ኢትዮጵያ በጠቢቡ ሰለሞን ሸንጎ! (ታሪኩ አባዳማ)

ልተወለደ አንጀትህ ሲሉ ማንነትህን እጥር ምጥን ባለ ቋንቋ መግለፃቸው ነው። በሌላ ሰው ቁስል ጨው መነስነስ የማይቀፍህ ጨካኝ አረመኔ ነህ ማለታቸው ነው። ተቆርቋሪነት የጎደለህ ፣ ፍላጎትህን ለማርካት ብለህ ከምንም አይነት ጥፋት የማትመለስ መንፈሰ ደካማ ነህ ማለት ነው። በስግብግብነት የሌላውን ትቀማለህ ፤ ያንተ ያልሆነውን ትመኛለህ ፤ የኔ ነው ብለህ ትደርቃለህ ፣ ታፈጣለህ ለኔ ካልሆነ ሁሉም ነገር ባፍጢሙ ይደፋ ብለህ ነገር ታበላሻለህ። ሌላው ጥሮ ግሮ ያፈራውን ሀብት ፣ ያቆየውን ቅርስና ባህል ፣ ያስከበረውን ታሪክ ታረክሳለህ… ጉልበትህን መከታ አድርገህ በድርቅና ያልሆንከውን ሁሉ ‘ሆንኩ’ ብለህ ትቀጥፋለህ… ባልተወለደ አንጀት።
ባልተፃፈ ህግ ያሻህን ትፈፅማለህ ፣ ተጠያቂነት የሚሉትን ቋንቋ ትጠየፋለህ… አይን ላወጣ ዘረፋ ፣ አደባባይ የወጣን እውነት ለመካድ የማያመነታ ህሊና ተክነሀል።
ባልተወለደ አንጀት በሚያሰኝ መልክ በተራ ወሮበላ ወኔ አገርን መበደል ፣ የአገርን ሀብት መመዝበር እና ማስመዝበር ፣ ታሪክ ማበላሸት እና ማዛባት የህዝብን መሰረታዊ ጥቅም የሚፃረር አድራጎት መፈፀም ብሎም ህዝብን ወደ ጥፋት መውሰድ ባልተወለደ አንጀት የሚሉት አባዜ ነው… ይህን አይነቱን አባዜ ከህግ እና ከፍትህ ጎራዴ ሌላ የሚዳኘው መላ የለም።
ኢትዮጵያ ወያኔ በቀየሰው የጎጥ ክፍፍል መርህ እየተቸበቸበች ፣ እየተሸነሸነች ፣ እየተመዘበረች ናት… የ80 ቋንቋ ተናጋሪ ህዝቦች አገር መሆኗ ሲታሰብ አካሄዱ እየተሰነጣጠረች የሚያሰኝ አይነት ነው። አንድ ሁለት ብሎ ነገሩን በዝርዝር ሲያሰሉት ጉልበት ያርዳል። እየዋለ እያደረ ዛሬ ዘረፋው እና ቅሚያው ከመንዛዛቱ የተነሳ ዘራፊው እና ‘መዝጊያ ገልባጩ’ መንግስት ስለ ራሱ ምግባረ ብልሹነት እየወተወተ ይገኛል። በኪራይ ሰብሳቢዎች ማጥ የተዋጥኩ ቀማኛ መንግስት ነኝ “… ምናባቴ ላድርግ (ምናባታችሁ ታመጣላችሁ)” የሚሉ መሪዎች የሚያላግጡባት አገር ሆናለች። የሌባ አይነ ደረቅ መልሶ ልብ ያደርቅ ይለዋል ወገኔ…።
ባልተወለደ አንጀት አገር ያደማ ፣ አገር ያጠፋ ፣ ህዝብ የበደለ ከወንጀለኛ በምን ይለያል ፤ በወንጀለኛ ተፈጥሮው ያልተወለደ አንጀት ድርጊት የሚፈፅምስ… ወያኔን እንዴት እንግለፀው። ባልተወለደ አንጀቱ ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያውያን ላይ ወንጀል እየሰራ ወይንስ በወንጀለኛ ተፈጥሮው የተነሳ ያልተወለደ አንጀት የሚያሰኝ ወንጀል እየፈፀመ? ወይንስ በሁለቱም…
ቀልቀሎ ስልቻ ፣ ስልቻ ቀልቀሎ መሆኑ አይደለም?
መልሱን ከጠቢቡ ሰለሞን ሸንጎ የምናገኝ ይመስለኛል…
ብላቴናው የኔ ነው በሚል ሙግት የገጠሙ ሁለት ኮረዳዎች ከጠቢቡ ሰለሞን ሸንጎ የቀረቡት ከዛሬ 2500 ዓመታት በፊት ነበር። ሁለቱም ሴቶች ‘እናት እኔ ነኝ’ ሲሉ የይገባኛል ጥያቄ አቀረቡ። ሁለቱ ተሟጋቾች ባንድ ቤት ተዳብለው ይኖሩ እንደነበር የታሪኩ ጭብጥ ያረጋግጣል። አንደኛይቱ ወልዳ የሞተባትን ህፃን ለሌላዋ አስታቅፋ ፣ የሌላዋን ጤነኛ ልጅ ሰርቃ ከጉያዋ ሸጉጣ መኝታዋ ውስጥ ተጠቅልላ ተኝታለች… ሲነጋ የተፈጠረው አምባጓሮ ወደ ንጉስ ሰለሞን ሸንጎ አደረሳቸው።
ጠቢቡ ሰለሞን በጥሞና የሁለቱንም እናት ነን ባዮች አቤቱታ ካዳመጠ በሁዋላ አውጥቶ አውርዶ ብዙ አሰላሰለ፤ በመጨረሻም አንዱን ወታደር ‘ጎራዴህን ወዲህ በል’ አለው። ከሸንጎው መካከል ተነስቶ ‘ይህ ብላቴና የማናችሁ እንደሆነ ፍርድ መስጠት ቸግሮኛል ስለዚህ እኩል ለሁለት ሰንጥቄ ላካፍላችሁ’ በማለት ብይን ሰጠ።
ከፊቱ የቆሙትን ሁለቱን ወላድ ወጣት ኮረዳዎች ለመዳኘት ጠቢቡ ሰለሞን ከጎራዴ ሌላ መላ አላገኘም። ባንድ ጎጆ ጥላ ስር ዕለታዊ ኑሯቸውን ይጋሩ የነበሩ እናቶች ለዚህ ይበቃሉ ብሎ ማንም አልገመተም።
ከሁለቱ አንደኛዋ ‘እናት’ ጠቢቡ ሰለሞን የሰጠውን ብይን በደስታ እንደምትቀበል ፈጥና ገለፀች… ‘ፍትህ ዛሬ መሬት ወረደች’ ስትል ፈነጠዘች። የጠቢቡ ፍርድ ፣ ዳኝነቱ እንደተመቻት በፈገግታ አስታወቀች። ‘ህፃኑን ቆራርጡት ፣ ገነጣጥሉት ፣ በልቱት ፣ ቅርጫ አስገቡትና ድርሻዬን ስጡኝ… አሁኑኑ ገነጣጥሉት አለች።’
‘የለም ንጉስ ሆይ’ አለች ሌላዋ ሴት ተሟጋች ‘ልጄን በጎራዴ መቀራመቱ ፣ መበለቱ አይስማማኝም። ከዚህ ይልቅ ህፃኑን ለዚያች ሴት ስጧት… ልጄ ፣ የአብራኬ ክፋይ ፣ የነብሴ ቅራፊ በህይወት ይኑር ፣ አይሙትብኝ’ ስትል እናታዊ አንጀቷ ፣ እናታዊ ደመ ነብሷ ባስጨነቀው ሲቃ የጠቢቡን ፍርድ ተቃወመች። ‘ልጄ እንደ ዶሮ ብልት አይገነጣጠልም’ ስትል ድምፁዋን ከፍ አድርጋ ጮኸች… ‘የለም አትገነጣጥሉት ብላ ተማፀነች።’
ጥበብ እና አርቆ አስተዋይነትን የሚፈትን ብርቱ ጉዳይ የቀረበለት ንጉስ ሰለሞን ሁለቱም ሴቶች ያቀረቡትን ለኔ ይገባኛል ጥያቄ አመዛዝኖ አይቷል። ፍርድ ላይ ከመድረሱ በፊት ሁለቱንም እናቶች አነጋግሯል ፣ ፈትሿል ፣ ፈትኗል… ብላቴናው የማንኛዋ ሴት እንደሆነ መገንዘብ ባይሳነውም የፍርዱን ሂደት ለሚከታተለው ዜጋ የጥበቡን ዳርቻ ለማረጋገጥ ሲል ፣ ምሳሌነቱም እነሆ ምእተ ዓመታትን ተሻግሮ ዛሬ ለምንገኘው የሰው ዘሮች ትምህርት እንዲሆን አደባባይ ላይ ጎራዴውን ሰብቆ እውነት እና ፍትህ ምንኛ ተወራራሽ መሆናቸውን አረጋግጧል… ። የፍትህ መሰረቷ እውነት እንጂ ጉልበት ወይንም ጮሌነት አለመሆኑን አሳይቷል።
ንጉስ ሰለሞን የዚያ ብላቴና መፃኢ ዕድል ከወላጅ እናቱ ህይወት ጋር የተቆራኘ መሆኑንም አስተውሏል… ለህፃኑ ዘላቂ ህይወት የሚበጀው ምን እንደሆነ በፍትሀዊ ብያኔው አረጋገጧል… ።
የዚህ ታሪካዊ ፍርድ እንደምታ ዛሬ ኢትዮጵያ ለተዘፈቀችበት የህልውና አደጋ ጥልቅ ትርጓሜ አለው። ሰለሞን ዙፋን ላይ በቆየባቸው ዘመናት ብዙ ብልህነት እና ጥበብን የተላበሱ ታላላቅ ቁምነገሮችን አከናውኗል – ይህን የሁለት ሴቶች ሙግት አስመልክቶ የሰጠው ብይን ጎላ ብሎ እንዲፃፍ የተፈለገበት ምክንያት ግን በቀላሉ የሚታይ አይደለም። በቅዱስ መፅሀፍ እና በቅዱስ ቁርአን ሳይቀር ይህ ታሪክ ሰፍሯል።
በሙግቱ እና በብይን አሰጣጡ ሂደት ውስጥ የሰው ልጅ መሰረታዊ ባህሪ ውስብስበነት ተንፀባርቋል። ሰብአዊ መስሎ ጭካኔ ፣ ህጋዊ ተፋራጅ መስሎ በደለኛ ፣ አዛኝ መስሎ አረመኔነት ተመዝግበዋል። ንጉሱም ቢሆን ጎራዴ ያነሳው ያንን ህፃን ለመሸርከት ጨክኖ እንዳልሆነ ይልቁንም የማንስ ማንነት ፈተና ሲገጥመው ነጥሮ መውጣቱ አይቀሬ መሆኑን በማመዛዘን ነው።
ስለ ኢትዮጵያ አያሌ ነገሮች ተፅፈዋል ፣ ዛሬም እየተፃፉ ናቸው። የቆየ ታሪኳን ፣ የሰው ዘር መገኛ መሆኗን ፣ በስልጣኔ ቀደምት ታሪክ ካላቸው አገሮች ተርታ የመቆሟን ፣ የጥቁር ህዝብ ክብር መግለጫ የሆኑ ገድሎች የተከናወኑባት ምድር መሆኗን… እንዲሁም በድህነት አረንቋ ተዘፍቃ የቆየች እናም በረሀብ አለንጋ የተጠበሰች እናም እርስ በርስ ጦርነት ስትደማ ብዙ እንግልት የተፈራረቀባት መሆኗን የሚያትቱ ሰነዶች የተከማቹባት ናት።
ኢትዮጵያ ሚሊየኖች በማህፀኗ ተፀንሰው ሰው ለመሆን የበቁባት፤ የሞሏት ልጆቿ የብዙ ቋንቋ ተናጋሪ ፣ ዘርፈ ብዙ ባህል ባለፀጋ ሆነው ሳለ ግን አሁንም በተፃፈውም ባልተፃፈውም ረጅም ታሪኳ ውስጥ ብዙ ውጣ ውረድ አልፈው እና ዘልቀው እስከ ዘመናዊው የመንግስት አስተዳደር የደረሰችበትን ማንነት ያጎናፀፏት መሆናቸውን እንገነዘባለን። ይህ ብቻ አይደለም…
ኢትዮጵያ በልጆቿ የርስ በርስ ግጭት የተነሳ በጎ የማይባል አያሌ ክፉ ዘመናትን አሳልፋለች ፤ በጎበዝ አለቆች ፉክክር ፣ በንጉሶች ገብር አትገብር ዘመቻ ፣ በተፈጥሮ ሀብት ሽሚያ እና ከቅርብ ዘመናት ወዲህ ደግሞ በፖለቲካ ስልጣን ይገባኛል ባይ ተቀናቃኝ ዜጎቿ መካከል ቀላል የማይባል ቂም ሲያከማች የቆየ ፍጭት ውስጥ ትገኛለች።
የፍጭቱ ባህሪ መልኩን ቀይሮ ህልውናዋን ጭምር አደጋ ላይ የጣለ ፍጥጫ ላይ ደርሳለች።
ኢትዮጵያ መብት የተረገጠባት ምድር በመሆኗ ዜጎች እንደ ማንኛውም አገር ለመብት መረጋገጥ ፣ ለህግ የበላይነት ጥያቄ መሰለፋቸው ተገቢም አስፈላጊም ነው። በማናቸውም ረገድ ህዝብ የሚያነሳው የመብት ጥያቄ የአገርን ህልውና እስካልተፃረረ ድረስ አላንዳች ገደብ መልስ ሊያገኝ ይገበዋል። ትናንትም ሆነ ዛሬ ህዝብ ለሚያቀርበው የመሰረታዊ መብት ጥያቄ ገዢዎች ቀና ወይንም ቀልጣፋ መልስ ሲሰጡ አላየንም። ዛሬ ገዢው ሀይል ህዝባዊ መሰረት የቆነጠጠ ሳይሆን ውሱን የሆኑ ስግብግብ ሀይሎች የሚያሽከረክሩት በጉልበት እና ስለላ መረብ የሚተማመን ሀይል ነው። ማናቸውንም ህዝባዊ ሰላማዊ ጥያቄ በመጨፍለቅ አገዛዙን መቀጠል ይፈልጋል። ይህ ሚስጢር አይደለም – ይህን አፈና ለመቋቋም እና ለማስወገድ ብሎም በህግ የበላይነት የሁሉም ዜጎች ጥያቄ መልስ እንዲያገኝ ብሎም ኢትዮጵያ ፀንታ እንድትቆም ለማረጋገጥ ያለሰለሰ ሙግት ማካሄድ አስፈላጊ ነው።
ወያኔ ገና ከምስረታው በሰነድ ላይ አስፍሮ የዘመተው ትግራይ ተገንጥላ የራሷን መንግስት እንድታቆም ነው። አላማው በማያሻማ ቋንቋ ተቀምጧል… በቅድሚያ ‘ትግራይ ከዚያ ኢትዮጵያዊ ነኝ’ ብሎ አደባባይ የደሰኮረው የግንጠላው መሀንዲስ መሪያቸው ያረጋገጠውን ልብ ይሏል። አንቀፅ 39 የተፃፈው ከዛሬ አርባ ዓመታት በፊት ነበር። ይህ የወያኔ አላማ ለፌዝ እና ለወጉ ያህል የተጨመረ አንቀፅ ሳይሆን ኢትዮጵያ የተሰኘች አገር ህልውነዋ እንዲያከትም ይሁነኝ ተብሎ የተስማሙበት ነው። ይህን አላማ ዳር ለማድረስ ዛሬ ድረስ ተግተው እየሰሩ ለመሆኑ ከበቂ በላይ ማስረጃዎች ሲቀርቡ ቆይቷል። ባልተወለደ አንጀት ኢትዮጵያ እና ኢትዮጵያውያን ላይ ሲፈፅሙ የቆዩትን የዘረፋ ፣ ግድያ ፣ በዘር መከፋፈል ብሎም ዳርድንበርን ለባእድ መቸብቸብ ድርጊቶች ማጣቀስ በቂ ይመስለኛል።
ወያኔ ባልተወለደ አንጀቱ 3ሚሊየን ሄክታር መሬት ለቱርክ ፣ ለህንድ ፣ ለሳውዲ እንዲሁም ሌሎች ባእዳን ከ30 እስከ 50 አመት ለሚደርስ ዘመን ፈርሞ አስረክቧል። ጎረቤት አገር ጂቡቲ ጠቅላላ ስፋቷ 2.3 ሚሊየን ሄክታር ነው። እንግዲህ 3ሚሊየን ሄክታር ሰነድ የሚያውቀው ለም መሬት ለባእዳን ሲሰጥ በዚህ መሬት ላይ ከትውልድ እስከ ትውልድ የኖሩ ኢትዮጵያውያን የት ደረሱ? እጃቸው ፊጥኝ እየተቀፈደደ እንደ ከብት ሲጋዙ የቆዩትን ወገኖቻችንን ወያኔ የት አደረሳቸው? ከአፅመ ርስታችን አትነቅሉንም ብለው ያንገራገሩ ኢትዮጵያውያንስ ከምን ደረሱ? ጋምቤላ በየቄያቸው የታረዱትን ገበሬዎች ደም ማን ይፋረድ? ባልተወለደ አንጀት…
ሰለማዊ የመብት ጥያቄ አንስተው የተሰለፉ ዜጎች ላይ ጅምላ ጭፍጨፋ ሲፈፅም መኖሩ ሌላው የወያኔ ማንነቱ ማረጋገጫ ነው። ድምፄን አልቀማም ብሎ አደባባይ የወጣን ሰልፈኛ በምርጫ 97 ወቅት ጨፍጭፏል። በህዝቡ ላይ የቋጠረውን ቂም ለመበቀል ሲል ባወጣው ስልት አዲስ አበባውያን ከተወለዱበት ፣ ካረጁበት ፣ እድር እና ደጀ ሰላም ከመሰረቱበት ሰፈራቸው በግድ ተፈናቅለው ገሚሱ ወደማያውቀው አንዳችም ማህበራዊ አገልግሎት ወደሌለበት ዱር እና ገደል ሌላውም ቤት አልባ የጎዳና ተዳዳሪ እንዲሆን አድርገውታል… ባልተወለደ አንጀት።
ዛሬ ድረስ አላባራ ያለው ጭፈጨፋ አፈሙዙን ወደ ኦሮሞ ህዝብ አዙሯል – መሰረታዊ ሰብኣዊ መብታችን ይከበር ፣ መሬታችንን አትቀሙን ብለው የተነሱ ዜጎች አደባባይ ተገድለዋል ፣ ከየመንደሩ እየተለቀሙ በየጉድባው ተገድለው በመጣል ላይ ናቸው። ኦሮሞ የሚኖርባት እያንዳንዷ ትናንሽ መንደር ሳትቀር የጦር ቀጠና ሆናለች… ወያኔ በመደበኛ ጦር ጥቃት እፈፀመ ነው… እናቶች ፣ አዛውንት እና ህፃናት እተጨፈጨፉ ናቸው… ባልተወለደ አንጀት።
በሰሜን ሱዳን በኩል ተቆርሶ ለባዕድ የተሰጠው መሬት ኢትዮጵያን ለማጥፋት ከታቀደው አላማ ውስጥ የሚካተት ሌላው ‘ባልተወለደ አንጀት’ የሚሰኝ ወንጀል ነው። በድንበሩ አካባቢ ኑሯቸውን ሲከውኑ የቆዩ ዜጎች እንደ ወንጀለኛ እየታደኑ ገሚሱ ተግደለዋል ቀሪዎቹ ዱር ወጥተዋል – አገራችን በታሪኳ ብዙ ክፉ እና ደግ ነገር ቢፈራረቅባትም አንዲህ አይነት ክህደት የሚፈፅም መንግስት ግን ከቶ ገጥሟት አያውቅም።
የአገሪቱ ጥሬ ሀብት ፣ ወርቅ እና ማዕድናት በነኝሁ አልጠግብ ባይ ሀይሎች አለገደብ እየተጋዘ ነው። በቅርቡ አንድ ባለሙያ እዚያው ወያኔ ፓርላማ ላይ ቀርበው ሲናገሩ ‘አገሪቱ አለርህራሄ እየተመዘበረች ነው ፣ ራቁቷን እንድትቀር እተደረገች ነው’ ብለዋል። በሌላ ቋንቋ ባልተወለደ አንጀት የሚካሄደው ዘረፋ እንኳን ለውጪው ታዛቢ ከውስጥ ሆነው ለሚያገለግሉ አንዳንድ ቅን ዜጎች ሳይቀር የሚዘገንን ነው።
እናም ለኔ ካልሆነች ድርሻዬን ቆርሼ እገነጠላለሁ የሚሉ ወገኖች ሌት እና ቀን ተዋድቀው ኢትዮጵያን ከጉያቸው አስገብተዋል። ኢትዮጵያ ላለፉት ሀያ አምስት አመታት በነሱ እቅፍ ውስጥ ናት። በውድቅት ሌሊት ሰርቃ እቅፏ ያደረገችውን ህፃን የሷ ነው ብላችሁ ካልሰጣችሁኝ በጎራዴ ቀልታችሁ ድርሻዬን ስጡኝ እንዳለችው ሴት መሆኑ ነው። እሷም ወላድ ናት ፣ እሷም ሴት ናት ግና ባልወለደ አንጀቷ የዚያን ብላቴና ቁራጭ ታቅፋ ቤቷ ለመመለስ ለምን ፈቀደች? የሚለው ጉዳይ ብዙ ያስተምራል። ኢትዮጵያ ከሰለሞን ሸንጎ ፊት ቆማ ፍትህ ትጠይቃለች።
እዚህ ላይ ‘አለበለዚያ ድርሻዬን ቆርሼ እገነጠላለሁ’ በሚሉት እቅፍ ውስጥ 25 ዓመታት የቆየችው ኢትዮጵያ ምን እየተፈፀመባት መሆኑን መቃኘቱ ጠቃሚ ነው። እነኝህ ወገኖች አትዮጵያን እና ህዝቦቿን በምን መልኩ እያሳደሩ ነው ለሚለው ጥያቄ መልስ መስጠት ተገቢ የሚሆነው ድርጊታቸው ማንነታቸውን ይበልጥ አጉልቶ የሚያሳይ በመሆኑ ጭምር ነው። ሲፈፅሙ የቆዩት ባልተወለደ አንጀት ወይንስ እንደ እናት ተቆርቋሪ በሆነ ልባዊ ፍቅር?
ያልወለደችውን ህፃን እናት ነኝ ብላ የሞገተችው ሴት እውነትም ሀሳቧ ሰምሮ ልጁን በህይወት እንድትረከብ ቢፈርድላት ኑሮ የዚያ ብላቴና ዕጣ ፈንታ ምን ይሆን ነበር? እናታዊ ፍቅር እየተመገበ ያድግ ነበር? ንጉስ ሰለሞንን ያስጨነቀው ጥያቄ ይኼ ነበር? እኛም ዛሬ የሚያስጨንቀን ይኼ ነው… ባልተወለደ አንጀት።
እናም ‘ኢትዮጵያ መገንጣጠል የለባትም – የዜጎች መብት በህግ የበላይነት ይረጋገጥ ማለት ከቶውንም ብሔራዊ ማንነትን እስከመካድ ድረስ ርቆ መሄድ አይገባውም’ በሚሉ ወገኖች ላይ የግንጠላ አቀንቃኞቹ ክስ ያቀርባሉ። ‘አሀዳዊ መንግስት ይመለስ ብለዋል ፣ ያፈጀውን የቀድሞ ስርዓት ለመመለስ የቆሙ ናቸው’ ሲሉ ይከሳሉ። ‘ዛሬ በጎጥ ዳር ድንበር ያሰመርነውን ‘ክልል’ ሊያፈርሱ ነው…’ ይላሉ።
ብትገነጣጠል አይከፋንም የሚሉት ወገኖች ያንን ‘መሬት ላራሹ’ ሲል በአንድነት ቆሞ የታገለን ትውልድ ፣ ያንን በ‘ነፃነት ለዘላለም ኑሪ’ ያለ ትውልድ ፣ ያንን ‘የብሔር ብሔረሰቦች መብት ይከበር’ ፣ ‘ህዝባዊ መንግስት ይቋቋም’ ‘የሀይማኖት እና የፆታ እኩልነት ፣ ሰብአዊ መብቶች ይረጋገጡ’ ፣ ያንን ከራሱ ምቾት እና ድሎት ይልቅ የህዝብ እና የአገር ጥቅም ይቅደም ብሎ የተሟገተ ትውልድ ይከሳሉ።
ከሳሽ እና ተከሳሽ ከሰለሞን ሸንጎ ቀርበዋል።
ሰለሞናዊ ፍትህ የሚያሻው ሙግት ላይ ደርሰናል። የተሟጋቾቹ ፍሬ ሀሳብ ፣ ያቀረቡት ጭብጥ በማያሻማ ቋንቋ ተብራርቶ ለችሎት ተሰምቷል። አብረቅራቂው ጎራዴ ስለቱን ቀስሮ ለመወንጨፍ ፣ ለመከታተፍ ተዘጋጅቷል። ንጉስ ሰለሞን ብይን ሊሰጥ ግራ ቀኙን እያማተረ ነው…
… ንጉስ ሆይ ኢትዮጵያ የማን ናት?

ተጨማሪ ያንብቡ:  ሁሉም ነገር ወደ አፋር ግንባር!!! ኢትዮጵያን ከመፈራረስ ለመታደግ ህወሓትን መደምሰስ ያስፈልጋል - አክሎግ ቢራራ (ዶር)
Share