የመጨረሻው መጀመሪያ እየተቃረበ ነውን? (ጌታቸው ማ. & ሳጅን ዮሮሱን)

የአሜሪካን ኢንተርፕራይዝ ኢንስቲትዩት ዘገባ እና የአሜሪካ መንግስት የጉዞ ክልከላ ምን ይነግረናል
አገራችን ኢትዮጵያ ከአምባገነኑ የደርግ መንግስት ተላቃ በዘረኛው የህወሓት ቡድን በአሜሪካ መልካም ፈቃድ ተይዛ ከ25 ዓመታት በላይ እስካሁን የዘለቀ የጭቆና ቀንበር ውስጥ ትገኛለች፡፡ በ1983 የሽግግር መንግስት በሚመሰረትበት ስዓት ሁላችን እንደምናወቀው አሜሪካዊው አቶ ሀርማን ኮህን ኦነግን፣ ደርግን፣ እንደነፕሮፌሰር መስፍን ያሉ ገለለትተኛ ግለሰቦችን እና ሌሎች አካላትን በአገለለ አኳኋን ሙሉ ስልጣኑን ለህወሓት እና ሻዕብያ አስረክበዋል፡፡ በጉዳዩ ለመሳተፍ ያገባኛል ብሎ ለንደን የከተመው ሌላው አካል ሁሉ ለምን ተሳታፊ እንዳልነበረ እስካሁንም ድረስ አጥጋቢ ምላሽ አላገኘም፡፡ ከጫካ ጀምሮ በተለያዩ መንገዶች በአሜሪካ ሲረዳ የነበረው ቡድን ስልጣን መያዙ ያሳደጉት ልጅ ለቁም ነገር እንደመብቃት የሚቆጠር ሲሆን በተቃራኒው አሜሪካን በኢምፔሪያሊዝም እና ካፒታሊዝም እየከሰሰ የነበረው አምባገነኑ መንግስቱ በወቅቱ እየወደቀች ከነበረችው ታላቋ ሶቬየት ጋር አብሮ ተንኮታኩቷል፡፡ ይህ የደርግ መውደቅ ለአሜሪካ ከቀዝቃዛው ጦርነት ድል እንደምርቃት የሚቆጠር ነው፡፡ ዘረኛው እና ጠባቡ ህወሓት ስልጣን ከያዘ በኋላ አንግቦ የተነሳውን ስውር አጀንዳ ለማስፈፀም ለአሜሪካ አንደ የቤት ድመት ሲጠሩት አቤት ሲልኩት ወዴት ማለት ግዴታ ነበረበት፡፡ በዚህም ህዝቡ ሳያውቅ እና ሳይፈቅድ ለአሜሪካ የጦር ሰፈር አርባምንጭ ላይ መስጠት፣ ኢትዮጵያ ሶማሊያ ውስጥ ጦሯን በሰላም አስከባሪ ስም ማስገባት፣ በአካባቢው ሁነኛ የቀኝ እጅ መሆን፣ እና ሌሎችም ናቸው፡፡
ሆኖም በጊዜ ብዛት፡-
በህወሓት መንግስት መጥገብ መጀመር እና ወደ እነቻይና ማዘንበል ወይም
የአሜሪካ ፍላጎት በኢትዮጵያ ላይ ማሽቆልቆል ወይም
በሁለቱም ምክንያቶች አሜሪካ የነበራትን ግንኙነት ቸል ያለችው ይመስላል፡፡
ለዚህም እንደማሳያ በኢትዮጵያ የነበራትን የጦር ሰፈሯን ለቀቀች፡፡ ኢትዮጵያም ጦሯን ቀስ በቀስ በለሁሳስ ከሶማሊያ በማስወጣት ላይ ትገኛለች፡፡ ሲቀጥል ቻይና እና ሳውዲ አረቢያ በጅቡቲ ትላልቅ የጦር ሰፈሮችን ለመገንባት ተፍ ተፍ ሲሉ አሜሪካ ዝም ብላ እየተመለከትች ትገኛለች፡፡ ይህ ሁሉ ሲሆን የአሜሪካ ትክክለኛ ፍላጎት ምንድነው የሚለውን ለተንታኞች እንተወው፡፡ ሆኖም ግን በአሜሪካ ኢንተርፕራይዝ ኢንስቲትዩት እና በአሜሪካ መንግስት በተመሳሳይ ጊዜ አንድምታ ለበስ ሪፖርቶች ወጥተዋል፡፡ የአሜሪካን ኢንተርፕራይዝ ኢንስቲትዩት ዝም ብሎ እንደማንኛውም ኢንስቲትዩት አይደለም፡፡ በአሜሪካ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ፣ ፖለቲካዊ እና በተለይም የጦር እና የውጭ ፖሊሲ ላይ በከፍተኛ ሁኔታ ተፅዕኖ የሚያሳድር ወግ አጥባቂ የምርምር እና ተሟጋች ድርጅት ነው፡፡ የኢንስቲትዩቱ ታላላቅ ሰዎች በተለይ ከጆርጅ ቡሽ መንግስት ጀምሮ ባለው መንግስት እጃቸው ረጅም የሆነ ጉምቱ ባለስልጣናት ይገኙበታል፡፡ ኢንስቲትዩቱ ከኒው አሜሪካን ሴንቸሪ እስከ የውጭ ፖሊሲ ጠበቃ እና የአይሁዶች ብሔራዊ ደህንነት ጉዳዮች ድርጅት ድረስ ግንኙነት ያለው ሲሆን የቡሽ እና ኦባማ መንግስት በኢራቅ እና ሶሪያ ላይ እንዲዘምቱ ካስደረጉት ተቋሞች አንዱ ነው፡፡ የተቋሙ ሰዎች ጦር ጠሪ እና ጭር ሲል የሚጨንቃቸው በእነሱ አጠራር ኒዎኮኖች ናቸው፡፡ አሁንም አሜሪካ ሩሲያ ላይ ጦርነት እንድትከፍት አበክረው እየወተወቱ ይገኛሉ፡፡
ስለዚህ ይህ ተቋም ነው ኢትዮጵያ ለመፍረስ ከተቃረቡ ሀገሮች ተርታ ግምባር ቀደም ነች ብሎ የዘገበው፡፡ ይህ ተቋም የያዘው መረጃ፣ ነገሮችን ማስደረግ የሚችልበት አቅሙ እና ሌሎች ተያያዥ ጉዳዮች እንዲሁ በቀላሉ ሊታለፉ አይገባም፡፡ ይህ በእንዲህ እንዳለ ስንት ውጥረት እና አሰቃቂ አደጋዎችን ከአለፍን በኋላ እና የነፃነት ትግሉ ወደፊት እየገፋ በአለበት ስዓት አሜሪካ ለዜጎቿ የጉዞ ክልከላ በተመሳሳይ ቀን አውጥታለች፡፡ ይህ ሁሉ መግለጫ ለምን ሊመጣ ቻለ? የታየንን መላምት እንዲህ አቅርበነዋል፡-
የአስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ምንም ሊሰራ ባለመቻሉ እና ህዝቡ አሁንም ተቃውሞውን በተለያየ መንገድ እየገለፀ ባለበት በአሁኑ ወቅት ህወሓት የመጨረሻውን ካርድ በመሳብ በሚቃወሙት ህዝብ ላይ የአየር ድብደባን እና ሌሎች መንገዶችን በመጠቀም ጭፍጨፋ ሊያካሂድ ይችላል፡፡ ይህን ተከትሎ ከፍተኛ እልቂት እና አለመረጋጋት ሊከተል ይችላል፡፡
ህወሓት እየተዳከመ ስለመጣ እና ህዝቡ ድንገት ፈንቅሎ ከመጣ ሊጥለው እደሚችል እና እና መንግስቱን ሊረከብ የተዘጋጀ ቡድን ባለመኖሩ ሀገሪቱ ወደ አልተፈለገ አለመረጋጋት ውስጥ ልትገባ ትችላለች በማለት
በኢትዮጵያ ላይ የተለየ ጥቅም ፈላጊ ሀገሮች ለምሳሌ እንደ ሳውዲ አረቢያ ዓይነት ሀገሮች የራሳቸውን አሻራ ለማስቀመጥ እያሴሩ ስለሚሆኑ
በመጨረሻ ራሷ አሜሪካ እንደለመደችው ነቅላ ልትጥለው እና ሌሎች ሀይሎችን ለራሷ እንዲጠቅሙ አድርጋ ለማሰባሰብ የምትሞክር መሆኗ እና ድንገት እንደ መጀመሪያው ግብፅ አብዮት ይህ ካልተሳካ አለመረጋጋት ሊፈጠር ስለሚችል፡፡ የሚሉት ናቸው፡፡
በእርግጥ በጉዳዩ ላይ እውቀት ያላቸው ሰዎች ሙያዊ ትንታኔያቸውን ቢያጋሩን የሁለቱ ዘገባዎች መውጣት ለኢትዮጵያ አንድምታው ምንድነው የሚለውን ስለሚያሳየን ቀሪውን ለባለሙያ ትተነዋል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የአንድ አገርና ህዝብ ዕድል ሊወሰን የሚችለው ከ2-5% በሚሆነውየህብረተሰብ ክፍል ብቻ
Share