በዕውቀቱ የተቀመጠበት ሸፋፋ ሚዛን (ዳዊት ግርማ)

በዕውቀቱ ስዩም ሰሞኑን “ከአሜን ባሻገር” የሚል ርዕስ ያለው መጽሐፍ አውጥቷል፡፡ ከ“መግባትና መውጣት” በኋላ ብዙ ጊዜ መታገሱን ልብ ይሏል፡፡ በመካከል ባለው ረጅም ክፍት ጊዜ በሕትመትና ማሕበራዊ መገናኛ ብዙሃንና በሚያወጣቸው መጣጥፎች ነበር የታደምነው፡፡ በውቀቱን የምናውቀው በቁምነገር አዘል ሸንቋጭ ጽሑፎቹና በሳል ቅኔዎቹ ነው፡፡ ስለልጁ የጽሑፍ ባለጸጋነት መተንተን ጊዜን ባጉል ማጥፋት ነው የሚሆነው፡፡ የተሰጥኦው ነገር “ሀ”ና“ለ” የለውም፡፡ ማንም የሚምልለት ነው በተለይ ግጥሞቹ፤ ነገሮችን የሚያይበትና የሚያቀርብበት መንገድ፡፡ የሰሞኑ “ከአሜን ባሻገር” መጽሐፉ ከወትሮዎቹ በተለዬ ቁም ነገር ይበዛበታል፡፡ የአቀራረብ ሁኔታው ከፍታ ላይ ነው አሁንም፡፡ በተለይ የዳሰሳቸው ታሪካዊና ፖለቲካዊ ጉዳዮች “ፕሮፌሰር” ያክል የማዕረግ ማማ ላይ ተቀምጠው፣ የዕውቀት ጥግ ላይ አለን ብለው የሚኮፈሱ የአገራችን ልሂቃን “በልጄን ላሳድግበት” ልማድ ያልደፈሩትንና ያልዳሰሱትን ጉዳዮች “ይበል” በሚያሰኝ የአቀራረብ፣ የንባብ፣ የመረጃና የምክንያታዊነት ርቀ’ት ሲተነትን እናገኘዋለን፡፡ መጽሐፉ በጥቅሉ ግሩም ቢሆንም ቅሉ አንዳንድ ስንኩል እይታዎችን ታዝቤበታለሁ፡፡ እነሱን መዳሰስ የዚህ ጽሑፍ ዓላማ ነው፡፡
ዘመናዊነትን ፈጥኖና በቀላሉ መቀበል፣ ዘመናዊነት በሃገር እንዳይሰርፅ ማነቆ የሆኑትን መንቀፍ መልካምነት አለው፡፡ ይህን ሁኔታ ሲነቅፍ በተደጋጋሚ እናስተውላለን፡፡ መንቀፉ ባልከፋ፤ የበውቀቱ ነቀፋ መነሻውና መድረሻው እዛው ድሮና የድሮው ማኅበረሰብ ላይ መሆኑን ነው የማያስማማኝ፡፡ በራሱ አገላለፅ“በዘመኑ መንፈስ” ንፅፅሩ ቢሰራ መልካምነቱ ይጎላል ባይ ነኝ፡፡ ያለፈው ማኅበረሰብ ላይ የሚሰነዘር ታሪክ ቀመስ ትችት ግቡ ያሁኑን ማኅበረሰብ ለማደስ እንጂ ያለፈውን የቀድሞውን ነቅፎ በዚያው ለመርካት መሆን የለበትም፡፡
ስለ አፄ ቴዎድሮስ የዘመናዊነት ምኞት፣ የቴክኖሎጂና ዘመናዊነት ትውውቅ፣ አንድነት፣ ለዚያም ስለከፈለው መስዋዕትነት ከቧልት በዘለለ አንዳች ቁምነገር ለማለት ያልደፈረ፤ ስለቴዎድሮስ “እጅ ቆረጣ” ዲስኩር ለማውራት ግን ብዕሩ ይሰላል፡፡ የአሁኑን ስርዓት አምባገነንነት ለመግለጽ የስርዓቱ አምባገነንነት በራሱ በቂ ነው፤ የግድ ወደአጼዎቹ ዘመን ወደኋላ መንደርደር ያለበት አይመስለኝም፡፡ በቴዎድሮስ ዘመን’ኮ አብዛኛው የዓለም መንግሥት በፈላጭ ቆራጭ የፊውዳል ስርዓት ስር ነበር፡፡ የኛዎቹን ነገሥታትነጥሎ መወረፍ አይጠበቅበትም፡፡
ስለ ልዑል አለማየሁ ቴዎድሮስ ሐውልት የመጎብኘት ነገር ሲያወሳ “ባጋጣሚ ከንጉስ ከመወለዱ ውጭ” ምን ሠራ? ብሎ ይጠይቃል፡፡ ልዑል ማለት በደምሳሳው የንጉሥ ልጅ ነው፡፡ የየትኛውም ሃገር ንጉሥ ልጅ ዝናው ናኝቶ ነው የምናውቀው፡፡ የሚናኘውም ምንም ስላደረገ ሳይሆን የንጉሥ ልጅ ስለሆነ ብቻ ነው፡፡ የኦስትርያው ንጉሥ ልጅ መቃብር የሚጎበኘው ለምንድነው? ባጋጣሚ የንጉሥ ልጅ ከመሆኑ ውጭ የሰራው ነገር የለም፡፡ በርግጥ ለሁለተኛ የዓለም ጦርነት መጀመር የልዑሉ መገደል ፊሽካ ነበር፡፡ ቢሆንስ በሴራ ተገደለ እንጂ ምን አስደናቂ ስራ ሰራ? እንቀጥል፡፡ የእንግሊዝ ልዑላን በእንግሊዛውያን ዘንድ ታዋቂና ተከባሪ ናቸው፡፡ ሹመታቸውና ጋብቻቸው ታላቅ ግርግርታና ሽፋን አለው፡፡ ታዲያ እኒህ የእንግሊዝ ልዑላን በትዕዛዝ ነው እንዴ የተወለዱት?
የበዕውቀቱ ሸፋፋ ዕይታ ባብዛኛው የሚመነጨው ለሃይማኖት ካለው ግንዛቤ ነው፡፡ የልጁ የብዕር ሰይፍ ብዙውን ግዜ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ላይ ይወረወራል፡፡ ብዙ ጊዜ መሠረታዊ ያልሆነ ትችጭ ይሰነዝራል፡፡ ለትችቱ መሸሸጊያ የቤተ ክርስቲያን ትምህርት ያለው ለማስመሰል ይጥራል፡፡ የቤተ ክርስቲያን ትምህርት እንዳለው የሚያሳይ አሳማኝ ምልክት አላይበትም፡፡ ያደገበት ባህል ለቤተ ክርስቲያን ጉልህ ቅርበት ስላለው ጠቅሞት ይሆናል፡፡ ከዚያ የዘለለ ድፍረት ግን “አወቅሁሽ ናቅሁሽ ነው” ይመስላል፡፡ ብዙው ሰው ከቤተ ክርስቲያን ታዛ “ዘኬ” አነፍንፏል፤ ይህን ግ የእውቀት እማኝ አድርጎ መውሰድ ያስታል፡፡ ልጁ ከአንዴም ሁለቴ “ኢ-አማኒ” ነኝ ብሎ ድምጹን ከፍ አድርጎ ይናገራል፡፡ ራሱን ኢ-አማኒ ያደረገ ሰው የሉላውን ሰው እምነትና ሃይማኖት መጎንተል ዘላንነት፣ ወንጀልም ነው፡፡ በተለይ ካህናትን በሸንቋጭ ቋንቋ የመዝለፍ ልማድ አለው፡፡ ነገር ግን ከኢ-አማኒ ወደአማኒ የሚሰነዘር ማንኛውም ሃይማኖት ነክ ጉንተላ ምክንያታዊ አይደለም፡፡

መቼ ነበር ይህ ልጅ እስልምናን ወይምፈረንጅ ጠቀስ አመጣሽ ቤተ እምነቶችን የሸነቆረው? ይህ ልጅ አቡነ ተክለ ኃይማኖትን በተቸበት አግባብ መሃመድን ቢነካ በእውኑ የበዕውቀቱን አንገት ከተቀረው ሰውነቱ ላይ ተሰክቶ ማግኘት የማይታሰብ ሊሆን ይችል ነበር፡፡ እስልምናም ሆነ ሌሎች የክርስትና ቅርንጫፎች በዚች ሃገር ታሪክ ውስጥ ጎታች ምዕራፍ አልነበራቸውም?

ልጅ በውቄ የቤተ ክርስቲያን ሊቃውንትን ሳይንስ-ጠል ሊያደርግ ሲዳክር በ“ከአሜን….” መጽሐፉ ታዝበነዋል፡፡ ስለ “ መሬት መዞር” አንድ ፈረንጅ ለሊቃንቱ ሲናገር እንዳልተቀበሉትና አለቃ ለምለም ወደሚባሉ የላቁ ሊቅ ፈረንጁን እንደመሩት ይነግረንና አለቃ ለምለምም ጉዳዩን ሰምተው ከነጩ ጋር ጠጅ ጠጥተው ሲዞርባቸው “ያገሬ መሬት አሁን ዞረች” ብለው ሳይንስን ላለመቀበል ከፌዝ ጋር እንዳቅማሙ ከትልቅ ነቀፋ ጋር ይተርክልናል፡፡ ይህን የሚለው ከማን ጋር አነፃፅሮ ነው? እኔ እስኪ ይኼን እውነት ከፈረንጆች ጋር ላነፃፅር፡፡ መቼም ከእውነቱ ጋር እንጂ ከፈረንጅ ጋር አታነፃፅር እንደማይለኝ ተስፋ አለኝ፡፡ ምክንያቱም ለርሱም ሆነ ለሌሎች “ዘመናዊ ትምህርት” ቀመስ ነቃፊዎች መነፅራቸው ምዕራባውያኑ ናቸውና፤ ይልቁንም ልጅ በዕውቀቱን ራሱ እንደነገረን “በአንድ ሃባ መፅሐፍ” የልጅነት ማኅተቡን አስበጥሰው ሃይማኖትን ያስተውት ሐዋሪያዎቹ ናቸውና፡፡ “የመሬት መሸከርከር” ነገር ሲነሳ የሳይንሱ መገኛ ምዕራብ አውሮፓውያን ራሳቸው በእልልታ አልተቀበሉትም ነበር፡፡ በተለይም የሮማካቶሊክ ልሂቃን፡፡ ስሙን የዘነጋሁት ተመራማሪ “መሬት እንደምትዞር” አረጋገጥኩ አለ፡፡ የዘመኑ ፈላጭ ቆራጭ ፓፓዎች ንስሃ ግባ አሊያ አንገትህ ይከላል ብለው አስፈራሩት፡፡ “ሰይጣን አሳስቶኝ ነው” ብሎ “ተፀፀተ”፡፡ ቀጥሎ እውቁ የግኝት ሊቅ ጋሊሊዮ ጋሊሊ “አውነቱን” አገኘሁት አለ፡፡ “ሰይጣን አሳሳተኝ” በል ተባለ ፓፓዎች ዘንድ ቀርቦ፡፡ ፈቃደኛ ሊሆን ባለመቻሉ አንገቱን ሊቀላ ችሏል፡፡የልጁን ክፍተት እዚህ ላይ በሰፊው ማየት እንችላለን፡፡ ይህ እንግዳ ግኝት ለሳይንስና ፈጠራ ቅርብ በሆኑትን ነጮች እንኳ በቀላሉ ቅቡል አልነበረም፡፡ የሮም ቤተክርስቲያን ፓፓዎች አውሮፖ ውስጥ ብዙ ግኝት ያመጡ የሳይንስ ሊቆችንና የተለየ ሃይማኖታዊ አቋም ያራመዱ ሊቃውንትን በእሳት አቃጥለው መጨረሳቸው ታሪክ ያወራው ሃቅ ነው፡፡ ጉዳዩ ወደ እኛ ሃገር እና ቤተ ክርስቲያን ሲመጣ ነው እንዴ ለበዕውቀቱ ለአቅመ- ወሬነት የሚበቃለት? የእኛዋቹ ሊቃውንት መልሳቸው ሁለት ነው፡፡ አንደኛው አንቀበልም፤ ሁለተኛው ደግሞበቀላል ፌዝ አዘል “ቤተ-ሙከራ” “ሰክረህ ሲዞርብህ” መሬት ትዞራለች አትበል! የሚል ነው፡፡ እንደ ሮማዎቹ ከዶግማ ጋር አላያያዙትም፡፡ ሌላው ቀርቶ ወደ ዛቻና ማስፈራሪያ አላደገም፡፡ አውሮፓውያኑ ግን “የሰይጣን ሃሣብ” ነው፡፡“ትምህርተ-ሃይማኖት” አፋለሰ ብለው ሰው ሰቅለዋል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  መንፈሳዊ ወኔና ስልጣን (ፕሮፌሰር መስፍን ወልደ ማርያም)

በአዲሱ መጽሐፉ ገፅ 91 ላይ “አንድ ፍሬሽንብራ የሚያክል ቄስ በአንዲት ቃል’አሰርሁ ፈታሁ’ እያለ ሃገር ሊያምስ ይችላል” ይላል፡፡ ምን ማለት ነው? “አንድ ፍሬ ሸንብራ” የሚለው ሃረግ የስድብ ቃና ነው ያለው፡፡ እንዲህ ብሎ አንድን ክብር ያለው የሃይማኖት አባት መዝለፍ ተከታዩን ከማሳዘኑ አልፎ የፀሐፊውን ደረጃም ያወርዳል፡፡

እዛው ገፅ ላይ ሌላ ሸንቋጭ ገለፃ አለ፡፡ “መንፈሳዊ ባለስልጣኖች ከዓለማዊ ባለስልጣኖች የሚበልጥ እንጂ የማያንስ ጉልበት ነበራቸው” የሚል፡፡ ከዚህ ዓረፍተ ነገር፤ ሁለት ህፀፆችን መንቀስ እንችላለን፡፡ የመጀመሪያው“መንፈሳዊ ባለስልጣኖች” በሚል ድፍረት በተቀላቀለበት ገለፃ መንፈሳዊ አባቶችን ይወርፋል፡፡ በቤተ ክርስቲያን ትውፊትና በአማኞቹ ዘንድ ክብር ባለው አጠራር ነው የሃይማኖቱ አባቶች የሚጠሩት፡፡ በስድ ውከላ ቤተ ክርስቲያኗን ማንኳሰስ አላማው ስለሆነ እንጂ የዛሬዎቹን “ጥቂት” ፖለቲካ መር የኃይማኖትመሪዎች ቢተች ጥቅሙ ለራሷ ለቤተ ክርስቲያኗም በሆነ ነበር፡፡ ሁለተኛው የመንፈሳዊ አባቶችን ስልጣን /power/ ሊያሳይ የሞከረበት ነው፡፡ አሁንም በንፅፅር ነው የማሳየው፡፡ ከየትኛው ቤተ እምነት ራሶች ጋር ተወዳድረው ነው የኛዎቹ “ባለጉልበት” የሆኑት፡፡ እስልምና አረብ አገራት ላይ ራሱ መንግስት ነው፡፡ አባቶችም አድራጊ ፈጣሪ መሆናቸው ግልፅ ነበር፡፡ ሌላው ቀርቶ በዓለም አብያተ-እምነት ታሪክ እንደ ሮማ ካቶሊክ ፓፓዎች ጉልበተ ብርቱ መንፈሳዊ መሪ ተከስቶ የሚያውቅ አይመስለኝም፡፡ እኒህ ፓፓዎች ታላቁን የሮም መንግስት በትረ ስልጣን ይዘውሩ ነበር፡፡ በጉባኤ ኬልቄዶን ለአንዷ ቤተ ክርስቲያን ወደ ሁለት መከፈል፣ በ16 መ/ክ/ዘመን ፕሮቴስታንቲዝም ለተባለው እንቅስቃሴ መጀመርና ለቤተ ክርስቲያን ወደ ሶስት ቅርንጫፍ ማደግ፣ ቤተ ክርስቲያን ወደ አንድነቷ እንድትመለስ በተጠሩ የተለያዩ ጉባኤዎች ላይ እንቅፋት በመሆን የሮማ ፓፓዎች ጡንቻ ከባድ ድርሻ ነበረው፡፡

የላሊበላን አብያተ ክርስቲያናት “አዳራሾች” (ገጽ 25፣26፣28፣31) ብሎ ከእምነትም ከሥነ ውበትም ጎራ ገፍቶ ያወርዳቸዋል፡፡ የላሊበላ ቤተ መቅደሶችየተሰሩትም፣የሰራቸው ቅዱስም መንፈሳዊና ለመንፈሳዊ ዓላማ ነው፡፡ ከታሪክና ሥነ-ህንፃ ፋይዳቸው፣ ከቅርስነታቸውም ጎን ለጎን አምልኮ የሚፈፀምባቸው መንፈሳዊ መካናት ናቸው፡፡ አዳራሽ ብሎ መንፈሳዊና ቅርሳዊ ይዘትና ልዕልናቸውን ያንቋሸሸበት ምክንያት ግልፅ አልሆነልኝም፡፡

በሌላ መልኩ በገፅ 162 ላይ እንዲህ ይላል፡ “ብዙ ያገራችን ገዳሞችና ጥንታዊ ህንፃዎች በሰላሙ ቀን ለቤትነት የሚያገለግሉ ምሽጎች ናቸው ማለት ይቻላል፡፡” አሁን ይኼ ምን ማለት ነው? ዓረፍተ ነገሩም ይዘቱም ግራ አጋቢ ነው፡፡ ገዳማት በሰላም ቀን መኖሪያ ቤቶች ናቸው ማለት ምንድነው?“አምልኮ ቦታን የሙጢኝ የሚል እምነት እንደሚወገድ” (ገፅ 171) ሲተነብይ እናገኘዋለን፡፡ አሁንም ቢሆን በዚህ አባባሉ ከዚች መከራ የበዛበት ቤተክርስቲያን ራስ ላይ ሊወርድ አልፈለገም፡፡

ቤተክርስቲያንን ለመጐንተል ቀልቡ የማያርፈውን ያህል ስለሰራችው መልካም ትሩፋት ለመዘከር ብዕሩ ይዶለዱምበታል፡፡ የቤተክርስቲያን ሊቃውንት የቀመሙትን ቅኔ ሲነጥቅ እንጂ ሲያሞግስ አንብበን አናውቅም፡፡ ስለ ሊቃውንቱ የዘመን አቆጣጠር (Calendar) ጥበብ /ግኝነት፣ ስለ ሥነ-ፈለክ ምርምራቸው፣ ሒሣብ፣ ፍልስፍና፣ ታሪክ፣ ሥነ-ህንፃ፣ ሥነ-ፅሑፍ፣ ፊደል፣ አሃዝ፣ ብራና ፍቀው ቀለም በጥብጠው እውቀት ስለማቆየታቸው በስህተት እንኳ ለማውራት ወይ ለመፃፍ ሲደፍር አላየሁትም፡፡ ለመንቀፍ፣ ለማንኳሰስና ለማላገጥ ግን ከብርሃን ፈጥኖ ይደርሳል፡፡

ሌላ ቦታ ላይልጅ በዕውቀቱ “ኡ ኡ” ብሎ ጮኾ ኢ-አማኒነቴን እወቁልኝ ሲል እናገኘዋለን፡፡ ኢ-አማኒነትን ለመግለጽ ሁለት ጊዜ ቃል በቃል አንድ ቦታ ላይ ደግሞ በአገባብ ሞክሯል- በ“ከአሜን ባሻገር” ላይ፡፡ ይህን ለማሳወቅ መጽሐፍ መፃፍ አይጠበቅም በህይወት ፍልስፍናውና በእለት-ተለት የኑሮ ዘይቤው ሊገልፀው ይችል ነበር፡፡ ምናልባት አማኒው ክፍል ከተከፋ ብሎ ይመስላል አንድ ቦታ ላይ ደግሞ “ለፋሲካ በዓል ማንኩስ” ሄጄ ይላል፡፡ ይህን የማመጣጠን ፓለቲካውን አልወደድኩለትም፡፡ በ“ማመጣጠንፓለቲካ” ብዙ ገፆች ላይ ሲዋዥቅ ይዤዋለሁ፣ በተለይ ታሪክንና ማንነትን በተነተነባቸው ክፍሎች፡፡ ኢ-አማኒ መሆን መብቱ ነው፤ በነጋሪትም አሳወጀ በህይወት ዘይቤው፡፡ ግን በእሱ ኢ-አማኒነት ውስጥ የሌላውን አማኒነት አንኳሶ መሳል ተንኳሽነት ነው፡፡ ከቤተ ክርስቲያን ጋር ቂም ሊጋባ ይችላል፣ በህይወት መንገዱም ላትመቸውት ችላለች፡፡ ቤተ ክርስቲያኗን በሰበብ አስባቡ መጎንተል ግን የተከታዩን ግለሰባዊ መብት እንደመፃረር ነው፡፡ በልጅነቱ በቁንጥጫ የመዘለጉትን ቄስ ሲጠላ አድጎበት፣ የኢትዮጵያን ቄስ በጅምላ ሊጠላ አይገባውም፡፡ የእሱ የጥላቻ አገላለፅ አዕላፋት የሚሆኑ የቄሱን ልጆች ያሳዝናልና፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  የቁጥር ጨዋታ?! – ፂዮን ግርማ

ከዚህ ወጣ ስንል፣ “ጉግስ፣ ጊጤ፣ ሰንጠረዥ አካዱራ፣ ገና የተባሉት ጨዋታዎች የጦርነት ቃና ነበራቸው” ይለናል፡፡ (ገፅ 162)፡፡ የየትኛውም ሃገር ጨዋታዎች (Games) በሁለት ተቃራኒ ቡድኖች መካከል የሚካሄዱና አንዱ ቡድን ወይም ግለሰብ ሌላኛውን ቡድን ወይም ግለሰብ ለማሸነፍ የሚደረግ ግብ ግብ ነው፡፡ እሱ ካልሆነማ የጨዋታው አጓጊነት አይኖርም፡፡ አሁን ያሉ ዘመናዊ ስፖርታዊ ጨዋታዎችን ስንወስድም በዚህ መንፈስ የተቃኙ ናቸው፡፡አሸናፊነት ግባቸው ይሆንና ያልቻለ ተሸናፊ ይሆናል፡፡ በዚህ ግብግብ ውስጥ መጎዳዳት አልፎ ተርፎምመገዳደል ሊኖር ይችላል፡፡ በዘመናዊ ስፖርት እንደ American football ጦርነት አካል ጨዋታ የለም፡፡ የኛን ጨዋታዎች የጦርነት ታሪካችን መግፍኤና ቆስቋሽ ሊያረጋቸው ይዳዳል፡፡ ጨዋታዎች እርሱ እንዳለው የጦርነት ቀደምት ሽሎች ሊሆኑም ላይሆኑም ይችላሉ፡፡ በጥናት እስካልተረጋገጠ ድረስ ከግለሰብ ግምት ያለፈ እውነታ አይኖረንም፡፡

ስለጡት ቆረጣ ባወራበት አንቀፅ ዮዲት ጉዲት ወደ አክሱም ወርዳ “በሴተኛ አዳሪነት” እንደተሰማራች ይነግረናል፡፡ “የቄስ ሚስት አወቅሽ አወቅሽ ቢሏት…” የሚለው ብሒል የሚሰራው እዚህ ጋር ነው፡፡ ከሚገባው በላይ ተጨብጭቦልህ ማማ ላይ ከወጣህ መውረጃው ነው የሚጠፋህ፤ ወጥም ትረግጣለህ፡፡ ሴተኛ አዳሪነት የተጀመረው ከሁለተኛው የጣሊያን ወረራ ጋር ተያይዞ እንደሆነ ነው በስፋት የሚታወቀው፡፡ ሴተኛ አዳሪነት /Prostitution/ እንደ ስራ ዘርፍና መተዳደሪያ ነው፡፡ በየት በየት አድርጎ ነው ከዛሬ 1100 ዓመት በፊት ኢትዮጵያ (አክሱም) ውስጥ ሴተኛ አዳሪነት አለ የሚለን? ምን አልባት ዘማዊነትን ሴተኛ አዳሪነት ብሎ ተረድቶት ከሆነ በትልቁ ስቷል፡፡ ሴተኛ አዳሪነት ነጮቹ commercial sex የሚሉት ነው፡፡ እሱም ገንዘብ ማግኛና ኑሮን ማሸነፊያ መንገድ ነው፡፡ ይህ ስራ ከሺ ዓመታት በፊት አገራችን ውስጥ ነበር ማለት ጸሐፊውንም ሆነ ምንጩን ከስህተት አያድናቸውም፡፡

የጉዞ ማስታወሻ “ጊዜ አልፎበታል” ይለናል ልጅ በውቀቱ፡፡ ገጣሚው የሚያስገርመኝ ጠባዩ እርሱ በግሉ ያመነበትን ጉዳይ ነባራዊ እውነታ አድርጎ መሳሉ ነው፡፡ “የጉዞ ማስታወሻ”ን Google Earth ተክቶታል አይነት ስብከት ያስቀምጣል፡፡ “የጉዞ ማስታወሻ” ሲባል “ደብረ ብርሃን ከአ/አ በስተሰሜን አቅጣጫ 130 ኪ.ሜ ርቀት ላይ፣ ከባህር ጠለል በላይ ምንትስ ጫማ ከፍታ…” ምናምን አይደለም`ኮ፡፡ የሕዝቡን ባህል፣ ወግ፣ ተረት፣ መልክዓ ምድር፣ የኑሮ ዘይቤ፣ የስልጣኔ ባህል፣ ትምህርት፣ ፍልስፍና፣ ፍቅር፣ ጥላቻ፣ ሐዘን፣ ደስታ፣ ሌሎችም ይገለጹበታል፡፡ የ“ገለጻ” ችሎታ በራሱ አንድ የሥነ ጽሑፍ ስልት ነው፡፡ እስኪ ዛል አንበሳን ከመሐመድ ሰልማን “ፒያሳ…” ልቆ የሚከስትልን ድረ ገጽ ይጠቁመን፡፡ እስኪ በሞቴ ስለአርማጭሆ በቂ መረጃና ምስል የትኛው ድረ ገፅ ላይ ነው ያለው?

ታሪክ ቀመስ ትንተና ከሰጠባቸው ምዕራፎች ባንዱ “ስምና ማንነት” በተሰኘው ጥግ ስር ጎጃም ኦሮሞ ልትሆን ለጥቂት ነበር የተረፈችው፡፡ እውነት ነው የኢትዮጵያ ሕዝብ እርስ በርሱ የተጋባ ነው፡፡ ይህን ማሳወቅም በጎ፡፡ ግን ይህን እውነታ ለመግለጽ ቀይረውበት ነው እንጂ አያቴኮ “ከበደ” ሳይሆን “በዳዳ” ነበር አይነት ዲስኩርን ምን አመጣው? እዚህ ድረስ መሄድስ ለምን አስፈለገ? ስለምኒልክና የሃገር አንድነት ዘመቻው ያቀረበው ትንታኔ እጅግ ግሩም ነው፡፡ እውነትና በታማኝ ዋቢዎች የተጣቀሰ ነው፡፡ እውነት ነው ዳግማዊ ምኒልክ በዘመቻው የአንድ ንጹህ ሰው ጡት አላስቆረጠም፡፡ ይህን እውነት በእውነትነቱ ብቻ ማስረዳት የምሁርነትም የጀግንነትም ምልክት ነው፡፡ በዕውቀቱ የዲግሪ መዓት የቆለለ “የታሪክ ምሁር” ነኝ ባይ ያልደፈረውን ነው የደፈረው፡፡ ለዚያውም በፍቱን ምክንያታዊነትና ማስረጃ ከግሩም ጥናት ጋር- ይበል የሚያሰኝ ነው፡፡ ይህን ለ“ማመጣጠን” ግን “የጎጃም ነገሥታት ኦሮሞ ናቸው”፤ “ነገሥታቱ ከኦሮሞ ሲጋቡ ነው ክብራቸው የሚጨምረው”፤ “የጎጃም አካባቢዎች ‘ኦሮሞ-ወረስ’ ናቸው”፤ ሌላው ቀርቶ “ከኦሮሞ ያልተቀላቀለ ጎጃሜ ክብሩ ያነሰ ነው” የሚለው ዲስኩር ግነት አከል አዎ-ኦሮሞ አገላለጽ ነው፡፡ የአካባቢውን ባህል የሚያውቅ ሰው ደግሞ ገለጻው ከእውነታ ምን ያክል እንደጎነ አያጣውም፡፡ ያለፈ የታሪክ ስህተት የሁላችንም ቀደምቶች መፈጸማቸው እሙን ነው፡፡ እሱን ለእነሱው ትተን እኛ የጸዳ ዛሬና ነገን ለመገንባት መትጋት አዋጪው ነገር ነው፡፡

ስለራስ ጎበና የሰጠው ታሪካዊ ትንታኔ ግሩም ነው፡፡ ራስ ጎበናን ለማክበር ግን “ንጉሥ ምኒልክ ‘አንቱ’ ብሎ ጎበናን ይጠራዋል” ማለት፣ አልፎም “የጎበና ንብረት ከምኒልክ ይበልጣል” ብሎ መቀኘት በእውኑ አጓጉል ግነትና ኢ-ምክንያታዊ ነው፡፡ አንድነታችን እንፈልገዋለን፤ ለዚያ የሚያሻውን መስዋዕትነት እስከመክፈል፡፡ ከጥንት ጀምሮ ኢትዮጵያዊነት ውሁድ፣ ቅልቅል እየሆነ መጥቷል፡፡ ይኼን ለማሳየት የሄደበት መንገድ ይበል የሚያሰኝ ነው፡፡ ግን አበበንም እንዳይከፋው ጫላንም እንዳይከፋው “በማመጣጠን” የሚቀርብ ነገር ሁሌም በጎ አይሆንም፣ ሕጸጽ ሊያስከትል ይችላልና፡፡ እንደውም ይሄን ክፉ ነገር የመንግስት መገናኛ ብዙሃን ሳናስበው ያሰረፁብን ይመስለኛል፡፡ እውነት በማመጣጠን አትቀርብም፣ እውነት ያው ራሷ እውነት ናት፡፡

በታሪክ የተከሰተን ድክመት ተምረንበት ለዛሬ በጎነት ትርፍ ማግኘት መልካም ድርጊት ነው፡፡ በሌላው ዓለም ወተትና ማር የመዝነብ ታሪክ እንደተመዘገበ ሁሉ በእኛ ላይ መሳለቅ ግን ደግ አይመስለኝም፡፡ “በታሪክ ውስጥ ያሉ ቁልፍ ቃላቶች (ቃላት?) ‘ታሠረ፣… ነገሠ… ዘመተ… ተሰቀለ’ የሚሉ ብቻ…” (ገጽ 80) ይለናል፡፡ የዓለም ታሪክም ከዚህ የተለዬ ዘገባ የለውም፡፡ የታላቋን አውሮፓ ታሪክ እንኳ ብንወስድ “ወረረ፣ አስገበረ፣ ቅኝ አደረገ፣ በዘር አገለለ፣ ገደለ….” እና መሰል ትርክቶች የዘለለ አይደለም፡፡ ዛሬ በዘር ማግለላቸውን በአንጻሩ ከማስቀጠላቸው በቀር ከታሪካቸው ተምረው አሁን የዓለማችን ቁንጮዎች ሊሆኑ ችለዋል፡፡ የዓለም ታሪክም እንዲሁ ነበር የእኛ የተለዬ አይደለም የሚለው አይደለም የእኔ መከራከሪያ፡፡ እርግጥ ነው ዓለም ከሰራው የተለዬ የእኛ ቀደምት አልሰሩም፡፡ ግን ግን የቀደሙትን በመተቸት ላይ ብቻ በዕውቀቱ ለምን ረክቶ ይቀራል ነው የእኔ መነሻ፡፡ የታሪክ ክስተቶችን የአሁኑን ለማስተማርና ለመገሰጽ ይጠቀምበት እንጂ የቀደሙትን ብቻ ዘልፎ አይቁም ነው፡፡ በዚህ ዘመን የታሪክ ደካማ ጎኖችን በማስቀጠል ለማትረፍ ደፋ ቀና የሚሉ ልሂቃንን መተቸት በአንጻሩ የበለጠ ጠቃሚ ይሆን ነበር፡፡ ታሪክን በዘመኑ አውድ ስንመዝነው በዓለም መድረክ ከተከሰተው ውጭ በእኛ ሃገር ብቻ ተለይቶ የተከሰተ ነገር የለም፡፡ የተከሰተውንም በ“ዘመኑ መንፈስ” ስናጤነው መጥፎም ቢሆን ቅሉ ጭራቅ ጎኑ ብቻ ገኖ ሊወጣ አይገባም፡፡ አሁን ያለውን ነባራዊ እውነታ መተቸቱ ግን የበለጠ ሃገራዊ ፋይዳ ይኖረዋል፡፡

ተጨማሪ ያንብቡ:  ዘር ማጥራትን ያህል ወንጀል ፈጽሞ ይቅርታ መጠየቅ ፌዝ ካልሆነ ድራማ ነው! ከግርማ ሞገስ

በዕውቀቱ ስዩም ከዚህ ሁሉ ያልፍና አንድ ዘለላ የፈረንጅ መጽሐፍ አንብቦ ‘ኃይማት ለምኔ’ ማለቱን ይነግረናል፡፡ እስኪ አብረን እንከታተለው፤ “The Future of an Illusion የሚል የፍሮይድን መጽሐፍ ካነበብኩ በኋላ ለአንዴና ለመጨረሻ ግዜ ከሃይማኖት ጋር ፍቺ ፈጸምኩ” ይለናል፡፡ ለስንት የጠበቅነው ግሩም ልጅ ለአንድ ባህር አቋርጦ ለመጣ መጽሐፍ እጅ ወደላይ ብሎ ማንነቱን ሲሰጥ እናየዋለን፡፡ ከራሱ አንደበት ሲወጣማ አብሶ በጣም ያስደነግጣል፡፡ እንዲህ ብሎን በሕዝብ ጭብጨባ ከወጣበት ማማ ላይ ወርዶ ሲከሰከስ እናየዋለን፡፡ የበዕውቀቱ ጠንካራ መንፈስ በአንድ የፈረንጅ መጽሐፍ የሚፈረካከስ አይመስለኝም ነበር፡፡

ወደ ሃይማኖት ቀመስ ጉዳዩ አንዴ ልመለስና በገጽ 216 ላይ “ክርስትና በጥንታዊ ቁመናው… ሌሎችን የሚችልበት…” ትዕግስት እንዳልነበረው ይነግረናል፡፡ ከክርስትና በዓለም መሰበክ በኋላ ኃይማኖቱ በአገራችን ገናናና ብሄራዊ ሆነ፡፡ በማይካድ ሁኔታ ከሰሜን እስከ ደቡብ ጫፍ ቢሄዱ ክርስትና በአገራችን ባህልና አስተሳሰብ ላይ ከባድ አሻራ ማኖሩን ይገነዘቧል፡፡ ሌሎችን የማሳነስ ነገር እንኳ ቢኖር የሃይማኖቱ አስተምህሮ ሳይሆን የግለሰቦች ዘዬ መሆኑ እርግጥ ሆኖ በየዘመኑ ደግሞ ሁሉም ኃይማኖቶችና የኃይማኖት መሪዎች ይፈጽሙት የነበረ ነው፡፡ ምስራቃውያኑ በተለይ ጃፓን በሕግ ለክርስትና በራቸው ዝግ ነበር፡፡ እስልምና በአረብ አካባቢ ብቻ ሳይሆን በየትኛውም የዓለም ጥግ አብላጫውን ይዞታ በተቀናጀበት ግዛት ሁሉ ‘የእኔ ብቻ’ አምባገነንነትን አብዝቶ ይተገብረዋል፡፡ የሮማ ካቶሊክ በግዛቷ ሌላውን የምትሰማበት ጊዜ አልነበራትም፡፡ ሌላው ቀርቶ በኃይማኖቶች ታሪክ ቅርብ ክስተት የሆነው ፕሮቴስታንቲዝም እንኳ በመካከለኛው ዘመን በርካታ ተከታዮች ባፈራባቸው የአውሮፓ ግዛቶች እንዳቅሙ ጉንተላና ማስፈራሪያ ይፈጽም ነበር፡፡ በዕውቀቱ ከታሪክ መዘዝኩ ብሎ ነው የኢትዮጵያን ክርስትና ከመጭራቅ የሚከሰው፡፡ ባለንበት ዘመን እስልምና ሳዑዲ ውስጥ ክርስትና እንዲገባ አይፈቅድም ብዬ የሞኝ መከራከሪያ አላቀርብም፤ ይልቁንም ኢትዮጵያ ውስጥ እስልምና በብዛት በሰፈነባቸው ግዛቶች ውስጥ በክርስቲያኑ ማኅበረሰብ ላይ ግፍ አልፈጸመም? ካቶሊኮች በመካከለኛው ዘመን በነፔድሮ ፓኤዝ፣ አልፎንሱ ሜንዴዝና ቤርሙዴዝ ጊዜ በተለይ ሱስንዮስን ከቀየሩ በኋላ ከጉንተላና ስራ ማስፈታት አልፈው ወደ16 ሺህ ገደማ የላስታና ጎንደር ንጹሃን ሰዎች መገደል ምክንያት አልነበሩም? ፕሮቴስታንቲዝም ዛሬ የኢትዮጵያን ክርስትና “ድንጋይ ከመሳም” ጋር አመሳስሎ አይወርፍም? የቅዱሳንን ገድል “ገደል” ብሎ መጽሐፍ አይጽፍም? ከዚህ የበለጠ የሌላውን ባህልና እምነት ያለማክበር ምን አለ? ፍትሃዊ ይሁን’ጂ እይታችን ጎበዝ! ገና ለገና ‘እኔን’ ባይ የለም ብሎ ምሳር ማብዛት ምንድነው?፡፡ ይህን የምለው የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ጠበቃ ሆኜ አሊያም የቤተ ክርስቲያኗ አባላትም መሰል ድርጊቶችን አይፈጽሙም ከሚል ጭፍንነት ላይ ቆሜም አይደለም፡፡ እንደየድክመቱ ሁሉም ይነቀፍ ዘንድ የተገባ ነው፡፡ ለአብሮነታችን የሚበጀውም እርሱ ነውና፡፡ ነገር ግን ልጅ በውቀቱ ሌላ ሌላውን አይዳስስም፣ አዚችኛዋ ላይ ግን ሳይበላው ያካል፡፡ ፍርደ-ገምድል ሆነብኝ፡፡ ሌላው ሌላውን ሁሉ እንተወውና እስልምና አሁን ላለው ተክለ ቁመና ለመብቃቱ ያኔ በተጀመረበት ዘመን የመጀመሪያዎቹ አማኞች ሲሰደዱ፣ አሳዳጆቹን አሳፍሮ መልሶ ተከታዮቹን ያስጠለላቸው እኮ በፍጹም ክርስቲያናዊ ባህልና እምነት የበለጸገው ንጉሥና ሕዝብ ነው፡፡ ይህን ይህንም መጥቀስ ይገባው ነበር፡፡ በቅርበት የሚያውቀውን ባህልና ቤተ እምነት በ“አወቅሁሽ ናቅሁሽ” ስልት ለርካሽ መስዋዕትነት ማቅረብ አጉራ-ዘለልነት ነው፡፡

በሌላ ጎኑ በጽሑፉ ውስጥ ለሥነ ጽሑፋዊ ውበት ሆን ተብሎ የተደረገ ማፈንገጥ በማይባል መልኩ እንደ “ምሽት” እና “ቢስማር” አይነት ቀበልኛ ቃላት መጽሐፉ ውስጥ ጥቅም ላይ ውለዋል፡፡

እንደመውጫ፡- ስለዳግማዊ አጼ ምኒልክና የዘመቻው ትርክት የተከራከረበት መንገድና ቀረበው በፍጹም ማስረጃ የታሸ እውነነታ፣ ፍትሃዊነትና ምክንያታዊነት በእውነት የደራሲውን ከፍታ አሁንም የመሰከረ ነው፡፡ በማር ስለተለወሰው አደገኛ መርዝ፣ ጸረ-ኢትዮጵያዊው ተስፋዬ ገ/አብን ተንኮሎችና ውሸቶች ፉርሽ ያደረገበት መንገድ እጅግ ግሩም ነው፡፡ እንዲሁም ሌሎች ታሪካዊ፣ ፖለቲካዊና ቧልታይ (Satiric) ወጎቹ በበጎ ጎን የሚነሱ ናቸው፡፡ በ“ከአሜን ባሻገር” ላይ የብዕሩን ከፍታ ማዬት ችለናል፤ ነገር ግን በእስከአሁን ቀይታው (ማለትም “መግባትና መውጣትን” ከጻፈ በኋላ ባገኘው የእፎይታ ጊዜ)፣ ካለው የሥነ-ጽሑፍ ተሰጥኦ፣ በነ“እንቅልፍ እና ዕድሜ” ካሳየን አቅም አንጻር ስንመዝነው ግን ከዚህ የተሸለ ነገር ይዞልን ሊመጣም በተገባው ነበር፡፡

 

15 Comments

  1. ወሬ በአህያ አይጫንም ፡፡
    ከመተቸትህ በፊት ወይም ቃላት ከማብዛት እና ስምህን ከመቀያየር
    እኔ ማን ነኝ ፡ የዕውቀቴ መጠን የት ድረስ ነው ብለህ አስተውል፡፡

    በእውቀቱ የታደለ ፀሀፊ ነው፡ ስለምን እንደሚጽፍ ጠንቅቆ ያውቃል፡፡
    ታላቅ የጥበብ ሰው ነው፡፡

    ቅናት ያስመስልብሀል ወንድሜ፡፡

  2. Germu
    Constructive criticism is way of correcting a person view thier is no one is perfect but I don’t know why u used this kind of word about the writer, this shows that u don’t use your brain examine things or if u like that person u just consume what ever given to u with out a question.

  3. ዳዊት ግርማ ትችትህ ሲመዘን በጣም ቀላል ነው :: በሃይማኖት ጉዳይ ላይ ያቀረብከው ምንም ማስረጃ ሳይኖርህ ብዙ ብለሃል :: አብዛኛው ትችትህ ከስሜታዊነትና ተቆርቁዋሪነት የመነጨ ይመስላል ::የበእውቀቱ ጽሁፎች በንባብና በማስረጃ የተደገፉም የዳበሩም ናቸው በተለይ ታሪክና ሃይማኖትን የተመለከቱት ::አንተም እንዚህን ለመተቸት ስትነሳ ማስረጃህን ከዘራ አድርገህ ቢሆን ለተመልካች ፍርድ ቀላል ይሆን ነበር ስለዚህ የቤት ስራህን ሳትሰራ ነው እርሳስህን ያስቀደምከው ::

  4. “ጥበብ መጄምሪያ እግዚአብሄርን መፍራት ነው”መፅሐፈ ምሳሌ ፩:፯
    ፅድቅና ኩነኔ ቢኖርም ባይኖርም፣
    ከክፋት ደግነት ሳይሻል አይቀርም።
    ግሩም አስተያየት ነዉ።ደራሲዉ እምነት አልባ እንደሆነ እራሱ አዉጆልናል እኔም አሜን ብዬ በእራሴ በኩል ተቀብያለሁ።እንግዲህ ይህ ከሆነ እዉነታዉ ደራሲው ግን በማያምንበት እምነት ዉስጥ ገብቶ ባልታጠበ እጁ ሊያቦካ ባልፀዳ እግሩ ሊያሞቦጫርቅ እንደፈለገ አልገባኝም።መብቱ እንዲከበር የሚፈልግ የሌላዉንም ማክበር አለበት።ደራሲዉ ብዙዎች እሳት የተጣሉት፣ በቅርቡ ሊቢያ ላይ በቢላ የታረዱለት፣አርባ ጉጉ ላይ እና መስል ቦታዎች ጉድጓድ የተወረወሩበትን እምነታቸውን ማጨማለቅ ማለት ጤነኛና አዕምሮው በሐሺሽ ያልጨለመ ከሆ አንድም ሚሊዮኖችን መናቅ ነው አሊያም የፈለኩትን ባደርግ ምን አገባችሁ ነገር ነው ።Salman Rushdie ከኢራን በኩል በሕይወቱ እንዲቀጣ ሕግ የተላለፈበ ለምን ይመስልሃል?በየትኛውም ማህበረሰብ ዉስጥ ሲኖር የዚያን ሕዝብ እሴቶች ማክበር ተወደደም ተጠላ ግድ ይላል።ይሕንን በአግባቡ ሣትረዳ መፅሐፍ ለማሣተም መሮጥሕ ታላቅ ስህተት እንደፈፀምክ ይሠማኛል።እኔ በአንተ አልከፋም ወደ ልቡናሕ እንድትመለስ እፀልያለሁ በሌላ በኩል ግን በክርስትና እምነት ላይ ያለሕ አመለካከት ግን እጅጉን የወረደ ነው።ክርስትናን እንድታመልክ እየሠበኩ አይደለም ይህም እንዳይሆን አንተን የማረከሕ ነጭ ሐሳቡን በመፅሐፍ አማካይነት ስለጫነብህ ለጊዜው ይከብዳል ነገ ግን የክርስቶስን መስቀል ትሸከማለሕ።እስከዚያዉ ግን እነደሠዉ አስብና የማሕበረሰቡን ዕሴቶች አክብር።

  5. ምን አይነት ጉድ ነው? ስለ ሃይማኖት ማውራት ዎይም መተችት አይችአልም? ስለ መሳፍንቶች ማውራት አይቻልም? I wont be surprised, next time around, this same guy will lecture us about the importance of freedom of speech and democracy.

  6. tichitu kemetsafu belete.lemin isliminan endineka felek?semim anbabim Beiwketun yiwedewal.mekakelegna gebi kalachew tor medawoch honen enanebewalen.
    Ante erasih set an new yasasategni bel.

  7. በእውቄ አድናቂህ ነኝ ፦ ነገር ግን የዚህን ጽሁፍ አቅራቢ ሃሳብ ከሞላ ጎደል እስማማበታለሁ። ይሄ በቤተክርስቲያን ላይ ያለህ የተንሻፈፈ አመለካከት ,,,,,,,,, በሌላው እምነት ላይ ትችት ብትጽፍ የሚከተልህን ታውቀዋለህ ,,,,, ለማንኛውም ከአባቶቻችን ላይ እጅህን አንሳ ከነድክመታቸው እንወዳቸዋለን ።

  8. በእውቄ ያለውን እውነታ ነው የፃፈው። እውነት ጣፈጠችህም መረረችህ ትጋታታለህ። ገና ለገና ለሌሎች እምነቶች በተለይም ለእስልምና ካለህ ጥላቻ የተነሳ በስሜታዊነት ለትችት መሮጥህ አስተሳሰብህ የተቀመጠበትን ሸፋፋ ጭንቅላት ያሳያል።

  9. The writer comments remind me of the politics in the sixties and seventies. We have learned now how little knowledge is dangerous the hard-way after paying so much blood and yet with no solution. The young author can learn from this Wiseman comments, he is simply telling him…have you seen the lifestyle and rules in the other fish tanks beside yours.
    My opinion of Atheist is someone who has reached a conclusion on the most important matter with a scientific speculation of the physical creation of an atom. I have no clue on how an Atheist will answer on how the most powerful aspects of who we are, our conscious/subconscious and love were created. At least all religions believe there is something beyond them.
    I want to say to the youth and middle age groups that ancient world cultures, religions, heritages and practices are very complex and are better to take it in small steps rather than making bold statements. The young author has made bold one sided comments on very serious matters. For those that are not aware, we are learning more and more on the sources seen and connections of Walelegn that transpired the sixties/seventies naïve revolution. Was it better to reform in Baby Steps… We could have achieved it by now without the roller coaster ride that is still getting worse to this day… too much blood of our youth is being wasted by the ignorance of our leaders.
    Has the young author been taken for a ride in creating his view by those… What was the motive of the author in unfairly hammering the poorest religion in the globe and bowing Amen to others? This is the key question of essence? Why isolate and hammer your own while other can be worse examples.

    Ato Girma – Thank you for your valuable review and comments.

  10. ስለ በዕወቀቱ ዳዊት ግርማ የይስሙላ ፣አገም ጠቀም ያለ ትችት መሰል ወቀሳ ከመጫሩ ባሻግር፣ይበልጥ ያተኮረው የቤተ ክስርቲያን ነጻ አውጪ በመሆን ነው።
    በዕውቀቱ በገጽ 147 “ከቴዎድሮስ ጋር በተደረገው ጦርነት ጦስ የባታ ማሪያም ቤተ ክርስቲያን ስትነድ የተመለከተች አንድ አልቃሽ፡-
    “ በሰማይ ላይ ሆነህ ፣ስታላግጥ በሰው
    እናትህ ነደደች፣ሐዘኑን ቅመሰው” ብላ አንጎራጉራ ነበር።
    ሴትዮዋ “እግዚአብሔር ሰጠ ፣እግዚአብሔር ነሳ” እያለ የመጣውን ሁሉ በጅልነትም በለው በጸጋ ተሸክሞ ከሚኖረው አብዛኛው ሰው የተለየች ናት።ሐሳቧ ከዘልማዱ አመለካከት ጋር መጋጨቱን የምንረዳው አጻፋ ምላሽ ከባለ ሥልጣን ጸሐፊ ኅሩይ ወልደ ሥላሴ እንዲህ ሆኖ መቅረቡ ነው። ‘ይቺ ሴት ያለ ዕውቀት በብስጭትና በሐዘን እንዲህ ብላ ገጠመች እንጂ…ይልና የቅዱስ ጳውሎስን ጥቅስ ያስከትላል። እዚህ ላይ በማመንና በማመዛዘን መካከል ያለ ግብ ግብ በግልጥ ይታያል።ኅሩይ የዕውቀቱ ምንጭ የተለመደው መጽሐፍ ነው።ሴትዮዋ ግን በራሷ ልብ ውስጥ የፈለቀውን ዕውቀት አዳምጣለች።” በአጭሩ በዕውቀቱ እንደ አንጎራጓሪዋ ፣ ዳዊት ግርማ እንደ ኅሩይ ወልደ ሥላሴ ዓይነት ሙግት ይዞ ነው ጽሁፉን የሚያጠነጥነው።
    ዳዊት ግርማ ‘ ክብር ያለው የሃይመኖት አባት መዝለፍ’ ሲል ግልጽ አይደለም።በሁለተኛው የዓለም ጦርነት ኢጣሊያ ኢትዮጵያን ስትወር አቡነ ጴጥሮስ ከዕውነት ጋር በመቆማቸው በጠላት ተረሸኑ።እንዲሁም አቡነ ሚካኤል በአየር ከአይሮፕላን ተገፍትረው በኢጣሊያን ተጣሉ። እነዚህ ሁለቱ የመላው ኢትዮጵያ ጀግኖች ናቸው።በሌላ በኩል በጊዜው አቡነ አብርሃም ደግሞ ለጣሊያን አድረው በአገራቸው ከሃዲ ባንዳ ሆኑ።በተለይ በሃይማኖት ተከታዮቻቸው ዘንድ እነዚህን ጳጳሳት የሚያስከብራቸው እና የማያስከብራቸው ተግባራቸው እንጂ የለበሱት ካባ አይደለም።
    ዳዊት ግርማ በመቀጠል “ቤተ ክርስቲያኗን መጎንተል የተከታዩን መብት እንደ መጻረር ነው።” የሃይማኖት ባርነት መብት ነው ውድቀት? የዳዊት ግርማ መብት ጥየቃ፣ የበዕውቀቱን ሐሳብን በነጻ የማሸራሸር መብት የሚሽር ነው?
    በአጠቃላይ የዳዊት ግርማ ጽሁፍ እውቀት ያነሰው፣ልማድ የነገሰበት፣ያለ ማስረጃ ባዶ ጩኽት ነው።አንድ ሙሉ ማጣጣፍ መልስ ያስፈልገዋል።አክራሪነት የጭፍን እምነት ውልድ ነው።ለኢትዮጵያችን ውድቀት ከታሪካችን፣ከሃይማኖታችን ፣ከኑሮ ክፍልስፍናችን ምክንያቶች መጥቀስ ይቻላል።ስለ አገራችን ማንኛውም ጉዳይ ያገባናል የምንል ወገኖች፣ለአገራችን ጥቅም በጋራ ወገነኞች እንጂ የሃይማኖት ነጻ አውጪዎ ባንሆን መልካም ነው።ሃይማኖቱ ቢሆን ለኢትዮጵያ ዕድገትና ብልጽግና ከሚሰጠው ጥቅም አንጻን ካልተቀረጸ ለዘመናት ባዶ አሜን አሜን ሆኖ እንዳይቀር ስጋይ አለኝ።

  11. ሰው ሁሉ የራሱ ድክመት አለው የበውቀቱም ችግር ከዚህ ያለፈ አይደለም ግን “የመውጊያ ስለት ላይ መቆም የሚጎዳው ራስን ነው”

Comments are closed.

Share