበረሰብ በዉቀቱ ለማገልገል በአምስት ለአንድ መጠርነፍ ግዴታ ሲሆንበት፤ በተወለደበት ሀገር እንደ ሁለተኛ ዜጋ መታየት፣ በገዛ ሃገሩ ባዕድ መሆንን፣ ተወዳድሮ ማሸነፍ ሳይቻል ሲቀር ስደትን አማራጭ የሌለዉ መፍትሄ አድርጎ ለመዉሰድ ይገደዳል ይሰደዳልም፡፡ እውነተኛ መግቢያ ባታገኝም ነብሱ ለግዜውም ቢሆን ማረፊያ በማግኘቷ በሀገሩ ካደመነበት ጥቁር ጭጋግ በመራቁ ለጊዜዉም ቢሆን ነብሱ እፎይታ ይሰማታል ነገ የሚል ተስፋ በልቡም ያጭራል:: ሆኖም የተፈጥሮ ጉዳይ ነዉና ሰው ከበቀለበት አፈር ተነጥሎ ሌላ ቦታ እስኪያፈራ ግዜ እንደሚወስድበት ሁሉ በስደት የሚኖርበት ባህል አፈር እና አየር አለመመቸት ከሀገር እና ከቤተሰብ ናፍቆት ጋር ተደምሮ ነፍሱን ምቾት ይነሳዋል፤ ሃሳቡና ቀልቡ ሁሌም ወደተወልደበት፣ አፈር ፈጭቶ፣ ጭቃ አቡኩቶ፣ የበሬ ጭራ ጎትቶ፣ ቦርቆ ወዳደገበት ቀየዉ ሽምጥ ይጋልበበታል በትዝታም ይቆዝማል፡፡

የወገን ጨዋታ በአይኑ እየዞረ ከዛሬ ነገ ይሻላል በሚል ተስፋ ከዚያም ሲያልፍ የኔንስ ሕይወት አንዴ ዉሃ በልቶታል ግን ወገኔን ቤተሰቦቼን ለምን ብሎ ሰዉነቱን ረስቶ ከክብሩ ዝቅ ብሎ ክብሩንና ማንነቱን ከማያዉቁለት በግ መሰል ተኩላዎች ጋር የተናጠቃትን ስጋ መሰል ጥሪት ተስፋ ወዳጣባት ሃገሩ መልሶ በሚልከዉ ገንዘብ የሀገሪቱን ኢኮኖሚ በሙስና ሀንጎቨርና በዘረኝነት አዙሪት የሚመራት መንግስት ነኝ ባይ ወንበዴ ዋነኛዉ የዉጭ ምንዛሬ ምንጭ ከመሆኑም ባሻገር ለወያኔ እብት ማስተንፈሻ ብሎም ከሰዉ በታች ሆኖ በላካት ጥሪት ለወንድሙ ሕይወት ቀነ ቀጠሮ መቁረጫ ምላጭ መግዣ መሆኑን ስረዳ ልቤ በሃዘን ይርዳል እረ ለመሆኑ ይህች ሀገር የማን ናት ብሎ ዉስጤ ይጠይቃል

ተጨማሪ ያንብቡ:  የማለዳ ወግ...ለአሚራና ቤተሰቦቿ የጎደለው ፍትህ ... !

ይህ ባለ ብዙ ጥያቄና ባለብዙ መልስ ባለቤት የሆነዉ ሃገሩን ናፋቂ ስደተኛ ለህዉሃት መራሹ አንባገነን መንግስት የዉጭ ምንዛሬ አቅም የመጀመሪያዉን ዱላ አቀባይ በመሆን መንግስት ከአሜሪካና አዉሮፓ ከሚያገኝዉ አመታዊ የገንዘብ ተፋሰስ ሰዎስትና አራት እጥፍ በዓመት በአማካኝ ከ3.5 ቢሊዮን ዶላር በላይ ገቢ ያደርጋል፡፡ ይህም ከዉጭ ቀጥታ ኢንቨስትመንት ከሚገኘዉ ገቢ ሲነፃፀር በ4 እጥፍ የሚበልጥ ሲሆን ወደዉጭ ሸቀጥ በመላክ የሚገኘውን  ገቢ 93 በመቶው ይሆናል ማለት ነዉ፡፡

ታድያ በንደዚህ ሁኔታ የተገኘን የዉጭን ምንዛሬ በመጠቀም ለሀገር እድገት ለልማት እንዲሁም በሀገራችን የሚታየዉን ዘርፈ ብዙ ችግሮች ለምፍታት ከመጣር ይልቅ ወንበዴዉና በወንበዴዉ ዉስጥ የተሰገሰጉ ሆዳችዉ የማይጠረቃ ቆዳቸዉ ከጅብ ጅማት የተሰሩ ነገራቸዉ ሁሉ እንብላዉ እንብላዉ የሆኑ በእብሪት የታበዩ ለማይረባ አይምሮ የተሰጡ የሀገር ሸክም ወንበዴዎች ጥቅማቸዉን ለማስጠበቅ ሌት ተቀን በወገኖቻችን ላይ ያማያባራ የግፍ ጎራዴዎቻቸዉን ከአፎቱ ከመዘዙ አመታት ተቆጠሩ::

ወገን በሰዉ ሀገር የብሶትና የናፍቆት እንባ ወደዉስጥ ያነባል፤ ከዛ ማዶ የአንድ ክልል ሰዎች ዳንኪራ ይረግጣሉ ዉስኪ ይራጫሉ ባንተ ገንዘብ ባንተ ምንዛሬ በተገዛ እርሳስ  ወንድምህ ለትምህርት እንደወጣ በዛዉ ጠባብተኛ፣ ትምክህተኛ፣  ሽብርተኛ፣  አብዮተኛ ተብሎ በወጣበት ይሰረዛል፤ ላይመለስ ይሸኛል:: ትላንት አንተ የላከዉ ገንዘብ የህዉሃት ወዳጆችና አጋፋሪዎች ደረታቸዉን በእብሪት አሳብጦ እንደ ጎልያድ የገዘፉ እንዲመስላቸዉ አድርጉአቸዋል፤ የህዝብ ሮሮ፣ የህዝብ ዋይታ፣ የህዝብ ጩሀት፣ የህዝብ ብሶትን የሚሰሙበት ጆሮ የሚያሰላስሉበት አይምሮ ተደፍኗል፤ ይልቁንስ ከህዝብ ይልቅ በሲንጋፖር፣ በቻይና፣ በታይላንድ እንዲሁም በአሜሪካና በተለያዩ የአዉሮፓ ሃገራት የሚገኙ አለማቀፍ ባንኮች ዉስጥ በድብቅ ያከማቹት የህዝብ ሀብት ያሳስባቸዋል፣ ያስጨንቃቸዋል:: እዉነታዉ ይህ ነዉ እነሱ ሐገራቸዉን በማይተረቃ የነዋይ ፍቅር አሳልፈዉ ሰተዋል! ለነሱ ሕዝብ ማለት የሀገር ሀብት ሳይሆን ለገቢ ምንጭነት የሚያገለግል ግኡዝ አካል የፋብሪካ ጥሬ ዕቃነት የበለጠ ዋጋ እንደሌለዉ ለማሳየት እሩቅ መሄድ ስያስፈልገን ያለፉትን አስራ አንድ ወራት መለስ ብሎ ኦሮሚያን፣ አማራን እንዲሁም ደቡብን ማሰብ በቂ ነዉ! ሃይ ባይም ያሻዋል:: ዛሬ በሀገር ዉስጥ ስላለዉ ትግልና ምላሹ እንዲሁም በላያችን ላይ ስለተደነገገዉ የአስቸቁአይ የግዜ አዋጅ በማተት ጊዜአችሁን አላጠፋም:: ግና ለወንበዴዉ ጉጀሌ አንዱ የአቅም ምንጭ ሰልሆንነዉ በስደት የምንኖር አገር አልባ ባላገሮች ወይም መንግስት አቆላምጦ የሚጠራን ዳያስፖራዎች በጋራ በመሆን ሕዉሃት መራሹ መንግስት ነኝ ባዩ ላይ የዉጪ ምንዝሬ ምንጭ ላይ ከፍ ያለ ጫና በመፍጠር ለዉጥ ማምጣት ስለሚቻልበት እዉነታ ጥቂት ማለትወደድኩ

ተጨማሪ ያንብቡ:  የወያኔን ባለስልጣናት ለምን የዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት መቅረብ እንዳልቻሉና ለምን ማቅረብ እንዳልተቻለ ያሬድ ኃ/ማርያም አስረዱ| ሊያደምጡት የሚገባ

በዉጪ ያለዉ የሀገሬ ሰዉ ሊገነዘበዉ የሚገባዉ ነገር ቢኖር ኪሱን አራቁቶ የሚልካት ገንዘብ የዳዊት ጠጠር መሆኗን የመረዳት ጉዳይ ነዉ::

ታድያ ምን ይደረግ? የሚለዉ አንገብጋቢ ጥያቄ ይመስለኛል. . . .

የመተባበሩ ጉዳይ ካለ ሁሉም ጋር መልሱ ያለ ይመስለኛል፤ “የሃገርህን ሰርዶ በሀገር በሬ” እንዲሉ አበዉ እራሱን እንደጎልያድ በትቢት የካበዉ ህዉሃት መራሹ አንባገነኑ መንግስት የቆመበት አንደኛዉ የገንዘብ ምሰሶ መሰረት መሆናችንን ለማሳየት ወደ ሀገር ቤት የምንልከዉን የዉጭ ምንዛሬ መሐለቅ በማቀብ በእብሪትና በማናለብኝነት መሰረታዊና እንደሰዉ የመታየት ብሎም ተፈጥሮአዊ መብቶቻቸዉ እንዲጠበቁላቸዉ የጠየቁ ወገኖችችን ላይ ያለ ሕግ አግባብ ሕፃን ሴት አዝዉንት ወጣት ሳይል  የሚወስደዉን የአፈና፣ የድብደባ፣ የእሰራትና፣ ግድያ እንዲያቆም ጫና እንፍጠር!! ብሎም በሀገራችን ዉስጥ የአንባገነን ስርዓት ያበቃ ዘንድ ከዛም የሁሉም ለሁሉም የሚሆን ዴሞክራሲያዊ ስርዓት ለመገንባት የበኩላችንን በመወጣት ከአባቶቻችን በአደራ የተቀበልናትን የደም ዉርስ በመጠበቅ ልጆቻችን የሚኮሩበት ሃገራዊ ቅርስ እናኑር::  በሀገራችንም የህዝብን ጥይቄ መሰረት ያደረገዉ የእንቢተኝነት እንቅስቃሴ ተሳታፊ በመሆን የለዉጥ ሂደቱ ላይ አሻራችንን በማኖር ከትዉልድ ተወቃሽነት እንዳን፤ ለመጭዉ ትዉልድም ከዘረኝነት የፀዳችና ልዕልናዋ የተከበረ ዲሞክራሲያዊት ሃገር በጋራ እንመስርት እላለሁ::

ሰላም ለሀገራችን!!

(መብራቱ ከስቶክሆልም)

Share